የፌዴራል መንግስት እና የሕወሓት የሰላም ስምምነት ኮሚቴ አባላት ለመጀመሪያ ጊዜ ጠቅላይ ሚኒስትር ዶክተር ዐቢይ አሕመድ በተገኙበት የገበታ ለሀገር ፕሮጀክት አካል በሆነው ‹ሀላላ ኬላ› ምክክር አድርገዋል። በውይይታቸውም በሰላም ስምምነቱ አፈጻጸም ዙሪያ የተከናወኑ ተግባራትን በመገምገምና በቀጣይ ትኩረት በሚያሻቸው የሁለትዮሽ ጉዳይ ላይ መነጋገር መቻላቸው ተገልጿል።
በዚህ ውይይት ላይ ጠቅላይ ሚኒስትር ዶክተር ዐቢይ አሕመድ የሰላም ስምምነት ሂደቱን በተመለከተ ወደትግራይ የሚደረጉ በረራዎች እንዲጨምሩ፣ በባንክ እንቅስቃሴ ዙሪያ ያለው ሂደት እንዲፋጠን፣ ሌሎች የእርስ በርስ መተማመንን የሚጨምሩ እና የዜጎችን አኗኗር ቀላል የሚያደርጉ አገልግሎቶች እንዲፋጠኑ መመሪያ ማስተላለፋቸው በብሔራዊ ደህንነት አማካሪያቸው በኩል መገለጹ ተሰምቷል፡፡
ጠቅላይ ሚኒስትሩ የተገኙበት የነዚህ ሁለት ቡድን የፊት ለፊት ምክክር ለያዝነው ሀገራዊ እርቅና ሰላም ከፍተኛ አስተዋጽኦ አለው ብዬ አምናለሁ። ተስፋ ሰጪ እንደሆነ ከተነገረለት ከፕሪቶሪያው የሰላም ስምምነት ወዲህ የመንግስትና ሕወሓት የሰላም ኮሚቴ አባላት በኬንያ ናይሮቢም ተገናኝተው መክረዋል:: በህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አፈ ጉባኤ ታገሰ ጫፎ የተመራ የልዑክ ቡድን መቀሌ ገብቶ ከሕወሓት ቡድን ጋር መክሯል። ከዚህ ሁሉ ሂደት በኋላ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ በተገኙበት የፊት ለፊት ውይይት አድርገዋል። ይሄ የሚያሳየው በሰላም ስምምነት ሂደቱ ላይ ከሁለቱም ወገን ቁርጠኝነት መኖሩን ነው።
እንደ ሀገር ያሳለፍናቸው ሁለት የጦርነት አመታት ምን እንደነበሩ ማስታወስ አይከብዱም። እንደ ሀገር፤ እንደ ህዝብ ብዙ ነገራችንን አጥተንባቸዋል። ሞትና የአካል ጉዳቱን፣ ስቃይና እንግልቱን፣ ረሃብና ስደቱን ደርሶብናል። በኢኮኖሚው፣ በፖለቲካው፣ በማህበራዊ ሕይወታችን ይሄ ነው የማይባል ስብራት ደርሶብናል። አሁን ላይ እያሰቃየን ያለው የኑሮ ውድነት እንኳን በዚህ ጦርነት ተምጦ የተወለደ ነው፡፡
የተፈረመውን የሰላም ስምምነት ሂደት ተግባራዊ ለማድረግ ገና የሚቀሩ ሂደቶች እንዳሉ ይታወቃል። አሁን ባለው ሂደት ግን ሀገራችን ተስፋ ሰጪ በሆነ አስተማማኝ ሰላም ውስጥ መሆኗን መናገር ይቻላል። የቀሩት የስምምነት ሂደቶች ወደ መሬት ወርደው ተፈጻሚ ሲሆኑ ደግሞ ከዚህ በተሻለ ሰላም ውስጥ እንደምንቆም እምነት አለን። እንደ ሀገር እንደ ህዝብ የምንፈልገውን አስተማማኝ ሰላም ለማምጣት ያለን አማራጭ አንድ ብቻ ነው እርሱም የሰላም ስምምነት ሂደቱ ተግባራዊ እንዲሆን የበኩላችንን መወጣት ነው፡፡
የህዝብ ሰላም ያለው በሁለቱ ሀይሎች መተማመን ውስጥ ነው። የሀገር ሰላም ያለው በሰላም ስምምነት ሂደቱ ውስጥ ነው። ይሄ የሰላም ስምምነት ሂደት እንዲቀላጠፍ ሁለቱም ሀይሎች እኩል ሀላፊነት እንዳላቸውና ለትግበራውም ሀገርና ህዝብን ባስቀደመ መልኩ ይሁንታን ማሳየታቸው የሚበረታታ ነው።
የዚህ ዓለም ምርጡ ጀግንነት በሰላም ውስጥ ማሸነፍ ነው። በመግደልና በመሞት ውስጥ ያለው ጀግንነት ጊዜ ያለፈበት ጀግንነት ነው። የዚህ ዓለም የከፋው ጀግንነት ደግሞ በሀገራችን እየሆነ እንዳለው በወንድማማቾች መካከል የሚፈጠር የብኩርና ጀግንነት ነው። ወንድሙን ገሎ ጀግና የተባለ ባለኒሻን ዓለም የላትም። አይደለም ወንድምን ጠላትን መግደል እንኳን በዚህ ዘመን ጀግና አያስብልም፡፡
ጀግንነት ሰላም ውስጥ ብቻ ነው ያለው። ጀግንነት ጥላቻን በፍቅር በመሻር ውስጥ ነው ያለው። እነጋንዲ፣ እነማንዴላ ዓለም መቼም የማትረሳቸው የሰላም ጀግኖች ናቸው። እነ ቼኮቬራ፣ እነማዘር ተሬዛ ዓለም ዳግም እንዲፈጠሩ የምትመኛቸው የሰው ልጅ ሁሉ ጠባቂዎች ነበሩ። ኢትዮጵያ የሰላም ጀግና የላትም። ሀገሬ የፍቅር አርበኛ የላትም። የእኛ ሀገር ጀግኖች በጦርነት ውስጥ የተፈጠሩ ናቸው፡፡
የእኛ ሀገር ጀግኖች በመግደልና በመሞት ውስጥ የቆሙ ናቸው። ጀግና በሰላም ውስጥና በጦርነት ውስጥ ሲፈጠር ሁለት አይነት ነው። የሰላም ጀግና ሞትን የሚጸየፍ፣ ጦርነትን የሚጠላ ነው። የሰላም ጀግና ጥላቻን የሚሸሽ፣ ሰውነትን የሚሰብክ ነው። የጦርነት ጀግና ግን በመግደል የሚደሰት፣ በመሞት የሚኮራ ነው። በማስጨነቅና በመጨነቅ የሚደሰት እንዲገድልና እንዲሞት ምክንያት የሚሻ ነው፡፡
አሁን ላለችው ጎስቋላ ሀገራችን የሚበጃት በሰላም ውስጥ የበቀለ ጀግና ነው። አሁን ላለው ድሀ ህዝብ የሚበጀው እንደ ሙሴ ከባርነት የሚያወጣው የሰላም አለቃ ነው። እንደ ኤልሳ የመከራውን ባህር የሚያሻግር፣ የጉስቁልናውን መንገድ የሚከፍል የፍቅር አርበኛ ነው:: እንደ ሀገር የሰላም ጀግና ርቦናል። ጦርነትን ሽሮ ሰላም የሚሰብክ፣ ፍቅር የሚያስተምር ጳውሎስን እንሻለን።
በሎጥ እኔነት ውስጥ ‹እኛ ወንድማማቾች ነን› መለያየትም ሆነ መጠላላት አያስፈልገንም እንዳለው አብረሃም የፍቅር ሰው እንሻለን። በጦርነት ማሸነፍ ሳይሆን በሰላም ውስጥ ማሸነፍ ነው ሀገራችንን ከኋላ ቀርነት የሚታደጋት። ጀግንነት ካማረን ከውጭ ጠላቶቻችን ጋር ይሁን። ዓድዋ ዛሬም ድረስ በኩራት የሚነሳው ጀግኖቻችን በጠላት ላይ ስለተነሱ ነው።
ዛሬም ድረስ እንደ አዲስ የሚወሳው በአንድነትና በህብረት የማይቻል የሚመስልን እውነት ስለቻልን ነው። ኢትዮጵያዊነት በአንድነት ተነስተን በጋራ ስንቆም እንደ ዓድዋ ነን። በጠላቶቻችን ላይ ጀግና መሆን እንችላለን። ተለያይተን ስንቆም ግን ገድለንና ሞተን ነውር የሞላው የብቻ ታሪክ ከመጻፍ ባለፈ አንጀግንም፡፡
አንዳንድ ጊዜ ለሀገራችን ስንል የምንከፍለው መስዋዕት አለ። አንዳንድ ጊዜ ለድሀ ህዝባችን ስንል የምንተወው ነገር አለ። አንዳንድ ጊዜ ለተስፈኛው ትውልድ ስንል በይቅርታ የምንሻገረው ስህተት ይኖራል። ሀገራችን ውስጥ የተፈጠሩ ጦርነቶች፣ ተፈጥረውም ብዙ ዋጋ ያስከፈሉን ነውጦች ትንሽ ባለማሰብ፣ ትንሽ ባለመታገስ የሆኑ ናቸው፡፡
ዛሬ ላይ ብዙ ዋጋ የከፈልንባቸው የእርስ በርስ ጥላቻዎች ተቀምጦ ባለመነጋገር እና የሰላምን ዋጋ ካለመረዳት የመጡ ናቸው። ይሄን የሚሽር ፖለቲካዊ እርምጃ ያስፈልገናል። ይሄን የሚሽር የሀሳብ ልዕልና ያስፈልገናል። ከመግደልና ከመሞት ወጥተን ጀግና የምንሆንበትን የሰላም መንገድ መፈልግ አሁን ላለችው ኢትዮጵያ ምርጡና አስተማማኙ የእድገት መንገድ ነው። አዎ..አሁን የቀረን አስተማማኙ መንገድ በሰላም ውስጥ ጀግና መሆን ብቻ ነው። አሁን የቀረን አዋጩ መንገድ ተነጋግሮ በመግባባት ችግሮችን መፍታት ብቻ ነው፡፡
ዓለም የሌለው የእኛ የሆኑ አንዳንድ ነውሮች አሉን። ቢፈለጉ ከእኛ ውጭ የትም የማይገኙ አንዳንድ የጦርነትና የጥላቻ እውቀቶች አሉን። በእኛው ተፈጥረው፣ በእኛው በልጽገው እኛኑ የበሉና እየበሉ ያሉ የጦርነት ታሪኮቻችን ብዙ ናቸው። ሰው በጦርነት ባለታሪክ ሊሆን አይችልም። ሀገር ገደሎ በመሞት ውስጥ ስልጣኔዋን ማረጋገጥ አትችልም። ታሪክ ያለው ድህነትን በማሸነፍ ውስጥ ነው፡፡
ጀብድ ያለው ኋላቀርነትን በመርታት ውስጥ ነው። እንደ ሀገር መቀጠል ካማረን ከጦርነት አስተሳሰብ ወጥተን ፍሬ ወዳለው የእድገትና የስልጣኔ እሳቤ መመልከት አለብን። እንደ ህዝብ ታሪካችን እንዲታደስ ሀይል ለበስ ከሆኑ ነውረኛ እውቀቶች ርቀን እርቅና ምክክርን ወዳስቀደሙ የመፍትሄ አቅጣጫዎች መማተር አለብን። ይሄ የአዲሷ ኢትዮጵያ አዲስ እውቀት ነው። ይሄ የነበሩ፣ ያሉና የሚኖሩ ሀገራዊ ችግሮቻችንን የሚቀርፍ የአዲስ ፖለቲካ ተራማጅ ስርአት ነው፡፡
ከዚህ በኋላ የምንመለስበት ትላንት የለም። ከዚህ በኋላ የምንመለስበት የጦርነት ታሪክ ሊኖረን አይገባም። ሀገራችን በብዙ ቆስላለች፣ ህዝባችን በብዙ ደክሟል። ትውልዱ የጦርነት ታሪክ፣ የጥላቻ ተረት መስማት ሰልችቶታል። ጆሮዎቻችን ስለ ሞት መስማት ሰልችቷቸዋል፣ አይኖቻችን የወገንን ስቃይ ማየት ታክቷቸዋል። እስኪ ሌላ እንሁን… እስኪ በመነጋገር መግባባትን፣ በመነጋገር ሀገር መፍጠርን የእውቀታችን መጀመሪያ እናድርገው፡፡
እስኪ ልዩነትን በሰላማዊ መንገድ መፍታት የፖለቲካችንና የፖለቲከኞቻችን ቀዳማይ መርህ ይሁን። ኮሽ ባለ ቁጥር ውረድ እንውረድ ይብቃን። እኔ ያልኩት ከሌላው ጋር አልገጥም ሲል ያን ልዩነት በምክክር መፍታት የቀጣይ እቅዳችን ቁልፍ ሚና ይሁን። በዚህ እውነት ውስጥ ነው አልወለድ ያለችውን ሀገራችንን ልንወልዳት የምንችለው። በዚህ መርህ ውስጥ ነው መምጫዋ የራቀንን ኢትዮጵያ ወልደን የምንስማት፡፡
እንደ መንግስት ሀገር ለማሳደግ እቅድ እናወጣለን። እንደ ግለሰብ ሕይወታችንን ለመቀየር በማሰብ እንጓዛለን። የአመት፣ የሁለት አመት እያልን እቅድና እስትራቴጂ እንነድፋለን። የአጭር ጊዜ፣ የረጅም ጊዜ እያልን በህዝብ ተወካዮች ፊት የጋራ አቅጣጫ እናስቀምጣለን። እኚህ ሁሉ ሀገራዊና ግለሰባዊ እቅዶቻችን የሚሰምሩት በሰላም በኩል ሲያልፉ እንደሆነ ግን ገና አልገባንም።
ሰላም አጥተን ገንብተን የፈረሱበን፣ ክበን የተናዱብን ጉዳዮቻችን ብዙ ናቸው። መንግስት እንኳን በሁለት አመቱ ጦርነት እጅግ በርካታ ትምህርት ቤቶችን፣ ሆስፒታሎችን፣ ጤና ጣቢያዎችን፣ አየር ማረፊያዎችን፣ መንገዶችን ሌሎችንም ብዙ ክበን የተናዱብንን ማህበራዊ መገልገያዎችን በመገንባት ላይ ነው። እቅድ ስናወጣ ሰላምን አጀንዳችን ማድረግ እንዴት አቃተን? ሰላም በሌለበት የሚመጣ ተስፋም ሆነ ብርሃን እንደሌለ እንዴት ጠፋን? እቅዶቻችን ያልሰመሩት፣ ሀገራዊ መሻታችን ያልተሳኩት በእቅዳችን ውስጥ ሰላም ስለሌለ ነው። በእቅዳችን ውስጥ ሰላምና ፍቅር፣ እርቅና ምክክር ሲኖሩ ነው ዘርተን የምንቅመው ወልደን የምንስመው፡፡
ጽንፈኝነትን የሚገል፣ እኔን የሚሽ የሰላም እቅድ ያስፈልገናል። ጦርነትን የሚጸየፍ፣ ጥላቻን የሚንቅ የፍቅር ሀሳብ ግድ ይለናል። ለጀመርነው የሰላም እርምጃ፣ ለጀመርነው የእድገት ራዕይ ጦርነትን ታሪክ ያደረገች ሀገር ታስፈልገናለች። በሰላም ማሸነፍን መልመድ አለብን። ተነጋግሮ በመግባባት ወንድማማችነትን ማስቀጠል እንደሚቻል ማወቅ አለብን።
ተጣልተን መታረቅ ይብቃን። ተገዳድለን መጨባበጥ ይብቃን። ከመጣላታችን በፊት፣ ከመገዳደላችን በፊት መግባባትን እንማር። ፖለቲከኞቻችን የፖለቲካ ጽንሰ ሀሳብ ሊገባቸው ይገባል። ነገ ላይ ትውልድ ገልጦ የሚያነበውን የጥላቻ ታሪክ መጻፍ ሌላ ጥላቻን ከመፍጠር ባለፈ አይጠቅመንም። በሰላም ውስጥ ጀግና መሆን እንደሚቻል የተረዳ ትውልድ ነው የሚያስፈልገን።
በወንድማማቾች መካከል የሚፈጠር ጥል፣ የሚፈጠር አተካራ ሀገር ከማበላሸት ባለፈ ትርፍ እንደሌለው የተረዳ ማህበረሰብ ነው የሚያስፈልገን። በወንድማማቾች መካከል የሚፈጠር የእልኸኝነት ጀብድ ነገ ላይ ምነው ባላደረኩት እንድንል ከማድረግ ባለፈ የሚያመጣልን ልዕልና የለም፡፡
የሁለት አመቱን ጦርነት መለስ ብለን ብናስተውለው ከዚህ እውነት የራቀ ሆኖ አናገኘውም። እነዚያ የሞቱ ነፍሶች፣ እነዚያ በማያውቁትና ባልገባቸው ፖለቲካ የተጎሳቆሉ ህጻናት፣ እነዚያ በረሃብና በስደት የተንገላቱ አዛውንቶች እኛ በፈጠርነው እልኸኝነት የተሰው ናቸው። በሀገር ላይ የተፈጠሩ የኢኮኖሚ ድቀቶች፣ በትውልድ ላይ የተፈጠሩ ስብራቶች፣ በማህበረሰቡ ላይ የተፈጠሩ ጫናዎች በገዛ እጃችን የመጡ ናቸው፡፡
ጀግኖቿን በሰላም ውስጥ የተዋወቀች ሀገር ታስፈልገናለች። ልዩነታችንን በመነጋገር እያጠበብን፣ አንድነታችንን በመመካከር እያጎለበትን ሰላማዊ ሀገር መፍጠር ነው የሚያወጣን። በጦርነት ያለቀስነውን ያክል የምንስቅበት፣ የተጎዳነውን ያክል የምንሽርበት የእርቅና የተግባቦት ጊዜ እንደሚሆን አምናለሁ። ሕወሓትና የፌዴራል መንግስት በሰላም ስምምነቱ ሂደት መሰረት ቀጣይ ሂደቶችን በመከወን ሌላ ተጨማሪ የሰላም ጉልበት እንደሚፈጥሩ በማመን ላብቃ፡፡
በትረ ሙሴ (መልከ ኢትዮጵያ)
አዲስ ዘመን የካቲት 3 ቀን 2015 ዓ.ም