አስማሚ ትርጉም፤
ትዝታ፡- በስሜት የሽመጥ ግልቢያ ነበርን ማስታወስ፣ ትናንትን እያሰቡ መብከንከን፣ ቀድሞ የተፈጸመን ድርጊት እያስታወሱ በስሜት ሃሴት ማድረግ፣ መባባት ወይንም ሆድ መባስ ወዘተ. ይሉት ብጤ የስሜት ቁርኝት ነው። “ትዝታ ነው የሚርበን፤ ላናገኘው ላያጠግበን” እንደተባለው መሆኑ ነው። ታዋቂው ነፍሰ ሄር ፖለቲከኛ አሰፋ ጫቦ በግለ ታሪክ መጽሐፋቸው ውስጥ “ለመሆኑ ትዝታ ምንድን ነው?” ብለው ከጠየቁ በኋላ መልሱን እንዲህ በማለት ከማይመለሱ ጥያቄዎች ጋር በመሸረብ ለማብራራት ሞክረዋል።
“ትዝታ ዘፈን ነው? እንጉርጉሮ? ወይንስ ማላዘን?… ትዝታ ልጓም የለውምና እንዳሻው ወደ ላይ፣ ወደ ታች፣ ወደ ውስጥ፣ ወደ ውጭ፣ ወደ ፊት፣ ወደ ኋላ ወደሚታይ፣ ወይ ሊታይ ወደማይችል፣ ይሄዳል፣ ይጓዛል፣ ይተናል፣ ይበናል፣ ይመላለሳል፣ ይመለሳልም። ‹ማን አለኝ ከልካይ!› እንዲሉ መሆኑ ነው።” ብለዋል። ስንቋጨው፡- ትዝታ መጥቶ ሂያጅ ተመላላሽ የስሜት መንገድ ነው።
ታሪክ፡- በቃል፣ በጽሑፍ ወይንም በተለያዩ የማስታወሻ ምልክቶች ትናንትን የሚተርክ፣ የነበር ኩነቶችንና ክስተቶችን የሚያመለክትንና የሚያጠና ንብርብር ማስረጃ ነው። ታሪክ በባህርይው ባለፉ ጉዳዮች ላይ ትኩረት ስለሚያደርግ አንዳንዴ የተፈጸመው እውነታ ከባህርይውና ከድርጊቱ እየተለጠጠ መጎላመስ፣ አንዳንዴም መበረዝ፣ መከለስ፣ መቅጠንና መድበስበስም ሊስተዋልበት ይችላል።
የሰው ልጅ ከሌሎች ፍጡራን የሚለየው መሠረታዊ የህልውናው ጉዳዮች (መብሉ፣ መጠጡ፣ አልባሳቱና መጠለያዎቹ) ስለተሟሉለት ብቻም ሳይሆን ትዝታና ታሪክም ዋነኛ ጉዳዮቹ ናቸው። ትዝታና ታሪክ ባይኖር የሰው ልጅ ዜና መዋዕል ምን ሊመስል እንደሚችል መገመቱ አይከብድም። በአጭሩ “ተኖረና ተሞተ” ብጤ ሳይሆን አይቀርም።
ነባራዊ እውነታ፡- ያለፉትን ትዝታና ታሪኮች ከዛሬ እውነታዎች ጋር እያዛመዱ መኖር ማለት ነው። “ነበር ባያኮራም” – ለዛሬ መሠረቱ ነውና በቅራኔም ሆነ በስምምነት አብሮ መኖር ግድ ይሏል። ትዝታና ታሪክ ከሰው ልጅ ነባቢት ነፍስ ጋር የተቆራኙ መሆኑም በሚገባ ይታወቃል።
አገሬ እያለፈችበት ያለው መራራ ጉዞ፤
አብዛኛው አገራዊ ታሪካችን በጦርነትና በድል ድርና ማግ እና በትዝታ የተሸመነ መሆኑ ተደጋግሞ ተብሏል። መቼም የተመዘዘ ሰይፍ ለበጎነት አይሰነዘርምና፤ አንዱን ወገን በለስ ሲቀናው ሌላኛው ደመኛ መሸነፉ፣ የተሸነፈው ሲበረታም የአሸናፊው ጉልበት ዝሎ መድከሙ የታወቀ ነው። ይህንን መሰሉን ወታደራዊ ስልትና ታክቲክ አፍታቶ ለመዘርዘር ሙያዊ ብቃታችን (Mandate) ስለማይፈቅድልን የማይነካውን ጉዳይ አንዳፈርም።
መሠረታዊው እውነታ ከላይ የጠቀስነውን ይምሰል እንጂ የሩቆቹም ሆኑ የቅርቦቹ ታሪካዊ ክስተቶችና አገራዊ ፈተናዎች ጥለውበን ያለፉት [በአብዛኛው] መራራ ጠባሳዎችና ክፉ ትዝታዎች ዛሬም ድረስ እንዳስነቡን፣ ጥቁር ማቅ አስለብሰው እንዳስቆዘሙንና ቅስማችንን ሰብረው እንዳስጎነበሱን የሚዘነጋ አይደለም። ይዘንጋ ቢባልስ መች ይሞከራል?
አገራዊ ታሪኮቻችንን ባልተዛቡ ማጣቀሻዎች በመዘከርና በትዝታ መስታወት መለስ ቀለስ በማለት ትናንትን ለመቃኘት መሞከሩ ተገቢም፣ አግባብም ነው የምንለው ያለ ብልሃት አይደለም። “ምክንያቱስ?” ቢባል ከዛሬ እውነታችን ጋር “ነበርን” ጎን ለጎን እያስታወሱ በነፃው ዐምዳችን ላይ ነፃ ሃሳባችንን መሰንዘሩ “ኢትዮጵያ ሆይ!” ለሚለው የውስጥ ጩኸታችን ማስታገሻ ስለሚሆን ብቻም ሳይሆን ትውልድ የሚማረውም በዚሁ መልክ ስለሆነ ጭምር ነው።
ታሪካችን የጦርነት ዐውድማ የበዛበት ነበር የምንለው በቂ ምክንያት ስላለን ነው። ኢትዮጵያ በታሪኳ ውስጥ “ዘገር ነቅንቃ፣ ሠራዊት አሰልፋና ድንበር ጥሳ” የሌላውን አገር ሉዓላዊነት ለመዳፈር ከቶውንም ቢሆን “ጀብደኝነት ተናንቋት”፣ “ወደፊት በሉልኝ ይለይልኝ!” ብላ ፎክራም ሆነ ተግብራ አታውቅም።
በአንጻሩ ግን የሩቅና የቅርብ ተስፋፊና እብሪተኛ ጠላቶቿ ለአንድም ዘመን ዐይናቸውን ከእርሷ ላይ ነቅለው አያውቁም። ዕይታቸውም በርቀትና በቅርበት ከመመልከት እያለፈ ምን ያህል ጊዜ እንደዘመቱባት በታሪካችን ሰነዶች ውስጥ በሚገባ ታጭቆ ተሰንዷል። “የዱባ ጥጋብ ያለ ስንቅ ያዘምታል” እንዲሉ፤ እየተመሙ የወረሯት ጠላቶቿ በሙሉ አፍረው የተመለሱት እጃቸውን አፋቸው ላይ ጭነውና በእፍረት ክንብንብ ተሸፍነው ስለመሆኑም አንጸባራቂውን የታሪካችንን የዘመናት ፈለግ ቆም ብለን በመመርመር ከጫፍ እስከ መዳረሻው መተረክ እንችላለን።
“ላም እሳት ወለደች እንዳትልሰው ፈጃት እንዳትተወው ልጅ ሆነባት” እንዲሉም የውጭ ባዕዳን ተስፋፊና ወራሪ ጠላቶቿ ብቻም ሳይሆኑ “የቤት ውላጅ ሞገደኛና ምናምንቴ” ልጆቿ ተብዬዎችም ሳይቀሩ በጓዳዋ ውስጥ እያንጎዳጎዱ እንደምን ሰላም ሲነሷት እንደኖሩ በታሪክና በትዝታ ብቻ ሳይሆን ነባራዊው የዛሬ እውነታ ጭምር ጥሩ ማሳያ ሊሆን ይችላል።
ኢትዮጵያ የግዛት ሉዓላዊነቷን ለማስከበር ከዋለችባቸው የጦርነት ዐውድማዎችና ከድል አድራጊነቷ መለስ ከባዕዳን ጋር “አትድረሱብኝ አልደርስባችሁም” በማለት በሰላም ቋንቋ ለመነጋገር ካደረገችው ጥረት በላቀ ሁኔታ ለሰላም ድርድርና ስምምነት ወንበር ስባ በመቀመጥ “ጥያቄያቸውን ለማድመጥና መፍትሔ ለመስጠት” ስትተጋ የኖረችው የራሴ ከምትላቸው “የቤት ውላጅ ልጆች” ጋር ነበር/ነውም።
ታሪክንንም ሆነ ትዝታችንን እየጠቃቀስን ጥቂት ዳሰሳ ለማድረግ ወደ ኋለኛው ዘመን ጥቂት አናፈግፍግ። የኢትዮጵያ ዘመነ መሣፍንት እየተባለ በአብዛኞቹ የታሪክ ሰነዶች የሚጠቀሰው ከ18ኛው ክፍለ ዘመን አጋማሽ እስከ 19ኛው ክፍለ ዘመን አጋማሽ ያሉት ዓመታት ናቸው። ወቅቱ አንዱ ብሔር ከአንደኛው ጋር፣ አንዱ መስፍን ከሌላኛው ጋር የሚቆራቆሱበት፣ የሚተነኳኮሱበትና አልፎም ተርፎ በጦርነት እስከ መፋለም የደረሱበት ወቅት ነበር።
አብዛኞቹ የታሪክ ምሁራን እንደሚስማሙት “የዘመነ መሣፍንት የታሪክ ጅማሬና መነሻ ራስ ሚካኤል ሥዑል ዳግማዊ ዓፄ ኢዮአስን ሚያዝያ ወር 1761 ዓ.ም ያስገደሉበት ቀን ሲሆን መጠናቀቂያውም ዳግማዊ ዓፄ ቴዎድሮስ የካቲት ወር 1847 ዓ.ም ሥልጣን ላይ ከወጡ በኋላ ነበር” እየተባለ ይታመናል። የዘመን አቆጣጠሩ አልፎ አልፎ የቀን፣ የወርና የዓመት መፋለስ ስለሚስተዋልበት በዋናነት ታሪካዊ ኩነቱ ላይ ማተኮሩ ይበጃል።
ይህ “የቤት ልጆች” እኔ እበልጥ፤ እኔ እበልጥ ፉክክር የተስተዋለበት ታሪካችን መልኩና አተገባበሩ ይለያይ ካልሆነ በስተቀር ምንም የዓላማ ለውጥ ሳይኖረው ዛሬም እየተሳበ እኛ ዘመን ስለመድረሱ መጠራጠር አይቻልም። የሩቁን ታሪካችንን እዚያው በርቀት እንዲሰነብት ትተነው ወደ ቅርቦቹ ታሪካችንና ትዝታችን መመለሱ ስለሚሻል የመንደርደሪያ ሃሳባችንን የጋዜጣው የዐምድ ስፋት ስለማይፈቅድልን አልፎ አልፎ ምሳሌዎችን ለመጠቃቀስ እንሞክር።
በግርማዊ ቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴ ዘመነ መንግሥት እ.ኤ.አ በ1960 ዓ.ም ግብጽ ውስጥ ተመሥርቶ ኤርትራን ከኢትዮጵያ ለመገንጠል (በወቅቱ ኤርትራ አንዷ የኢትዮጵያ ጠቅላይ ግዛት መሆኗ ይታወሳል) ይንቀሳቀስ ከነበረው ቡድን ጋር እ.ኤ.አ በ1972 በንጉሠ ነገሥቱ ፈቃድ የሰላም ንግግር ለማድረግ ተሞክሮ እንደነበር የመረጃና ደኅንነት ከፍተኛ ባለሙያ የነበሩት በላይ ገብረ ጻድቅ በቅርቡ ባሳተሙት መጽሐፍ ውስጥ ዝርዝሩን አስፍረዋል። (የመረጃና ደኅንነት ሙያ እና የኢትዮጵያ ገጽታው – 2014 ዓ.ም)።
የወታደራዊው ደርግ ሊቀመንበርና በኋላም የኢሕዴሪ ፕሬዚዳንት የነበሩት ኮሎኔል መንግሥቱ ኃይለ ማርያም በጻፉት ቅጽ አንድ “ትግላችን” መጽሐፋቸው ውስጥ በንጉሱ ዘመን ከኤርትራ አማፂያን ጋር የተጀመረው የሰላም ንግግር በእርሳቸውም ዘመነ ሥልጣን ተጠናክሮ መቀጠሉን እንዲህ በማለት ገልጸዋል።
“የኤርትራን ክፍለ አገር ከኢትዮጵያ አስተዳደር ለመነጠል ወይንም ለመገንጠል መንስዔ ስለሆኑት ምክንያቶች፤ ችግሩ ከተከሰተበት ጊዜ ጀምሮ በገንጣዮቹና በኢትዮጵያ አንድነት ኃይሎች መካከል…በቅድመ አብዮት ኢትዮጵያ ለ13 ዓመታት [እና ከዚያም በኋላ] በኢትዮጵያውያን ወንድማማቾች መካከል የሚፈሰውን ደም በአስቸኳይ ለማቆምና ችግሩን በጦር ሜዳ ሳይሆን በጠረጴዛ ዙሪያ በሰላም ለመፍታት በአብዮቱ የመጀመሪያ ዓመታት…እስኪሰለቹን ድረስ ደግመን ደጋግመን ጠይቀናል” (ገጽ 316)።
ችግሩ ከጊዜ ወደ ጊዜ እየተባበሰ መሄዱን ያስተዋሉት የውጭ አገር መንግሥታትም ልክ ዛሬ እየተደረገ እንዳለው በአሜሪካው ፕሬዚዳንት በሚ/ር ጂሚ ካርተርና በወቅቱ የሶቪዬት መሪ በፕሬዚዳንት ሚኻኤል ጎርባቾቭ አማካይነት በኤርትራ አማጽያንና በኢትዮጵያ መንግሥት መካከል ዕርቀ ሰላም እንዲወርድ ሙከራ መደረጉን ሌ/ጄ አዲስ ተድላ ባሳተሙት የግለ ታሪክ መጽሐፋቸው ውስጥ ሂደቱን በዝርዝር ተርከዋል (በገጠመኞች የታጀበ የሕይወት ጉዞ፤ ገጽ 492 – 495)።
ኢህአዴግን ለሥልጣን ያበቃው በሕዝባዊ ወያኔ ሓርነት ትግራይ (ሕወሓት)፣ በኦሮሞ ነፃነት ግንባር (ኦነግ)፣ እና በኤርትራ ሕዝብ ነፃ አውጭ ግንባር (ህግሓኤ) መካከል በግንቦት 1983 ተደጋግሞ ተሞክሮ የከሸፈው የለንደኑ የሰላም ውይይትም በታሪካችን ውስጥ በፀፀትና በቁጭት ሲተረክ የሚኖር የትዝታችን አንዱ ገጽታ ነው።
“የክፉ ዘመን ስህተት ፈጥኖ ከውል አይደርስ” እንዲሉ፤ ኢትዮጵያ የራሴ በምትላቸው ሲፈጸምባት የኖረውና እየተፈጸመባት ያለው አበሳ ገና ተዝቆ ያለቀ አይመስልም። የግዛት አንድነቴን አላስነካም በማለት ከውጭ ወራሪዎች ጋር ስትፋለም ዘመናት መግፋቷ ያነሰ ይመስል፤ በውስጥ መከራዋ እየተናጠችም ቢሆን አንገቷን ሳትደፋ መኖሯ አንድም የፈጣሪዋ ልዩ እርዳታና ጥበቃ ስላልተለያት ሲሆን ሁለትም አናብስት የመከላከያ ጀግኖቿ፣ የሕዝባዊ ሠራዊቶቿና የጸጥታ ኃይሏ እየከፈሉ ባለው የደምና የመስዋዕትነት ውጤት መሆኑ ለአፍታም ቢሆን ሊዘነጋ አይገባም። የሕዝቧ የደጀንነት ሚናና ተግባርም እጅግ ደምቆ ማሽብረቁን የምንገልጸው የትናንት ወዲያውን ታሪክ በማስታወስ ብቻም ሳይሆን የበቀደሙ ትዝታችንም ለምስክርነት የሚደበዝዝ አይደለም።
በቅርቡ የኢትዮጵያ መንግሥት ከሕወሓት ጋር በደቡብ አፍሪካ ፕሪቶሪያ ከተማና በኬኒያ ናይሮቢ ያደረጋቸው የሰላም ንግግሮችና ስምምነት ያለፉት ተከታታይ ታሪኮቻችን ዛሬም እልባት ያለማግኘታቸውን የሚያመለክት ብቻ ሳይሆን የአገሬ “የሰላም ጥማት” ገና እንዳልረካ ጭምር የሚያሳይና የልብ ስፋቷንም መጠን በግልጽ የሚያረጋግጥላት ጽኑ ማስረጃዋ ነው።
በመነሻችን ላይ የተጠቀምንባቸውን የመንደርደሪያ ሃሳቦች እንደገና አስታወሰን ርዕሰ ጉዳያችንን ለመደምደም እንሞክር። አገር በባዕድ ወራሪ ሲደፈር መደበኛ የአገር ሠራዊት ብቻ ሳይሆን ሕዝቡ ራሱ በነቂስ ሆ! ብሎ በመዝመት በደምና በመስዋዕትነት ለሉዓላዊነታችን ክብር ዘብ በመቆም “አገሬን አላስደፍርም” ብሎ በነፍስና በስጋ መወራረድ የተለመደና የሚቀጥል የዜግነት አደራና ግዴታ ነው።
እንዲህ እንደዛሬው የመሰለ መከራ ሲገጥመንና መራር ትዝታውም ከልብ አልጠፋ ብሎ እየተፈታተነ ሲታገለን፤ በሰላምና በጥበብ ችግሮችን ተጋፍጦ ማሸነፍ ብልህነት ብቻም ሳይሆን “ላም እሳት ወለደች…” ብሂልን የሚያስታውስ ስለሆነ ጉዳትን ለሰላም መስዋዕት አድርጎ ማቅረብ ምን ያህል የልብ ስፋት እንደሚጠይቅ ለመረዳት የሚከብድ አይሆንም።
በተለይም ባለፉት ጥቂት ዓመታት በአገሪቱ ላይ የዘነበው መከራና መቅሰፍት ሲታሰብ የደረሰው የሕይወት፣ የአካል፣ የሥነ ልቦና ቀውሱና የቁስ ውድመቱ በኢትዮጵያ ምድር የእስካሁኑ ታሪክ ተፈጽሞ ስለመመዝገቡ እርግጠኛ ለመሆን ጥልቅ ፍተሻ ማድረግን ይጠይቃል። ቢሆንም ግን ለሰላም ሲባል የቆሰሉ እጆችንና ልብን ከፍቶ በከንቱ የሚፈስ የደም ምንጭን ለማድረቅ መወሰን መራራና የሚያንገሸግሽ ቢሆንም የነባር ታሪክሽ ወግ ነውና የእናትነት ግዴታሽን ጨክነሽ ለመወጣት ኢትዮጵያ ሆይ ጽናቱን ይስጥሽ።
“ትዝታዬ ይረፍ፤ ታሪኬም ይተኛ፣
ካሰብኩት እስኪደርስ የሩቅ መንገደኛ።”
አለች ይባላል፤ መከራዋ እንደ ዕንቆቆ መርሮባት ፈተናው ያንገዳገዳት ብሶተኛ እናት። ሰላም ይሁን።
(በጌታቸው በለጠ /ዳግላስ ጴጥሮስ)
gechoseni@gmail.com
አዲስ ዘመን ኅዳር 24/ 2015 ዓ.ም