ለሁለት ዓመታት ያህል በመንግስትና በሕወሓት መካከል ሲደረግ የነበረው ጦርነት ጥቅምት 23 ቀን 2015 በፕሪቶሪያ በተካሄደው የሰላም ስምምነት ህገ መንግስታዊ ስርዓቱን መሰረት አድርጎ ሉዓላዊነትንና የግዛት አንድነትን እና ብሔራዊ ጥቅምን ባከበረ መልኩ ዕልባት አግኝቷል። የተደረሰው ስምምነት ደም አፋሳሹን ጦርነት ለማስቆም፣ ዕርዳታ እና መሠረታዊ አገልግሎቶች ለማስጀመርና የአገሪቱን የድንበርና የግዛት አንድነት እንዲሁም ሕገ መንግስታዊ ስርዓት እንዲከበር የማድረግ ዓላማ አለው።
በአጠቃላይ ሲታይ በደቡብ አፍሪካ ፕሪቶሪያ የተፈረመው የሰላም ስምምነት እንዲሁም ይህንን ተከትሎ በኬንያ ናይሮቢ የተፈረመው ባለ 12 ነጥብ የማስፈጸሚያ ሰነድ የሚከተሉትን መሰረታዊ ነጥቦች የያዘ ነው።
ህገ መንግስታዊ ስርዓትን ማጽናት
ህገ መንግስታዊ ስርዓቱ ከኢፌዴሪ ህገ መንግስት የሚመነጭ ነው። በህገ መንግስቱ አንቀጽ 102 በፌዴራልና በክልል የምርጫ ክልሎች ነጻና ትክክለኛ ምርጫ በገለልተኝነት እንዲካሄድ የማድረግ ስልጣን ያለው የምርጫ ቦርድ እንደሆነ በግልጽ ተደንግጓል። ሆኖም ከዚህ ድንጋጌ በተቃረነ መልኩ በትግራይ ክልል ‹‹ምርጫ›› ተካሂዷል በሚል የትግራይ መንግስት መቋቋሙን ስሁት በሆነ መልኩ ለማወጅ መሞከሩ የሚታወስ ነው። በወቅቱም የኢትዮጵያ መንግስት በትግራይ የተካሄደውን ‹‹ምርጫ›› እንዳልተካሄደ የሚቆጠር፤ በመግለጽ ተቀባይነት እንደሌለው አስታውቆ ነበር።
ይህንኑ ሃሳብ የሚያጸና ውሳኔ በደቡብ አፍሪካ ፕሪቶሪያ በተካሄደው ስምምነትም ስፍሮ እናገኘዋለን። ምርጫው ህገ ወጥ በመሆኑም በትግራይ የሽግግር መንግስት ይቋቋማል፤ በሂደትም ምርጫ ተካሂዶ ክልሉን የሚያስተዳድር መንግስት ይጸናል። ስለሆነም አሁን ባለው ሁኔታ የትግራይ ህዝብን ሰላም የሚያስጠበቅውና ህጋዊ ውክልና ያለውም የፌዴራል መንግስት ብቻ ነው። ከዚህ ውጭ በትግራይ ህዝብ ተመርጫለሁ የሚል ህጋዊ አካል የለም። ስለሆነም ከዚህ ውጭ የሚቀርቡ ጉዳዮች በፕሪቶሪያው ስምምነት መሰረት ተቀባይነት የላቸውም፤ በዚህ ጉዳይ ሊቀመጥ የሚችል ቅድመ ሁኔታም የለም።
በሌላ በኩል የፕሪቶሪያው ስምምነት በግልጽ ካስቀመጣቸው ነጥቦች ውስጥ ሌላኛው በአንድ አገር ውስጥ አንድ መከላከያ ሰራዊት ብቻ መኖር አለበት የሚለው ነጥብ ነው። በስምምነቱ ላይ ዋነኛ ጉዳይ የሆነውን ትጥቅ ማስፈታትን በተመለከተ ሁለቱም ወገኖች በኢትዮጵያ ውስጥ አንድ የመከላከያ ኃይል ብቻ እንዳለ ከስምምነት ደርሰዋል።
ስለዚህም ከተለያዩ አካላት የሚወጡ መረጃዎች እንደሚያመላክቱት ትጥቅ የማስፈታቱን ሂደት በጥሩ ሁኔታ ለማስኬድ እየተሰራ ይገኛል። ይህንን ሁኔታ የተለያዩ ቅድመ ሁኔታዎችን በማስቀመጥ ለማጓተት መሞከር አይችልም። በፕሪቶሪያው ስምምነትም ሆነ በናይሮቢው የማስፈጸሚያ ሰነድ መሰረት ስምነቱን ወደ ተግባር ከመለወጥ ውጭ ሊቀመጥ የሚገባ ቅድመ ሁኔታ አይኖርም።
ሌላው በፕሪቶሪያው ስምምነት የፌዴራል መንግስትና ሕወሓት ውሳኔ ካሳለፉባቸው ጉዳዮች መካከል የኢትዮጵያን ሉዓላዊነትና የግዛት አንድነትን የማስጠበቅ ስልጣን የኢትዮጵያ መንግስት ብቻ እንደሆነ በውል ሰፍሯል። በተለይም ከውጭው ዓለም ጋር የሚደረጉ ግንኙነቶችና ስምምነቶች ሁሉ ሊከናወኑ የሚችሉት በፌዴራል መንግስት ብቻ መሆኑ ከስምምነት ላይ የተደረሰበት ነጥብ ነው። ይህው ሃሳብም በህገ መንግስቱ አንቀጽ 51 ንኡስ አንቀጽ 8 ላይ በግልጽ ሰፍሮ ይገኛል።
በአጠቃላይ የፕሪቶሪያው ስምምነት የኢትዮጵያን ሉዓላዊነትና የግዛት አንድነት የሚያጸናና የዜጎችን ሰቆቃ የሚቀርፍ ስምምነት በመሆኑ ያለምንም ቅድመ ሁኔታ የሚተገበር ነው። ስምምነቱ የኢትዮጵያን አንድነትና ሉዓላዊነት ከማጽናቱም ባሻገር በጦርነት ሰቆቃ ውስጥ የነበሩትን የትግራይ፤ የአማራና የአፋር ህዝቦችን እፎይታ አጎናጽፏል።
ከፕሪቶሪያው ስምምነት ቀጥሎ የተካሄደው የናይሮቢ ስምምነት መተማመንን የፈጠረና ኢትዮጵያ የጀመረችውን የሰላም መንገድ የሚያጸና ነው። በተለይም በጦርነቱ ምክንያት የተቋረጡ መሰረተ ልማቶችንና ሰብዓዊ ድጋፎችን በሚፈለገው መልኩ ለማድረስ መሰረት የጣለ ነው። በዚሁ መሰረትም በትግራይና በአማራ ክልሎች አንዳንድ አካባቢዎች ተቋርጠው የነበሩ የቴሌኮሙኒኬሽን፤ የኤሌክትሪክና የባንክ አገልግሎቶች መልሰው ወደ አገልግሎት እንዲገቡ ለማድረግ አስችሏል። የሕዝቡን ችግር በፍጥነት ለመቅረፍም ሥራዎች በስፋት እየተሰሩም ይገኛሉ።
የፕሪቶሪያው የሰላም ስምምነት ምንም አይነት ቅድመ ሁኔታ እንደሌለውና በስምምነቱ መሠረት እንደሚፈፀምም የኢፌዴሪ የመንግስት ኮሙኒኬሽን አገልግሎት ሚኒስትር ዶክተር ለገሰ ቱሉ መግለጻቸውም የሚታወቅ ነው።
በአጠቃላይ ለአገር ሉዓላዊነትና የግዛት አንድነት መሰረት የሆነውና የዜጎች ሰቆቃ እንዲበቃ ያደረገው የፕሪቶሪያው ስምምነት ቅድመ ሁኔታ የለውም፤ ስለሆነም በስምምነቱ መሠረት መፈጸም ከሁሉም ወገን የሚጠበቅ ግዴታ ነው። ያለውም ብቸኛው አማራጭ ይሄው ብቻ ነው!
ግጭትን በዘላቂነት ማስቆም
የኢትዮጵያ መንግስትና ሕወሓት በደቡብ አፍሪካ ለ10 ቀናት ከመከሩ በኋላ በዘላቂ ግጭት ለማቆም ተስማምተዋል። ባለፉት ሁለት አመታትም የኢትዮጵያ ህዝብ የአገር ሉዓላዊነትና የግዛት አንድነትን ለማረጋገጥ በርካታ መስዋዕትነት የከፈለ ህዝብ ነው።በመስዋዕትነቱም የአገሩን ሉዓላዊነት አጽንቷል፤ አንድነቱን አጠናክሯል፤ ዳር ድንበር አስከብሯል። የኢትዮጵያን መፍረስ ለሚመኙ ባዕዳን በቂ ትምህርት ሰጥቷል።
የኢትዮጵያ ህዝብና መንግስት ወደማይፈልጉት ጦርነት ከመግባታቸው በፊት በርካታ የሰላም ጥረቶችን ሲያደርጉ ቆይተዋል። ሽማግሌዎችንና ታዋቂ ሰዎችን ጭምር በመላክ ለሰላም ያላቸውን ፍላጎት በተደጋጋሚ ገልጸዋል። ከዚህም አልፎ ኢትዮጵያ አውዳሚው ጦርነት ውስጥ ሆና የሰላም ያለህ ሲሉ ቆይተዋል። ለሰላም ሲባል ስትል የትም ቦታ፤ በማንኛውም ጊዜ እና በማንኛውም ርዕሰ ጉዳይ ለመወያየት ፍቃደኝነታቸውን ገልጸዋል። ጥረቱም ፍሬ አፍርቶ በመንግስትና በሕወሓት መካከል ታሪካዊ የሚባል የሰላም ስምምነት ተፈርሟል።
በአፍሪካ ህብረት ጥላ ስር በደቡብ አፍሪካ ፕሪቶሪያ በተካሄደው የሰላም ስምምነት ሁለቱም ወገኖች ታሪክ ጽፈዋል። አስራ ሁለት አንቀጽ ያለው የሰላም ስምምነት በማውጣት ሰላምን አውጀዋል። በፕሪቶሪያ የተካሄደው ስምምነት ለዘመናት መፍትሄን በጠብመንጃ ለማምጣት ሲኬድበት የነበረውን ኋላ ቀር አስተሳሰብ የሰበረና ስልጡን የሆነ አካሄድን ለአገራችን ያስተዋወቀ ነው። ስምምነቱ የኢትዮጵያን መሰረት ከማጽናቱም ባሻገር በጦርነት ሰቆቃ ውስጥ የነበሩትን የትግራይ፤ የአማራና የአፋር ህዝቦችን እፎይታ አጎናጽፏል።
“በዘላቂነት የጦር መሳሪያ ድምጽ እንዳይሰማ ለማድረግ እና በሰሜን ኢትዮጵያ ለሁለት ዓመት የዘለቀው ግጭት እንዲቆም ተስማምተናል” ብለዋል ሁለቱ አካላት።
ሕወሓት እና መንግሥት በአንድ ድምጽ ግጭቱ ከፍተኛ ሰብዓዊ እና ቁሳዊ ኪሰራዎችን አስከትሏል ካሉ በኋላ፤ የኢትዮጵያን ሕዝብ ጥቅም ከግምት በማስገባት ግጭቱን ምዕራፍ ከኋላችን ትተን “በሰላም እና በመቻቻል ለመኖር” ተስማምተናል ብለዋል።
ትጥቅ ማስፈታት
የኢትዮጵን ሉዓላዊነት እና የግዛት አንድነት ማረጋገጥ እና መጠበቅ መሠረታዊ ጉዳይ ነው ያሉት ሕወሓት እና ኢትዮጵያ መንግሥት፤ የኢፌዴሪ ሕገ- መንግሥትን ለማስከበር ተስማምተዋል።
በስምምነታቸው መሠረት ‘ኢትዮጵያ አንድ የአገር መከላከያ ሠራዊት ብቻ ነው ያላት’ በሚለው ጉዳይ ተስማምተዋል። በስምምነቱ ላይ የሕወሓት ኃይሎች “ከቀላል ጦር መሳሪያዎች” ጀምሮ በ30 ቀናት ውስጥ ትጥቃቸውን ይፈታሉ።
የኢትዮጵያ ፌደራል የፀጥታ ኃይሎች “በትግራይ ክልል ውስጥ የሚገኙትን ሁሉንም የፌደራሉን ተቋማትና አየር ማረፊያዎችንና አውራ ጎዳናዎችን ጨምሮ ዋነኛ መሠረተ ልማቶችን” ሙሉ ለሙሉ እንደሚቆጣጠሩ ተጠቅሷል።
“መሬት ላይ ያለውን የጸጥታ ሁኔታ ከግምት ውስጥ በማስገባት የሕወሓት ተዋጊዎች ትጥቅ የሚፈቱበት፣ የሚበተኑበት እና ወደ ማሕበረሰቡ ተመልሰው የሚቀላቀሉበት ዝርዝር ፕሮግራም ላይ ተስማምተናል” ብለዋል። ይህም በአሁኑ ወቅት በተለያየ ደረጃ ተግባራዊ እየተደረገ መሆኑን እየተገለጸ ነው። እስከ ኅዳር 24 ቀን 2015 ድረስ ሕወሓት ከባድ መሳሪያዎችን እንደሚፈታና አነስተኛ መሳሪያዎችን በሂደት የማስፈታቱ ሂደት እንደሚቀጥል በኬንያ የኢትዮጵያ አምባሳደር ባጫ ደበሌ ተናግረዋል።
የሰብዓዊ እርዳታ አቅርቦት
የኢትዮጵያ መንግሥት ከሰብዓዊ ድርጅቶች ጋር በመሆን የሰብዓዊ እርዳታ ለሚያስፈልጋቸው የተፋጠነ እርዳታ እንዲያደርስ ከመግባባት ላይ ተደርሷል።
ካለፈው ሳምንት ጀምሮ ሰብዓዊ ድጋፍ የጫኑ 67 ተሽከርካሪዎች ወደ ትግራይ ተጉዘዋል። ተሽከርካሪዎቹ ወደ ሽሬ፣ ሽራሮና አክሱም ምግብና ምግብ ነክ ያልሆኑ ድጋፎችን ማዳረስ ጀምረዋል። ከ67 ተሽከርካሪዎች መካከልም መድኃኒትና የህክምና ቁሳቁስን የያዘ ተሽከርካሪም መካተታቸውን መረጃዎች ያሳያሉ።
ዓለም አቀፉ የቀይ መስቀል ማህበርም ወደ ሽሬ የሙከራ በረራ ማድረጉንና ርዳታ በአየርም በየብስም ለማድረስ እየሰራ መሆኑን መግለጹ አይዘነጋም። ካሳለፍነው ሳምንት ጀምሮም ማህበሩ በትግራይ በዘጠኝ የህክምና ተቋማት መድሃኒቶችንና አስቸኳይ ዕርዳታዎችን በማከፋፋል ላይ ይገኛል። ዩኑሴፍም ከስምምነቱ ወዲህ ዛሬ ወደ ትግራይ የመጀመሪያው ሕይወት አድን ድጋፍ በተለይም ለህፃናት እና ሴቶች አስገብቷል። እስከ ትላንትና በስቲያ ድረስ ሰብዓዊ ዕርዳታ የጫኑ 317 መኪኖች ወደ ትግራይ ገብተው ለህብረተሰቡ ድጋፍ በማድረግ ላይ ናቸው።
በተመሳሳይም መንግስት አስቸኳይ ሰብዓዊ ድጋፍ የሚያስፈልጋቸውን ዜጎች ለመድረስ ከዓለም አቀፍ የልማት አጋሮች ጋር በመተባበር በሶስት አቅጣጫ (ኮሪደር) ወደ ትግራይ ክልል የሰብዓዊ ድጋፍ እያጓጓዘ መሆኑን የመንግስት ኮሙኒኬሽን አገልግሎት አስታውቋል።
በኢትዮጵያ ፌደራል መንግስትና በሕወሓት መካከል በፕሪቶሪያ የተደረሰውን ስምምነት ተከትሎ መንግስት ቃል የገባውን በትግራይ የሰብዓዊ ድጋፍ አቅርቦትና የመልሶ ግንባታ ስራዎችን እያከናወነም ይገኛል። ባለፉት አራት ቀናትም ዋና ዋና የሰብዓዊ ድጋፍ በተለያየ አቅጣጫ እያቀረብ እንደሚገኝም ነው የመንግስት ኮሙኒኬሽን አገልግሎት የገለጸው።
በዚህም በጎንደር ኮሪደር ሕዳር 17- ከጎንደር በሁመራ በኩል ወደ ሽሬ 1 ሺህ 137 ሜትሪክ ቶን የምግብ እህል የጫኑ 30 የዓለም ምግብ ፕሮግራም የጭነት መኪኖች የተላኩ ሲሆን፥ በተጨማሪም 212 ሜትሪክ ቶን እህል የጫኑ 10 የጭነት መኪኖች ከጎንደር ወደ ማይፀብሪ መጓዛቸውንም አስታወቋል።
ከዚህ ባለፈም ኅዳር 18 ቀን የዓለም ምግብ ፕሮግራም በ24 መኪኖች 1 ሺህ 43 ሜትሪክ ቶን የምግብ እህል ከጎንደር ወደ ሽሬ ሲላክ፥ ኅዳር 19 ቀን ከሽሬ ወደ ማይፀብሪ የእርዳታ እህል የሚያጓጉዙ 11 ከባድ ተሽከርካሪዎች እየተጫኑ መሆኑንም ገልጿል።
ኅዳር 20 ቀን 380 ሜትሪክ ቶን የምግብ ድጋፍ የጫኑ 17 የዓለም ምግብ ፕሮግራም የጭነት መኪኖች ከጎንደር ወደ ማይፀብሪ (ዲማ) መላካቸውን በመጥቀስም፥ ከጎንደር ወደ ሽሬ የምግብ ድጋፍ ያደረሱ 9 የጭነት ተሽከርካሪዎች ወደ ጎንደር ተምለሰዋልም ነው ያለው።
እንዲሁም በኮምቦልቻ ኮሪደር ኅዳር 17 ቀን ከኮምቦልቻ የተነሱ 626 ሜትሪክ ቶን የምግብ ድጋፍን የጫኑ 22 የጭነት ተሽከርካሪዎች ዛታ የደረሱ ሲሆን፥ ኅዳር 18 ቀን የዓለም ምግብ ድርጅት 54 የምግብ እህል የጫኑ ተሽከርካሪዎች ከኮምቦልቻ ተነስተው ወደ ኦፍላ፤ ራያ አላማጣ መድረሳቸውም ተገልጿል።
ኅዳር 19 ቀን በደቡባዊ ዞን ውስጥ ለሚገኙት ባላ፣ ኮረምና ሌሎችም ወረዳዎች የሚላክ የምግብ እህል ጭነት እየተካሄደ መሆኑንም ነው አገልግሎቱ የጠቀሰው። በሰመራ ኮሪደርም ኅዳር 17 ቀን 34 የተለያየ ድጋፍ የጫኑ ተሽከርካሪዎች መቐለ የደረሱ ሲሆን፥ 77 ሜትሪክ ቶን ምግብ ነክ ያልሆኑ ቁሳቁስ፣ 1 ሺህ 223 ሜትሪክ ቶን የምግብ እህል እንዲሁም 95 ሺህ 272 ሊትር ነዳጅ መቐለ ደርሰዋል ብሏል።
ኅዳር 18 ቀን በካቶሊክ ሪሊፍ ሰርቪስ በኩል የተላኩ በድምሩ 175 መኪኖች መቐለ ሲደርሱ፥ ኅዳር 20 ቀን የምግብ ድጋፍ የጫኑ 140 ተሽከርካሪዎች ከሰመራ ወደ መቐለ ጉዞ መጀመራቸውንም ነው ያስታወቀው።
ከዚህ በተጨማሪም ኅዳር 20 ቀን በተባበሩት መንግስታት ድርጅት የሰብዓዊ የአየር በረራ አገልግሎት በኩል ከአዲስ አበባ ወደ መቐለ የመንገደኞች የአውሮፕላን በረራ መከናወኑንም በመግለጫው አመላክቷል።
በአጠቃላይ በኢትዮጵያ መንግስትና በሕወሓት መካከል የተደረሰውን የሰላም ስምምነት ተከትሎ በተለይ በሰሜኑ የአገሪቱ ክፍል በግጭት የተጎዱ የትግራይ፣ አማራና አፋር አካባቢዎች የሰብዓዊ ድጋፍ እንዲደርስ በማድረግ ረገድ በመንግስትና በሰብዓዊ ድጋፍ ሰጪ አካላት ከፍተኛ ትኩረት ተሰጥቶት በመከናወን ላይ ይገኛል።
መንግስት የፕሪቶሪያውን የሰላም ስምምነት መሰረት በማድረግ የሚጠበቅበትን ሃላፊነት በተሟላ መልኩ እየተወጣ ነው። አቅም በፈቀደና አጋር አካላት ማቅረብ በቻሉት መጠን የሰብዓዊ እርዳታና መድሃኒት በሁሉም አቅጣጫ ወደ ትግራይ ክልል እንዲገባ እያደረገ መሆኑን መረጃዎች ያሳያሉ።
የተቋረጡ መሰረተ ልማቶችን መልሶ መገንባት
በፕሪቶሪያው ስምምነትም ሆነ ቀጥሎ የተካሄደው የናይሮቢ ስምምነት መተማመንን የፈጠረና ኢትዮጵያ የጀመረችውን የሰላም መንገድ የሚያጸና ነው። በተለይም በጦርነቱ ምክንያት የተቋረጡ መሰረተ ልማቶችንና ሰብዓዊ ድጋፎችን በሚፈለገው መልኩ ለማድረስ መሰረት የጣለ ነው። በዚሁ መሰረትም በትግራይና በአማራ ክልሎች ተቋርጠው የነበሩ የቴሌኮሙኒኬሽን፤ የኤሌክትሪክና የባንክ አገልግሎቶች መልሰው ወደ አገልግሎት እንዲገቡ ለማድረግ ተችሏል።
በአጠቃላይ ሕወሓት በሕገ መንግሥቱ መሰረት የተቋቋሙ የፌደራል ተቋማትን አክብሮ ለመንቀሳቀስ የተስማማ ሲሆን፣ ይህም የፌደራል መንግሥቱ የፌደራል ተቋማትን ንብረት፣ የአገሪቱን ዓለም አቀፍ ድንበርን የመጠበቅ ኃላፊነት የመንግሥት ይሆናል።
ሕወሓት በየትኛውም የአገሪቱ ክፍል ውስጥ ታጥቀው የሚንቀሳቀሱ አማፂ ቡድኖችን ከመደገፍም ሆነ አብሮ ከመስራት ለመታቀብ ተስማምቷል። የፌደራል መንግሥቱ የአገር መከላከያ ሠራዊትን፣ የደኅንነት አካላትን እና ሕግ አስከባሪ አካላትን ሕገ መንግሥታዊ ግዴታቸውን እንዲወጡ ሲያሰማራ አክብሮ ለመንቀሳቀስ ተስማምቷል።
ሕወሓት ለግጭት እና አመጽ የሚደረጉ ምልመላዎች፣ ሥልጠናዎች ወይም ዝግጅቶችን ከማድረግ ይታቀባል። ሕወሓት ያለ ፌደራል መንግሥቱ እውቅና ከማንኛውም የውጭ አካል ጋር ግንኙነት ማድረግ ያቆማል።
የፕሪቶሪያው ስምምነትም ሆነ በናይሮቢ የተፈረመው የማስፈጸሚያ ሰነድ የሰላም ስምምነቱ ሕገ መንግሥታዊ ሥርዓቱንና ብሔራዊ ጥቅማችንን ባስከበረ መልኩ የተፈጸመ ነው። ስምምነቱ ላይ መድረስ የተቻለውም የጸጥታ ኃይሎችና የደኅንነት ኃይሎች በከፈሉት መስዋዕትነትና ባስመዘገቡት ድል፣ ሕዝቡ በአንድ ላይ በመቆሙ እና መንግሥት ሰላምን ለማምጣት ባለው ቁርጠኝነት ነው።
እስማኤል አረቦ
አዲስ ዘመን ህዳር 23 ቀን 2015 ዓ.ም