ወደ ፍቅር ጉዞ..
ተያይዞ..
ቂምን ከሆድ ሽሮ..
ኦላን ይዞ..
የዛሬ ጽሁፌን በክብር ዶክተር አርቲስት ቴዎድሮስ ካሳሁን ሙዚቃ ስንኞች ጀምሬአለው። በቴዲ ሙዚቃ ውስጥ ኦላ ተብሎ የተጠቀሰ ቃል አለ። ኦላ ማለት ፈጣሪ ማለት ነው። ፍቅርና ፈጣሪ የአንድ ሳንቲም ሁለት መልኮች ናቸው። ፍቅርን ሁሉ እግዚአብሄርን ያውቁታል፣ እግዚብሄርን የሚያውቁ ሁሉ የፍቅር ጌጦች ናቸው። ይሄን እውነት ለማጠንከር አንድ የመጽሀፍ ቅዱስ ጥቅስ ልጥቀስ በቆሮንቶስ መልዕክት ላይ “ፍቅርን የማያውቅ እግዚአብሄርን አያውቅም፣ እግዚአብሄር ፍቅር ነውና”ይላል። በዛው ቅዱስ መጽሀፍ ላይ “በእግዚአብሄር መንፈስ የሚኖሩ እነሱ የእግዚአብሄር ልጆች ናቸው” የሚል ሌላ ጥቅስ አለ። ከዚህ እውነት በመነሳት ምን እንደሚያስፈልገን መረዳት እንችላለን። ከዚህ እውነት በመነሳት አሁን ላይ ምን እንዳጣን ማወቅ ይቻለናል። የሚያስፈልገን እንደ እግዚአብሄር ልጆች በእግዚአብሄር መንፈስ ውስጥ በፍቅር መኖር ነው። ምክንያቱም የእግዚአብሄር መንፈስ ፍቅርና ሰላም፣ አንድነትና ወንድማማችነት ነው። የእግዚአብሄር መንፈስ ጥልና ክርክር፣ ሞትና እንግልት በሌለበት መንገድ ወንድማማችነትን ማጠንከር ነው። እየሄድንበት ያለው ፍቅር አልባ፣ ሰላም አልባ አካሄድ ብዙ ዋጋ አስከፍሎናል። እስኪ ደግሞ ወደ ሰላም እንመለስ፤ እስኪ ደግሞ በፍቅር የእግዚአብሄር ልጆች እንሁን፡፡
ፈጣሪን የሚያውቁ ልቦች ሁሉ ፍቅርን ያውቃሉ፤ ሰላምን ይከተላሉ። ሀገራችን የእምነት ሀገር ናት፤ የእምነት መለኪያውና መመዘኛው ደግሞ የኔ በሚሉት ፈጣሪ ፍቃድ ውስጥ መኖር ነው። ሁላችንንም በሚያግባባ መልኩ የፈጣሪ ፍቃድ ፍቅርና ሰላም፣ ከሰው ልጆች ጋር ሁሉ ተቻችሎ መኖር ነው። የፈጣሪ ፍቃድ ነገሮችን በይቅርታ በማለፍ ውስጥ መኖር ነው። ይሄን የፈጣሪን ፍቃድ ተለማምደን መኖር ይጠበቅብናል። የሚጠቅመን ድምጻዊ ቴዲ አፍሮ እንዳለው ኦላን ይዞ ወደ ፍቅር መሄድ ነው። የሚጠቅመን ቂምን ከሆድ ሽሮ ወደ ፍቅር መጓዝ ብቻ ነው። የሚጠቅመን ኢትዮጵያን አስቀድመን በወንድማማችነት መተባበር ነው። የእኛን ሰላም፣ የእኛን ፍቅር፣ የእኛን አንድነት የሚሹ በርካታ ሀገራዊ ጉዳዮች ከፊታችን አሉ። ፍቅርን ለብሰን፣ ሰላምን ተጎናጽፈን ባለፉት ሁለት ዓመታት በጦርነትና በመለያየት ከከሰርነው በላይ የምናተርፍበት ሰሞን ላይ ነን። በእርቅና በምክክር የጎደሉትን የምንሞላበት፣ የተቀደዱትን የምንደፍንበት ጊዜ ላይ ነን። ኢትዮጵያን የምናፈቅር ሁሉ በዚህ ሰላም ላይ በመሳተፍ የዜግነታችንን መወጣት አለብን።
ሰው ፍቅርን ሲያፈቅር፤ ሰው ሰላምን ሲያስቀድም ያኔ ነው እውነት መሆን የሚጀምረው። ሰላምና ፍቅር በሌለበት ልብ ውስጥ የሚመጣ ጸጋና በረከት የለም። ሀገራችን በረከት የራቃት በእኛ በልጆቿ ሰላም አልባነት ነው። ህዝባችን በችግር፣ በኑሮ ውድነት የሚሰቃየው ፍቅር ባልነካው ልባችን ነው። ሀገራችን በረከቷ እንዲመለስ ፍቅርን አፍቅረን፣ ሰላምን አስቀድመን መራመድ አለብን። ራሳችንን ከፍቅርና ከሰላም ስናርቅ የእግዚአብሄር መንፈስ ይርቀንና በምንም የማይሞሉ ብዙ ጎደሎዎችን፣ ብዙ ቀዳዳዎችን እንፈጥራለን። እነዛ ቀዳዳዎች ወደጦርነት፣ ወደጥላቻ፣ ወደ መገፋፋት ወስደውን እኛንም ሀገራችንንም ያከስሩናል። ባለፉት አመታት በሀገራችን የሆነው ይሄ ነው። የምናሸንፈው በፍቅር ብቻ ነው። የምናሸንፈው በሰላም ብቻ ነው። እንደ ሰላምና ፍቅር ማሸነፊያ አልተሰጠንም፡፡
ሰው ሰለጠነ የሚባለው ችግሩን በሰላም ሲፈታ ነው። ዘመናዊነት ከሚተረጎምባቸው መንገዶች ውስጥ አንዱ ልዩነትን በምክክር መፍታት ነው። የሚቀረን ይሄ ነው፤ ችግሮቻችንን በሰላማዊ መንገድ መፍታትና ልዩነትን በምክክር ማርገብ። እንደሚታወቀው ሀገራችን በድግግሞሽ ፖለቲካ፣ በድግግሞሽ አስተሳሰብ፣ በድግግሞሽ ልማድ ውስጥ ለበርካታ ዘመን ኖራለች። ይሄ አጉል ልማድ ከኪሳራ ባለፈ ያተረፈልን ነገር የለም። አሁን ፖለቲካችንንም፣ አስተሳሰባችንንም፣ ልማዳችንንም ከትላንት አላቀን ሰላምና ፍቅርን ታሳቢ ባደረገ መልኩ ልንለማመደው ይገባል። ታሪክ እንደሚነግረን እኛም እንደምናውቀው አብዛኛው ችግሮቻችን ከፖለቲካና ከፖለቲከኞቻችን ውስጥ የሚወለዱ ናቸው። የፖለቲከኞቻችን ችግር ደግሞ የሀገርና ህዝብ ችግር ሆኖ ብዙ ነገሮችን ሲያሳጣን እያየን ነው። ፍቅር የሌለው፣ ሰላም የሌለው ፖለቲካና ፖለቲከኛ ለሀገር ጠንቅ ከመሆን ባለፈ እርባና የለውም። ከሁሉ በፊት ልቦቻችንን ሰላምና ፍቅር ልናለምዳቸው ይገባል። ፍቅርን የሚያውቅ ልብ በሌሎች ላይ ክፉ መሆን አይቻለውም። ለዛም ነው ከለመድንውና ከተለማመድንው አስተሳሰብ ወጥተን ወደ አዲስ እሳቤ እንራመድ ስል የተነሳሁት፡፡
እንደ ሀገር ጥቅም የሌላቸውን ብዙ ነገሮች ተለማምደናል፤ አሁንም በነዛ ነገሮች ውስጥ ነን። እነዛ ብዙ ነገሮች ዛሬ ላይ ተስፋዎቻችንን፣ ራዕዮቻችንን እየነጠቁን ነው። የኢትዮጵያን ከፍታ፣ ስልጣኔና ቀደምትነት እያደበዘዙ ነው። ለሰላም የተዘረጉ እጆች ለጦርነት ሲበረቱ ስናይ፣ ለአንድነት የተጉ ልቦች ለመለያየት ሲፈጥኑ ስናይ ያሳዝናል። ከለመድነው አስተሳሰብ ወጥተን ለሰላም እጅ መስጠት አለብን። መትረዬስ የያዙ እጆቻችን፣ ቃታ የጨበጡ መዳፎቻችን ወደ ሰላም ወደ ልማት መዞር አለባቸው። ክፋት ያነገቡ ልቦቻችን፣ ጥልና መለያየትን የቀመረ አእምሯችን ወደ ፍቅርና ሰላም መመለስ አለበት። ኢትዮጵያ የምትፈጠረው በዚህ ውስጥ ነው። በሰላም ኢትዮጵያን ማሻገር ቀጣዩ እቅዳችን ሊሆን ይገባል። የኢትዮጵያ ህዝብ ሰላም ወዳድ ህዝብ ነው። ስለሰላም የሚነግረው፣ ስለፍቅር የሚያስተምረው ቢኖር ፍቅርን የሙጥኝ ብሎ የሚኖር ህዝብ ነው።
ታሪኮቻችን የአንድነት ታሪኮች ናቸው። ታሪኮቻችን የሰላም ታሪኮች ናቸው። ከዛ እዚህ የደረስነው አብረን እየበላን አብረን እየጠጣን በክፉና በደጉ ተያይዘን ነው። የኢትዮጵያን ከፍታ የማይፈልጉ አንዳንድ የውስጥና የውጪ ሀይሎች ያጣሉናል እንጂ ህዝባችን ጥንትም አንድ ላይ ነው። ባለፉት ሁለት አመት በሰላም እጦት የከፈልናቸው መስዋዕቶች በእያንዳንዳችን ልብ ውስጥ ጥቁር ጠባሳ ትተው አሉ። እነዛ ጊዜያቶች እንዳይመለሱ ሁላችንም የድርሻችንን መወጣት አለብን። በጋራ እስካልቆምን ድረስ የምንደርስበት የስኬት ተራራ የለም። ተራራዎቻችን ሁሉ በፍቅር ተጀምረው በሰላም የሚያበቁ ናቸው። ኢትዮጵያን እያሰቡ መኖር፤ ይሄን አይነት አካሄድ ደግሞ ኢትዮጵያን እያሰበ የሚኖር ትውልድ ለመፍጠር ወሳኝነት አለው። ዛሬ ላይ በፍቅርና በሰላም የምንዘራቸው ዘሮች ነገ ላይ የስልጣኔ ዋስትናዎቻችን ናቸው።
እንደ መንግስት፣ እንደ ዜጋ ለሀገራችን ብዙ ምኞት አለን። ብንጠየቅ ስለሀገራችን የምንመልሰው በጎ መልስ አለ። ህዝባችንን ከድህነት ማውጣት የሁላችንም የጋራ ፍላጎት ነው። ግን እንዴት የሚለውን መልስ አልደረስንበትም። ህልምና ምኞት እንጂ ህልምና ምኞታችንን ወደመሆን የሚያመጣ ጥበብ የለንም። የሆነ ቦታ ላይ ጥበብ ጎሎናል፤ ምክንያቱም በችግሮቻችን እየተሸነፍን፣ ለችግሮቻችን እጅ እየሰጠን የመጣንበት ሁኔታ ነው ያለነው። የሰው ልጅ ሰላም እስካልገባው ድረስ ምንም ቢገባው ትርጉም የለውም። የምንፈልጋቸው ነገሮች ሁሉ ህልውና የሚያገኙት በሰላም ውስጥ ነው። ሰላም ሀገር ከሚገነባባቸው፣ ትውልድ ከሚቀረጽባቸው አውዶች ውስጥ መሀሉ(አስኳሉ) ነው። ለሀገራችን መሀል መሆን አለብን፤ መሀል ስንሆን ዳርም አለን። ዳር ስንቆም ግን ሌላ ነን። ዳር ቆመን ስለሰላም ማውራት አንችልም። ለሀገራችን ችግር የሆኑ ሰዎች ዳር የቆሙ ሰዎች ናቸው። በሀገራችን ጉዳይ ላይ መሀል ሆነን ስለሰላም መናገር መቻል አለብን፡፡
ሀገራዊ ህልሞቻችን የሚሳኩት ችግሮቻችንን በሰላም መፍታት ስንችል ብቻ ነው። አሁን ላይ አምነን መቀበል የሚገባን እውነት ይሄ ብቻ ነው። ሀገራችንን ከፍ ለማድረግ ልዩነቶቻችንን በንግግር ከመፍታት የተሻለ ሌላ አማራጭ የለንም። ልንለማመደው የሚገባን ህይወት ሰላምን በሰላም ማምጣት እና ሀገርን በምክክር መፍጠር ነው። በጦርነት ሰላምን ማምጣት ሞክረነው ያልተሳካልን ነገር ነው። ስለሀገርና ህዝብ የምናስብ ከሆነ፣ ስለ ተሻለች ኢትዮጵያ የምንጨነቅ ከሆነ ሰላምን በሰላም ማምጣትን መለማመድ አለብን። ችግሮቻችንን በችግር እየፈታን፣ በተፈጠረና በተደራረበ ችግር ውስጥ እየኖርን ህልሞቻችንን መኖር አንችልም። በችግር ላይ ችግር ደርበን ህዝባችንን ከድህነት ማውጣት ያልቻልነው ልዩነታችንን በምክክር ማጥበብ ተስኖን ነው፡፡
ፍየል ወዲህ ቅምዝምዝ ወዲያ ከሆነ ፖለቲካ መላቀቅ አለብን። ፍላጎታችን ሰላም ከሆነ ስለሰላም ብቻ ማውራት አለብን። የሚከፈለውን መስዋዕት ከፍለን የሰላም አምባሳደሮች ልንሆን ይገባል። ከሰሞኑ በህወሀትና በፌደራል መንግስት መካከል ስለተፈረመው የሰላም ስምምነት የኢትዮጵያውያን ደስታ ምን ያክል እንደሆነ ሁላችንም የምናውቀው ነው። ያ ደስታ፣ ያ ፍንደቃ ሊቀጥል ይገባል። ያ እፎይታ፣ ያ እልልታ ሊቀጥል ይገባል። በየትኛውም መስፈርት ቢታይ ኢትዮጵያ ሀገራችን የሚያስፈልጋት ሰላም ብቻ ነው። ህዝባችን በብዙ ድህነት፣ በብዙ ማጣት ውስጥ ያለ ህዝብ ነው። ጦርነትና ሽብር ጨምረንበት በስቃዩ ላይ ስቃይ ልንሆነው አይገባም። በአንድ ሀገር ላይ ሰላም ሁሉንም ነገር ነው። ለዚህ ሁሉንም ለሆነው ሰላም ሁሉንም ሆነን ልንጠብቀው ይገባል። ባለፉት ታሪኮቻችን ሁሉንም አይነት ነውጥ አስተናግደናል፤ ካለፈው ተምረን ወደ ፊት መራመድ ነው የሚያዋጣን፡፡
ዝቅታውን ለምን እንመርጣለን? ጦርነት እኮ ዝቅታ ነው፣ ጥላቻ እኮ ዝቅታ ነው። ከፍታውን እንምረጥ፤ ፍቅር ያለበትን፣ ሰላም የሞላበትን ከፍታ እንከተል። አንድነት የሞላበትን፣ ይቅርታ የተትረፈረፈበትን ከፍታ የእኛ እናድርግ። ሰላም ብዙ ትርፍ አለው፤ በሰላም ማሸነፍን ስላልተለማድን ግን ትርፉን አናውቀውም። በእኔና በእናንተ ሰላም፣ በፖለቲከኞቻችን ሰላም የምታተርፈው ኢትዮጵያ ናት። በኢትዮጵያ ትርፍ ውስጥ ደግሞ ህዝብ ተጠቃሚ ይሆናል። በኢትዮጵያ ትርፍ ውስጥ ደግሞ ትውልድ ይፈጠራል። የመልማት፣ የማደግ፣ የመበልጸግ ህልሞቻችን ሁሉ እውን የሚሆኑት ኢትዮጵያ ሀገራችን በሰላም ማሸነፍ ስትችል ነው። እናም ማሸነፊያችንን ጦርነት ሳይሆን ሰላም እናድርግ። መለያየት ሳይሆን አንድነት እናድርግ። በሰላም የሚያሸንፉ ልቦች፣ በሰላም የሚያሸንፉ መሪዎች፣ በሰላም የሚያሸንፉ ፖለቲከኞች እነሱ እውነተኛ የህዝብ አገልጋዮች ናቸው። እነሱ እውነተኛ የስልጣኔና የዘመናዊነት መጀመሪያዎች ናቸው፡፡
እስከዛሬ ዋጋ ያስከፈሉን ነገሮች እጅግ ቀላል የሆኑ ነገሮች ናቸው። ሰው እጅግ ቀላል ለሆኑ ነገሮች እጅ ሲሰጥ ዋጋ ያላቸውን ጸጋዎቹን መሰወር ይጀምራል። ልብ ብለን ካየን በሰላምና በእርቅ ማለቅ በሚገባቸው ጉዳዮች ነው እየሞትንና መከራ እየደረሰብን ያለው። ማስተዋል ከቻልን ከጦርነት በኋላ በምንታረቅባቸው ነገሮች ነው ከጦርነት በፊት መነጋገር ያልቻልንው። ልብ ካልን ሊረቱን አቅም በሌላቸው ነገሮች ነው እየተረታንና ሰላማችንን እያጣን ያለነው። ሰላማችንን ለትንሽ ነገር አሳልፈን መስጠታችን ይቁም። በትንሽ ነገር ትልቅ ነገራችንን ማጣታችን በዚህ ትውልድ ላይ መቆም አለበት። ሀይላችንን፣ እውቀታችንን፣ ወድማማችነታችንን ለትንሽ ነገር አሳልፈን ስንሰጥ ትልቅ ነገር ይርቀናል፡፡
ወደ ላይ እንይ፤ ምክንያቱም ከላይ ሁሉም አለ። ሰላም እርቦን፣ አንድነት ናፍቆን በየሀይማኖታችን ሰማይ ስናይ ነበር። ፈጣሪ ታርቆን ሰላም ሰጥቶናል። ከሰማይ ማህጸን ላይ ሰላም ተወልዶልናል። ሰላማችንን ማቆየት ግን የእያንዳንዳችን ሀላፊነት ነው። ሰላማችን እንዲቆይ በሰላም ምስራቅ ላይ ቆመን ይቅር ለእግዜርን እንለማመድ። ሞትና መርዶ ባደበየው ልባችን ላይ የሰላምን ጮራ እንፈንጥቅ፤ በእርቅና በይቅርታ በልባችን ላይ ጸሀይ እናውጣ፤ ንጋትን እንፈንጥቅ። ሰላም ጠምቶት የደደረ ጭንጫ ልባችን በፍቅር ይረስርስ። ነፍሳችን እፎይ ትበል፤ በሰላም እንረፍ። እኛ ለመከራዎቻችን ተሸንፈን ሳይሆን፣ መከራዎቻችን በእኛ ተሸንፈው እጅ እንዲሰጡን የሰላም ሰዎች እንሁን። አበቃሁ፤ ለመውጫዬ ግን የመግቢያየን ስንኞች ላስታውስ፤ ሰላም!
ወደ ፍቅር ጉዞ..
ተያይዞ..
ቂምን ከሆድ ሽሮ..
ኦላን ይዞ..
በትረ ሙሴ (መልከ ኢትዮጵ)
አዲስ ዘመን ህዳር 18 ቀን 2015 ዓ.ም