ትውልድ የሚታነጸውና የሚቀረጸው በአርዓያና በምሳሌ ጭምር ነው ብዬ በብርቱ ስለማምን ከዚህ በቀደመው መጣጥፌ ስለ ብራዚሉ ፕሬዚዳንት ሉላ ዳ ሲልቫ አስነብቤ ነበር ። ዛሬ ደግሞ በሌላ አርዓያና ምሳሌ በሚሆን መሪ ተመልሻለሁ። እንደ አምላኬ ፈቃድ በቀጣይ መጣጥፎቼ በየጣልቃው ከአፍሪካም ከሀገራችንም መሪዎች ጋርም አስተዋውቃችኋለሁ ። በዚሁ አጋጣሚ ለልጆቻችንና ለትውልድ ምሳሌና አርዓያ እንድንሆን እጠይቃለሁ ። በነገራችን ላይ ሁላችንም መሪዎች ነንና በየአለንበትና በየተሰማራንበት ኃላፊነታችንን እንወጣ። ኃላፊነታችንን ስላልተወጣን የዘራነውን እያጨድን እንገኛለን።
የቻይና ጉዳይ በተነሳ ቁጥር ዛሬ ድረስ እንደ ትንቢት ወይም ንግርት/forshadow/ ሆኖ የሚወሳ የናፓሊዎን ቦናፓርት አባባል አለ። “ቻይናን ተዋት ። ትተኛ ። አትቀስቅሷት ። ስትነቃ አለምን ስለምትገለባብጠው፤ ብሎ ነበር ። እንደተነበየው አልቀረምም “ቻይናም ናፓሊዎን ያለውን አምና የተቀበለች ይመስል ፤ “ለ200 አመታት በሯን ጠርቅማ ለሽ አለች ፤ “ይለናል የCNN GPS አዘጋጅና የዋሽንግተን ፖስት አምደኛ ፋሪድ ዘካሪያ፡፡ በ1979 ዓ.ም የቻይናም የአለምም ታሪክ ላይመለስ የተቀየረበት አመት ነው። ሶቪየት አፍጋኒስታንን በመውረር የቁልቁለት ጉዞዋን አሀዱ ስትል ፤ ቻይና በምንጊዜም ባለውለታዋ ፕሬዝዳንት ዴንግ ዣውፒንግ አማካኝነት የኢኮኖሚ ማሻሻያን አወጀች ። ከዚህ በኋላ ለ30ና 40 ተከታታይ አመታት በተመዘገበ ዕድገት በመቶ ሚሊየኖች የሚቆጠሩ ዜጎች ከድህነት አረንቋ ወጡ ። ቻይናም ከአሜሪካ ቀጥላ 2ኛዋ ኃያል ሀገር ለመሆን በቃች ። በጥቂት አመታት አንደኝነቱን ከአሜሪካ ትረከባለች ተብሎ ይጠበቃል።
በ2ኛው የአለም ጦርነት አሜሪካ ከጃፓን ጋር ጦርነት ላይ ስለነበረች ፤ የጠላቴ ጠላት ወዳጄ ነው በሚል ስሌት የቻይና ወዳጅ ሆነች። የጸጥታው ምክር ቤት አባል እንድትሆን ደገፈቻት ። ሆኖም ይህ ያልተቀደሰ ጋብቻ ብዙ አልዘለቀም ይለናል ፋሪድ፤ ኮምኒስት ፓርቲው በ1949 ወደ ገዥነት ሲመጣ የሁለቱ ሀገራት እህል ውሃ አለቀ ። ሆኖም ከማኦ ዜዱንግ ሞት በኋላ የሀገራቱ ግንኙነት እንደገና ታደሰ ። ዴንግ ቻይና ከርእዮተ አለም ይልቅ ለኢኮኖሚያዊ ዕድገት ቅድሚያ ትሰጣለች፤ ድመቷ ነጭ ትሁን ጥቁር ዋናው ቁምነገር አይጥ መያዟ ነው ሲሉ በዘመናዊ ቻይና ታሪክ ሲዘከር የሚኖር ንግግር አደረጉ።
ከዚህ በኋላ በቻይና የተስተዋለው ዕድገትና ብልጽግና ተአምር ነው ይለናል ፋሪድ ፤ THE POST-AMERICAN WORLD በተሰኘው ማለፊያ መጽሐፉ ፤ በሰው ልጆች ታሪክ ለመጀመሪያ ጊዜ የቻይና ኢኮኖሚ ለ30 ተከታታይ አመታት በየአመቱ 9 በመቶ ዕድገት አስመዝግቧል። በእነዚህ አመታት ከ400 ሚሊየን በላይ (አንዳንድ ምንጮት 1ቢሊየን ያደርሱታል) ቻይናውያን ከከፋ የድህነት አረንቋ ወጥተዋል ። የአብዛኛው ቻይናዊ ገቢ በሰባት እጥፍ አድጓል ። ቻይና በማደግ ላይ ያሉ ሀገራት የሚጎመጁለት ዕድገት እያስመዘገበች ነው ።
የ”The economist”ጸሐፊ ጄፍሪ ሳቸስ “በአለም የእድገት ታሪክ ቻይና ያስመዘገበችውን ብልጽግና የሚስተካከል የለም፤” ይለናል ። ባለፉት ጥቂት አመታት በቻይና የተመዘገበው ፈጣን የኢኮኖሚ ዕድገት የሚታመን አይደለም ። ለ30 ተከታታይ አመታት በየስምንት አመቱ የሀገሪቱ ኢኮኖሚ በእጥፍ አድጓል ። በ2008 ዓም ቻይና 200 የአየር ማቀዝቀዣዎችን ታመርት ነበር ሲል ፋሪድ ያስታውሰናል ። በ2005 ዓ.ም ግን 48 ሚሊየን ኤይር ኮንዲሽነሮችን አመረተች ። ቻይና ዛሬ ላይ ይሄን በአንድ ቀን ታመርተዋለች ። ፋሪድ ዘካሪያ በ1993 ዓም ሻንጋይን ስጎበኝ ምስራቁ የከተማው ክፍል ፑዶንግ ያለማ ገጠር ነበር ። ዛሬ ግን የፋይናንስ መናኸሪያ ፤ የሰማይ ጠቀስ ፎቆች ከተማ ነው ። በምሽት እንደ ገና ዛፍ የሚያበሩ ህንጻዎች የተገጠገጡበት ይለናል ። ከለንደን የፋይናንስ መናኸሪያ ካናሪ ኋርፍ ስምንት እጥፍ የሚበልጥ ፤ ከቺካጎ አነስ ያለ ከተማ ሆኗል። ቾንግኪንግ በቺካጎ አምሳል እየተገነባ ያለ ሌላ ከተማ ሲሆን፤ በየአመቱ 300ሺህ ሰዎች ለመኖሪያነት ይጎርፉበታል።
በአለማችን በፈጣን ዕድገት የሚያስመዘግቡ 20 ከተሞች በሙሉ በቻይና የሚገኙ ናቸው ። ምዕራባውያን ለንግድ መናኸሪያዋ ሻንጋይ ቢያደሉም ፤ የፖለቲካ ፣ የባህል ፣ የስነ ጥበብና የኢኮኖሚ መዲና የሆነችው የቤጂንግ ዕድገትም ለማመን የሚከብ ነው ። ከተማዋ የ2008 ኦሎምፒክን ለማስተናገድ እንደገና ፈርሳ ተሰርታለች በሚያስብል ሁኔታ ተለውጣለች ። ትነጻጸር ከተባለ የሀውስማን የእጅ ስራ ከሆነችው ፓሪስ ጋር ነው የምትነጻጸር ይለናል ፋሪድ ፤ በቤጂንግ ኦሎምፒክ ሰበብ በአለማችን ትልቁ የአውሮፕላን ማረፊያ ፤ ስድስት የመሬት ውስጥ የባቡር መስመር ፤ 43 ኪሜ የሚረዝም የቀላል ባቡር መስመር ፤ አዳዲስ የመኖሪያ መንደሮች ፤ 125 ኪሜ የሚረዝም የአረንጓዴ ቀበቶ ፤ 12 ስኩየር ኪሜ የሚሰፋ የኦሎምፒክ ፓርክ ገንብታለች ። የአዲሷን ቤጂንግ ፕላን ለተመለከተ ቀድሞ ወደ አእምሮው የሚመጣው የአልበርት ስፒር የእጅ ስራ የሆነችው የድህረ ጦርነቷ በርሊን ናት ። የአልበርት ልጅ አልበርት ስፒር ጁኒየር በቤጂን ኦሎምፒክ ፓርክ የ8 ኪሜ ሰፊ መንገድ ዲዛይን ላይ ተሳትፏል ። ቤጂንግን አባቴ ዲዛይን ካደረጋት በርሊን ጋር ማነጻጸር የሰማይና የምድር ያህል ልዩነት አለው ይለናል ።
ቻይና በአለማችን በድንጋይ ከሰል ፣ በብረትና ሲሚንቶ ምርት የሚወዳደራት የለም ። በ2005 ዓም በቻይና 28 ቢሊየን ስኩየር ፊት ስፋት ባለው ስፍራ ግንባታ ይካሄድ ነበር ። ይህ ከአሜሪካ ጋር ሲነጻጸር በአምስት እጥፍ ይበልጣል ። ባለፉት 15 አመታት ወደ አሜሪካ የምትልከው ኤክስፖርት በ1600 በመቶ አድጓል ። በዘመነ የኢንዱስትሪ አብዮት እንግሊዝ የአለም የስራ ቦታ(ወርክሾፕ)ነበር የምትባለው ። ይሄ ስያሜ ዛሬ ለቻይና ተሰጥቷል ። የአለማችንን ሁለት ሶስተኛ የፎቶኮፒ ማሽን ፣ ማይክሮዌቭ ኦቨን ፣ የዲቪዲ ማጫዎቻና ጫማ ቻይና ታመርታለች ። በአለማችንም በአሜሪካም ግዙፉ ወልማርት በየአመቱ 18 ቢሊየን ዶላር የሚያወጡ ሸቀጦችንና ምርቶችን ከቻይና ያስገባል ። የቻይና ንግድ ከሀገር ውስጥ ጥቅል ምርቷ የ70 በመቶ ድርሻ መያዙ ኢኮኖሚዋ ለአለም ገበያ ምን ያህል ክፍት እንደሆነ ያሳያል ይለናል ፋሪድ ዘካሪያ። ባለፉት 15 አመታት ከአሜሪካ የምታስገባው ሸቀጥና ምርት በሰባት እጥፍ አድጓል። ፕሮክተርና ጋምብል ናው የተባሉ የአሜሪካ ኩባንያዎች ከቻይና በየአመቱ 2ነጥብ5 ቢሊየን ዶላር ገቢ ያገኛሉ። ስታርባክስ ከአሜሪካ ይልቅ በቻይና ያሉ የካፌ ቅርንጫፎቹ ቁጥር ብልጫ አላቸው ። ቻይና ለአለማቀፍ ብራንዶች በሯ ክፍት ነው።
የሚያማምሩ ሕንጻዎቿም በውጭ አርክቴክቶች ዲዛይን የተደረጉ ናቸው ። የቤጂንግ ኦሎምፒክ የመክፈቻ ስነ ስርዓትን እንዲያማክር የመረጠው ታዋቂውን አሜሪካዊ የፊልም ዳይሬክተር ስቴቨን ስፒልበርግን ነው። ቻይና ከፍተኛ የውጭ ምንዛሬ ያካበተች ሀገርም ናት ። 3.13 ትሪሊየን ዶላር አላት ። ከአውሮፓ ሕብረት ሶስት እጥፍ ፤ ከጃፓንና ጀርመን ደግሞ የ50 በመቶ የሚበልጥ፤ ይህ ቻይና ለየትኛውም የኢኮኖሚ ቀውስ የማትበገር ሀገር መሆኗን ያረጋግጣል ። ቻይና የአለማችን ታላቋ ሀገር ናት ። ይህ ብቻ አይደለም ። ቻይና ባለፈጣን የኢኮኖሚ ዕድገት ፣ ግዙፍ ማኑፋክቸረር ፣ 2ኛው ግዙፍ ሸማች ፣ ግዙፍ ቆጣቢና ከአሜሪካ ቀጥላ ለጦሯ ከፍተኛ በጀት የምትመድብ ሀገር ናት።
ቻይና በመቶዎች ለሚቆጠሩ አመታት በድህነትና ኋላቀርነት ፣ በንጉሳዊ አገዛዝ ፣ በእርስ በርስ ጦርነት ፣ ደም አፋሳሽ በሆነ አብዮት ማቅቃለች ። በማኦ ዜዱንግ “ታላቁ እመርታ” የሕብረት ስራ ማህበራትን ለማስፋፋት በተካሄደ የባህል አብዮት 38 ሚሊየን ቻይናውያን አልቀዋል። በሚሊየኖች የሚቆጠሩ ባለሙያዎች፣ ልሒቃንና ተመራማሪዎች በዚሁ የባህል አብዮት ተጨፍጭፈዋል ። ከዴንግ ዣውፒንግ የማሻሻያ መርሀ ግብር በኋላ ግን ቻይናውያን እንደ አንድ ልብ መካሪ እንደ አንድ ቃል ተናጋሪ ሆኑ ይለናል ፋሪድ ዘካሪያ ፤ ዛሬ የቻይና መሪዎች ፣ የንግዱ ማህበረሰብ አባላትና የሕዝቡ ከሊቅ እስከ ደቂቅ ፍላጎት የተጀመረውን ተአምራዊ እድገት ማስቀጠል ነው ። ላለፉት 30ና 40 አመታት እየተመዘገበ ያለው ፈጣንና የኢኮኖሚ ዕድገት ፣ ብልጽግናና መረጋጋት ለአፍታ እንዲስተጓጎል አይፈልጉም።
አሜሪካ ስታስነጥስ የተቀረው አለም ጉፋን ይይዘዋል የሚለው አባባል ዛሬ ዛሬ ቻይና ስታስነጥስ የተቀረው አለም ጉፋን ይይዘዋል ወደሚል እየተቀየረ ነው ። የቻይና የተጽዕኖ አድማስ ወሰን ፣ ባህር ፣ ውቅያኖስና አህጉር አይወስነውም ። እንዲህ ያለ ተጽዕኖ ያላቸው ሀገራት ድንገት አይፈጠሩም ። ኢኮኖሚያዊ ፣ ፖለቲካዊ ፣ ወታደራዊ ተጽዕኗቸው በአንድ ጀምበር አልተፈጠረም። በአንድ ጀምበርም አይጠፋም ። ይህ ተጽዕኖ አሜሪካ፣ ብሪቴን ፣ ፈረንሳይ ፣ ጀርመንና ራሽያ ላለፉት 200 አመታት ከፍ ዝቅ እያለ መቀጠሉን ፋሪድ ያስታውሳል። “DENG XIAOPING: THE MAN WHO MADE MODERN CHINA”የሚለው መጽሐፍ ደራሲ ማይክል ዲሎን ደግሞ፤ ዴንግ ዣዋፒንግ ከ1970ዎቹ ጀምሮ በአራቱ አዘማኞች ማለትም በግብርና ፣ በኢንዱስትሪ፣ በወታደራዊ ሳይንስ፣ በሳይንስና ቴክኖሎጂ 1ቢሊየን ሕዝብ ከድህነት አረንቋ ከማውጣት ባሻገር ቻይናን ከኃያላን ተራ አሰልፈዋል። ይህ የዴንግ ኢኮኖሚ ማሻሻያ ለዘመናዊ ቻይና ወሳኝ መታጠፊያ ነው ። ዛሬ ከአሜሪካ ቀጥላ ግዙፍ ኢኮኖሚ ገንብታለች። የአሜሪካ ጥቅል የሀገር ውስጥ ምርት ከ25 ትሪሊየን ዶላር በላይ ሲሆን የነፍስ ወከፍ ገቢዋ ደግሞ ከ76 ሺህ ዶላር በላይ ነው ።
የቻይና የሀገር ውስጥ ጥቅል ምርት ወደ 20 ትሪሊየን ዶላር የሚጠጋ ሲሆን የነፍስ ወከፍ ገቢዋ ደግሞ ወደ 15 ሺህ ዶላር ይጠጋል ። በ1989 ዓም በቻይናሚን አደባባይ የተቀሰቀሰውን አመጽ በኃይል ለማክሸፍ የሔዱበት ርቀት የፕሬዚዳንት ዴንግን ስም ክፉኛ አጠልሽቶታል ይለናል ማይክል ፤ ዴንግ ዣውፒንግ ሲሹዋን ጠቅላይ ግዛት ከሚገኝ አናሳ ማህበረሰብ የተገኙ ፤ በግል ጥረታቸውና በትምህርት ለቻይና ኮምኒስት ፓርቲ ከፍተኛ አመራርነት የበቁ ናቸው በማለት ይነግረናል ። ዴንግ ዣውፒንግ ራሳቸውን ለኮምኒዝም አሳልፈው የሰጡና ከ1958 እስከ 1961 ዓም ታውጆ የነበረው ታላቁ እምርታ/Great Leap/አካል የነበሩ መሪ ናቸው ይለናል ማይክል፤ ከማኦ ዜዱንግ ጋር በተፈጠረ የመስመር ልዩነት በባህል አብዮቱ ወቅት ለስደት ተዳርገው ነበር ሲል ያስታውሰናል።
ቮጌል እዝራ ደግሞ፤”DENG XIAOPING AND THE TRANSFORMATION OF CHINA” በተሰኘ ማለፊያ መጽሐፉ ፤ ማኦ በአንድ ወቅት ዴንግን የቻይናን ኢኮኖሚ የሰፋ መርፌ ሲሉ ይገልጹታል። ዴንግን የቻይናን ተአምራዊ የኢኮኖሚ ማሻሻያ በጥብቅ ዲሲፕሊን የመሩ ፤ ማኦ ዜዱንግን የማምለክ አባዜን የሞገቱ ይላቸዋል ። የቻይናን የኢኮኖሚና የማህበራዊ ፖሊሲዎችን ለቀቅ በማድረግ ለእድገት ያመቻቹ ፤ ኢኮኖሚውን ለምዕራባውያን የከፈቱ መሪ ፤ የዴንግ ዣውፒንግ የኮምኒስት ፓርቲ አባልነት መሠረት የተጣለው በ1920ዎቹ በሀገረ ፈረንሳይ ትምህርት ላይ እያለ ነው ። ግማሽ ክፍለ ዘመን የተሻገረው የዴንግ የፖለቲካ ህይወት ብዙ ውጣውረድ አሳልፏል ይለናል ቮጌል። በ1978 ወደ ስልጣን እስኪመጡ ድረስ ዘለፋን ፣ መገፋትንና ስደትን አስተናግደዋል። ወደ አገዛዝ ከመጡ በኋላ የተሳሳተውን የማኦ የኢኮኖሚ ፖሊሲ በመቀየር የቻይናን ገበያ ለአለም ከፍተዋል ።
ዴቪድ ሻምባው “CHINA AND THE WORLD”በተሰኘው መጻፉ ቻይና የቀጣዩን አለም አሰላለፍ ከሚወስኑ ኃይላት ግንባር ቀደሟ ናት ይላል ። የትኛውም ሀገር ፣ ማንኛውም ማህበረሰብ የቻይናን ጉልህ ስፍራና ተጽዕኖ ባላየ ባልሰማ ሊያልፈው አይችልም ። ቻይና ከ30 አመት በፊት አይደለም በአለማቀፍ መድረክ በጎረቤቶቿ እንኳ ይሄ ነው የሚባል ተጽዕኖ መፍጠር የማትችል ፤ ጂኦፖለቲካዊ ጠቀሜታዋም ዝቅተኛ ነበር ሲል ያስታውሰናል ። ዛሬ ግን ይለናል ዴቪድ ሻምባው ባስመዘገበችው ፈጣንና ተከታታይ የኢኮኖሚ ዕድገት የተነሳ ተጽዕኖዋን የማታሳርፍበት ሀገርና ዘርፍ የለም ። በማዕድን ፍለጋ ፣ በውጭ ምንዛሬ ገበያ ፣ በመካከለኛው ምስራቅ ነዳጅ ፣ በላቲን አሜሪካ የግብርና ውጤቶችና በሩቅ ምስራቅ ፋብሪካዎች ሳይቀር ተጽዕኖዋ የጎላ ነው። በኢኮኖሚዋ ፣ በወታደራዊ ኃይሏ ፣ እያደገ በመጣው ባህላዊ ተጽዕኖዋ፣ በዲፕሎማሲያዊ እንቅስቃሴዋና በገነባቻቸው ተቋማት ወደፊት እየመጣች ነው። ቻይና የሆሊውድን ፊልም ስክሪፕት ከመመርመር አንስቶ ቻይናን አዋርደዋል ያለቻቸውን ተዋንያን እስከማገድ ደርሳለች።
ስለቻይና እና ቲቤት የሰብዓዊ መብት አያያዝ የተቹት ማት ዲመን ፣ አንጀሊና ጆሊና የዳላይ ሌማ አድናቂው ሪቻርድ ጌሬ ለቻይና ሲባል ከሆሊውድ ገለል እየተደረጉ ነው ። የወል ስትሬት ጆርናሉ የምርመራ ጋዜጠኛ ሰሞኑን ለንባብ ባበቃው “The red carpet” በተሰኘው መጽሐፉ ፤ ሆሊውድም ሆነ ሌሎች የመዝናኛው አለም ኩባንያዎች የቻይናን ሰፊ ገበያ ላለማጣት ሲሉ ራሳቸውን ለቅድመ ምርመራ አሳልፈው ሰጥተዋል ይለናል ። “Seven years in Tibet”እና “TRANSFORMERS 4”የተሰኙ ፊልሞች ከኮምኒስት ፓርቲው የቻይናን ገጽታ ያጎድፋሉ የሚል ቅሬታ ስለቀረበባቸው እንደገና ተከልሰዋል።
ለዚህ ትውልድ የቻይና ፈጣን ዕድገት እንደ ዋዛ የሚታይ ሳይሆን ሌት ተቀን ትኩረት ሰጥቶ የሚከታተለው ጉዳይ ነው ። ባለፉት 40 አመታት እንደቻይና በፍጥነት ያደገና የዘመነ ሀገር የለም ። ከኋላቀርነትና ከድህነት ተላቅቃ በአለማችን 2ኛውን ኢኮኖሚ ገነባች ። በአጭር ጊዜ ውስጥ አንደኝነቱን ከአሜሪካ ትረከባለች ይለናል ዴቪድ ፤ በአለማቀፍ መድረክ የሚኖራት ተጽዕኖም የዛኑ ያህል ያድጋል ።
ከአሜሪካ ፣ ከራሽያ ፣ ከአውሮፓ ሕብረትና ከጎረቤቶቿ ጋር ያላት ግንኙነት በእነሱ ፍላጎትና ጥቅም ብቻ የተመሠረተ መሆኑ ከቀረ ሰነባበተ። ኢኮኖሚዋ አለማቀፋዊ እየሆነ ነው። ከአንታርቲካ እስከ ህዋ እየሰፋ ነው ይላል ዴቪድ ፤ ፈጣኑና ዘመናዊው ወታደራዊ ዕድገቷ በጎረቤቶቿ ላይ ፍርሀትና ስጋት እየፈጠረ ነው። እንደ ጃፓንና ፊሊፒንስ ያሉ የደቡብ ምስራቅ እስያ ሀገራት ለዚህ ጥሩ ማሳያ ናቸው ። እስከ ቀደሙት 20 አመታት ደቡብ ምስራቅ እስያ በአሜሪካ ተጽዕኖ ስር ነበር። የቻይናን ፈጣን ዕድገት ተከትሎ ግን ቀጣናው የሁለቱ ኃያላን መፎካከሪያ እየሆነ ነው ። የጂኦፖለቲክስ ስበቱ ወደ ቻይና እያመዘነ ይገኛል ።
ፈጣሪ የሀገራችንን ሰላም ያጽናልን! አሜን፡፡
በቁምላቸው አበበ ይማም (ሞሼ ዳያን)fenote1971@gmail.com
አዲስ ዘመን ሐሙስ ኅዳር 15 ቀን 2015 ዓ.ም