ከብዙ መውጣት መውረድና ድካም በኋላ የሰሞኑ የሰላም ወሬ በዚህም በዚያም ሲነፍስ መንፈሴ ሁሉ አረፍ አለ። አየሩ ሁሉ ተቀየረ። ጥሩ ጥሩ መዓዛ ሸተተኝ። ሰላም ነዋ፤ የምንሻው ሰላም። ዋጋው ተመን የማይወጣላት ሰላም አይደል። የሰው ልጆች ሁላ፣ በምድር ላይ የሚኖሩ አእዋፋት፣ እንስሳት እጽዋት በአጠቃላይ ህይወት ያላቸው ሁሉ የሚሹት ዋናው ጉዳይ ነውና ሁሌም ‹‹ሰላም… ሰላም… ሰላም ይሁን ለሰው ልጆች ሁሉ ሰላም›› የሚለው ቢዘመር ብሰማው ምኞቴ ነው ። ምክንያቱም ካለሰላም ምንም ነገር የለም። ሰላም ከሌለ ወጥቶ መግባት፤ ዘርቶ መብላት፤ ነግዶ ማትረፍ፤ ወልዶ መዳር… ሁሉ ተረት ተረት ይሆናሉ። አይደለም ይሄ የበሰለ ምግብ ጠቅልሎ መጉረስ ያለ ሰላም ሊሆን አይችልም።
በእርግጥ የጦርነትን አስከፊነት በቦታው ላይ ሆኜ አላየሁም። በአካል ተገኝቼ አልተሰቃየሁም። ነገር ግን የወገኖቼን ስቃይ እዚሁ ሆኜ አይቼዋለሁ። በአእምሮዬ ኖሬዋለሁ። ቤት የነበራቸው ከቤታቸው ተፈናቅለው። ሰርተው የሚበሉ ተመጽዋች ሆነው። ሀብታም ያልናቸው ንብረታቸው ወድሞ፣ ቤታቸው ተቃጥሎ፣ ተዘርፎ የሞቱት ሞተው የተረፉት ሲያነቡ አይቻለሁ። ለቅሶም በማዕረግ ሰላም ሲኖር ነው። ካልሆነ ለቅሶ በአይን በእንባ መሆኑ ቀርቶ አንጀት እያረረ ወደ ውስጥ ይሆናል። አንዳንድ ቦታዎችም ይሄ አልሆነም ለማለት ያስቸግራል። ብዙ አስከፊና አሰቃቂ ነገሮች አጋጥመዋል።
ይሄ ተረት ተረት አይደለም። በሀገራችን የሆነ በየመገናኛ ብዙሀኑ የተዘገበ ነው። የሰብአዊ መብት ተቋማት ያረጋገጡትና የመሰከሩት እውነት ነው። በእኛ ዘመን ባለፉት ሁለት ዓመታት የገጠመን ነው። የጦርነት አስከፊነት በሶሪያ፣ በሊቢያ፣ በየመን፣… እያልኩ ለመጥቅስ አይደለም። ወቅታዊውን ሩሲያና ዩክሬንን እያነሳሁ አይደለም። ያነሳሁት በዘመናችን በአገራችን ያየነውን አስከፊ ጦርነት ነው። ልጅን ከእናት የሚለይ፣ ሰዎችን ከቀያቸው የሚያፈናቅልና የሚያሰድድ፣ ንብረት የሚያወድም፣…. በቅርብ ርቀት ያየነው ነው። በራሳችን ወገን ራሳችን ላይ ሆኖ ስናየው ደግሞ ህመሙ ዘልቆ ወደ ልባችን ይገባል። አንጀት ያላውሳል። እናም ደጋግሜ ደጋግሜ ያንን ሳስብ ጦርነት አይበጅም! ለማንም አይሆንም! ኪሳራ እንጂ ትርፍም የለውም እንድል እገደዳለሁ።
ምክንያቱም ጦርነትን በተለያየ መንገድ አይቼዋለሁ። በማህበራዊ ህይወት፣ በኢኮኖሚ፣ በስነልቡና፣… እንድንፈተን አድርጎናል። እናም ሰው እንዴት ሰላምን ይጠላል ስል ለራሴ ደጋግሜ ሰላምን ሰበኩ። ሁሉም ሰው ወደደም ጠላም የሚያስፈልገው ሰላም ነው። ሰላም አስፈላጊ መሆኑ ማንም ለማንም ሊነግረው አይገባም። ሆኖም ደግሞ የግጭት አትራፊዎች፣ ተቀጣሪና ተገዢዎች አይጠፉምና ከሰላም ይልቅ ጦርነት ሲሰብቁ ይውላሉ፤ ያድራሉ። በፊትም አሁንም ምናልባትም ወደፊት ከሰላም ይልቅ ጦርነት ለእኛ ይሆናል ብለው እጃቸውን የሚያወጡ አይኖሩም ብሎ ማሰብ አይቻልም።
ሰሞኑን ጠቅላይ ሚኒስትሩ በፓርላማ ማብራሪያቸው፣ ‹‹ሰላምን የሚጠሉ የጦርነት ነጋዴዎች አሉ፤ ጦርነት የሚጠሉ የሰላም አምባሳደሮች አሉ። ግራ የሚያጋባው ሰላምም ጦርነትም የማይፈልጉት ላይ ነው›› ያሉትን ደጋግሜ አዳመጥኩ። እርግጥ ነው ሰላምን የማይፈልጉ በመኖራቸው እኮ የሰላም ድርድር ተካሂዶ እንኳን አርፈው አልተቀመጡም። በውጪ ሆነው ቀዝቃዛውን አየር እየተነፈሱ፣ በርገራቸውን አማርጠው እየገመጡ፣ በተንፈላሰሰ ኑሮ ሆነው ልጆቻቸውን እያስተማሩ፣ ወጣቶቹም እየተማሩ፣ ረሀብን ሳያዩ፣ የጥይት ድምጽ ሳይሰሙ ውለው እያደሩ ጦርነት ይቀጥል ሲሉ አደባባይ ወጥተዋል። ምክንያቱም ትርፍ አለዋ። ዶላር ይሰበስቡበታላ። ደሀው እየሞተ እነሱ በግጭት ይነግዳሉ።
ሀገራችን ግን የሚያስፈልጋት ሰላም ነው። ልማት ነው። መስራት መለወጥ ነው። ከተመጽዋችነት መውጣትና መጽዋች መሆኑ ነው ግባችን። ለዚህ ደግሞ ሰላም ያስፈልጋል። ይሄንኑ በማሰብ መንግስት የሰላም እጆቹን የዘረጋው ገና ከለውጡ ማግስት ነው። ለሀገራችን ግጭት ጦርነት አያስፈልጋትም፤ የሚያስፈልገን ሰላም ነው፤ አንድነት ነው። እናም ችግሮችን በራሳችን መንገድ በውይይት መፍታት፣ ጥፋቶችን በይቅርታና በምህረት መተላለፍ ለነገዋ ኢትዮጵያ መሰረት መጣል ነው ብሎ የሰላም እጁን በየአቅጣጫው ዘርግቶ ነበር።
ለዚህም ጠቅላይ ሚኒስትሩ ከሹመታቸው ማግስት በየአካባቢው በመዘዋወር ችግሮችን ለማድመጥ ጥረት አድርገዋል፤ መፍትሄ ያሉትንም ለማስቀመጥ ሞክረዋል። በዋነኛነት ግን ለሁሉም የሚሆነው ሰላምና አንድነት ነውና ይሄንኑ እናስቀድም ሲሉ ደጋግመው ተናግረዋል፤ መክረዋል። ባህላዊ በሆኑ ሃይማኖታዊ በሆኑ ልምምዶቻችን ችግሮቻችንን እንፍታ ሲሉ ነበር ደጋግመው ተማጽነዋል።
በዚህም አላቆሙም እኔ ሰላም ብሆን ጎረቤት ሰላም ውሎ ሰላም ካላደረ ሰላም የለምና እኛ ብቻም ሳንሆን ከጎረቤቶቻችን ጋር ፍቅር እንሁን ብለው ጥረት አደረጉ። ከኤርትራ ጋር 20 ዓመት ላላነሰ ጊዜ የቆየውን ችግር በሰላማዊ ጉርብትና በመቀየር የሰላምን ሀያልነት ለአለም አሳዩ። ይሄም ለትልቅ ሽልማት ያበቃቸው ሀገራችንንም በዓለም አደባባይ ደምቃ እንድታይ የዓለም አቀፍ መገናኛ ብዙሀን አጀንዳ እንድትሆን ያደረገ ክስተት ሆኖ አልፏል። ይሄ በእያንዳንዳችን ልብ ደግሞም በታሪክ መዝገብ ታትሞ ይኖራል።
ሰላም በቀላሉ የማይገኘ ከተገኘም ጉልበቱ ሀያል ነውና ይሄንኑ ሀያልነቱን ለማስቀጠል በተለይም በሰሜኑ የሀገራችን ክፍል የነበረውን ሁኔታ ወደ ሰላማዊ መንገድ ለማምጣት ብዙ ጥረት ተደርጓል። ታዋቂ ሰዎችን፣ የሰላም እናቶችን ወደ ክልሉ ሄደው የሕወሓት አመራሮችን እንዲያነጋግሩ ሰፊ ጥረት፣ ተደጋጋሚ ሙከራ ተደርጓል። ሆኖም ግን በወቅቱ የተገኘው ምላሽ ሰላምን የሚያመጣ ሳይሆን ለብዙዎች ሞት፣ አካል መጉደል፣ መፈናቀል፣ መራብና መጠማት፣ ስቃይና እንግልት ምክንያት ሆኗል።
አባቶች አንድን የሞተ ሰው ጉዳይ ሊያነሱ ሲሉ ‹‹ሙት ወቃሽ አያድርገኝ እና›› ብለው ይጀምራሉ። እናም እላለሁ ያለፈውን በማንሳት ጊዜና ጉልበት ማባከን አያስፈልገም። መጸጸትም አይበጅም። ይልቅ አሁን ለተጀመረው የሰላም አየር መዝለቅ አጋዥ መሆን ያስፈልጋል። ምንም ቢሆን ከትናንቱ ጥፋት የነገው መልካም ነገር ይበልጣል ብሎ ማመን ይሻላል። ለዚህም መስራት ይጠቅማል። መንግስትም ቀደም ሲል ሲለው የነበረውን አሁንም ወደፊትም የሚለውን የሰላም መንገድ አጥብቆ ከመሻት ወደ ኋላ አላለም።
የሀገራችንን ችግሮች በሀገራችን ሽምግልና እንፍታ ብሎ ባይሳካ ለአፍሪካዊ ችግሮች አፍሪካዊ መፍትሄ የሚለው ውጤት አምጥቷል። ይሄ የራስን ችግር በራስ የመፍታት ራዕዩን አሳክቷል። የአፍሪካ ህብረት አደራዳሪነት በደቡብ አፍሪካ ፕሪቶሪያ ከተማ የተደረሰው የሰላም ስምምነትም የመንግስት የቀደመው የሰላም ፈላጊነቱ ውጤት ነው። ለሰላም የዘረጋው እጁንም እስከ ሰላም ስምምነቱ አድርሷል። ይሄ የሰላም መሻት ውጤት አምጥቶ ዛሬ የሰላም አየር በሰሜኑ የኢትዮጵያ ክፍል፣ የሰላም አየር በሀገራችን መተንፈስ ጀምረናል። አሁን የምንጠብቀው ዛሬ የተጀመረው የሰላም አየር ዘላቂ እንዲሆን ነው። ቁስል ጠባሳ እያየን ሳይሆን ቂምና ቁርሾን ትተን በአንድነት ሰላማችንን ማስጠበቅ የጎደለብንን በጋራ መሙላትን መለማመድ አለብን። መቼም በምን ውስጥ ምን አይጠፋም እንደሚባለው ሁሉ በሰላም መሻት ውስጥ ጦርነት ናፋቂ አይጠፋምና ጆሮ እንንፈገው!።
አልማዝ አያሌው
አዲስ ዘመን ሐሙስ ኅዳር 15 ቀን 2015 ዓ.ም