ባሳለፍነው ሳምንት በኢትዮጵያዊው ጀግና፣ በጄኔራል ታደሰ ብሩ የሕይወት ታሪክ ላይ ያጠነጠነ መጽሐፍ በዙፋን ኡርጋ ተጽፎ ለምርቃት በቅቷል። ታሪካችንን ሙሉዕ ለማድረግና የዛሬውና የነገው ትውልድ በጀግኖች አባቶቹና እናቶቹ የጀግንነት ገድል ብሔራዊ ኩራት እንዲኖረው ለማድረግ እንዲህ ዓይነቶቹ መጻሕፍት መታተም ፋይዳቸው ትልቅ ነውና ይበል የሚያሰኝ ነው። በዛሬው ጽሑፌም ከጄ/ል ታደሰ ብሩ የሕይወት ታሪክ ጋር በተያያዘ ሁለት ገጠመኞቼን በማስቀደም ጥቂት ነገሮችን ለማንሳት ወደደኹ።
ጀግናው ጄኔራል ታደሰ ብሩ የኦሮሞ ምድር ያፈራቸው ጀግና ኢትዮጵያዊ ሲሆኑ፤ ጀግንነታቸው ከኢትዮጵያ ምድር አልፎ በአኅጉረ አፍሪካ ጭምር ከፍ ያለ ነው። ስለ እኚህ ከፍተኛ ወታደራዊ መኮንን ጀግንነትና ደቡብ አፍሪካ ድረስ ስለተሻገረው ዝናቸው ያወቅኩባቸው ሁለት አጋጣሚዎች ነበሩ። የመጀመሪያው በደቡብ አፍሪካ፣ በዌስተርን ኬፕ ዩኒቨርሲቲ ትምህርቴን በምከታተልበት ወቅት በሆነ አንድ አጋጣሚ ነበር።
አጋጣሚው ይህን ይመስላል። በምማርበት በዌስተርን ኬፕ ዩኒቨርሲቲ፣ የሮቢን ሙዚየም የማይቡዬ ቤተ-መዛግብት/አርካይቭ ክፍል ኃላፊ፣ የመዛግብት ጥናት መምህራችን የሆነች ደቡብ አፍሪካዊት ፕሮፌሰር ሴት- በአንድ ወቅት በዩኒቨርሲቲው አርካይቭ ካለው የፎቶ ስብስቦች ውስጥ ሁለት ፎቶችን አምጥታ አሳየችኝ። ፎቶዎችን እያቀበለችኝ፤ ‘‘ከነጻነት ታጋያችን፣ ከታታ ማዲባ/ኔልሰን ሮሂላላ ማንዴላ ጋር አብረው የተነሱትን እኚህን ኢትዮጵያዊ፣ ጀግና የጦር መኮንን ታውቃቸው ይሆን?!’’ ስትል ጠየቀችኝ።
እኔም ፎቶውን በኢትዮጵያዊ የጀግንነት ኩራት ትኩር ብዬ እያየሁ… አዎን አውቃቸዋለሁ! ኔልሰን ማንዴላ ያሰለጠኑትና በወቅቱ የኮልፌ ፈጥኖ ደራሽ ማሰልጠኛ አዛዥ የነበሩት ጄኔራል ታደሰ ብሩ ናቸው። አልኳት። ‘‘ኦ! ትክክል ነህ፤ ይገርማል እነዚህን ፎቶዎች ያሳየኋቸው አብዛኛዎቹ ኢትዮጵያውን ተማሪዎች አያውቋቸውም። እነዚህ ፎቶዎች በቤተ-መዛግብታችን/ በአርካይቫችን ውስጥ ለብዙ ጊዜ ቆይተዋል። እዚህ ዩኒቨርሲቲ በስኮላር ሺፕ ለሚመጡ ኢትዮጵያውያን ተማሪዎች ሁሉ፤
‘‘እናንተ ኢትዮጵያውያን ለእኛ ለደቡብ አፍሪካውያን ከዘረኛው አፓርታይድ አገዛዝ ነጻ እንድንወጣ ላደረጋችሁት አስተዋጽኦ ባለውለታዎቻችን ናችሁና ሁሌም አመስጋኞቻችሁ ነን በማለት ይህን ታሪካዊ ፎቶዎች እያሳየኋቸው በኩራት እነግራቸዋለሁ።’’ አለችኝ።
በርግጥም፤ የነፃነት አርበኛ፣ የሰላም አባት፣ የይቅር ባይነት ተምሳሌት፣ የአይበገሬነት የፅኑ መንፈስ ባለቤት፣ የመለያየትንና የዘረኝነትን ፅኑ ግንብ በወንድማማችነት መንፈስ ያፈረሱ፣ የጠላትነትን ክፉ የጥላቻ ዘር በፍቅር ያመከኑ፣ በሰላምና እርቅ ጥሪያቸው ለበቀል የተመዘዙ የጥፋት ሰይፎችን ወደ ሰገባቸው እንዲመለሱ ያደረጉ፣ የሰው ልጆች ሁሉ አንድነት፣ የሰብአዊነት ክብር ምልክት በመባል የሚታወቁት- ታታ ማዲባ/ኔልሰን ማንዴላ- የነፃነት ትግል ሕይወት ውስጥ ኢትዮጵያና ኢትዮጵያውያን ያለን ስፍራ በእጅጉ የተለየና ታላቅ ነው። የዚህ ታሪክ ተጋሪና የፀረ-አፓርታይድ ትግሉ አጋር ከሆኑ ኢትዮጵያኖች መካከል ደግሞ ኢትዮጵያዊው ጄ/ል ታደሰ ብሩ በግንባር ቀደምትነት የሚጠቀሱ ናቸው።
ይህን ኢትዮጵያና ኢትዮጵያውያን በልባቸው ውስጥ ያላቸውን ታላቅ ስፍራና ክብር በተመለከተ፤ ራሳቸው ማንዴላ በፃፉት ‘‘Long Walk to Freedom’’ በሚለው መጽሐፋቸው ውስጥ እንዲህ በማለት ነበር የገለጹት፡-
‘‘Ethiopia has always held a special place in my own imagination and the prospect of visiting Ethiopia attracted me more strongly than a trip to France, England and America combined. I felt I would be visiting my own genesis, unearthing the roots of what made me African.’’
ሌላኛው ጄ/ል ታደሰ ብሩን በይበልጥ ታሪካቸውን እንዳውቅ ያደረገኝ አጋጣሚ ደግሞ ይህን ይመስላል። ከጥቂት ዓመታት በፊት የደቡብ አፍሪካው- የአፍሪካ ናሽናል ኮንግረስ ፓርቲ/ኤ.ኤን.ሲ መቶኛ ዓመቱን ለማክበር ሲዘጋጅ- የደቡብ አፍሪካ መንግሥት በኤ.ኤን.ሲ ፓርቲ እና በኔልሰን ማንዴላና የትግል ጓዶቹ የፀረ-አፓርታድ ትግል ዙሪያ የሚያጠነጥን ዶክመንተሪ ፊልም ለመሥራት የደቡብ አፍሪካ DV8 እና የእንግሊዝ ቢር ኸርት ሊሚትድ የተባሉ የፊልም ካምፓኒዎች የተጣመሩበት ቡድን ወደ ኢትዮጵያ መጥተው ነበር።
ይ ህ ዶክመንተሪ ፊልም ዋናው ዐፅመ-ታሪኩ የሚያጠንጥነው ኔልሰን ማንዴላ ለወታደራዊና ለፖለቲካዊ ስልጠና ወደ ኢትዮጵያ መጥተው ወደ አገራቸው በሚመለሱበት ወቅት በአሰልጣኛቸው በጄ/ል ታደሰ ብሩ በተበረከተላቸው ቡልጋሪያ ሠራሽ ማካሮቭ ሽጉጥ ላይ ነው። ታዲያ ማንዴላ ሥልጠናቸውን አጠናቀው ወደ አገራቸው ደቡብ አፍሪካ ሲመለሱ ይህን ማካሮቭ ሽጉጥ በጆሐንስበርግ ከተማ በሚገኘው የኤ.ኤን.ሲ ፓርቲ ኅቡዕ መሰብሰቢያ ግቢ ውስጥ ባለ አንድ ዛፍ ስር በምስጢር ቀብረውት ነበር።
ማንዴላ በኢትዮጵያ በተመለሱ ማግሥትም በዘረኛው የአፓርታይድ መንግሥት ‘‘በአገር ክዳት’’ ወንጀል ተከሰው ወደ ወኅኒ እንዲወረወሩ ተደረጉ። ማንዴላ ከ27 ዓመታት እስር በኋላ ከእስር ቤት ሲወጡ ያቺን የኤ.ኤን.ሲ ፓርቲ የትጥቅ ትግል ማብሰሪ የሆነች ማካሮቭ ሽጉጥ ከቀበሩበት ለማውጣት ወደ ጆሐንስበርግ የቀድሞው የፓርቲያቸው ኅቡዕ መሰብሰቢያ አዳራሸ ግቢ ከትግል ጓዶቻቸው ጋር አምርተው ነበር።
ይሁን እንጂ ቦታው በመቀያየሩና ጊዜው በመርዘሙ የተነሳ ማንዴላ በትክክል ቦታውን ለመጠቆም አልቻሉም ነበር። እናም ከኢትዮጵያዊው አሰልጣኛቸው ከጄ/ል ታደሰ ብሩ በስጦታ የተበረከተላቸውን ያችን ማካሮቭ ሽጉጥ ከተቀበረችበት ቆፍሮ በማውጣት ከኤ.ኤን.ሲ 100ኛ ዓመት ምስረታ በዓል ጋር በማስተሳሰር- የፀረ- አፓርታይድ ትግል ረጅሙ ጉዞ ታሪካዊ ቅርስና አሻራ እንድትሆን በማሰብ የተደረገው ሙከራም ሳይሳካ ይቀራል።
ሽጉጡን ቆፍሮ ለማውጣት የተደረገው ሙከራ ባይሳካም የደቡብ አፍሪካ መንግሥት በኔልሰን ማንዴላና በኤ.ኤን.ሲ የፀረ-አፓርታይድ ትግል ታሪክ ውስጥ ደማቅ አሻራ ያላትን ከኢትዮጵያዊው ጄኔራል ታደሰ ብሩ ለማንዴላ የተበረከተችውን ሽጉጥ የደቡብ አፍሪካውያን የነጻነት ትግል ቋሚ ማስታወሻ ቅርስ ናት። እናም ታሪኳ በሚገባ ሊዘከር ይገባል ሲል ‘‘the Mandela’s Gun’’ በሚል አርእስት ዶክመንተሪ ፊልም ለመስራት ነበር የደቡብ አፍሪካና የብሪቲሽ የፈልም ካምፓኒዎች የተጣመሩበት ቡድን ወደ አገራችን የመጡት።
በዚህ ዶክመንተሪ ፊልም ፕሮጀክት ውስጥ የማንዴላን የኢትዮጵያ ቆይታ፣ ወታደራዊና ፖለቲካዊ ስልጠና በተመለከተ የጥናት ምርምር ሥራ ለመሥራት Senior Researcher ሆኜ ለመሥራት ዕድሉ ገጥሞኝ ነበር። በወቅቱ በዚህ ፕሮጀክት ውስጥ መሳተፌ ስለ ጄ/ል ታደሰ ብሩ በይበልጥ ለማወቅ ትልቅ ዕድል ነበር የሰጠኝ። ታዲያ በወቅቱ ስለጄ/ል ታደሰ ቃለ-መጠይቅ ካደረኳቸው መካከል ታናሽ እኅታቸው ወ/ሮ ጸሐይ ታደሰ እና የማንዴላ የቅርብ ሰውና ሌላኛው አሰልጣኛቸው የነበሩት ኮሎኔል ፈቃዱ ዋኬኔ ይገኙበታል።
ከ ወ/ሮ ፀሐይ ጋር በነበረን ቆይታም ታላቅ ወንድማቸው ጄ/ል ታደሰ በሕይወት በነበሩበት ጊዜ አስፈላጊ ያሏቸውን መረጃዎችና ታሪካዊ ሰነዶች እንዳስረከቧቸውና እነዚህን መረጃዎችም በብረት ሳጥን ውስጥ ቆልፈው እንዳስቀመጧቸው አጫውተውኝ ነበር። ጄኔራሉ በተለይ ለነጻነት፣ ለፍትሕና እኩልነት ካደረጉት ትግላቸው ባሻገርም ከእነ ፕ/ር ኤፍሬም ይስሐቅ ጋር በመሆን በአብዛኛው በመሀይምነት ጨለማ ውስጥ የነበረውን የገጠሩን ኢትዮጵያዊ ከመሀይምነት እንዲላቀቅ ትልቅ አስተዋጽዖ ማድረጋቸውን ነግረውኛል። በወቅቱ ለማስተማር ይጠቀሙበት የነበረው የፊደል ሰራዊት ያየዘው የፊደል ገበታም ለታላቅ ወንድማቸው፣ ለጄ/ል ታደሰ ብሩ መታሰቢያነት በሚል በመኖሪያ ቤታቸው መግቢያ ግድግዳ ላይ በክብር ተሰቅሎ አስተውያለኹ።
ወ /ሮ ጸሐይ እንደነገሩኝ፤ ወንድማቸው ለነጻነትና ለፍትሕ ሲታገሉ የነበሩ ታላቅ ኢትዮጵያዊ ነበሩ። ከደቡብ አፍሪካውያን የፀረ-አፓርታይድ ተጋድሎ ታሪክ ጋር በተያያዘም ጄኔራሉ ለወታደራዊና ለፖለቲካዊ ሥልጠና ወደ ኢትዮጵያ የመጡትን ኔልሰን ማንዴላን ለእውነትና ለፍትሕ፣ ለሰው ልጆች ነጻነት በጽናት እንዲቆሙ አስተምሯቸዋል። ዘረኛውን የአፓርታይድ ሥርዓት ለማስወገድ ማንዴላና የትግል አጋሮቻቸው ለጀመሩት የትጥቅ ትግል መታሰቢያ ይሆን ዘንድም ጄ/ል ታደሰ ብሩ ለማንዴላ ሽጉጥ አበርክተውላቸው ነበር።
ይህች ሽጉጥም ከነፃነት ምድር፣ ከጥቁር ሕዝቦች የነጻነት ተጋድሎ ታሪክ፣ የጥቁር ሕዝቦች ታሪክ፣ ቅርስና የስልጣኔ እምብርት ከሆነችው ከኢትዮጵያዊው መኮንን ከጄ/ል ታደሰ ብሩ ዘንድ በስጦታ የተገኘች ናትና በማንዴላና በትግል ጓዶቻቸው/በኤ.ኤን.ሲ ፓርቲ ልብ ውስጥ ትልቅ ስፍራ ያላት ናት።
ይ ህች ሽጉጥ ተራ ሽጉጥ አይደለችም፤ ይህች ሽጉጥ የከበረውን የሰውን ልጅ ደም በከንቱ ለማፍሰስ የተሰጠችም ሽጉጥ አይደለችም፣ ይህች ሽጉጥ ኢትዮጵያውያን ጀግኖች ለነፃነታቸው ክብር የከፈሉትን ክቡር መስዋዕትነት የምታሳስብ፣ ለጥቁር ሕዝቦች ነፃነት ተምሳሌት ትሆን ዘንድ ከጥቁሮች አናብስት ምድር ለማንዴላ የተበረከተች ማስታወሻ ናት።
ይህቺ የጄ/ል ታደሰ ብሩ ስጦታ የሆነች ሽጉጥ፤ ማንዴላና ደቡብ አፍሪካውያን ፈጣሪ በሰጠን ውብ ምድር ላይ ነፃነት፣ እውነትና ፍትሕ … ድል ነስተው እስኪወጡ ድረስ የአንቺ ሥፍራ የከበረ የአገራችን ጥቁር አፈር ነው ሲሉ፣ ያችን ነፃነት ዓርማ የሆነች ሽጉጥ በዘረኞቹ የአፓርታይድ አራማጆች ስብከትና የጥይት አረር በጥቁሮች ሕዝብ ደም ለጨቀየችው፣ በሕዝቦቿ ግፍና ሰቆቃ ለተጨነቀችው ምድራቸው በአደራ አስረከቧት።
በኢትዮጵያዊው ጀግና በጄ/ል ታደሰ ብሩ ልብ ውስጥ የናኘው የኢትዮጵያዊነት የነጻነት ሕያው መንፈስ፣ አይበገሬነት፣ ቆራጥነትና የጀግንነት ወኔ- ከኢትዮጵያ ምድር ተሻግሮ በማንዴላና በደቡብ አፍሪካውያን የነጻነት አርበኞች ልብ ውስጥ ትልቅ የነጻነት ሐውልት ተክሏል። እናም ኢትዮጵያዊውን ጀግና፣ ጄኔራል ታደሰ ብሩ የፀረ-አፓርታይድ ትግል አጋር አፍሪካዊው፣ ጄኔራል መባላቸውን ትክክል የሚያደርገው ይህ የከበረ ታሪካቸውና እኛም እንደ ኢትዮጵያዊ የምንጋራው አኩሪ የታሪካችን አካል መሆኑ ነው!!
ሰላም!!
ዲያቆን ተፈሪ ወርቁ
አዲስ ዘመን ሰኞ ጥቅምት 28 ቀን 2015 ዓ.ም