ጥቂት ስለ ርዕሱ፤
ለዚህ ጽሑፍ የሰጠነው ርዕስ የተውሶ መሆኑን ከምሥጋና ጋር ቀድመን ለአንባብያን እናስታውቃለን። የተወሰደውም ከራስ ቢትወደድ መኮንን እንዳልካቸው (ከ1883 – 1956 ዓ.ም) “አልሞትኩም ብዬ አልዋሽም” የመጽሐፍ ርዕስ ነው። መጠነኛ ገጾች ያሉት ይህ ቤሳ ልቦለድ ታትሞ ለንባብ የበቃው በ1944 ዓ.ም ሲሆን ከሌሎች ሰባት ያህል ታሪኮች ጋር ተዳብሎም “አርሙኝ” በሚል ርዕስ ተደጋግሞ በመታተም ለንባብ የበቃ ተወዳጅ ታሪክ ነው።
የትረካው ዋና ይዘት የ1928 ዓ.ም የፋሽስት ወረራን ለመመከት ወደ ጦርነት ዘምቶ የነበረ አንድ ጀግና ኢትዮጵያዊ ወደ ድሉ መቃረቢያ ግድም ከፍ ያለ አካላዊ መስዋዕትነት ከፍሎና መላ ሰውነቱ በመርዝ ጋዝ እንዳልነበረ ሆኖ ወደ ቤቱ ሲመለስ ሚስቱ የፋሽስት መኮንን በመውደድ እንዴት እንደ ካደችው የሚተርክ ነው።
ይኼው የመጽሐፍ ታሪክ ወደ ባለ ሦስት ገቢር ተውኔት ተለውጦ የካቲት 11 ቀን 1952 ዓ.ም በዕለተ ዓርብ የየካቲት 12ን የሰማዕታት መታሰቢያ ምክንያት በማድረግ ከምሽቱ ሁለት ሰዓት ጀምሮ ግርማዊ ንጉሠ ነገሥትና ግርማዊት እቴጌ በክብር እንግድነት በተገኙበት በቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴ ቴያትር (የዛሬው ብሔራዊ ቴያትር) ተመርቆ ለሕዝብ ዕይታ ቀርቦ የነበረ በትራዤዲ ዘውግ ሥር የሚመደብ ቴያትር ነው።
ደራሲው ራስ ቢትወደድ መኮንን እንዳልካቸው ሀገሪቱ ካፈራቻቸው ታላላቅ ልጆቿ መካከል እንዱ ሲሆኑ አርበኛ፣ በቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴ ዘመነ ሥልጣን የመጀመሪያው ጠቅላይ ሚኒስትር፣ ከንቲባ፣ አምባሳደር፣ የውጭ ጉዳይ ተደራዳሪ፣ የሕግ ምክር ቤት ፕሬዚዳንትና የበርካታ መጻሕፍት ደራሲ ነበሩ።
ሕወሓት እየተወነበት ያለው ተመሳሳይ ርዕስ፤
የዛሬው ጥቅምት 24 ቀን 2015 ዓ.ም አሸባሪው ትህነግ ፤ “አልሞትኩም ብዬ አልዋሽም” የሚለውን የልቦለድና የተውኔት ርዕስ ተውሶ “ምታ ነጋሪት፤ ክተት ሠራዊት” በማለት ጥቅምት 24 ቀን 2013 ዓ.ም የሰሜን ዕዝ መከላከያ ሠራዊታችንን ከድቶ ወደ አማራና አፋር ክልሎች ጀሌዎቹን ለወረራ ያዘመተበት ዕለት ነው። ካንዴም ሁለቴ የጀግናውን የመከላከያ ሠራዊትን ክንድ ቀምሶ ቅስሙ የተሰበረው ወራሪው ትህነግ “ካፈርኩ አይመልሰኝ” በሚል እብደትና እብሪት ለሦስተኛ ጊዜ ጦር ሰብቆ ከገባባቸው ክልሎች በምን ዓይነት አይቀጡ ቅጣት ዋጋውን አግኝቶ ወደ ኋላ እንዳፈገፈገና አሁን በምን ዓይነት አጣብቂኝ ውስጥ ገብቶ “በነፍስ ውጭ፤ ነፍስ ግቢ” ትንቅንቅ ላይ እንደሚገኝም የምንሰማውና የምናየው ነው።
ጥቂት የቃላት ማሻሻያ የተደረገበት የሚከተለው ሕዝባዊ የሁለት ስንኝ ግጥም ከላይ የጠቀስነውን ሃሳብ በሚገባ የሚወክል ስለመሰለን እነሆ ልናስታውሰው ግድ ሆኗል፤
“አንተ ጨካኝ ፈሪ ጨካኝ አዘዘብህ፣
እንደ ገና ዳቦ እሳት ነደደብህ።”
እርጅና ጉልበቱን የጫነባቸው ጥቂት የሕወሓት መሪዎች ዓይን እያላቸው የማያዩ፣ ጆሮ እያላቸው የማይሰሙና ልባቸውና መንፈሳቸው በትዕቢት ታጅሎ የወፈረና የሰባ መሆኑ ተደጋግሞ በእኩይ ድርጊታቸው ማሳያነት እውነቱ በግላጭ ሲገለጥ ኖሯል። አካላቸው ብቻም ሳይሆን አስተሳሰባቸው ጭምር የጃጀው እነዚህ መሪ ተብዬዎች የትግራይ ወጣቶችን በጭካኔ ሲያስፈጁና ሕዝቡን ለመከራ ሲዳርጉ አንዳችም የኅሊና ወቀሳ የሚሉት ሰብዓዊ ባህርይ የሚስተዋልባቸው አይመስልም። ይህ ቀን የእብሪት ወረራቸው የተጀመረበት ዕለት ነበር ከማለት ይልቅ “የሙት ዓመት የቁም ዝክራቸውን” ዋንጫ መጎንጨት የጀመሩበት ዕለት ነበር ማለቱ ይቀላል።
እንዴት? ቢሉ “የቀብራቸው ግባ መሬት” የተጀመረው ልክ የጀብደኝነት ወረራ በጀግናው የመከላከያ ሠራዊትና በኢትዮጵያ ሕዝብ ላይ ለመፈጸም “ሀ” ባሉበት ዕለት ስለሆነ ነው። የወረራቸውን ፊሽካ የነፉትም “አልሞትኩም ብዬ አልዋሽም” እንዲሉ የሞታቸውን ከፈን መከናነባቸው እንደማይቀር እያመኑ ነበር።
በዘመነ ደርግ “ገንጣይና አስገንጣይ” እየተባለ በመወገዝ ከቀድሞ የሀገሪቱ ሠራዊት ጋር ለዓመታት በጦር ሜዳ የተፋለመውን ይህንን የባሩድ ሱሰኛ ቡድን ብልሁ የሰሜን አርሶ አደር የገለጸበትን አንድ ታሪክ እናስታውስ። ለገለጻው ማነጻጸሪያነት የተጠቀመው በአካባቢው የመንገድ ኮንስትራክሽን ላይ ይከወን የነበረን አንድ አጋጣሚ መነሻ በማድረግ ነበር።
የመንገዱን ግንባታ ያከናውኑ የነበሩት የአውራ ጎዳና መ/ቤት ባለሙያዎች በታላላቅ ማሽነሪዎች ተራራውን እየነደሉና ለዘመናት ተገሽሮ የኖረውን ታላላቅ ቋጥኝ ድንጋይ እየፈረካከሱና እየከሰከሱ ጥርጊያ መንገዱን ሲያሳምሩ ያስተዋለው ያ ጠቢብ ባለ ሀገር ነገሩን ይከታተል የነበረው በአንክሮ ነበር። እናም የመከላከያ ሠራዊቱ የወራሪውን ኃይል በአይቀጡ ቅጣት እያርበደበደ ወደፊት ሲገሰግስና የሽምቅ ተዋጊ ኃይሉም እንዳልነበረ ሆኖ ሲበታተን አስተውሎ ከሚከሰከሰው የቋጥኝ ድንጋይ ጋር በማመሳሰል እንዲህ በማለት እንደተቀኘ በወቅቱ በስፋት ይወራ ነበር።
ድንጋይ አይሞት ያሉት ሞት ተፈረደበት፣
እየከሰከሱ መኪና ነዱበት።
እስቲ በል ተፈጨው እስቲ በል ተቦካ፣
እስቲ በል ተጋገር፣
አንተም ማን አለኔን አብዝተኸው ነበር።
የዚህ አርሶ አደር ግጥም ለትናንት ብቻም ሳይሆን ለዛሬም ጭምር የሚያስተላልፈው ወቅታዊ መልእክት ከዐውዳችን ጋር የሚስማማ ነው።
የአሸባሪው ትህነግ ትልቁ ችግሩ ፈሪ ሆኖ እያለ ራሱን እንደ ጀግና ቆጥሮ ማቅራራቱ ነው። ፊሪ ሰው ዘመኑን የሚፈጀው እንደባነነና እንደ በረገገ ነው። ስለዚህም ሳይሆን አይቀርም “ፈሪ ካልጋ ላይ እየባነነ መውደቅ ልማዱ ነው” የሚባለው። ከተረጋጋ እንቅልፍ እየባነነ የሚያነጋ ሰው በጨለማ መደነባበሩ አይቀሬ ነው። ዕቃ መስበር ብቻም ሳይሆን እርሱም መሰበሩ አይቀርም።
የሕወሓት ሞት “ሀ” ብሎ የጀመረው መንግሥታዊ ሥልጣኑን በያዘ ማግሥት ነበር። ከዚያን ጊዜ ጀምሮ ነው “አልሞትኩም ብዬ አልዋሽም” ማለትን መለማመድ የጀመረው። አንዳንድ አብነቶችን እናስታውስ። ጀግና ማለት ካሸናፊነቱ በኋላ ተረጋግቶ ለአዳዲስ ድሎች የሚዘረጋ እንጂ የትናንቱን ገድል እየተረከ በማላዘን የሚኖር አይደለም።
ትህነግ ግን እንደዚያ አልነበረም። “ራሱን ጀግና” እያለና እያሰኘ በማንቆለጳጰስ የኖረው የደርግ ሥርዓትን በየደቂቃውና በየሰኮንዱ እያብጠለጠለና የእርሱን ሠራዊት ጀግንነት እየተረከና እያስተረከ ነበር። ገና በጠዋቱ በአብዛኛው የኢትዮጵያ ሕዝብ ልብ ውስጥ ሞቶ መቀበሩ ጠፍቶት ነበር ማለት አይቻልም። ለማሳያነትም የስሙን፣ የአርማውንና የርዕዮተ ዓለሙን ይዘት ማስታወሱ ብቻ በቂ ይሆናል።
ሀገር እየመራ እያለ እንኳን “ሕዝባዊ ወያኔ ሓርነት ትግራይ – ሕወሓት” / ትህነግ የሚለውን የጫካ ስሙን ለመለወጥ አልፈለገም። ይህ የሚያሳየን የመንግሥትን ሥልጣን ጨብጦ እንኳን ፍርሃቱ እንዳለቀቀውና የሕዝብ ቁጣ ወደ ወጣበት ጫካ እንደሚመልሰው በማመኑ ነበር። ፍርሃቱ ከዓመታት በኋላ ተግባራዊ መሆኑ በእጅጉ የሚያስገርም ነው። በአርማውም ላይ ጎላ ብሎ ይታይ የነበረው የክላሽንኮቭ ጠብመንጃ መሆኑ ትዝ ይለናል። “አብዮታዊ ዲሞክራሲ” የሚለው የፖለቲካ ፍልስፍናውም ሞቶ መቃብር ውስጥ ከገባው የምሥራቅ አውሮፓ ኮሚኒስታዊ ርዕዮተ ዓለም የተቀዳ ነበር።
ለምን እንደዚህ ሲሸበር ኖረ? መልሱ ግልጽና ቀላል ነው። እብሪተኛና ፈሪ ስለሆነ ብቻ ነው። በጓዳውና በውስጡ “አልሞትኩም ብዬ አልዋሽም” የሚለው እውነት ያቃጭልበታል፤ ላይ ላዩን ግን “ጀግና” እያለ ራሱን ሲሸነግል ኖሯል። ስለዚህም ነው ሕወሓት በአገዛዝ ዘመኑ ሳይቀር የኖረው በፍርሃት እያላበው ነበር የምንለው።
በዚህ ጸሐፊ እምነት ይሄው ቡድን ከጅምሩ የሰሜንን ዕዝ የተዳፈረው “አሸንፋለሁ” በሚል ሞራል ሳይሆን ፍርሃት ውስጡን እየናጠ መረጋጋት ስለነሳው ብቻ ነው። ቀደም ሲል በኢትዮጵያና በኢትዮጵያዊያን ላይ የፈጸማቸው በደሎችና የዘመነ ገዢነቱ ግፎችና ዘረፋ መረጋጋት ስለነሳው ጀግናውን የሉዓላዊነታችንን ዘብ ለመዳፈር በርግጎ ዘራፍ አለ። ድል የቀናው ስለመሰለውም በአደባባይና በዓለም ፊት “ኢትዮጵያን ለማፈራረስ እስከ ሲዖል ድረስም ቢሆን እወርዳለሁ” በማለት መሬት ጠበበኝ ብሎ እስከ ማቅራራት ደረሰ።
በሁለተኛውና በሦስተኛው ወረራውም የግፉ ዋንጫ ሞልቶ እስኪገነፍል ድረስ ንጹሐንን ለመጨፍጨፍ፣ የሀገርን ንብረትና ሀብት ለማውደም በግፍ ጭካኔ በረታ። ፍርሃቱ ባያስበረግገው ኖሮ በተቀጠቀጠ ሸንበቆ የሚመሰለውን የጀሌውን ሠራዊት አሰልፎ እንደምን ከመቶ አሥራ አምስት ሚሊዮን በላይ ከሚገመት ሕዝብና ከሕዝብ አብራክ ከወጣ ጀግና ሠራዊት ጋር ይላተም ነበር?
ፈሪ ባይሆን ኖሮ ለሃያ ሰባት ዓመታት ያህል በመጨረሻው የሀገሪቱ የሥልጣን ወንበር ላይ ተቀምጦ እያለም ቢሆን ከየካቲት እስከ የካቲት የዋለበትን የጦር ሜዳ ፊልም ሲያሳየን ባልኖረ ነበር። ፈሪ ባይሆን ኖሮ በአምሳሉ የቀረጻቸውን ጋዜጠኞችና ፕሮፓጋንዲስቶች ከበረሃ የቋንቋ አጠቃቀምና ድምጸት በማረቅ ባስተካከላቸው ነበር። ዛሬም ከሠላሳ ዓመት በኋላ እንደ ስሙና አርማው ለመለወጥ እየተናነቀው ያለው የቅስቀሳ ስልቱ ነው። ፍርሃቱን የሚሸሽግበት ውሸት፣ ትምክህት፣ እብሪት፣ ትዕቢት፣ ማን አለብኝነት ዋናዎቹ የትህነግ መታወቂያዎች ናቸው።
የሦስተኛ ዙሩ የወረራ ታሪኩ ተቀልብሶ ሊደመደም ቋፍ ላይ ደርሶ የመቃብር ጉድጓዱን ቁልቁል እያስተዋል እንኳን “ጀግናው የሕወሓት ሠራዊት” እያለ ማቅራራቱ ፈሪ ብቻ ተብሎ የሚደመደም ሳይሆን “ጅል” የሚል ቅጽልም ሊታከልበት ይገባል። “ፈሪና ጅል ሁለት ጊዜ ያለቅሳል። አንዴ ሲመክሩት አንዴ ሲቀጡት” ይባላል። የሕወሓት ፈሪነትና ጅልነት ግን ከሁለትም አልፎ ሦስተኛ ደረጃ ላይ ደርሷል። “አንድም ሲመክሩት፣ አንድም ሲያስመክሩት፣ አንድም ሲቀጡት። ” ሀገረኛው ተሟጋች፤ “ምንሽም ምንሽ አይበጀን፤ ሞትሽ ነው የሚክሰን” ያለው በሚገባ ትህነግን ይገልጻል።
ቡድኑ እየተወነ ያለው “አልሞትኩም ብዬ አልዋሽም” በሚል ባለ ሦስት ገቢር የትራዤዲ ተውኔት ነው። “በግባ መሬት” ሊጠናቀቅ ቋፍ ላይ የደረሰው የታሪኩ መጋረጃ ሊጣልና የመድረኩ ብርሃን እየደበዘዘ ያለውም በፈጣን ሁኔታ ነው። አልገባውም እንጂ “ልጡ ተርሶ፤ መቃብሩ ተቆፍሮ” አልቃሽና አስለቃሾቹ እያረገዱለት ሊሸኙት የቀረው አንድ ሐሙስ ብቻ ነው። “ክፉን ከነክንፉ” እንዲሉ ቀጣዮቹ ወርተረኞች በአምሳሉ የፈለፈላቸው መጋለቢያ ጌኛዎቹ ስለመሆናቸው ጥርጥር አይገባንም።
ኢትዮጵያ በአሸናፊነት እንደምትወጣ እንኳን ከእኛ ከልጆቿ ከጠላቶቿም የተሰወረ አይደለም። አሸባሪውን የትህነግ ቡድን ጅል ነው የሚያሰኘው አንዱ ምክንያት ሽንፈቱ ብቻም ሳይሆን አስተሳሰቡ ጭምር ነው። በኢኮኖሚያቸውና በፖለቲካ ጡንቻቸው ሊጋርዱት የሚሞክሩት “ጌቶቹ” ለጊዜው ጮኸው ሲያጯጩኹለት “የሙጥኝ” በማለት ሥራቸው ለመሸጎጥ መሞከሩ የትም ሊያደርሰው እንደማይችል የገባው አይመስልም። ወይንም እውነቱ ገብቶት እያለም ልቡን እንደለመደው አደንድኖ በዕብሪቱ ገፍቶበትም ሊሆን ይችላል።
እስከ ዛሬ ድረስ እንደ በቀቀን ፕሮፓጋንዳውን ሲያራግቡለት የኖሩት ቅጥረኞቹ “ዓይንህ ላፈር” በማለት ገሸሽ እያደረጉት ነው። ሥርዓተ ቀብሩ ሙሉ ለሙሉ ተፈጽሞ ታሪኩን በግባ መሬት ለመደምደም የሚቀረው አንዱ ወሳኝ ክስተት በመከራ ውስጥ እያለፈ ያለው ራሱ የትግራይ ሕዝብ “በቃኸን! ማንነትህ በሚገባ ተገልጾልናል” ብሎ ከትከሻው ላይ አሽቀንጥሮ ሲጥለው ነው። ያኔ ሕወሓት ይሉት የሀገር ጉድ አፈር ለብሶ ድንጋይ ይንተራስና በነበር ሲረገም ይኖራል። ሰላም ይሁን።
በ(ጌታቸው በለጠ /ዳግላስ ጴጥሮስ) gechoseni@gmail.com
አዲስ ዘመን ሐሙስ ጥቅምት 24 ቀን 2015 ዓ.ም