ሀይዌል ዊሊያምስ፣”DAYS THAT CHANGED THE WORLD”በሚል ርዕስ ለንባብ ባበቃው ድንቅ መጽሐፍ፤ የመጀመሪያውን የባሕር ላይ ጦርነት በአቴናውያንና በፐርዥያ መካሄዱን፤ የሮማን ገዢ የጁሊየስ ቄሳርን መገደል፤ የእየሱስ ክርስቶስ ስቅለት፤ ኮንስታንቲኖፕል የቤዛንታይን ግዛት መቀመጫ መደረጉ፤ የኦቶማን ኢምፓየር ቤዛንታይንን በመርታት ኮንስታንቲኖፕል በመቆጣጠር ስሟን ወደ ኢስታንቡል በመቀየር ዛሬ ላይ የቱርክ (የቱርኪዬ) መዲና መሆኗን፤ የጀርመን ኮንፌደሬሲ መመስረት፤ የእስልምና መወለድ፣ የአውሮፓውያን አዳዲስ እሳቤ መጀመር፤ የፍራንኮች ቅዱስ ጦርነት፤ የሞንጎል ኢምፓየር ማንሰራራትንና ሌሎችን ሁነቶች በወሳኝ አለማቀፍ ክስተትነት ያነሳሳል።
ወደ አህጉራችንም ሆነ ወደ አገራችን ስንመጣ የአድዋ አንጸባራቂ ድል፤ የጣሊያን ፋሽስት ዳግም ወረራ፤ የጣሊያን የአዲስ አበባ ጭፍጨፋ፤ የጣሊያን 2ኛ ወረራ መቀልበስ፤ የኢትዮጵያ አብዮት፤ የሕወሓት አገዛዝ የተጀመረበት፤ የ1997 ምርጫ፣ የጠቅላይ ሚንስትር ዐቢይ ወደ አመራር መምጣትና የአሸባሪው ትህነግ ወደ መማጸኛ ከተማው መቀሌ መሸሸና መመሸግ፤ የሕዳሴው የመጀመሪያ የውሃ ሙሌት፤ የመጀመሪያው ኃይል ማመንጨት፤ የአረንጓዴ አሻራ የተጀመረበት፤ የስንዴ ምርትን ከውጭ ማስገባት እንዲቆም አቅጣጫ መቀመጡ፤ በአገሪቱ ታሪክ ታይቶና ተሰምቶ የማያውቀው በከሀዲውና አሸባሪው ትህነግ የጥቅምት 24 ቀን 2013 ዓ.ም በሰሜን ዕዝ ላይ ጥቃትና ጭፍጨፋ የወሳኞች ሁሉ ወሳኝ መታጠፊያና የታሪክ ማርሽ ቀያሪ ሆነው ሲዘከሩ ይኖራሉ። የቀድሞው በኢትዮጵያ የአሜሪካ አምባሳደር ቲቦር ናጅ፤ ሰሞኑን በዋሽንግተን ኤግዛማይነር ላይ ባስነበቡን መጣጥፍ ጦርነቱን ሕወሓት እንደጀመረው አረጋግጠው፤ የሰሜን ዕዝ ጥቃትን የደቡብ ካሮላይና ሚሊሻ የአሜሪካን የጦር ካምፕ በማጥቃት የእርስ በርስ ጦርነት ከመቀስቀስ ጋር አነጻጽረውታል።
በ21ኛው መቶ ክፍለ ዘመን ከአጽናፍ እስከ አጽናፍ እግር እስኪቀጥን ቢታህሳስ እንደ አሸባሪው ትህነግ/ሕወሓት ጁንታና ጉጀሌ ያለ አሪዮስና አረመኔ የፖለቲካ ቡድን የለም። በዚህ ጊዜ በአለማችን የትኛውም ክፍል እንደ አሸባሪው ትህነግ ያለ እፉኝት የፖለቲካ ስብስብ በዲያጎን ፋኖስ እንኳ ቢፈለግ አይገኝም። በአፍሪካም ሆነ በላቲን አሜሪካ አልያም በእስያ ከአሸባሪው ትህነግ ጋር በዘመነ ጓዴነት (ኮንቴም ፓራሪስ) ሊነጻፀር የሚችል ምንም አይነት እኩይ ኃይል የለም። በዚህ ሁለት ዓመት ያረጋገጥነው ይሄን ሀቅ ነው። ለግማሽ ክፍለ ዘመን የዘለቁት እኩይ ተግባሮቹ እንዳሉ ሆነው። ገና ከምስረታው እንደሱ የደርግን ወታደራዊ አገዛዝ ለመታገል ጫካ የገቡትን እንደ ኢህአፓ፣ ኢዲዩና የትግራይ ድርጅቶችን እንደራደር፣ ልዩነታችንን በውይይት እንፍታ እያለ እያግባባ እውነት መስሏቸው ለድርድር ሲመጡ አንድ በአንድ የጨረሰ አረመኔና ከሀዲ ስብስብ ነው። እነ ስሁልን፣ ሙሴን፣ ሀየሎምንና ሌሎቹ በሀሳብ የተለዩትን እልፍ አእላፍ ታጋዮችንና ልጆቹን፤ የዛሬ ዓመት በሰሜን ዕዝ፣ በመከላከያ ሰራዊታችን፣ በአገራችንና በሕዝባችን ላይ እንደፈጸመው ክህደት ከጀርባ ወግቶ ወይም በጥይት ደብድቦ የጨረሰ አሪዮስ ነው። ለጊዚያዊ ፖለቲካዊ ጥቅም ሲል የሀውዜንን ሕዝብ በገበያ ቀን በአውሮፕላን አስፈጅቶ ሙሾ የሚያወርድና የአዞ እንባ የሚያነባ የሀፍረተቢሶች ስብስብ ነው።
በ77 ድርቅ ለትግራይ ሕዝብ የተላከ እርዳታን ሽጦ የጦር መሳሪያ የገዛ የማፍያ ስብስብ ነው። አገዛዝ ላይ በነበረባቸው 27 የግፍና የዘረፋ ዓመታት በከፋፍለህ ግዛ መርሁ በኢትዮጵያውያን መካከል ልዩነትንና ጥላቻን ሲጎነቁል የኖረ ከፋፋይ ቡድን ነው። ከማዕከላዊ መንግስት ስልጣን ከተነቀለ ወዲህም በተላላኪዎቹና ምንደኞቹ አማካኝነት እዚህም እዚያም ግጭትንና ሽብርን ስፖንሰር ሲያደርግና ስምሪት ሲሰጥ የባጀ እንዲሁም ደባን ሲጎነጉን ሴራን ሲሸርብ የመሸበት እኩይ ነው። ከጠቅላይ ሚንስትሩ የግድያ ሙከራ አንስቶ በመላ አገሪቱ ከተፈጸሙ የሽብር ወንጀሎች ጀርባ እጁ እንዳለበት የሚነገርለት ተስፋ የቆረጠ አጥፍቶ ጠፊ ነው። በእነዚህ ሁሉ ዓመታት የራሱን የሽብር፣ የሴራ፣ የደባ፣ የዘረፋና የእብሪት ክብረ ወሰን ሲሰባብርና ሲያሻሽል፤ ወደ አዲስ ምዕራፍ ሲያሸጋግር እና ልምድ ሲቀምር የኖረ መርገምት፣ ባንዳና ከሀዲ ነው። ታሪክም ትውልድም ዘላለም በማይረሷት በዚያች ጥቁር ቀን ማለትም ጥቅምት 24 ቀን 2013 ዓ.ም በሰሜን ዕዝ የፈጸመው ክህደት፣ ዘግናኝ ሽብርና ጥቃት የዚህን አረመኔ ስብስብ ማንነት ገሀድ አውጥቶታል።
ላለፉት 21 ዓመታት የቀን ሀሩር የሌሊት ቁር እየተፈራረቀበት፤ በቀበሮ ጉድጓድ የዕድሜውን ሲሶ ገብሮ ሲጠብቀው፤ በትግራይ ሕዝብ ደስታና ሀዘን ተካፋይ፤ ከትግራይ ሕዝብ ጋር ተጋብቶና ተዋልዶ የኖረ፤ በእርሻው በዘሩ በአረሙ በአጨዳውና በበራዩ እንዲሁም አንበጣን በመከላከል እንደ ቀንጃ (ረዳት ገበሬ) ተለይቶት በማያውቀው፤ ከሬሽኑ እየቀነሰ ለልጆቹ ትምህርት ቤትና ጤና ተቋም ሲገነባ፤ በኮቪድ 19 ለችግር ለተጋለጡ አሁንም ከእጅ ወዳፍ ከሆነች አበሉ ያካፈለ እሩህሩህና ለወገኑ ሟች የሆነ ሰራዊት በአረመኔውና ጉግማንጉጉ የአሸባሪው ትህነግ እፉኝት ቡድን ለማየት የሚዘገንንና ለመስማት የሚሰቀጥጥ ትውልድና ታሪክ ይቅር የማይለው ክህደትና ግፍ የተፈጸመበት በዛሬዋ ቀን 2013 ዓ.ም ነው።
ክቡር ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ፣ “ ለስግብግቡ ጁንታ ግፍ እስትንፋሱ፤ ጭካኔ ነፍሱ ነው። “ ያሉትን እዚህ ላይ ያስታውሷል። ጥቅምት 30 ቀን 2013 ዓ.ም በወልቃይት ማይካድራ ትህነግ በዘር ማጥፏት እና በጦር ወንጀለኝነት የሚያስጠይቀውን 1600 ንጹሐንን በማንነታቸው የጅምላ ጭፍጨፋ ፈጽሟል። በወቅቱ የመንግስታቱን ድርጅት የጦር ወንጀል ሳይፈጸም እንዳልቀረ በመግለጽ ማጣራት እንደሚያደርግ ሲገልጽ፤ እንደ አምንስቲ ኢንተርናሽናል ያሉ አለማቀፍ ተቋማትን ጨምሮ እነ ሲኤንኤንና ቢቢሲም ይሄን ዘግናኝ ጭፍጨፋ የተቀባበሉት ቢሆንም እዚህ ግባ የሚባል ፖለቲካዊና ዲፕሎማሲያዊ ጫና አለማድረጋቸው አገሪቱን ዛሬ ለምትገኝበት ውጥንቅጥ ዳርጓታል።
አሜሪካ ምዕራባውያንና አለማቀፍ ተቋማት ሲጠቃ ጩኸቱን ሲያስተጋቡ ሲያጠቃ ግን ድምጻቸውን ከማጥፋት ባሻገር የሳተላይት ድጋፍ ይሰጡታል። የዚህ አረመኔ ግፍ መቼ በዚህ ይቆምና፤ ጠቅላይ ሚኒስትሩ በወቅቱ በፌስ ቡክ ገጻቸው ባሰፈሩት ፅሁፍ፣ ጀግናው የመከላከያ ሠራዊት ሽራሮን ሲቆጣጠር፣ እጅና እግራቸውን የፊጥኝ ታስረው የተረሸኑ የመከላከያ አባላትን ማግኘቱን ገልጸዋል። በየቦታው ከዚህ የከፋ ጭካኔና ግፍ ሊያጋጥም እንደሚችል ጠቁመዋል። ጭካኔው ልብ የሚሰብር መሆኑን ጠቅላይ ሚንስትሩ በወቅቱ ገልጸው ዓላማውም ኢትዮጵያን መስበር ነበር፤ ኢትዮጵያ ግን ከአልማዝ የጠነከረች መሆኗንም አመልክተዋል። ሰሞኑን ባስተላለፉት መልዕክት ይሄን ሀሳባቸውን ደግመውታል።
የጁንታው ዓላማ ሠራዊቱንና ሕዝቡን አስቆጥቶ ለበቀል እርምጃ ማነሳሳት እንደሆነም ጠቁመው፤ ኢትዮጵያም ልበ ሰፊ ሕዝብና ሠራዊት እንዳላት አስታውቀዋል። ሠራዊቱ ለሰብዓዊነት የተናጠል ተኩስ አቁም አውጆ እስከወጣበት ሰዓት ድረስ ሰብአዊ እርዳታና አገልግሎት እየሰጠ እንደነበር አስታውሰው፤ ነጻ ባወጣቸው አካባቢዎች ሕዝቡን እየመገበ፣ እያከመና እየተንከባከበ ነበር ብለዋል።
ሌተናል ጄኔራል ባጫ ደበሌ የዛሬ ዓመት በጥቃቱ ሰሞን የሰሜን ዕዝ ጎብኝተው ሲመለሱ የሰጡት ጋዜጣዊ መግለጫ የአሸባሪው ትህነግ እፉኝት ስብስብ ምን ያህል ከትግራዋይና ከኢትዮጵያ የስነ ልቦና ውቅር፣ ሀይማኖትና ወግ ያፈነገጠ መደዴና ወፍ ዘራሽ እንደሆነ ያሳያል። ይህ ስግብግብና አረመኔ ቡድን እውን ከትግራይ ሕዝብ አብራክ የተገኘ ነው !? የሚል ጥያቄ ለማንሳት ያስገድዳል። አረመኔው ስግብግብ ጁንታ ሰራዊቱ በተኛበት በውድቅት ሌሊት በማረድ፣ በቦንብና አውቶማቲክ በማርከፍከፍ የአውሬነት ጥጉን አሳይቶናል። አስከሬን ከሙሽራ ባልተናነሰ ክብር በሚሰጥበት አገር አስከሬን ገፎ ከማዋረድ ባሻገር የአውሬ ሲሳይ እንዲሆን አድርጓል። ለስልጣንና የሸረበውን ሴራ ለማስፈጸም ሲል ምንም ከማድረግ እንደማይመለስ አረጋግጧል። ከዚያ በኋላ በማይካድራ ጋሊ ኮማ አጋምሳ ጭና ሰሞኑን ደግሞ በሀይቅ በኮምቦልቻና በውጫሌ ይሄን አብሮ አደግ አረመኔነቱን በአደባባይ አስመስክሯል።
ይሁንና ክቡር ጠቅላይ ሚንስትሩ በሰሜን ዕዝ ጥቃት ወቅት እንዳሉት፣ ዛሬም ሕልውናችን በሉዓላዊነታችን በግዛት አንድነታችን ላይ ጦርነት ተከፍቶብናል። ይህ የጡት ነካሽ፣ የከሃዲና የባንዳ ስብስብ የተናጠል የተኩስ አቁሙን እንደ መልካም አጋጣሚ በመውሰድ በአማራና በአፋር ክልሎች በሕዝባዊ ማዕበል የውጭ አገር ቅጥረኛ ወታደሮችን (መርሲናሪስ) ሳይቀር በማሳተፍ ወረራውንና ጥቃቱን እያስፋፋ ይገኛል። አሸባሪው ትህነግ በትግራይ ክልል በሚገኘው የመከላከያ ሰራዊት ሰሜን እዝ ላይ ጥቃት በመሰንዘሩ አገር እና ህዝብ ለማዳን ሲባል መከላከያ ሠራዊቱ የኃይል እርምጃ እንዲወስድ እንደታዘዘው ሁሉ ዛሬም ሁሉንም ክልሎች ያሳተፈ ክተት ታውጇል።
አገር እና ህዝብ ለማዳን ሲባል ኃይል የመጨረሻው አማራጭ ሆኗል። ለዚህ ነው ጠቅላይ ኤታማዦር ሹም ጀኔራል ብርሃኑ ጁላ በወቅቱ” ሳንወድ ተገደን አሳፋሪ ጦርነት ውስጥ ገብተናል “ ያሉት፤ ሕገ መንግሥታዊ ሥርዓቱን ለመጠበቅና አገርን ከውጭ ወራሪ ለመከላከል አገራዊ ተልዕኮ ተቀብሎ በግዳጅ ላይ የነበረን የአገር መከላከያ ሠራዊት ላይ የተከፈተው ጥቃት” የአገር ክህደት” ነው ሲሉ ገልጸውታል። በሌላ በኩል ብልፅግና ፓርቲ የተከሰተውን ጦርነት አስመልክቶ በወቅቱ አውጥቶት የነበረው መግለጫ ዛሬም ወቅታዊ ሆኖ ስላገኘሁት እንዳለ እንደሚከተለው አቅርቤዋለሁ። የትግራይ ሕዝብ ከመላው የኢትዮጵያ ሕዝብ ጋር በመሆን በአገር ላይ ክህደት ፈጽሟል ያለውን የሕወሓት ኃይል እንዲታገል ጥሪ አቅርቦ። “የትግራይ ሕዝብ ከሌሎቹ ብሔር ብሔረሰቦችና ሕዝቦች ጋር ጠንካራ ታሪካዊ አንድነትና ውህደት ያላቸው፣ ባህላዊና ጥንታዊ ሃይማኖታዊ እሴቶችን የሚጋሩ፣ በጋብቻና በደም የተሳሰሩ፣ በፀረ ጭቆና ትግል ከሌሎች ሕዝቦች ጋር ሆነው በአንድ ጉድጓድ ክቡር መስዋዕትነት እየከፈሉ አሁን ላለንበት የአገረ መንግሥት ምሥረታ ጉልህ አሻራ ያሳረፉ ሕዝቦች ናቸው፤” ያለው መግለጫው፣ በማስከተል “ የሕወሓት አጥፊ ቡድን የአገርንና የሕዝብን ሰላም፣ አደጋ ላይ ለመጣል የሚያደርገው ሴራ መሆኑን አውቃችሁ ከኢትዮጵያ ሕዝብ ጋር ያላችሁ ወንድማዊና ቤተሰባዊ ግንኙነታችሁ ሳይቋረጥ የትግራይን ሕዝብ የሚያለያዩ ሙከራዎችን በፅናት እንድትታገሉ የከበረ ጥሪያችንን እያቀረብን በዚህ አሸባሪ ቡድን ላይ ዕርምጃ በመውሰድ ኅብረ ብሔራዊ አንድነታችንን ለማስቀጠል በምናደርገው ትግል ውስጥ ከጎናችን እንድትሆኑ፤ “ ሲል ጥሪውን አቅርቧል። የትግራይ ክልል የፀጥታ ኃይሎች በአገሪቱ ከሚገኙ የፀጥታ ኃይሎች ጋር በጋራ በመሆን ሕዝባዊነታችሁን ጠብቃችሁ ለአንዲት ሉአላዊት አገር መከበርና ቀጣይነት ክቡር መስዋዕትነት በመክፈል ላይ መሆናችሁን ብልፅግና ፓርቲ ከልብ እንደሚገነዘብ ገልጿል።”ምንም እንኳ በክልሉ አምባገነን የሆነው የሕወሓት ቡድን በትግራይ ሕዝብ ላይ እያደረሰ ያለውን እንግልትና ስቃይ የታዘባችሁ ቢሆንም ባለው ፀረ ዴሞክራሲያዊ አካሄድ ምክንያት ለውጡን ከሕዝባችሁ ጋር ሆናችሁ ማጣጣም ሳትችሉ ቀርታችኋል፤” ያለው መግለጫው፣ “ ሆኖም ለረዥም ዓመታት የክልሉን ሕዝብ ሰላም ደኅንነት በኃላፊነት መንፈስ ወስዳችሁ ስትጠብቁ የቆያችሁ የክልሉ ፖሊስ፣ ልዩ ኃይል አባላትና ሌሎችም በሕዝብ ትከሻ ላይ ሆኖ እየቀለደ ባለው ዘራፊና አጥፊ የአሸባሪው ትህነግ ቡድን ላይ ዕርምጃ ለመውሰድ እየተደረገ ያለውን ትግል በመቀላቀል ሕዝባዊነታችሁን እንድታረጋግጡ በድጋሚ ጥሪያችንን እናቀርባለን፤ “
እንደ ማውጫ
መንግስት ስግብግቡን የአሸባሪው ትህነግ ጁንታ ቡድን ከሁለት ዓመት በላይ የለውጡ አካል እንዲሆን በአደባባይም በጓዳም ለምኖታል። ከሰማይ በታች ያሉ የሰላም አማራጮቹን ሁሉ አሟጦ ተጠቅሟል። በሰሜን እዝ ላይ ጥቃቱን ለመሰንዘር ጥቂት ሰዓታት ቀርተውት እያለ እንኳ አይተ ደብረጺዎን ገብረሚካኤል ጋር ክቡር ጠቅላይ ሚንስትር ስለክልሉ ኢኮኖሚና እና ስለአዲሱ የብር ለውጥ ተነጋግረዋል። በዚህ አላበቃም በዛው ምሽት አዲሱ የብር ኖቱም ወደ መቀሌ ተልኳል። ይህ መንግስት እስከ መጨረሻዋ ደቂቃ ድረስ ለሰላምና ለፖለቲካዊ መፍትሔ የነበረውን ቁርጠኝነት ያሳያል። ክህደትና አረመኔነት ምሱ የሆነው እፉኝቱ የአሸባሪው ትህነግ ጁንታ ግን ታሪክም ትውልድም ይቅር የማይለውን ክህደት ፈፅሟል። በዚህም ቀዩን መስመር አልፏል። የኢፌዲሪ መንግስትም በሚገባው ቋንቋ ለማነጋገር ተገዷል።
ስግብግቡና ከሀዲው የአሸባሪው ትህነግ ጁንታ የሰሜን ዕዝን በውድቅት ሌሊት ካጠቃ፤ በዚህም የአገሪቱን ሉዓላዊነት ከተዳፈረና ቀዩን መስመር ካለፈ በኋላ የኢፌዲሪ መንግስት ሕግን ለማስከበር ሲንቀሳቀስ ጁንታው ተወረርሁ፤ ጦርነት ተከፈተብኝ እያለ በተለመደው ቅጥፈቱ አለምን እንዳዳረሰው ሁሉ ሰሞኑን እያስፋፋው ያለውን ወረራ ለመቀልበስና ግብዓተ መሬቱን ለማፋጠን ሕዝብ ዳር እስከ ዳር ሲነሳ ደግሞ ተመሳሳይ እየየውን ያቀልጠዋል። ከሰሞነኛው የደሴና የኮምቦልቻ ጊዜያዊ የድል ስካር ነቅቶ በአሜሪካና በአውሮፓ ደጋፊዎቹ በየጎዳናው እንዲከባለሉ ያደርጋል። የተወሰነውን አለማቀፍ ማህበረሰብና ሚዲያም ማደናገሩን ካቆመበት ይቀጥላል።
ይሄን ሸሩን ቀድሞ ማምከንና ማጋለጥ፤ የሕዝብ ግንኙነትና የዲፕሎማሲ ስራውን ማጠናከር ከመልሶ ማጥቃቱ እኩል ትኩረት ሊሰጠው ይገባል። ይህ ኃላፊነት ለመንግስት ብቻ የሚተው ሳይሆን ለአገራችን ሁላችንም ቃል አቀባይ፣ አፈ ቀላጤ መሆንን የሚጠይቅ ስለሆነ ከዲያስፖራው ጋር ተናቦ መስራት ይጠበቅብናል። ሳይጠቀስ መታለፍ የሌለበት፤ ክቡር ጠቅላይ ሚንስትር፣ “ ይህን ሕዝብ ማገልገል በራሱ ክብር ነው !” ያሉለትም ሆነ፤ መከላከያ ሰራዊታችን “ ለዚህ ሕዝብ መሞት ክብር ነው !” ያለለት የኢትዮጵያ ሕዝብ ልዩነቱን ወደ ጎን ብሎ ከመንግስት እና ከመሪው ጎን ከመሰለፍ አልፎ የገንዘብና የአይነት ድጋፍ በማድረግ ደጀንነቱን አጠናክሮ መቀጠል ይጠበቅበታል። የኢትዮጵያን ሕዝብ ደጀን ያደረገ ጀግና ሰራዊት ባጠረ ጊዜና መስዋዕትነት እጅን በአፍ የሚያስጭን ድል በማስመዝገብ ያንዣበበውን የህልውና ስጋት እንደሚገፍ ቅንጣት ታክል አንጠራጠርም።
#መቼም አንረሳውም።
በቁምላቸው አበበ ይማም (ሞሼ ዳያን)fenote1971@gmail.com
አዲስ ዘመን ሐሙስ ጥቅምት 24 ቀን 2015 ዓ.ም