ጥቅምት 24/2012 ዓ.ም የሰሜን እዝ በከሃዲው የአሸባሪው ትህነግ ቡድን ከጀርባ ከተወጋ ዛሬ ሁለተኛ ዓመቱን ደፍኗል። ኢ- ሰብአዊ ድርጊቱ ከተፈጸመ ከሰባት መቶ ቀናት በላይ ቢቆጠሩም በኢትዮጵያ ላይ ጥሎት ያለፈው ቁስል ዛሬም አልጠገገም። “የወጋ ቢረሳ የተወጋ አይረሳም” ያንን የአውሬዎች አሳፋሪ ተግባር ዛሬም፣ ነገም እስከወዲያኛውም ብንረሳው የጀግኖቹ መስዋእቶች አጥንት እሾህ ሆኖ ሲወጋን ይኖራል።
ኢትዮጵያ ይቅር ባይነች፣ የህዝቦቿም ልብ ቂም አይዝም፣ ይህን የእንቁ ልጆቿን በግፍ የፈሰሰ ደም ግን ኢትዮጵያም ህዝቦቿም ይቅር አይሉትም፣ መቼም አይረሱትም። ይቅር የማይሉት፤ የማይረሱት የልባቸው ስብራት ከፍያለ ከመሆኑም በላይ እንዳይደገም ስለሚፈልጉ ጭምር ነው ።
መከላከያ ሰራዊት አገሬ፣ ወገኔና ዳር ድንበሬን ከውጪ ጠላት ጠብቃለሁ ብሎ ከሃያ ዓመታት በላይ ጨርቄን ማቄን ሳይል በቀበሮ ጉድጓድ ኖሯል። በኖረበት ዓመታትም ከራሱ አስበልጦ ለሕዝብ አለኝታ መሆኑን በተግባር አሳይቷል። የወር ደመወዙን ሙሉ በሙሉ ተቆራጭ አድርጎ ትምህርት ቤቶችን ገንብቷል፣ በህክምና እጦት ለሚንገላታው ወገኑ ጤና ጣቢያዎችን አሰርቷል፣ የአንበጣ መንጋን ገበሬውን ሲያሰቃይ እጁን አጣጥፎ አልተቀመጠም፣ አብሮ አርሷል አብሮ አጭዷል።
ሰብል ሲሰበስብ ውሎ የደከመ ጎኑን ለማሳረፍ በተኛበት ግን የእናት ጡት ነካሾች ጥይት ሲያርከፈክፉበት ያን ሁሉ መስዋእትነቱ ቆመው እንዲያስቡ አላደረጋቸውም። በጥይት መሞት የወታደር ወጉ ነው፣ በዘረኝነት የታወሩና የሰከሩ ባንዳዎች ግን ጥይት አልበቃ ብሏቸው ሰይጣን እንኳን የሚቀናበትን ግፍ መከላከያ ሰራዊቱ ላይ ለመፈጸም አላመነቱም።
አብሮ በልቶ ጠጥቶ፣ ተጋብቶና ተዋልዶ የኖረን ሰራዊት መግደል ብቻ አይደለም ለአስከሬኑ የክብር ረፍት እንኳን ነፍገው በጅብ አስበልተዋል። በጥይት መግደል የዘረኝነት ጥማቸውን አልቆርጥ ብሎ ሰራዊቱ በህይወት እያለ በመኪና ሄደውበታል፣ ልብሱን አስወልቀው እርቃኑን ሰድደውታል። ብቻ ስንቱን ግፍ ዘርዝሮ ይዘለቃል፤ መከላከያ ሰራዊት ላይ የተፈጸመውን ግፍ ኢሰብአዊ ድርጊት ብቻ ብሎ መኮነን የሆነውን ክህደት ማለዘብ ይሆናል።
መንግስት የአሸባሪው ትህነግ የሽብር ቡድን በመከላከያ ሰራዊት ሰሜን እዝ ላይ ጥቃት የፈጸመበት የዛሬዋን ቀን “ጥቅም 24 ን አንረሳውም ” በሚል መሪ ቃል ታስቦ እንዲውል ውሳኔ ማስተላለፉ ተገቢ ነው። ቀኑን ትውልድ ሊዘክረውና ሊማርበት ይገባል። ከዚህ ጎን ለጎንም “መቼም የትም እንዳይደገም” በሚለውም ሀሳብ ቢጠናከር ተገቢ ይመስለኛል። ሀሳቡ ለቀይ ሽብር ሰማእታት ብቻ ሳይሆን መከላከያ ላይ ለተፈጸመው ግፍ የበለጠ ይሰራል ባይ ነኝ።
የአሸባሪው ትህነግ የሽብር ቡድን ኢትዮጵያን ለማፍረስ የመጨረሻ ያለውን እርምጃ ጥቅምት 24/2012 ዓ.ም በመከላከያ ሰራዊት ላይ በመፈጸም በኢትዮጵያውያን ላይ ግልጽ ክህደት በመፈጸም ብቻ አላበቃም። ከሰራዊቱ የጦር መሳሪያ በመዝረፍና ከባድ ጥቃት በማድረስ ኢትዮጵያን ያፈራርሳል ያለውን ሁሉ የጥፋት እርምጃ ወስዷል።
በመከላከያ ሰራዊቱ የተወሰደበትን ጥቃት ፈጣን በሆነ አጸፋዊ እርምጃ በመቀልበስ የቡድኑን ሕልውና የሚያሳጥሩ እርምጃዎች ቢወስድም ቡድኑ በምእራባውያን ከመቃብር አፋፍ እየተመለሰ በኢትዮጵያ ሕዝብ ላይ ተጨማሪ ሁለት ወረራዎችን ፈጽሟል።
የኢትዮጵያ ሉዓላዊነትን ለመንካት በሽብር ቡድኑ የተወሰደው እርምጃ መቼም የሚረሳ ባለመሆኑ ይህ ቀን በሁሉም ኢትዮጵያውያን ዘንድ ታስቦ ይውላል። “መቼም የትም እንዳይደገምም” ሲታሰብም ይኖራል። መከላከያ ሰራዊታችን ከፍ ተብሎ የሚታሰብበት ቀንም ይሆናል።
ኢትዮጵያውያን ቀኑን “ ጥቅምት 24ን አንረሳውም ” በሚል መሪ ሃሳብ በሰራዊታችን ላይ የተፈጸመውን ግፍ ሲዘክሩ፤ እኔም እንደ አንድ ኢትዮጵያዊ በማህበራዊ፣ ኢኮኖሚያዊና ፖለቲካዊ መስክ ሰራዊት ነኝ በሚል ቁርጠኝነት ሊሆን ይገባል። ኢትዮጵያውያን በሁሉም ዘርፍ ተደራጅተው አገራቸውን ከአደጋ ለመጠበቅ ከራሳቸው ጋር ቃል እየገቡ መሆን ይኖርበታል።
በመላው አገሪቱ የሚገኙ የመንግስት ተቋማት ያለን ሰራተኞች እና መላው ህዝባችን አንድ ላይ በመሆን ለ45 ሰኮንዶች እጃችንን ደረታችን ላይ አድርገን ቀኑን ስናስብ፤ በእለቱ የደም ልገሳን ጨምሮ የሻማ ማብራት ፕሮግራም ስናካሂድ ዛሬ ላይ በሰላም እንደ አገር ያለነው ሰራዊቱ በከፈለው መስዋእትነት መሆኑን በማስተዋል ሊሆን ይገባል። ኢትዮጵያዊ ሁሉም በዚህ የመሳተፍ የሞራል ግዴታ አለበት።
የኢፌዲሪ ጠቅላይ ሚንስትር ዐቢይ አሕመድ የዛሬ ዓመት ይህን ዕለት በማሰብ በማህበራዊ የትስስር ገጻቸው ላይ ባጋሩት ጽሑፍ፤ “አቻምና ጥቅምት 24 ግፍ የተፈጸመባቸው ጀግኖቻችን ታሪክ ፈጽሞ የሚረሳ አይደለም። . . . ዛሬ የቆምነው ለእኛ ሲሉ የግፍ ጽዋን በተጎነጩ ጀግኖቻችን አጥንት ላይ ነው። እነዚያ ብርቅዬ የኢትዮጵያ ልጆች “ከወገኔ በፊት እኔ ልቅደም” ብለው ደማቸውን ለአፈር፣ ሥጋቸውን ለአሞራ ባይሰጡ ኖሮ የዛሬው ቀን ዛሬን ባልመሰለ ነበር” ብለዋል።
ቀኑ የሰሜን እዝ የመከላከያ ሰራዊት አባላትን በማሰብ እኛም ለአገራችን ሰራዊት በመሆን ቃል የምንገባበት እንዲሆን ይጠበቃል። እለቱ የኢትዮጵያ ጠላቶች አንገታቸውን የሚደፉበት ኢትዮጵያውያን ግን ቀና የሚሉበትና አገራቸውን ለመጠበቅ ቃላቸውን የሚያድሱበት መሆን ይገባዋል።
አሸባሪው ትህነግ አገር ለማፍረስ ያሰለፈውን መንጋ መመከት የሚቻለው እንደ ህዝብ በመንቀሳቀስ ነው። ቡድኑ እየዘረፈ እና እየገደለ አገር ለማዳከም የሚያደርገውን እንቅስቃሴ በጋራ መግታት፤ የፈለፈላቸው ሸኔን የመሰሉ ድርጅቶችን ጨምሮ አገር ለማፍረስ የቋመጡ ኃይሎችን እንደ ህዝብ መታገል ያስፈልጋል።
የሽብር ቡድኑ ጥቅምት 24 የፈጸመው ግፍ መዳረሻው አገር ማፍረስ በመሆኑ ተስፋ የቆረጠና ለመሞት የተዘጋጀ ቡድን በማሰለፍ እንዲሁም ሰርጎ ገቦችን በማደራጀት አገርን የማወክ እንቅስቃሴውን ለመቀጠል ቢጥርም ዛሬም የኢትዮጵያ የቁርጥ ቀን ልጆች ደማቸውን አፍስሰው አጥንታቸውን ከስክሰው እኩይ ተግባሩ እንዳይፈጸም የብረት መዝጊያ ሆነዋል።
ይህ ቡድን ኢትዮጵያን ለማፍረስ ከሚፈልግ የውጭም ሆነ የውስጥ ኃይል ጋር በማበር የጀመረውን እኩይ ተግባር መግታት የሚቻለው በጋራ በመሰለፍ በመሆኑ በሁሉም የአገሪቱ አቅጣጫ ያለው ኢትዮጵያዊ አገርን ከወራሪዎች ለመታደግ ቆርጦ ሊነሳ ይገባዋል።
በሰላም ውይይት ስም የኢትዮጵያን እጅ ጠምዝዞ የአሸባሪውን እስትንፋስ ለማቆየት የሚደረግ ማንኛውም ጥረት ለማክሸፍ በውጪም ይሁን በአገር ውስጥ ያሉ ሁሉም ኢትዮጵያውያን በጋራ ሊቆሙ የግድ ነው። ለዚህም በየጊዜው እየተካሄዱ በሚገኙ ሰላማዊ ሰልፎች ላይ በስፋት መሳተፉን አጠናክሮ መቀጠል የዜግነት ግዴታ ነው።
እየተካኄደ ያለው የሰላም ውይይት የአገር ሉአላዊነትንና የህዝቦችን በሰላም የመኖር መብት ታሳቢ ያደረገ፤ አሻበሪው ቡድን አራተኛ ዙር ጦርነት መክፈት የሚያስችለውን እድል ሆነ አቅም ሊፈጥርለት የሚገባ መሆን የለበትም። መከላከያ ሰራዊት ላይ የዛሬ ሁለት ዓመት የተፈጸመው ግፍና ክህደት መቼም የትም የማይደገምበት ትክክለኛው ሃዲድም ይህ ነው።
ቦጋለ አበበ
አዲስ ዘመን ሐሙስ ጥቅምት 24 ቀን 2015 ዓ.ም