ሽብርተኛው ትህነግ ዛሬም ጣዕረ ሞት ላይ ሆኖ፤ ጉድጓዱ ተምሶ ፣ ልጡ ተርሶ ፤ ምላሱ አልሞተም። የመጨረሻዋን ህቅታ ለኑዛዜና ለንስሀ ሊጠቀምባት ሲገባ በየአቅጣጫውና ከተለያየ ምንጭ የውሸት መዓት እየነዛ ይገኛል። የተካነበትንና ጥርሱን የነቀለበትን ውሸት በጀ ብሎ ተያይዞታል። የደቡብ አፍሪካው ውይይት ከመጀመሩ የተኩስ አቁም ስምምነት ተደረሰ፤ ወልቃይትና ጠገዴ እንዲመለሱ ተወሰነ ከሚለው አንስቶ፤ ትግራዋይ ላይ ዘር ማጥፋት እየተፈጸመ ነው፤ የኢትዮጵያ ጦር ከኤርትራ ጋር ሆኖ ወረረን ፤ ወዘተረፈ የሚሉ የውሸት ፍላጻዎችን ሌት ተቀን እያንበለበለ ነው።
እነ ማርቲን ፕላው ፣ ከአለማቀፍ ሚዲያውና ተቋማት ጋር በመናበብ የትህነግ ውሸት እያራገቡ ነው ። አንቶኒ ብሊንከን ፣ ሊንዳ ቶማስ ፣ ማይክል ሀመርና የአውሮፓ አጋሮቻቸው እነ የአለም ባንክን ጨምሮ ጫናቸውን ያጎርፉታል። በሰሞነኛው የፕሪቶሪያ ውይይት*(ድርድር ላለማለት ነው፤)በመንግስታቱ ድርጅት የአሜሪካ አምባሳደር በቲዊተር ገጻቸው ያስተላለፉትን ማስፈራሪያና ዛቻ የምናስታውሰው ነው።
ሌላው በጣም የገረመኝ የአፍሪካ ኮሚሽን ሊቀመንበር ሙሳ ፋቂ መሐመት፤ በካናዳው ጠቅላይ ሚኒስትር ጄስቲን ቱርዶ ለይፋዊ የስራ ጉብኝት ተጋብዘው ካናዳ ከመግባታቸው ፤ የአሜሪካ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር አንቶኒ ብሊንከን ተከታትለው ካናዳ በመግባት ከመሐመት ጋር ተገናኙ። ይህ መቼም በአጋጣሚ የሆነ አይደለም። አሜሪካ ኢትዮጵያ ላይ ጫና ለመፍጠር የሄደችበትን ርቀት ቁልጭ አድርጎ ያሳያል። ማይክል ሀመር ራሳቸውን ከታዛቢነት ወደ ዛኛው ወገን አካልነት የቀየሩበትን አግባብ ልብ ይሏል። ወደ ተነሳሁበት የሽብርተኛው ሕወሓት የማያልቅ ውሸት ስመለስ ክቡር ጠቅላይ ሚኒስትር በአንድ ወቅት በማህበራዊ ትስስር ገጻቸው ባስተላለፉት መልዕክት ልነሳ።
“የውሸት ጀንበር ሲጠልቅ የሤረኞች ወጥመድ ይበጠሳል”ነበር ያሉት። ይህ መልዕክት ቢተነተንና ቢተረጎም ራሱን የቻለ ዳጎስ ያለ ስንክሳር ይወጣዋል። አሸባሪው ሕወሓት ቁጥሩ ቀላል ያልሆ ትግራዋይንም ሆነ አለማቀፍ ማህበረሰቡን ከጎኑ ያሰለፈው በውሸት በተለወሰው የቁጭት ትርክትና ሀሰተኛ መረጃ ነው ። ለትግራዋይ ሊያጠፉህ ነው ፤ ሊውጡህ ነው ፤ ጠላቶችህ ከበቡህ መጡብህ እያለ እየቀሰቀሰ ለሰብዓዊ ጋሻነት ከመጠቀም አልፎ ከእነልጆቹ እየማገዱት ነው።
ከተቀረው ኢትዮጵያዊ አቆራርጠው አግተው ለማይጠረቃ ፖለቲካዊ ጥቅማቸው ምስ እያደረጉት ነው። ለምዕራባውያን ደግሞ የዘር ማጥፋት ወንጀል ተፈጸመብን ፣ ሕዝባችን ሆን ተብሎ እንዲራብ ተደረግ ፣ በመድሀኒት እጦት አለቀ ፣ ተደፈረ ፣ ተዘረፈ ፣ ወዘተረፈ በሚል የበሬ ወለደ ውሸት ከጎኑ ያሰልፋል።ሆኖም ጠቅላይ ሚኒስትሩ እንዳሉት የውሸት ጀምበር ሲጠልቅ ትግራዋይን ያጠመደው የአሸባሪው ወጥመድ ይበጠስና ትግራዋይ አርነት መውጣታቸው ሩቅ አይሆንም። በትግራይ ከተሞች ውጊያ ላለማካሄድ ተገቢውን ጥንቃቄ እያደረገ ወደፊት እየገሰገሰ ነው።
ሰሞኑን በፍጹም ወታደራዊ ዲስፕሊንና በጥንቃቄ ነጻ ባወጣቸው ከተሞች ከተራበው ትግራዋይ ጉሮሮ እየቀማ ለሰራዊቱ ስንቅ እንዲሆን ከዝኖት የነበረውን የምግብ እህል ከማከፋፈሉ ባሻገር ተጨማሪ ዕርዳታ ለማድረስ እየሰራ ነው። ከሕዝብ ጋርም በመወያየት እያረጋጋ ሲሆን፤ በሽብርተኛው ተቋርጠው የነበሩ ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ ተቋማትን በአጭር ጊዜ ውስጥ ለማስጀመር እየተጋ ነው። ሆኖም ዛሬም እነ አሜሪካና ተቋሞቻቸው የሽብርተኛውን ነጭ ውሸት እንደ ገደል ማሚቶ እያስተጋቡት፤ እንደ በቀቀን እምዕራባውያን አለማቀፉ ማህበረሰብ አለማቀፍ ሚዲያዎች እነ አመነስቲ ኢንተርናሽናል ሂውማን ራይትስ ዎች ወዘተረፈ ሀገራችንን እንደ ጎን ውጋት ቀስፈው የያዟት አሸባሪው ሕወሓት ላለፉት አራት አመታት በጭፍራው በምንደኛው በሎቢስቶችና በታሪካዊ ጠላቶቻችን ሌት ተቀን በተቀናጀና በተናበበ አግባብ በተነዛ የተዛባና ሀሰተኛ መረጃ ስለሆነ የውሸት ጀንበር ሲጠልቅ ምዕራባውያንንና አለማቀፍ ማህበረሰቡን ያጠመደው የአሸባሪው ሕወሓት ወጥመድ ሲበጠስ እውነታው ገሀድ ይወጣል።
እኔም ለዚህ ነው የጠቅላይ ሚኒስትርን አባባል ከታላቅ ይቅርታ ጋር ወደራሴ ወስጄ”የውሸት ጀምበር ስትጠልቅ ፣ የኢትዮጵያ ጸሐይ ትወጣለች !?”ያልሁት። አዎ ሀቃችንንና ፍትሐችንን ታቅፈን አጨብጭበን እንድንቀር ያደረገችን የከሀዲው ጀምበር ላትመለስ ትጠለቃለች። እየጠለቀችም ነው። አለምም ዘግይቶም ቢሆን እውነቱን ያውቀዋል።እንደ አሸባሪው ትህነግ በሕዝብ እና በሀገር ላይ አይን ያወጣ ክህደት የፈፀመ ዋሾና መልቲ ስብስብ በዲያጎን ፋኖስ እግር እስኪቀጥን ከአጽናፍ እስከ አጽናፍ ቢፈለግ አይገኝም፡፡
በውሸት እንደሱ ጥርሱን ነቅሎ የጎለመሰ ድርጅት የለም። ውሸት ፣ ሴራ ፣ ክህደት ፣ ሌብነት ፣ ጭካኔና ተንኮል ለህልውናው እንደ ደም ስርና ልብ ናቸው ። ያለውሸትና ግጭት ውሎ ማደር አይችልም። ሕዝብን ሀገርን ብቻ አይደለም ራሱን ሳይቀር የሚዋሽ መርህ የሚባል ነገር ያልፈጠረበት መርገም ነው። ገና ከጅምሮ በ1967 ዓም ትግል ሜዳ የወረደው በሀሰተኛና የተሳሳተ ትርክት ድቡሽት ላይ በተቀለሰ ሰቀላ ስር ዶልቶ ነው። የ47 አመታት ባተሌና አጥፍቶ ጠፊ ታሪኩ በውሸት ብዕር የተከተበ ነው። የሕግ የበላይነትን ለማረጋገጥ ከአሸባሪው የትህነግ ጁንታ ጋር ተገደን የገባንበት ትንቅንቅ በአውደ ግንባር ብቻ የተወሰነ አይደለም የሚባለው ከዚህ ታሪካዊ ዳራና ተፈጥሮአዊ ባህሪው በመነሳት ነው።
አዎ ጦርነቱና ዘመቻው በእፉኝቱ ትህነግ ስፖንሰር ከሚደረገው ተልኮና ስምሪት ከሚሰጠው ዲጂታል ወያኔ ህልቁ መሳፍርት ከሌለው የሀሰት መረጃና ሆን ተብሎ ከተዛባ መረጃ እና የሴራ ኀልዮት ጋር ነው። ይህ የከሀዲና የሌባ ስብስብ ከ27 አመታት ፈላጭ ቆራጭ አገዛዝ በኋላ በህዝባዊ አመጽና በለውጥ ኃይሉ ከመንበሩ ከተፈነገለ በኋላ በመማጸኛ ከተማው መቀሌ መሽጎ 24 ሰዓት የውሸት ፣ ሆን ተብሎ የተዛባና የሴራ ኀልዮትን ፍላጻ እያንበለበለ ይገኛል። ባለፉት አራት አመታት ብቻ ወደ 1000 የሚጠጉ ኦፊሴላዊ ሀሰተኛ መግለጫዎችን አውጥቷል። በዚህም በሀገሪቱ ግጭቶች ተቀስቅሰዋል። ንጹሐን ተገድለዋል። ወልደው ከብደው ከኖሩበት ቀዬ ተፈናቅለዋል። በሀገራችን ላይ የጫና ናዳ ወርዷል። እየወረደም ነው።
ጥቅምት 24 ቀን ፣ 2013 ዓም በሰሜን ዕዝ ላይ ለማየት የሚዘገንን ለመስማት የሚሰቀጥጥ ግፍ በስግብግቡ የትህነግ ከሀዲ ቡድን መፈጸሙን ተከትሎ መንግስት የሕግ የበላይነትን ለማስከበር ሲንቀሳቀስ እና ተገዶ ወደ ጦርነት ሲገባ የትህነግ የፕሮፓጋንዳ ወናፍ በተናበበና በተቀናጀ አግባብ በማህበራዊና መደበኛ ሚዲያ የሀሰትና የተዛባ መረጃውን እያራገበ ይገኛል። ጦርነቱን እራሱ ለኩሶ እያለ የተወረርሁ ድቤውን ይደልቃል ።
ሶስት ሳምንት ባልሞላ ጊዜ ለዛውም በውድቅት ሌሊት ሰራዊቱ ላይ ክህደት ፈጽሞ አጥቅቶና የሀገሪቱን 80 በመቶ ከባድ መሳሪያ ዘርፎ ድባቅ ተመቶ ከፍተኛ ፖለቲካዊና ወታደራዊ መሪዎቹን አጥቶ ምላሱ ግን የሌለ ግዳይ ከመጣል አልቦዘንም ። ዛሬም አይጥ ጉድጓዱ ገብቶ እንደ ቅጠል አረገፍናቸው ይልና መልሶ የዘር ማጥፋት ተፈጸመብን እያለ እየየውን ያቀልጠዋል ። እዚህ ላይ ፍጥርጥሩን አበጥረው የሚያውቁት የዛን ጊዜው ሌተናል ጀኔራል የዛሬው ጄነራል አምባሳደር ባጫ ደበሌ “ሕወሓት ሞቶም ይዋሻል።” ያሉትን ማስታወስ የተገባ ነው።
በማህበራዊም ሆነ በመደበኛ ሚዲያው ሀሰተኛው፣ የተዛባው ሆነ አሳሳቹ መረጃ የትየለሌ በመሆኑ ሕዝብ በአሰስ ገሰስ የመረጃ አረንቋ መዋጡን ለማረጋገጥ የትህነግ ምንደኛ የፕሮፓጋንዳ ጭፍራ ማህበራዊ ሚዲያውንና ዘርፎ ያቋቋመቸውን መደበኛ ሚዲያውን እንዴት በውሸት እንዳጥለቀለቀው መመልከትና መረዳት ይቻላል። ከጦርነቱ ይልቅ የመረጃ አውደ ውጊያው አየሩን ፣ ምድሩንና መልካው ብቻ ሳይሆን ቨርቹዋል የሆነውን ዲጂታል አለምንም አዳርሶታል፡፡ አብዛኛው ኢትዮጵያዊ የሴረኛውን የትህነግ ወታደራዊ ቡድን ውሸትና ቅጥፈት ጠንቅቆ የሚያውቀው ቢሆንም ጥቂት የዋሆችን ማቄሉና ማሞኘቱ አልቀረም። ከዚህ አልፎ ማሸበሩና ማደናገሩ አልቀረም።
አሸባሪው ትህነግ በሒትለሩ ጆሴፍ ጎብልስ “ውሸት ሲደጋገም እውነት ይሆናል” በሚል ቀመር ለሚነዛው ሀሰተኛ ፕሮፓጋንዳ የሴራ ኀልዮትን ፣ ሚስ ኢንፎርሜሽን እና ዲስ ኢንፎርሜሽን አንሰላስሎ እየተጠቀመ ይገኛል። ሚስ_ና_ዲስ ኢንፎርሜሽን ተመሳሳይ ትርጉም ያላቸው ስለሚመስል እየተተካኩ ጥቅም ላይ ሲውሉ ይስተዋላል። ብያኔአቸው ግን ለየቅል ነው።
ሚስ ኢንፎርሜሽን የተሳሳተ ወይም አሳሳች መረጃ ሲሆን ዲስ ኢንፎርሜሽን ደግሞ እውነትን ለመሸፋፈን ወይም የሕዝብ አስተያየት ላይ ተዕጽኖ ለማሳደር ሆን ተብሎ የሚነዛ የሀሰት መረጃ ነው። እፉኝቱ ትህነግ በፕሮፓጋንዳ ጭፍራው አማካኝነት ስልጣን ላይ እያለም ሆነ ከተፈነገለ በኋላ አሳሳች ፣ እውነት የሚያጠየም እና የሴራ ኀልዮትን እያዛነቀ ሌት ተቀን እየባዘነ ይገኛል። በተለይ በሰሜን ዕዝን አረመኔያዊ ክህደት መፈጸሙን ተከትሎ መንግስት ሉዓላዊነትን ለማስከበር ከወሰነበት ደቂቃ አንስቶ እስከዚች ደቂቃ ድረስ ምን አልባት በየዕለቱ በአስር ሺህዎች የሚቆጠሩ ሀሰተኛ ፣ እውነትን የሚበርዙና የደባ መረጃዎችን በተቀናጀና በተናበበ መንገድ በማህበራዊና በመደበኛ ሚዲያ እያንበለበለ ይገኛል።
በጀግናው የጥምር ኃይል በቀናት አውደ ውጊያ ድባቅ ሲመታ ያለ የሌለ ጊዜውን ፣ ጉልበቱንና የዘረፈውን ሀብት ለፕሮፓጋንዳ ማሽነሪው እያዋለው ይገኛል።የሚያሳዝነው አሸባሪው ሕወሓት የፖለቲካ ትርፍና ጥቅም እስካገኘበት ድረስ ምንም አይነት ዋጋና መስዋዕትነት ይከፈልለት ስህተቱን ከማመን ይልቅ አይኑን በጥሬ ጨው ታጥቦ መዋሸትን የሚመርጥ ከሀዲ ነው።
ለ17 አመቱ ትጥቅ ትግል ከ60 ሺህ በላይ የትግራይ ወጣቶች ሞተዋል። ቁጥራቸው ከዚህ የማያንስ አካል ጉዳተኛ ሆነዋል። በኢትዮ ኤርትራ ጦርነት ከ70ሺ በላይ ዜጎች ተሰውተውና ተቀራራቢ ቁጥር ያላቸው ለአካል ጉዳት ተዳርገው ትህነግ ግን ህይወትና አካል ለገበሩለት ትግራዋይና ሌሎች ዜጎች በትንሹ ሊታመንላቸው አልቻለም። አሁንም ለዕብሪቱና ለዘረኝነቱ ልጆቻቸውን ከጉያቸው እየነጠቀ እየማገደ እውነትን ለመናገር አይናቸውን ለማየት ድፍረት የለውም።
እንደ መቋጫ
እውነተኛ መረጃን ተደራሽ በማድረግ የተጋነኑና በማህበረሰቡ ዘንድ ሽብር የሚለቁ መረጃዎችን መከላከል ይቻላል፡፡ መንግስትም ሆነ ባለድርሻ አካላት ወቅታዊና እውነተኛ መረጃዎችን ከስር ከስር የማድረስ ኃላፊነት አለባቸው፡፡ እግረ መንገድ ሕዝብን ካልተገባ ውዥንብር መከላከል ይቻላል፡፡ ዳሩ ግን ትክክለኛ መረጃን የማድረስ ጉዳይ ለአንድ ወገን የሚተው ጉዳይ ሳይሆን የሁሉንም ኃላፊነት የሚጠይቅ መሆኑ ሊጤን ይገባል፡፡
አንድ መረጃ ከማጋራት ወይም ከመለጠፍ በፊት ትክክለኛነቱን ማረጋገጥ ይሁን ለሌላ ተግባር በምንጭነት ከመጠቀም በፊት ከሌሎች ምንጮች ጋር ማመሳከር የተቀናጀ ጥረትና ቁርጠኝነት ይጠይቃል፡፡ በሀሰተኛ መረጃ መወናበድ የለበትም። ይህ እንዳይሆን ግን መንግስት ወቅታዊ መረጃ የመስጠት ግዴታ አለበት።
የተለያዩ ማህበራዊ ሚዲያዎችን የምንጠቀም ሰዎች ስለምናጋራው ጹሑፍ ፣ ምስልና ድምፅ ቆም ብለን ማሰብ ፣ ለዋቢነት ፣ ለአጋዥነት ስለምንከፍተው ድረ ገፅ ፣ ጦማር ታማኝ ምንጭ መሆን አለመሆን ማጣራት በማስከተል አስተያየት ( ኮሜንት ) ከመስጠታችን በፊት ማውጣት ፣ ማውረድና ማመዛዘን ይጠበቅብናል ፡፡ ይህን ማድረግ ከቻልን ሀሰተኛ ፣ የተዛባና የጥላቻ መረጃ ዘርጋፊዎችን ፣ ነዥዎችንና ለፋፊዎችን በሒደት ማስቆም እንችላለን፡፡
መንግስት የሕግ የበላይነትን ለማስከበር ከወሰነ በኋላ ሁሉም ኢትዮጵያዊ ያለ ልዩነት ከጎኑ ከመቆሞ ባሻገር በቢሊዮን የሚቆጠር ገንዘብ እና ግምቱ ቀላል ያልሆነ የአይነት ድጋፍ በማድረግ ደጀንነቱን እንዳረጋገጠው ሁሉ በውጭም በአገር ቤት ያሉ ዜጎች በተወሰነ ደረጃ የዲጂታል ወያኔን ፕሮፓጋንዳ እየመከቱ ቢሆንም ፤ እውነትን ይዞና ተገዶ ወደ ጦርነት እንደገባ ሀገርና ሕዝብ ለዛውም ከትህነግ ጋር ለሚደረግ የጸረ ፕሮፓጋንዳ ትግል ሁሉም ዜጋ በተቀናጀና በተናበበ አግባብ ሊንቀሳቀስና ጀግናው የመከላከያ ሰራዊትና ሚሊሻ በጦር ግንባር ያስመዘገበውን አንጸባራቂ ድል እኛ በእሱ መስዋዕትነት በሰላም እየኖርን በእጅ ስልካችንና በኮምፒውተር ቁልፎች የምንደኛውንና የቅጥረኛውን የዲጂታል ወያኔ ጭፍራ ፕሮፓጋንዳ መክተን የፕሮፓጋንዳ አውደ ውጊያውን ማሸነፍና የጀግናው ሰራዊታችንን አኩሪ ድል መደገምና ማህበራዊም ሆነ መደበኛ ሚዲያውን በሀገር ፍቅር ሱናሚና በአርበኝነት ማጥለቅለቅ ይጠበቅብናል።
ለሀገራችን ሁላችንም አምባሳደር ፣ ጋዜጠኛና ሕዝብ ግንኙነት ነንና። ይህ ዘርፈ ብዙ ጦርነት በድል እስኪደመደም ሁላችንም የእውነት ፣ የፍትህና የሉዓላዊነት ሰራዊት መሆን አለብን ። ለዚህ ክቡር አላማ የህይወት መስዋዕትነት ብንጠየቅ እንኳ ወደ ኋላ የማንል ጊዜያችንን፣ እውቀታችንንና ገንዘባችን ሰውተን የድሉ ተቋዳሽ መሆን ይጠበቅብናል።
እዚህ ላይ ሳላነሳ የማላልፈው መንግስት ጊዜ ሳያጠፋ የተጣራ መረጃ ለሀገር ውስጥና ለውጭ ሚዲያዎች የሚያደርስ ፤ “የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ የመረጃ ማጣሪያ፤ “ ማቋቋሙ የዲጂታል ወያኔን ፕሮፓጋንዳ በተወሰነ ደረጃ መመከትና በአለማቀፍ ማህበረሰቡና በምዕራባውያን ዘንድ የነበረውን ብዥታ ለማጥራት መንቀሳቀሱ ይበል የሚያሰኝ ሆኖ መረጃ የማጣራቱ ተግባራ ለዚህ አካል ብቻ ሳይሆን ሁሉም የመንግስት ሚዲያ መረጃ የማረጋገጫ / ፋክት ቼክ / ክፍል ሊያደራጅ ይገባል።
በዘመነ ማህበራዊ ሚዲያ ሚሰና ዲስ ኢንፎርሜሽንና እና የሀሰት ዘገባን ተከታትሎ ማምከን የሚቻለው እውነትን የማጣሪያና የማረጋገጫ ራሱን የቻለ ክፍል ሲኖር ነውና። ዜጋውም የዚህ አካል ሊሆን ይገባል። ከዚህ ጎን የሕዝቡንየሚዲያ ግንዛቤ media literacy ለማሳደግ የሚያግዙ ስራዎች ሊሰሩ ይገባል። በመንግስት ሚዲያዎች ላይ አጥቶት የነበረውን አመኔታ ለመመለስ ብዙ ስራ ይፈልጋል። ሌላው መንግስት ግትርነቱን ትቶ ሎቢ ሊቀጥር ይገባል። የሕዝብ ግንኙነትና የገጽታ ግንባታ ስራ ያለ ሎቢስት አንዲት ጋት ፈቀቅ እንደማይል ሰሞኑንም እየታዘብን ነው።
ሀገራችን ኢትዮጵያ በጀግኖችና እውነተኛ ዜጎች ታፍራና ተከብራ ለዘላለሞ ትኑር !
አሜን።
አዲስ ዘመን ጥቅምት 20 ቀን 2015 ዓ.ም
በቁምላቸው አበበ ይማም (ሞሼ ዳያን) fenote1971@gmail.com