አሸባሪው ትህነግ ላለፉት ሁለት ዓመታት ኢትዮጵያውያን የሰላም አየር እንዳይተነፍሱ፣ ወጥተው እንዳይገቡ ሌት ተቀን ሳይታክት ሲሠራ ቆይቷል። ይህንን ህልሙን ለማሳካት ከታሪካዊ የውጭ ጠላቶች ጋር በማበር የበላበትን ወጪት ሰባሪ እንደሆነ አስመስክሯል። የስልጣን ጥም ያናወዛቸው የቡድኑ ጥቂት አመራሮች የትግራይ ሕዝብን ለብዙ ችግሮች ዳርገውታል። ወንድም ከሆኑ ሕዝቦች ጋርም ደም በማቃባት ታሪክ የማይረሳው ወንጀል ፈጽሟል።
ቡድኑ በስልጣን ዘመኑ ልዩነት ይፈጥራሉ ያላቸውን ማናቸውንም ነገሮች በማራገብ እና ሕዝብን ከሕዝብ በመከፋፈል በሕዝቦች መካከል አለመተማመን ለመፍጠር ሠርቷል። በዚህም እንደ አገር ያስከፈለንና እያስከፈለን ያለው ዋጋ ቀላል አይደለም።
ዜጎች የዘመናት የውስጥ መሻት ፍትህ፣ ዴሞክራሲ፣ እድገትና መሻሻል ቢሆንም፣ ቡድኑ ለሦስት አስርት ዓመታት በዘለቀው የስልጣን ቆይታው በዜጎች ላይ እንደ መዠገር ተጣብቆ ደማቸውን ከመምጠጥ ባለፈ አንዳች የፈየደላቸው ነገር አልነበረም።
ይባስ ብሎ ባለፉት ሁለት ዓመታት የኢትዮጵያን ሉዓላዊነት በሚያስከብረው የመከላከያ ሰራዊት ላይ የክህደት ጥቃት በመፈጸም አገርን በግልፅ የማፍረስ ዘመቻ ውስጥ ይገኛል። ከአንድም ሦስት ጊዜ በአገርና ሕዝብ ላይ የእብሪት ጦርነት ፈፅሟል። በዚህም በርከት ያሉ የግፍ ተግባራትን በአማራና አፋር ሕዝቦች ላይ ፈፅሟል።
በእነዚህ የእብሪት ጦርነቶች እንዳሰበውና እንዳለመው ዳግም ወደስልጣን መምጣት አልቻለም፤ ከዚያ ይልቅ እራሱ በጫረው እሳት እየተቃጠለ ወደ አመድነት እየተለወጠ፤ ወደ መቃብር እየወረደ ይገኛል። ከሞት እንዲታደጉት ለጋላቢዎቹ የተደጋገሙ ጥሪዎችን አቅርቧል። ለጥሪውም ምላሽ የሚሰጡ ድምጦች እየተበራከቱ ከመጡም ውለው አድረዋል።
መንግሥት በተደጋጋሚ ሲያቀርብለት የነበረውን ችግሮችን በሰላማዊ አማራጭ የመፍታት አማራጭ ከጣለበት በማንሳት የመቆመሪያ ካርድ ለማድረግ እየተንቀሳቀሰ ካለም ሰነባብቷል። ጋላቢዎቹም ይህንኑ ጉዳይ እንደገደል ማሚቶ እያስተጋቡ የውስጥ ጉዳያችንን ዓለም አቀፍ አጀንዳ ለማድረግ እየሠሩ ነው።
የኢትዮጵያ ሕዝብና እና መንግሥት የአሸባሪውን ትህነግን አገር የማፍረስ ሴራ ጠንቅቀው ይረዳሉ። የቡድኑ እውነተኛ ባህሪ (ፍጥረታዊ ማንነቱን) ከማንም በላይ ያውቃሉ። በነፃነት ስም ጫካ ከነበረበት ጊዜ አንስቶ የትግል አጋሮቹን በጅምላ በመጨፍጨፍ እና በክህደት የሚታወቅ ቡድን ነው። በስልጣን ዘመኑም የኢትዮጵያን ሕዝብ በተደጋጋሚ ክዷል። በሕዝባችን የጋራ የእምቢተኝነት ትግል ከስልጣን መወገዱ እንደማይቀር ሲረዳም ቀድሞ የሚታወቅበትን የመከፋፈል ሴራ ይዞ በትግራይ ሕዝብ ጉያ ውስጥ ተሸሽጓል። በስልጣን ዘመኑ በሴራ ሊያፈርሳት ያልቻለውን አገር የትግራይን ሕዝብ በመነጠልና በሕዝቡ ውስጥ ጥላቻን በመዝራት የኢትዮጵያ ሉአላዊነት ከማይፈልጉ ታሪካዊ ጠላቶቻችን ጋር በመሆን ለማፍረስ እየሠራ ይገኛል።
መንግሥትና ሕዝብ አገርን ከአሸባሪው ትህነግ የጥፋት ተልዕኮ የመታደግ ኃላፊነት አለባቸው። ይህንን ኃላፊነት ለመወጣት የማንንም ይሁንታ አይጠይቁም፤ በቀደመው የአገሪቱ ረጅም ታሪክም ጠይቀው አያውቁም።
ይህንን ኃላፊነታቸውን ለመወጣት እንደቀደመው ዘመን ልዩነታቸውን ሁሉ ወደ ኋላ ትተው በህብረት እየተንቀሳቀሱ ነው። ይህ ደግሞ ታሪካዊ ጠላቶቻችንን ጨምሮ አሸባሪውን ትህነግ የሚጋልቡ ኃይሎች ክፉኛ አሳስቧቸዋል። እረፍት ነስቷቸዋል። ከመቼውም ጊዜ በተሻለ መልኩ ተናበው እንዲሠሩ እያደረጋቸው ነው።
ቀደም ባለው ወቅት የመናበብ ሥራቸው አገርን የህልውና ስጋት ውስጥ ጨምሮ የነበረ ቢሆንም አሁን ግን ሁኔታዎች ሙሉ በሙሉ መልካቸውን እየቀየሩ ነው። የኢትዮጵያ ጥምር ጦር በሽብርተኛው ቡድን በወረራ የተያዙ የአማራና የአፋር ግዛቶችን ከማስለቀቅ አልፎ የኢትዮጵያን ሉአላዊ ግዛት ለማስከበር በትግራይ የሚገኙ ቁልፍ ቦታዎችን እየተቆጣጠረ ይገኛል።
ይህ በብዙ መስዋእትነት የተገኘ ድል ነው፤ አገርን ከህልውና ስጋት መታደግ፤ ሕዝባችን ቀና ብሎ እንዲሄድ ያስቻለ ታላቅ የታሪክ ክስተት ነው። የሕዝባችንን አይበገሬነት፤ የጥምር ኃይሉን ጀግንነት በተግባር ያስመሰከረ ነው። አሸባሪውን ትህነግ ጨምሮ ጋላቢዎቻቸውን ያስደነገጠ ነው።
በዚህ ሁኔታ ውስጥ መንግሥት ካለፉት የሽብርተኛ ቡድን ተደጋጋሚ ክህደቶች አንድ ነገር መማር እንደሚኖርበት ይታመናል። የአሸባሪው ቡድን የሰላም /የድርድር ጥያቄ ትንፋሽ ገዝቶ፤ ዳግም እራሱን አደራጅቶ ወረራ ለመፈፀም የሚደረግ የቂል ቀልድ መሆኑን ነው።
አንዳንድ ምዕራባውያን አገሮች ሆኑ ታሪካዊ ጠላቶቻችን በድርድር ሰበብ የኢትዮጵያን የግዛት አንድነት የሚፈታተን፣ ጫና ውስጥ የሚከት ድርጊቶችን ከመሞከር ይቆጠባሉ ተብሎ አይታሰብም አሁን አሁን በአደባባይ እየሆነ ያለውም ይኸው ነው።
የኢትዮጵያ ሕዝብ መንግሥት የኢትዮጵያን ሉአላዊነት ለማስከበር ከሚያደርገው ዘመቻ ጎን ለጎን የሰላም አማራጭ ለመጠቀም በሆደ ሰፊነት እየሄደ ያለበት መንገድ መልካም ቢሆንም፤ ከአሸባሪው ትህነግ የክህደት ባህሪ አንፃር ማንኛውም ነገር በአግባቡ ማየት መልካም ነው።
ቡድኑ ከተካነበት የሃሰት ፕሮፓጋንዳ አንጻር ዓለም አቀፉን ኅብረተሰብም ሆነ ሕዝባችን የፕሮፓጋንዳው ሰለባ እንዳይሆኑ በተደራጀ መንገድ መንቀሳቀስ ያስፈልጋል። ለዚህ የሚሆን አቅም መፍጠርም ወሳኝ ነው።
ዛሬ ላይ እንደ ትናንቱ ቡድኑ የምዕራባውያንን የመገናኛ ብዙኃን በመጠቀም «የመከላከያ ሰራዊት በትግራይ ሕዝብ ላይ ግፍ እየሠራ ነው—ወዘተ» የሚሉ ዘገባዎችን በስፋት እያስነገረ ነው። ይህንንም እየተቀባበሉ የሚያስተጋቡ ምዕራባውያን ተቋማትና አገራት ተበራክተዋል።
የቡድኑ የጥፋት ህልም እንዲሳካ የሚደረገው ርብርብ ከሁሉም በላይ ከአሸባሪው ትህነግ በላይ የቡድኑ አጀንዳ ባለቤቶች የቱን ያህል ብዙ እንደሆኑ አመላካች ነው። ይህ በራሱ ከፍ ያለ ጥንቃቄ የሚሻ ጉዳይ ነው። በጥበብና በማስተዋል ልንሻገረው የሚገባ ወቅታዊ አገራዊ ተግዳሮት ነው።
ከዚህ አንጻር መንግሥት ለሰላም በሩን ክፍት አድርጎ በአፍሪካ ህብረት ማዕቀፍ ስር ንግግር ለማድረግ እየሄደበት ያለው መንገድ የሚደገፍ ነው። ከዚህ ጎን ለጎን ግን ጦር ሰብቆ በዱር ገደሉ ኢትዮጵያን እየወጋ የሚገኘው ኃይል ህልውናው እንዲሟጠጥ መሥራት ሌላው የቤት ሥራ ነው።
በትህነግ የጭቆና ቀንበር ስር ታግቶ የሚገኘውን የትግራይ ሕዝብ መታደግ ሌላው የመንግሥት ሕገመንግሥታዊ ኃላፊነት ነው። ነፃ በወጡ አካባቢ ለዜጎች በበቂ መልኩ እርዳታ የሚደርስባቸውን መንገድ ማመቻቸት፤ በቀጣይ በተራድኦ ድርጅት ስም ገብተው ለቡድኑ የሎጂስቲክስ አቅም የሚሆኑ ድርጅቶች በአግባቡ ተከታትሎ እርምጃ መውስድ ያስፈልጋል።
በአጠቃላይ አሸባሪው ትህነግ ከሴራ ጉንጎናው የማይፀዳ፤ ለኢትዮጵያ መፍረስ አሰልሶ የሚሠራ ድርጅት መሆኑን ምንጊዜም መዘንጋት የለብንም። የእናት ጡት ነካሹ ትህነግ፣ ምዕራባውያን እንዲሁም ታሪካዊ ጠላቶቻችን ከጎነጎኑልን አደገኛ ወጥመድ መውጣት እና ሉአላዊነትን ማስከበር የምንችለው ሁሉንም አማራጭ በጥበብና በማስተዋል አይተን መጠቀም ስንችል ነው። ጠንካራ አገር፣ ጠንካራ ሕዝብና ይህን አስጠብቆ የሚያቆይ መንግሥት ኖሮን ዳግም ወደ ኃያልነታችን ለመመለስ የዛሬውን ውስብስብ ችግር የሚፈታ ጫንቃ ሊኖረን ያስፈልጋል።
ዳግም ከበደ
አዲስ ዘመን ጥቅምት 20 ቀን 2015 ዓ.ም