የትግራይ ሕዝብ እና ወራሪው እና አሸባሪው የትህነግ ቡድን የአንድ ሳንቲም ሁለት ገጽታዎች ናቸው፤ቡድኑ ያለ ትግራይ ህዝብ፤ የትግራይ ሕዝብ ያለ ቡድኑ ከባህር እንደወጣ ዓሳ ማለት እንደሆነ አድርገው የሚያስቡ አሉ። በአንፃሩ የትግራይ ህዝብና የትህነግ ለየቅል ናቸው። ሁለቱን ነጥሎ ማየት ያስፈልጋል የሚል ሀሳብ የሚያነሱም ብዙዎች ናቸው። እንደኔ አመለካከት ሊጠናና ሊሰላ ወይም የመከራከሪያ ነጥብ ሊሆን የሚገባው የትግራይ ሕዝብ ለትህነግ ምን መሰዋት ከፈለ? በሌላ በኩል ደግሞ ቡድኑ ለትግራይ ሕዝብ ምን ጠቀመው? ወይም ምን አመጣለት? በሚለው ላይ ሊሆን ይገባል ባይ ነኝ።
በዚህ አጭር ጽሁፌ ይህንን ሀሳብ መንደርደሪያ በማድረግ ትህነግ በ1969 ዓ.ም በደደቢት በረሃ ከተመሰረተ ጀምሮ አሁን እስካለንበት ወቅት ድረስ ያለውን እውነታ በወፍ በረር ለማየት እሞክራለሁ።
“ከአጋም የተጠጋ ቁልቋል እድሜ ልክ ሲያለቅስ ይኖራል” እንደሚባለው ለኔ የትግራይ ህዝብ ከአጋም የተጠጋ ቁልቋል ነው። ምክንያቱም በሴራ እና በበታችነት ስሜት በ1960ዎቹ መጨረሻ ወደ ጫካ የወረደው አሸባሪው የትህነግ ቡድን ከጥንስሱ ጀምሮ በትግራይ እናቶች የማህፀን ክፋይ ደም የጨቀየ ነው።
በዚያ በደርግ ዘመን ይደርስ የነበረውን ግፍና መከራ ለመታገል ብሎም ከቀይና ነጭ ሽብር ሰይፍ ለማምለጥ በአራቱ የትግራይ ማዕዘን ወደ በረሃ ከጎረፉ የትግራይ ወጣቶች ውስጥ ሕዝባዊ አመለካከት የነበራቸውን ከትግራይ ህዝብ አብራክ የወጡ የህዝብ ልጆችን በሴራ በማስወገድ ጸረ- ህዝብነቱን አሃዱ ብሎ የጀመረ አሸባሪ ቡድን ነው ።
ቡድኑ በዚህ ፀረ-ህዝብነቱ ብሩህ አዕምሮና ህዝባዊ አመለካከት እንዲሁም ተሰሚነትና ተደማጭነት ያላቸው ታጋዮች ቀጣይ ስጋት ይሆናሉ በሚል በስፋት መግደሉ ይነገራል። በጦርነቱ ከሞቱት ይልቅ በቡድኑ ሴራ ለህልፈት የተዳረጉ ይበልጣሉ የሚሉም ብዙ ናቸው። በ17 ዓመቱ የትጥቅ ትግሉም የትግራይ እናቶች ከ60 ሺ በላይ የማህጸናቸውን ፍሬ ገብረዋል።
ለትግራይ እናቶች ሾተላይ የሆነው የጁንታው ቡድን በ1977 በአገሪቱ የተከሰተውን ድርቅና ይህን ተከትሎ የተፈጠረው ረሃብ የትግራይን ህዝብ እንደቅጠል ሲያረግፍ ቡድኑ ሰብአዊ ድጋፍና እርዳታ ለህዝቡ እንዳይደርስ በማድረግ የትግራይ ህዝብ ለከፋ እልቂት ዳርጓል ፤ ህዝቡ ተስፋ ቢስ እንዲሆን በማድረግ ወደ ጦር ሜዳ ገብቶ የሳት እራት እንዲሆን ሰርቷል። ለእርዳታ የመጣ ገንዘብን ለጦር መሳሪያ መግዧ ከማዋል ጀምሮ፤ የእርዳታ አቅርቦቶችን በመሸጥ ለተመሳሳይ ተግባር አውሏል።
እንዲሁም የማፊያው ቡድን በሸረበው ሴራ የደርግ መንግስት ለገበያ በወጣው በሃውዜን ህዝብ ላይ የቦንብ ናዳ እንዲያወርድ ፤ እልቂቱን በድብቅ በመቅረጽ የወገኖቹን ደም ለፕሮፓጋንዳ ያዋለ የጭራቆች ስብስብ ነው። በጥቅሉ የማፊያው ቡድን በትግራይ እናቶች ማህጸን ፍሬ በሆኑ ለጋ ወጣቶች እየቆመረ ከ17 ዓመታት የትጥቅ ትግል በኋላ አራት ኪሎ ቤተ መንግሥትን መግባት የቻለ ነው።
የማፊያው ቡድን በትረ ስልጣኑን ከተቆጣጠረ በኋላ ስልጣን ላይ በነበረበት 27 ዓመታት ለትግራይ ሕዝብ ምን አመጣለት? ብለን ስንጠይቅ የአንድ ጎጥ ተወላጆች ባንኩን፣ ታንኩን ፣ ንግዱን፣ መርከቡን፣ ፕሌኑን ወ.ዘ.ተ ተቆጣጥረው የአገሪቱን አንጡራ ሀብት ሲዘርፉ ነበር። ነገር ግን ልጆቻቸውን የጦር ሜዳ ሲሳይ አድርገው ለዚህ ስልጣን ያበቋቸው የትግራይ እናቶች የሚጠጡት ንጹህ ውሃ እንኳን አላገኙም። በስመ ትግሬ የአንድ ጎጥ ተወላጆች አገር ሲዘርፉ ልጇን በጦርነት የገበረች የትግራይ እናት ግን የልጇን ፎቶ ታቅፋ ነው የቀረችው።
በጥቅሉ በትህነግ የአገዛዝ ዘመን የትግራይ ሕዝብ ከሌላው የኢትዮጵያ ህዝብ የተለየ ያገኘው ጥቅም የለም። ይልቁንም በጨቋኝና በተጨቋኝ ትርክት የትግራይ ሕዝብ ከሌሎች እህት ወንድም ከሆኑ ህዝብ ጋር ተስማምቶ እንዳይኖር ሴራ እየሸረበ በጎሪጥ እንዲተያይ ሲያደርግ ቆይቷል።
ቡድኑ ቀደም ባለው ጊዜ ባንኩን፣ ታንኩን ፣ ንግዱን፣ መርከቡን በእጁ ስር አድርጎ ተቆጣጥሮ በነበረበት ወቅት ዞር ብሎ ያላየውን የትግራይን ህዝብ ከጠዋት ከማታ ሳያስበው ከአራት ኪሎ ቤተመንግስት ሲነቀል፤ የአማዞን ጫካ የአለም ሳንባ እንደሆነ ሁሉ ትህነግ በትግራይ ሕዝብ ጉያ ተደብቆ ልትቋረጥ ያለችውን እስትንፋሱን ማቆያ ጫካ አድርጎ እየተጠቀመበት ይገኛል።
ይህ የሽብር ቡድን በተደጋጋሚ መንግሥት ለሰላም የዘረጋውን እጅ በማጠፍ “ከፈላጭ ቆራጭነቴ ተነስቼ እንዴት እኩል እታያለሁ” በሚል ትዕቢት ዳግም የትግራይ እናቶችን የማህጸን ፍሬ የሆኑ ህጻናትን ጭምር በአደንዛዥ እጽ እያሳበደ የእሳት እራት እያደረገ ይገኛል።
በዚህም የጁንታው አመራሮች ልጆቻቸውን በአሜሪካና አውሮፓ በቅንጡ ትምህርት ቤት እያስተማሩ የአገር መከላከያ ሰራዊትን ከጀርባው ወግቶ ባስጀመረው የሰሜኑ ጦርነት የረገፉ የትግራይ የድሃ ልጆችን ቤት ይቁጠረው።
እንዲሁም ማንም ቤተሰብ ልጁን ለትህነግ የጦር ሜዳ ሲሳይ አድርጎ ካልገበረ የሰብአዊ እርዳታም ሆነ ድጋፍ እንደማያገኝ በምርኮ የተያዙ የክልሉ ተወላጆች ሲናገሩ ተደምጠዋል። የሰብአዊ ድጋፍና እርዳታን ለጦርነት በማዋል የትግራይ ሕዝብ በርሃብ አለንጋ እንዲገረፍ በማድረግ ህዝቡ ተስፋ ቆርጦ ወደ ጦርነት እንዲማገድና እንዲያልቅ እያደረገ ይገኛል።
ለአብነት በቅርቡ የጥምር ጦሩ ዘልቆ በገባባቸው በትግራይ ክልል አንዳንድ አካባቢዎች ህዝቡ የሚበላው አጥቶ ፆሙን እያደረ ነገር ግን ቡድኑ ለጦርነት ሲል ደብቆ ያስቀመጠው የዩኤስ ኤይድ እርዳታ ተገኝቶ ለሕዝቡ ሲከፋፈል ተመልክተናል።
በጥቅሉ የማፊያው ቡድን ከጥንስሱ ጀምሮ ለአምስት አስርት ዓመታት የትግራይን ህዝብ የጦር ሜዳ ሲሳይ ከማድረጉ ባሻገር በተለይ የሰሜኑ ጦርነት ከተቀሰቀሰ ጀምሮ የትግራይ ህዝብ ከአለም ጋር እንዳይገናኝ እና ሀሳብ እንዳይቀያየር አፍኖ ይዞ በትምህርት፣ በቴክኖሎጂ፣ በልማት ወ.ዘ.ተ ወደ ኋላ በማስቀረት ወደ ድንጋይ ዘመን ቀይሮታል ቢባል ማጋነን አይሆንብኝም።
ታዲያ የትግራይ ሕዝብ ለዘመናት ውድ ልጆቹን እና ሕይወቱን ለትህነግ ገብሮ በምላሹ ቡድኑ ምን ወረታ ከፈለ ብለን ስንጠይቅ? ምላሹ አይደለም ለትግራይ ህዝብ ለሌሎች እህትና ወንድም ህዝቦች የእግር እሳት ነው የሆነው። በተለይ በስልጣን ዘመኑ ህዝባዊ አመለካከት ያላቸውን የኢትዮጵያ የቁርጥ ቀን ልጆች ጥፍር ነቅሏል፣ አኮላሽቷል አገር ዘርፏል፣ ክዷል… በጥቅሉ የኢትዮጵያ ህዝብ ላይ ህልቆ መሳፍርት የሌለው በደል አድርሷል። ሆኖም ከሌሎች የኢትዮጵያ ብሔረሰቦች በላይ ቡድኑ ለዘመናት የነገደው በየትግራይ ሕዝብ ደም፣ ስጋና አጥንት ላይ ነው።
የትግራይ ህዝብ ይህን የሽብር ቡድን ከሌሎች እህት ወንድሞቹ ጋር ድርና ማግ ሆኖ ለአንዴና ለመጨረሻ ጊዜ ከጫንቃው አሽቀንጥሮ የሚጥልበት ጊዜው አሁን ነው። የሽብር ቡድኑ “የእናት ጡት ከጣለ ህጻን ጀምሮ ምርኩዝ ይዞ መንቀሳቀስ እስከሚችል የ75 እና 80 ዓመት አዛውንት ድረስ ያለ ማንኛውም የትግራይ ተወላጅ ጦር መሳሪያ ባይኖርህ ድንጋይ ይዘህ በእህት ወንድሞችህ ላይ ወደ ጦር ሜዳ ዝመት” ብሎ የጎሰመውን የጦርነት ነጋሪት የትግራይ ህዝብ “አሻፈረኝ” በማለት የጥፋት ቡድኑ መንግሥት ወደ አቀረበው ሰላማዊ ድርድር እንዲቀርብ ግፊት ማድረግ፤ አልያም ከሌሎች የኢትዮጵያ ህዝብ እህት ወንድሞቹ ጋር በመሆን ለዘመናት በደሙ የነገደውን “የትግራይ እናቶች ሾተላይ” ግብዓተ መሬቱን መፈጸም ይኖርበታል።
ሶሎሞን በየነ
አዲስ ዘመን ጥቅምት 15 ቀን 2015 ዓም