የሚሻለን ምንድነው? እንደ አገር፣ እንደ ማህበረሰብ የሚጠቅመን ምንድ ነው? አሁን ላለችው አገራችን፣ አሁን ላለው ፖለቲካና ፖለቲከኛ የሚበጀን ምንድ ነው? የሚጠቅመንን እስካላወቅን ድረስ በማይጠቅሙን ነገሮች ውስጥ መኖራችን ግድ ይሆናል። አሁን ላለንበት ወቅታዊ ሁኔታ ምን ሊጠቅመን እንደሚችል ማወቅ አገራችንን ሊታደግልን የሚችል የመጀመሪያው መልካም ውሳኔ ነው። በማይጠቅሙን ብዙ ሀሳቦች ላይ ተነጋግረንና ውሳኔ አሳልፈን እናውቃለን፤ መልካም ያልናቸው እነዛ ሀሳቦች ግን ሲረዱን አልታዩም። አሁን ከአሸባሪው ትህነግ ሆነ ከውጪ ጫናዎች አገራችንን የምንጠብቅበት ጊዜ እንጂ በከሰረ ሀሳብ እርስ በርሳችን የምንናቆርበት አይደለም።
የሚሻለን የተሻለውን መምረጥ ብቻ ነው። የተሻለው ነገር ደግሞ የተሻለ አገር ሊፈጥር የሚችል ሀሳብ፣ እውቀት፣ ምክክር፣ ንግግር፣ ሰላም፣ አንድነት ነው። አገር ሊጠቅሙ የሚችሉ ቁም ነገር አዘል ሀሳቦችን ወደ ጎን ብለን በማይጠቅሙን የሰፈር ወሬዎች ላይ ተጠምደን ብዙ እድሎቻችንን ገፍተናል። አጀንዳ ሊያዝላቸው ቀርቶ ሊደመጡ እንኳን በማይገባቸው አሉባልታዎች ላይ ተጠምደን የአንድ ትውልድ ያክል እድሜ አባክነናል። አሁን በነቃና በተቆጨ ልብ የሚሻለንን የምንመርጥበት ጊዜ ላይ ነን።
ከአሸባሪው ትህነግ ውንብድና መርጦ በተወናበደ አስተሳሰብ ለሀያ ሰባት ዓመት የተወናበደች አገር ፈጥሯል። አሁንም በእውቀትና በአስተውሎት ባልጠራ አካሄድ እንደ ትላንቱ አንድ ቦታ እየረገጠ በአንድ አይነት ድርጊት ውስጥ ይገኛል። እኛስ ምን መረጥን? አገር ወዳድ ነን የምንለው እኛ የነውረኞችን ሀሳብ ተረት የሚያደርግ ሀሳብና አንድነት ያስፈልገናል። ቡድኑ ከምዕራባውያን ጋር ነው። እንደሱ ጭካኔና ውንብድናን በተላበሱ ሸኔና አልሻባብ ጋር ነው። የኢትዮጵያን መፍረስና መውደቅ ከሚመኙት ታሪካዊ ጠላቶቻችን ጋር ነው። እኛስ ከማን ጋር ነን?
እኛ ከራሳችንና ኢትዮጵያን ከሚያፈቅሩ ወንድሞቻችን ጋር ልናብር ይገባል። እውነትን ሽተው ስለኢትዮጵያ ከሚጮሁ አንደበቶች ጋር ልንቆም ይገባል። የኢትዮጵያን ሉአላዊነት አሳልፌ አልሰጥም ብሎ ብዙ ጫናና አድሎ እያስተናገደ ካለው ከመንግስት ጎን ልንቆም ይገባል። ባገኘነው አጋጣሚ ሁሉ አገራዊ ክብራችንን ከፍ ሊያደርጉ በሚችሉ አጋጣሚዎች ውስጥ መሆናችንን መረዳት ይኖርብናል። ከሰሞኑ አሸባሪውን ትህነግ በመቃወም የትግራይ ተወላጆች አደባባይ ወጥተዋል። መነሻቸውን ከአራት ኪሎ በማድረግ ሽሮ ሜዳ በሚገኘው የአሜሪካ ኤምባሲ ፊት አሸባሪ ቡድኑን በመቃወም ከነመፈክራቸው ድምጻቸውን አሰምተዋል። ቡድኑ ለትግራይ ህዝብ አስቦ እንደማያውቅና ለራሱ ሲል የድሀ ልጆችን እያስጨረሰ እንደሆነ ተቃውሟቸውን ገልጸዋል። ትግራይ ጦርነት ሳይሆን ሰላም እንደሚያስፈልጋትና ቡድን ግን ደግሞ የሰላም አማራጮችን ረግጦ ንጹሀንን እያስጨረሰ እንደሆነ በመግለጽ የአሜሪካ መንግስት በቡድን ላይ ርምጃ እንዲወስድ ድምጻቸውን አሰምተዋል።
የሚሻለን የሚሻለውን መምረጥ ነው። ልክ እንደ ትግራይ ተወላጆች ሁሉ ስለ አሸባሪው ትህነግ እዚም እዛም መጮህ ያስፈልጋል። ከሰላም የበለጠ የሚሻለን አልነበረም። ከውይይትና ከምክክር በላይ የሚያስፈልገን አልነበረም። መንግስት ይሄን ሲመርጥ ቡድኑ ግን ይሄን አልመረጠም። ምክንያቱም አሸባሪ ቡድን ስለሆነ በሰላምና በመመካከር ውስጥ የሚያተርፈው የለም። ብቸኛ አላማው ስልጣንና ኢትዮጵያን ለእሱ እንደምትመች አድርጎ መፍጠር ስለሆነ ከሰላም ይልቅ ጦርነትን፣ ከምክክር ይልቅ ፉክክርን መርጦ የሚንቀሳቀስ ነው። እንደዛማ ባይሆን በዚህ ልክ በባልተሰቃየን ነበር። ሰሞኑን ከአንድ የፖለቲካ ምሁር ያደመጥኩት አንድ ደስ የሚል እውነት ነበር … አሸባሪውን ትህነግ ሲገልጡን እንዲህ ነው ያሉት ‹ሕወሓት ካለጦርነት መኖር የማይችል ቡድን ነው። በጦርነት ተወልዶ በጦርነት ስላደገ የሰላምን ዋጋ አያውቀውም። ዛሬ ላይ በንጹሀን ላይ ይሄን ያክል ዘግናኝ ግፍ የሚያደርሰው፣ ለትውልድ የሚሆኑ ትምህርት ቤቶችን፣ ሆስፒታሎችን፣ ባንክ ቤቶችን የሚያፈርሰው፣ ምንም የማያውቁ ህጻናትን የሚገለው፣ ሴቶችን የሚደፍረውና አረጋውያንን የሚያሰቃየው ህዝብ በመንግስት ላይ እንዲነሳ በማሰብ ነው“ ሲሉ።
የትኛውም ዜጋ ለቡድኑ እኩይ አላማ ማስፈጸሚያ እንዳንሆን ራሳችንን መጠበቅ አለበት። የአሸባሪውን ትህነግ እና የጀሌዎቹን እኩይ አላማ ተረድቶ ኢትዮጵያን ለአውሬዎች አልሰጥም ካለው መንግስት ጎን መቆም ይጠበቅብናል። የሚሻለን አንድና አንድ ኢትዮጵያን ከሚያፈቅሩ መልካም ልቦች ጎን መሰለፍ ነው። እዛም እዚም የምንሰማቸው ሞትና መፈናቀሎች ቡድኑ ሆን ብሎና አስቦበት በህዝብና በመንግስት መካከል ልዩነትን ለመፍጠር የሚያደርገው የተንኮል ርምጃ ስለሆነ ለዚህ እኩይ አላማው ማራመጃ እንዳንሆን ራሳችንን በማስተዋል መክበብ አለብን። ሙህሩ እንዳሉት..በሰላም በመነጋገር ጦርነትን ማስቀረት እየተቻለ ግን ደግሞ አሸባሪው ትህነግ ጦርነትን የመረጠበት አንዱና ዋነኛ ምክንያት በህዝብና በመንግስት መካከል አለመተማመንን ለመፍጠር ነው። ህዝብ በመንግስት ላይ እምነት አጣ ማለት የቡድኑ ጊዜ ነው ማለት ነው። ቡድኑ ህዝብና መንግስትን ሆድና ጀርባ አድርጎ የስልጣን መደላድሉን አቋራጭ ማድረግ ይፈልጋል። ለዛም ነው ሸኔንና አሸባሪ ቡድኖችን አሰማርቶ ብዙ ሞትና እንግልቶችን እየፈጠረ ያለው።
አሸባሪው ትህነግ መች ጦርነት መጀመር እንዳለበት፣ መች ማቆም እንዳለበት በስሌት ውስጥ ነው። ርምጃው ሁሉ ኢትዮጵያን ወደሚጎዳ ነው። መች ገርፎ ማልቀስ እንዳለበት፣ መች ዋሽቶ ማስመሰል እንዳለበት ያውቃል። አርሶ አደሩ ምርት የሚሰበስብበትንና ምርት የሚያመርትበትን ጊዜ እየጠበቀ ነውጥ ሲፈጠር ነበር..ኢትዮጵያን ለማፍረስ፣ ኢትዮጵያን ለማስራብ ብዙ ለፍቷል.. በአንድነት ድምጾች ግን አልተሳካለትም። አሁንም እንዳይሳካለት ለማድረግ የሚሻለንን መምረጥ አለብን። ለቡድኑ የማይመች ወጣትና ህዝብ መፈጠር አለበት። አምኖ የሚጠይቅ ሳይሆን ጠይቆ የሚያምን ትውልድ አገራችን ትሻለች።
ቡድኑ ስለመረጠ ኢትዮጵያን ለማፍረስ ያዋጣኛል ያለውን ሁሉንም አማራጭ እየተጠቀመ ነው። ከውጪ ታሪካዊ ጠላቶቻችንን ጨምሮ አንዳንድ አገራትንና ዓለም ዓቀፍ ተቋሟትን፤ ከአገር ውስጥ አሸባሪው ሸኔና ሌሎች አሸባሪ ቡድኖችን በመጠቀም በኢትዮጵያ ላይ ኪሳራ ለማድረስ እየለፋ ነው። የእስከዛሬ የአንድነት ጽናታችን በርትቶ አላማውን እንዳያሳካ አድርገነዋል። ባለፉት የስልጣን ዘመኑም ቢሆን ኢትዮጵያን ከመጥቀም ይልቅ ራሱን በመጥቀም ስራ ላይ ነበር ያሳለፈው። ስልጣንና ብሄርተኝነትን መሰረት ባደረገ የፖለቲካ ፍልስፍና ለሶስት አስርት ዓመታት አገራችንን ወደ መቀመቅ የከተተ ሆኖ አልፏል። ሸኔ ሕወሓት በሀያ ሰባት ዓመት የስልጣን ዘመኗ አምጣ የወለደችው የበኩር ልጇ ነው። ዛሬ ላይ ኢትዮጵያን በማፍረስ ዘመቻ ላይ ቀኝ እጇ ሆኖ እያገለገላት ያለው የዛ ዘመን ውለታውን እየከፈለ ነው።
ከአሸባሪው ትህነግ ከውሸትና ከጭካኔ ወጥቶ አያውቅም። መሰረቱ በንጹሀን ደምና እንግልት የጸና ነው። ገሎና አጭበርብሮ ወደ ስልጣን መጣ። አሁንም በመግደል ወደ ስልጣን ለመምጣት እየባዘነ ነው። ሁሉን ትተን ያለፉትን ሁለት ዓመታት ብናስተውል እንኳን ለማመን የሚከብዱ ውሸቶችንና ነውሮችን በኢትዮጵያ ህዝብ ላይ ፈጽሟል። ይሄ ቡድን በብዙ ውሸትና በብዙ ጨካኝ ወንበዴዎች የተዋቀረ ነው። አላማው ሰላም ቢሆን ብዙ የሰላም አማራጮች ነበሩት። ግን አይደለም..አላማው ኢትዮጵያን ማፍረስ ስለሆነ የሰላም አማራጮችን ሳይቀበል ቀይቷል። ይሄን ቡድን የምንነቅለው የሚሻለንን ስናውቅ ብቻ ነው። የሚሻለን ደግሞ አንድነትና ወንድማማችነት ነው። የሚሻለን ስለአገራችን አንድ አቋም ይዘን በይበቃል ስንጮህ ነው። የሚሻለን የሚሻለውን ስናውቅ ነው።
አሁንም ቢሆን ቡድኑ ወደ ሰላም ድርድር እንዲመጣ እድሎች አሉት። የእስከዛሬውን የመንግስትን ጥሪ ትተን የሰሞኑን የአፍሪካ ህብረትን የሰላም ጥሪ ብናይ እንኳን ቀድሞ የይሁንታ ምላሽ የሰጠው የኢትዮጵያ መንግስት ነው። የአፍሪካ ህብረት የሰላም ምክክሩን የሚመሩ አካላትን ጨምሮ የትና መቼ የሚለውን ገልጾ የሰላም ውይይቱ እንዲጀመር ለሁለቱም ተፋላሚ ቡድን (ለሕወሓትና ለፌደራል መንግስት) ጥሪ ማቅረቡ ይታወሳል። በዚህ ጥሪ ላይ ምላሽ በመስጠት ለሰላም ጥሪው ያለውን አቋም በመግለጽ መንግስት ቀዳሚው ሆኗል። መንግስት የትም መቼም ያለምንም ቅድመ ሁኔታ ለሰላም ቅድሚያ መስጠቱን በብዙ አቅጣጫ ልናየው እንችለዋለን። የዜጎችን ሞትና እንግልት ለማስቀረት ከማሰብም በላይ ችግሮች በሰላማዊ መንገድ እንደሚፈቱ በማመንም ጭምር ነው። መንግስት ለአገርና ህዝብ ቅድሚያ መስጠትን ከምናይበት መንገድ አንዱ ከአሸባሪ ቡድን ጋር ለሰላም ድርድር መቀመጡ ነው።
የሚሻለን ምንድነው? ይሄ ለፖለቲከኞቻችንም ሆነ ለፖለቲካችንም ወሳኝ ጥያቄ ነው። የሚበጀን ምንድነው? ይሄ አሁን ላለነው ኢትዮጵያን እንወዳለን ለምንለው ለእኔና ለእናንተ ወሳኝ ጥያቄ ነው። ለሚመጣውም ሆነ ላለውም ትውልድ ወቅታዊ ጥያቄ ነው። የሚሻለንን ማወቅ አለብን። የሚጠቅመንን.. የሚበጀንን መለየት አለብን። በተመረጡ ሀሳቦች፣ በተመረጡ እውቀቶች የምንከባከብበት ወቅት ላይ ነን። አገራችን በሰላም ውስጥ ተጸንሳ እንድትፈጠር የሰላም ሰዎች መሆን የመጀመሪያው ውለታችን ነው። ሰላምን እንደ ትልቅ የእውቀትና የስልጣኔ በትር አድርገን ነውጥ ፈጣሪዎችን በመቃወም አደባባይ መውጣትን መለማመድ አለብን።
አገር በሰላም ውስጥና ከሰላም ውጪ ባሉ ጽንሰ ሀሳቦች ውስጥ የተለያየች ናት። በሕወሓት ውንብድና ያሳለፍናቸው አስራ ሁለት የመከራ ወራቶች አገራችንን ምን ያክል ዋጋ እንዳስከፈላት ሁላችንም የምናውቀው ሀቅ ነው። በብዙ ነገር የደከምንበት ወቅት ነው። አሁን ላይ ለተፈጠሩብን የህይወት ምስቅልቅሎች ተጠያቂው ሕወሓት ነው። ይሄን ቡድን የምናሸንፈው ደግሞ የሚሻለንን ስናውቅ ብቻ ነው..የሚሻለን ደግሞ ባለአገር መሆን ነው።
አገራችንን በተመለከተ ሁለት ምርጫዎች አሉን.. ራሳችንን በእውቀትና በምክንያታዊነት አጅበን ጠላቶቻችን የማይችሉን ማድረግ ወይም ደግሞ ሳንጠይቅና ሳንረዳ በውሸታሞች ተረትተን ለክፉ ሀሳባቸው መጠቀሚያ መሆን ነው። ወቅቱ ራሳችንን በእውቀትና በምክንያታዊ ሀሳቦች ከበን ለክፉዎች የማይመች እንድንሄድ የሚጠይቅ ነው። አሸባሪ ቡድን ተስፋ እንደሌለው ሊገባን ይገባል። ተስፋ ያለው ኢትዮጵያን ብለው በቆሙ ልቦች ውስጥ ነው። እናም ኢትዮጵያን ብለን እንቁም..። የሚሻለን ይሄ ነውና።
በትረ ሙሴ (መልከ ኢትዮጵ)
አዲስ ዘመን ጥቅምት 8 ቀን 2015 ዓ.ም