ዓለም የስልጣኔዋን ያክል በስይጥንና አስተሳሰብ ስር ከወደቀች ሰነባብታለች። የዚህ የስይጥንና እሳቤ ደግሞ ከባለጸጎቹ አገራት ዘንድ መሆኑ እጅግ ያስደንቃል። ስልጡን አገራት የስልጣኔአቸውን ያክል በደላቸውም እየከፋ የመጣበት ሰሞን ላይ ነን። የሰው ልጅ ከትናንት እስከዛሬ ስር በሰደደ ራስ ወዳድነት ውስጥ ነው። የአገራችን ወቅታዊ ሁኔታ ደግሞ ለዚህ ጥሩ ማሳያ ነው። በዚህ ሁለት አመት ውስጥ በአገራችን ውስጥ በተከሰተው ጦርነት የምዕራባውያኑ ባለጸጋ አገራት ደባ ምን ያክል እንደሆነ መረዳት እንችላለን። ሸፍጥ ባነገበ የይምሰል አንደበት ከአሸባሪ ጋር ቆመው ለንጹሀን እልቂት ምክንያት የሆኑ አገራትን ባሳለፍናቸው ሁለት የጦርነት አመታት ውስጥ ለማየት ችለናል። እውነትና ፍትህ የሚያሻቸውን ሕዝቦች ድምጽ ሽረው ከአሸባሪ ጋር በማበር መከራን የፈጠሩና ከኃላፊነት የጎደሉ አንዳንድ ባለጸጋ የምዕራቡ ዓለም አገራት ማንነታቸውን በግልጽ ያሳዩበት ጊዜ ነበር ማለት ይቻላል፤ ያለፉት ሁለት አመታት።
ሁሉም አገራት ማንም የማይነካው፣ ማንም ጣልቃ የማይገባበት የራሳቸው የሆነ የሉአላዊነት ድንበር አላቸው። ሁሉም መንግሥታት አገርና ሕዝባቸውን የሚጠብቁበት የመተዳደሪያ ሕገመንግሥት አላቸው። ከዚህ በተጨማሪ የትኛውም አገር በየትኛውም አገር የውስጥ ጉዳይ ላይ ጣልቃ የመግባት መብት እንደሌለው ዓለም አቀፉ ሕግ ይደነግጋል። ይሄ ግን ወረቀት ላይ እንጂ ወደ መሬት ሲወርድ ሌላ ነው። በተለይ ራሳቸውን የዓለም ፈጣሪ አድርገው ያዩ ኃያላን ነን ባይ ጥቂት ወዳጆቻቸው ይሄ እውነት ከንቱ እንደሆነ እንደርስበታለን። ለእኩይ ሀሳባቸው ለሚተባበሩ መልካም እየሆኑ፤ እንደ ኢትዮጵያ ላሉ ሀሳባቸውን ለሚቃወሙ እየከፉ ብዙ የክህደት ጎዳናዎችን ተራምዳዋለች። ባሳለፍነው ሁለት አመት ውስጥ አሸባሪውን የትህነግ ቡድን እየደገፉ ከጦርነቱ በላይ፣ ከድህነታችን በላይ መከራ ሆነውብን እንደሰነበቱ ሁላችንም የምናውቀው ሀቅ ነው። ያለፉትን ሁለት የጦርነት አመታቶች ከአሸባሪው ትህነግ ቡድን ጋር ብቻ ሳይሆን ራሳቸውን የዓለም ፈጣሪ አድርገው ከሚያዩት ኃያላን ጋርም ነው ታግለን እንደመጣን ማሰብም ማመንም ያለብን።
እነዚህ አገራት የኢትዮጵያን ፖለቲካ፣ ኢኮኖሚና ማህበራዊ እንቅስቃሴ እኔ ካልገባሁበት..እኔ ካልመራሁት በማለት እንደ ጥንቱ ቀኝ ገዢና ቀኝ ተገዢ በኢትዮጵያ ላይ የበላይነታቸውም ለማሳየት ሞክረው አልተሳካላቸውም። ባላቸው ነገር ሁሉ ከሃሳብና ቴክኖሎጂ ጀምሮ፤ እስከ ሎጂስቲክስና የጦር መሳሪያ የደረሰ ድጋፍ ከእነዚሁ የኢትዮጵያ ጠላቶችና አንዳንድ ምዕራባውያን አገሮች ለአሸባሪው ትህነግ ሲደርስ መቆየቱም የሚታወቅ ነው። እንደዚያም ሆኖ ግን ኢትዮጵያዊነትን አንገት ማስደፋትና ማንበርከክ አልተቻላቸውም። በዚህ ስልጡን ዘመን ላይ እንደ እነዚህ አገራት በተንሻፈፈና ፍትሃዊነት በጎደለው መርህ ፈርጣማ ክንዳቸውን በመጠቀም በሌሎች አገራት ላይ ተጽዕኖ የሚያደርሱ አገራት ቀላል የሚባሉ አይደሉም። እውነትን ደብቀው፣ ፍትህን ሸሽገው ለእነሱ እንዲመች አድርገው በሚሰሙት ወሬና በሚነዙት አሉባልታ ለድሀ አገራት በእንቅርት ላይ ጆሮ ደግፍ ሆነው የቆሙ ኃያላን ጥቂት የሚባሉ አይደሉም። እነማን እውነትን ሽተው ከእውነት ጎን እንደቆሙና እነማን አሸባሪን ወደ ስልጣን ለማምጣት ሸር ሲሸርቡ እንደነበር የምናውቀው ሃቅ ነው።
የአሸባሪው ትህነግ ቡድን ኢትዮጵያ ውስጥ ያደረሰው ግፍና በደል እየታወቀ፣ ባለፉት የስልጣን ዘመኑ በአገርና በሕዝብ ላይ ያደረሰው ታሪካዊ ስህተት እየታወቀ ባለጸጎቹ አገራት ግን ለዚህ አሸባሪ ቡድን ሽፋን በመስጠት ላይ ናቸው። በተለይ ታሪካዊዎቹ የኢትዮጵያ ጠላቶች እና አንዳንድ ምዕራባውያን አገሮች ባለፉት ሁለት አመታት ውስጥ አሸባሪውን ትህነግ በመደገፍ ያልተገባ አካሄድ በመሄድ በመንግሥት ላይ ተጽዕኖ በማድረስ ዓይን ያወጣ የሽብር ቡድኑን ወዳጅነታቸውን አሳይተዋል። እንደ እውነቱ ከሆነ ጦርነቱ ገና ድሮ መጠናቀቅ ይችል ነበር፤ ነገር ግን የአሸባሪው ትህነግን ቡድን በማገዝና የልብ ልብ እንዲሰማው በማድረግ ዛሬ ድረስ እንዲዘልቅ ሆኗል። ሁላችንንም በሚያስማማ መልኩ በአሜሪካ የፖለቲካ ሥርዓት ውስጥ ሁሉንም መሪ አንድ የሚያደርግ መርህ አለ እርሱም ራስ ወዳድነት ነው። እነዚህ አገራትም ለራሳቸው ጥቅምና ፍላጎት ቅድሚያ ሳይሰጡ ሌሎች አገራትን አግዘውና ረድተው አያውቁም። ከትናንት እስከዛሬ የእነዚህ አገራት እጅ እየተዘረጋ ያለው በልከክልህ እከክልኝ መርህ ነው። ኢኮኖሚያቸው ያደገውና የበለጸጉትም በዚህ ፖለቲካዊ አስተሳሰብ ላይ ተመስርቶ ነው። ጥልቅ በሆነ ራስ ወዳድነት ላይ።
ሸፍጥ ያነገበው የእነዚህ አንዳንድ ምዕራባውያን ኃያላን ነን ባይ አገራት ደግሞ ደባ በድሀ አገራት ላይ አዲስ ነገር አይደለም። የኖሩበትና ዛሬም እየኖሩበት ያለ ነገር ነው። አስገራሚው ነገር ግን ከአሸባሪ ቡድን ጋር አብረው ሰላም ለማምጣት መሞከራቸው ነው። ይሄ አካሄዳቸው ደግሞ በምን ዓይነት መንገድ ላይ ተራምደው እዚህ እንደደረሱ ከማሳየቱም በላይ ከእውነት ይልቅ ለእነሱ ፍላጎት ተገዢ ለሆነ አሸባሪ ቡድን ልባቸውን የከፈቱ እንደሆኑ ነው። እነዚህ ኃያላን ከትናንት እስከዛሬ በሌሎች አገራት የውስጥ ጉዳይ ላይ ጣልቃ በመግባት ራሳቸውንና ሕዝባቸውን ለመጥቀም ሲሠሩ ኖረዋል፤ እየሠሩም ናቸው። የኋላ ታሪካቸውን ያጠና ሰው ብዙ ልክ ያልሆኑ ነገሮች ላይ ይደርሳል። እነሱ ጣልቀ ገብተውበት ልክ የሆነ አገርና ሕዝብ የለም። በዓለም ታሪክ የፈረሱና መንግሥት አልባ ሆነው የቀሩ አገራት በእነዚሁ አገራት እንዳልነበሩ የሆኑ ናቸው። ለአብነት ብናይ እንኳን ዩጎዝላቢያ የፈራረሰችው፣ በአፍጋኒስታን ያ ሁሉ እልቂት የመጣው በዚችው አገር ጣልቃ ገብነት ነው። በሊቢያ የሆነው የመንግሥት ግልበጣ፣ በኢራቅና በሌሎች አገራትም የተከሰተው ጥቁር ጠባሳ በእነዚሁ አገራት ጣልቃ ገብነት የመጣ ነው።
የኃያላኑ ጣልቃ ገብነት ከመፈጠሩ በፊት እነዚህ አገራት ከፍ ባለ የለውጥና እድገት ጎዳና እና ሰላማዊ በሚባል አውድ ውስጥ ነበሩ። እርግጥ ማህበራዊና ፖለቲካዊ ቀውስ ሊኖር ይችላል፤ ነገር ግን ያን ያክል አስታራቂ የሚያሻውና የሌሎች አገራት ጣልቃ ገብነት የሚያስፈልገው ጉዳይ አልነበረም። ሆኖም አስታራቂ መስለው በገቡት እነዚህ አገራት ምክንያት ግን ታሪካቸውን አጡ። በዚህም አሁን ላይ ከእኚህ አገራት መካከል የፈረሱና ታሪክ የሌላቸው መስለው ያሉም ተፈጥረዋል፡ እንደ አገር ቢቆጠሩም ያኔ የነበራቸው አቅምና ልዕልና ዛሬ ላይ የለም። በእኛ አገርም እየሆነ ያለው እና እንዲሆን የሚፈለገውም ይሄ ነው። አስታራቂ መስሎ በመግባት አገር ማፍረስ። ባይሆንማ የቆሙት ለእውነትና ለፍትህ ቢሆን ከአንዴም ሦስት ጊዜ የሰላም አማራጮችን ገፍቶ ጦርነት በከፈተው አሸባሪ ኃይል ላይ ርምጃ ይወስዱ ነበር። ከአንዴም ብዙ ጊዜ መንግሥት ለሰብዓዊነት ሲል የወሰደውን የተናጠል የተኩስ አቁም ጥሶ በንጹሀን ላይ ለከፈተው እልቂት ተጠያቂ ያደርጉት ነበር። በሕፃናት ላይ፣ በሴቶች ላይ፣ በአዛውንቶች ላይ ላደረሰው ጥቃት፣ ለፈጸመው ግፍ፣ ላደረሰው የብሔር ተኮር ጭፍጨፋ ወንጀለኛነቱን በግልጽ ሊናገሩ በተገባ ነበር።
እነዚህ አገራት እውነት ቢኖረው ኖሮ አሸባሪው ትህነግን ለመወንጀል ብዙ አማራጮች ነበሯቸው። ዕድሜአቸው ያልደረሰ ሕፃናትን ለውትድርና በማሰለፉ፣ ለሰብዓዊነት ሥራ የተቀመጠን ነዳጅ በመዝረፉና በሌሎች ዓለም አቀፍ ወንጀሎቹ ተጠያቂ ሊያደርጉት ይችሉ ነበር። ግን የሌባ ልጅ ሌባ ሆነና እሽሩሩ ከማለትና አይቶ እንዳላየ ከማለፍ በስተቀር የወሰደው እርምጃ የለም። ከሀዲው የአሸባሪው ትህነግ ቡድን ስልጣን ላይ በነበረባቸው ሃያ ሰባት አመታት ውስጥ እንደ አሜሪካ የተጠቀመ አገርና ሕዝብ አልነበረም። ዛሬም እነዚህ አገራት የዚህን ቡድን ወደ ስልጣን መምጣት ይፈልጉታል። ጥቅማቸው ስለቀረባቸው ነው ዛሬ ላይ በማዕቀብና ርዳታ በመከልከል እያስፈራሩ ያሉት። የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት በተለይ የጸጥታው ምክር ቤትን ጨምሮ ይመለከተኛል የሚሉ አገራትና ተቋማት እጅግ ለበዛ ጊዜ በኢትዮጵያ ጉዳይ ላይ ስብሰባ መክረዋል። አላማቸው ግን ከእውነት ባፈነገጠ መልኩ አሸባሪውን ቡድን በመደገፍ ኢትዮጵያ ላይ ጫና ማሳደር ስለነበረ ጠብ የሚል መፍትሄ ላይ መድረስ አልቻሉም።
ሁሉም ጋ የየራሱ በምክንያት የተፈጠረ እውነት አለ። የኢትዮጵያ መንግሥት እውነትና እየተከተለው ያለው አቋም የሕዝብ ይሁንታ እንደሆነ ዓለም ያውቀዋል። አሸባሪው ትህነግ ማለት በሕዝብ የማይወደድ አረመኔ ቡድን እንደሆነ የትኛውም የውጭ ኃይል ኃያላኑን ጨምሮ ያውቁታል፤ ግን ትግላቸው ለዚህ አረመኔ ቡድን ነው። የሽብር ቡድኑን በተመለከተ የአሜሪካ ዝምታ ትርጉም ያለው እንደሆነ ለብዙዎቻችን ግልጽ ነው። አገርና ሕዝብን ጎድቶ ራስን የመጥቀም አላማ እንደሆነ የታወቀ ነው። ይሄን ማንነቱን እያወቁ ነው ዝምታውንም፣ ድጋፉንም፣ የሰላም አማራጩንም እንደየጊዜውና ቡድኑ እንዳለበት ነባራዊ ሁኔታ እያመቻመቹ ለመጓዝ የመረጡት፤ እና የኢትዮጵያውያን ስቃይና እንግልት ምናቸውም ያልሆነው። ከላይ እንዳልኳችሁ አሸባሪውን ትህነግ ለማስቆም በቂ ምክንያቶች ነበራቸው። በጣም ነው የሚገርመው ንጹሀን ሲገደሉ፣ ሕፃናትና ሴቶች ሲደፈሩ፣ ዕድሜአቸው ያልደረሰ ሕፃናት ለጦርነት ሲመለመሉ ዝም እያሉ የኢትዮጵያ መንግሥት በሚወስደው የመከላከል ርምጃ ላይ ግን ቅሬታቸውን ያሰማሉ። ይሄ ሸፍጥ ከመሆን ውጪ ምን ሊሆን ይችላል?
አሸባሪው ትህነግ እና እነዚህ አገራት ኢትዮጵያ ላይ ካላቸው ፍላጎት አንጻር ሚዛን ላይ ቢቀመጡ አንድ ዓይነት ናቸው። የሽብር ቡድኑ ተግባርና እንቅስቃሴ ከእነዚህ አገራት ፍላጎት የተቀዳ ነው፤ እነዚህ አገራት በኢትዮጵያ ላይ እያራመዱ ያለው ሁነት የአሸባሪው ትህነግ አላማን ነው። ለዚህም ነው የሁለቱም ፍላጎት አንድ ዓይነትና ከአንድ የምኞት ወንዝ ፈልቀው ወደ አንድ አቅጣጫና ግብ የሚፈስሱት የሚለውን ሃሳቤን እንድገልጽ ያደረገኝ። ሁለቱም በራስ ወዳድነት የተሰለቡ ናቸው። አሸባሪው ትህነግ በስልጣን ላይ በነበረበት ጊዜ የኢትዮጵያን ጥቅም ለባዕድ አገራት አሳልፎ ሲሰጥ ነበር፤ የዚህ ዕድል ተጠቃሚ ከሆኑት አገራት ውስጥ ደግሞ እነዚህ አንዳንድ የምዕራቡ ዓለም ኃያል ነን ባይ አገራት ተጠቃሽ ናቸው። በሽብር ቡድኑ የስልጣን ዘመን አገራቱ ከኢትዮጵያ የተጠቀሙትን ያክል እኛ ዜጎቿ አልተጠቀምንም። አሁንም ያ ጥቅማቸው እንዳይቀርባቸው ሲሉ ነው አንዴ በማዕቀብ፣ አንዴ በዛቻ መንግሥትን እያስፈራሩ ከሽብር ቡድኑ ጎን ሆነው የሚታዩት። እውነትና ፍትህ ከገባቸው ጥቂት አገራት በቀር አብዛኞቹ አጋሮቻቸውም እነሱኑ የሚከተሉ ናቸው። እንደ ተቋም ብናይ እንኳን ሁሉም ማለት በሚያስደፍር መልኩ የእነዚሁ አገራት ተቀጥላና ጅራቶች፣ አገራቱ የሚያስነጥሱትን በብዙ እጥፍ አስተጋብተው የሚያስነጥሱ ናቸው።
ከቡድኑ እኩይና አረመኔያዊ ተግባር አንጻር የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት፣ የአውሮፓ ኅብረትና ሌሎች ተቋማት አሸባሪውን ትህነግ በዓለም አቀፉ ፍርድ ቤት በወንጀለኝነት የማቆም ስልጣን እያላቸው ቢሆንም፤ ያን ግን አላደረጉም። እንደዚያም ሆኖ ኢትዮጵያዊነትን ያሸነፈው የለም። ኃያል ነን ባዮቹ እውነትን ይዞ የቆመውን የኢትዮጵያን ሕዝብ እንዳሰቡት መነጣጠልና ፍላጎታቸውን ለማስፈጸም ተስኗቸዋል። በመሆኑም እኛ ኢትዮጵያውያን ለጠሉን እጅ ሳንሰጥ፣ መውደቃችንን ለሚጠባበቁ መንገድ ሳንከፍት በጀመርንው የአንድነት መንገድ ነውረኞችን ታግለን ማሸነፍ ይጠበቅብናል። የሰው ልጅ ከፍትህ ይልቅ ክህደትን፣ ከእውነት ይልቅ ሀሰትን፣ ከቁም ነገር ይልቅ ቧልትን የመረጠበት ጊዜ ላይ ነን። በዚህ ሁለት አመት ውስጥ አሸባሪው ትህነግ በንጹሃን ላይ ያደረሰው ግፍና በደል አፍ አውጥቶ የሚናገር ቢሆን ኖሮ ዓለም ጉድ ትል ነበር። ግን ዓለምን ጨብጠናታል ብለው የሚታበዩት ነውረኞች ከነውረኞች ጋር አብረው የድሆች ድምጽ እንዳይሰማ እያደረጉ ነው። ሆኖም ግፍ እየበዛ ሄዷልና ኃያላኖች የሚዋረዱበት ጊዜ ይመጣል፤ አሸባሪዎች ተንቀው ቅኖች ከፍ የሚሉበት ቀን ከፊታችን አለ። ያ ቀን የእኛ ቀን ነው..
በርባን ይፈታ..በርባን ንጹህ ነው የሚል የኃያላኖች ድምጽ እየተሰማ ነው። ዛሬ ላይ አሸባሪው ትህነግ በርባንን ነው። በአንድ ነፍስ ሳይሆን፣ በአንድ ሺ ነፍስ ሳይሆን፣ በሚሊዮን ነፍስ ይጠየቃል። እኛ ኢትዮጵያውያን የራሳችን የሆነ የክብር ድንበር ያለን ኩሩ ሕዝቦች ነን። ዓለምን ጥበብ አስተምረናል። ማንም ከመሬት ተነስቶ አውቅልሀለው የሚለን ሕዝቦች አይደለንም። በፍቅር እንጂ በጠብ ለመጣብን ቁጡ ነን። ኃያላኖቹ ይሄን ቢረዱ እንዴት መልካም ነው። ግን ያውቁታል..ኢትዮጵያዊነት ምን እንደሆነ ያውቁታል። ለዚያም አይደል ባለ በሌለ ኃይላቸው የተነሱብን? ለዚያም አይደል..በታሪክ፣ በስልጣኔ የበለጠችን አንድ አገር አለች ከአሸባሪ ጋር አብረን እናዳክማት ሲሉ የተነሱት? ግን አይችሉንም፤ ድሮም አልቻሉንም..አሁንም አይችሉንም።
ሺህ ነፍስ የበላውን በርባንን ፈተው ከነፍስ በላ ጋር አሸሼ ገዳዎ ለማለት የሚቋምጡ ብዙ አገራት በመንግሥት ላይ ተጽዕኖ እያደረጉ ቢገኙም እኛ ግን ህልውናችንን ለነፍሰ በሎች አሳልፈን አንሰጥምና በአንድነት በመቆም አሸባሪውን ትህነግና አሸርጋጆቹን ስለ ክብርና ሉዓላዊነታችን ስንል ከመከላከል ሥራችን ወደ ኋላ አንልም። የአገራችን ጉዳይ የእኛ ጉዳይ ነው፤ የታሪካዊ ጠላቶቻችና የአንዳንድ ምዕራባውያን ወይም የተባበሩት መንግሥታትና ሌሎች መሰል የዘመናዊ ቅኝ ግዛትነት እሳቤን አራማጅ ተቋማት ጉዳይ አይደለም። ሆኖም እነዚህ አገራትና ተቋሞቻቸው በአንድ ነገር ይረታሉ፤ በሕዝቦች የጋራ ድምጽ፣ በሕዝቦች በጋራ መቆም። ሕዝብ በጋራ ድምጹን ካሰማ፣ በጋራ ከቆመ ኃያላኖቹ አቅም አይኖራቸውም። እስከዛሬ ጣልቃ በመግባት ያፈራረሷቸው አገራት ሕዝብ በጋራ ያልቆመባቸው ስለሆኑ ነው። አገራችንን ከአሸባሪው ትህነግ ወዳጆች ልንጠብቃት የምንችለው..በአንድነት ብቻ ነው።
በትረ ሙሴ (መልከ ኢትዮጵ)
አዲስ ዘመን ጥቅምት 7 ቀን 2015 ዓ.ም