የአሸባሪውን ትሕነግ ታሪክ ከስር መሠረቱ በቅጡ የሚያውቁትና የሚረዱት ገብረመድህን አርዓያ የተባሉት ፀሐፊ እንደከተቡት፤ “ሕወሓት ከጥንስሱ ጀምሮ እንደተልዕኮ እና መመሪያው ለዘመናት ከብዙ የውጭ ወረራዎች እና ያልተሳኩ የቅኝ ግዛት ጥረቶች በአባቶቻችን ጽኑ ተጋድሎ የቆየውን ኢትዮጵያዊነት ለማፍረስ፤ ሕዝብን በዓለም ታይቶ በማይታወቅ የቋንቋ እና የዘር ልዩነት ከፋፍሎ ለብቻው የትግራይን ሪፐብሊክ ለማቋቋም፤ ትግራይን ከአማራ ቅኝ ገዢዎች ነጻ ማውጣት፤ ኢትዮጵያ የምትባል በአጼ ምኒሊክ የተፈጠረችን ሀገር ከዓለም ካርታ ላይ ማጥፋት፤…” የሚሉ እና ሌሎች ዝርዝር ግቦችን እና ዓላማዎችን አንግቦ የተነሳ ድርጅት እንደነበርና ከኢትዮጵያዊነት የተጣላ ስለመሆኑ ይገልፁታል።
እኚህ ፀሐፊ አሸባሪው ትሕነግን የገለፁበትን መንገድ እኔም ሙሉ በሙሉ እስማማለሁ። ለምን ከተባለም፣ ላለፉት 30 ዓመታት በኢትዮጵያ ምድር የተከናወነውን ማስታወስ ብቻ በቂ ነው። ይህም ብቻ አይደለም አሸባሪው ትሕነግ የሰሜን ዕዝን ሲወጋ ዓላማው ምን እንደሆነ ሙሉ ለሙሉ ፍንትው አድርጎ አስረድቶናል። በዚህ እኩይ ተግባሩም ባለፉት ሁለት ዓመታት ኢትዮጵያ ወደ ጦርነት እንድትገባ ቢያደርጋትም፤ በልጆቿ ብርቱ ክንድ ጠላቶቿ አሳፍራለች። በምዕራባውያን ቡራኬ የሚዘወረው አሸባሪው ትሕነግም የመጨረሻው መፍጨርጨር ላይ ይገኛል። ጫና በመፍጠር የኢትዮጵያን መንግሥትና ሕዝብ ማንበርከክ እንደማይችሉ የገባቸው እኚሁ አንዳንድ የምዕራቡ አገራት ደግሞ ሰላማዊ ድርድር እያሉ መወትወት ከጀመሩ ሰነባብተዋል።
ቀድሞውንም ለሰላም ደጁ ክፍት የነበረው የኢትዮጵያ መንግሥትም ምንም እንኳን የሽብር ቡድኑ ተግባር የከፋ ቢሆንም የሰላም ንግግሩን በጀ! ብሎ ያለ ቅድመ ሁኔታ ለማካሄድ ተቀበለ። ይሁንና ግን አሸባሪው ትሕነግ እርቅና ሰላምን ፈጽሞ የሚፈራቸው በመሆኑ በሰላማዊ መንገድ ወደ ድርድር የማይመጣባቸው ምክንያቶች በመደርደር ወደ ሰላማዊ መድረክ ላለመምጣት እየታገለ ይገኛል። ወደ ሰላማዊ ንግግር ከማይመጣባቸው በርካታ ምክንያቶች መካከል ጥቂቶችን ለማንሳት ያህል፡-
አንደኛው፣ የማይጨበጥ ተስፋው ነው። አሸባሪው ትሕነግ በዚህ የክህደትና የእጅ አዙር ጦርነት ተስፋ ካደረጋቸው ነገሮች አንዱ ተመልሶ ስልጣን መቆናጠጥ ቢሆንም፤ ፈፅሞ እንደማይሳካ ተረድቶታል። ሆኖም ለዚህ ቀቢጸ ተስፋው መሳካት ሲል በሚሊዮን የሚቆጠሩ የትግራይ ወጣቶችን ሕይወት ቀጥፎና ለአካል ጉዳይ የዳረገ ዳርጓል፤ በሚሊዮን የሚቆጠሩ የትግራይ ነዋሪዎችን በረ ሃብ አለንጋ እንዲገረፉና ለዓመታት ከመላው የኢትዮጵያ ወንድሞቻቸውና ጎረቤት አገራት ወዳጆች ጋር እንዳይገናኙ እንደ መያዣ አድርጎ በተስፋ መቁረጥ ስሜት ውስጥ አስገብቷቸዋል።
ታዲያ ሰላም ከሰፈነና ነገሮች ከተረጋጉ የትግራይ ህዝብ ከጦርነቱ ምን አተረፍን ሲል በጥያቄ ያጣድፋቸዋል፤ ሥራ አጥ ወጣት ከጉሮሯቸው ላይ ይቆማል፤ ልጆቻቸውን በየጦር ሜዳው የገበሩ ወላጆች ልጆቻችን ከምን ደረሱ ይሏቸዋል። ታዲያ አሸባሪው ትሕነግ ለዚህ ሁሉ ጥያቄ ምላሽ ስለማይኖረው፤ ሰላም ከሰፈነ ይሄ ግፉ ተጠያቂነትን ያመጣበታልና ሰላምን ፈጽሞ ይፈራታል። ለዚህም ፈጽሞ ችግሩ በድርድርና በሰላማዊ መንገድ እንዲጠናቀቅ አይፈልገውም።
ሁለተኛው፣ የውጪ ኃይሎች ግፊት ስላለበት ነው። አሸባሪው ትሕነግ ይህ ጦርነት ሲጀምር ታሪካዊ የኢትዮጵያ ጠላቶች እና አንዳንድ ምዕራባውያን አገሮች ከበስተጀርባው ቀጥተኛ ድጋፍ እንደሚያደርጉለት ቃል የተገባለት፤ በሎጀስቲክስና ቴክኖሎጂ ጭምር ሲደግፉትና የእነዚሁ ኃይሎችም በቀጥታ ጦርነት ጭምር ተሳትፈው የተገኙበት ነበር። በመሆኑን ይሄ የውጪ ኃይሎች ተስፋና ግፊት ቡድኑ ራሱን እንደ አሸናፊ ኃይል እንዲቆጥር እና በእነዚህ ኃይሎች ላይ በመተማመን የእነሱኑ ተልዕኮ ለመፈጸም ሲል ስለ ሰላም ሳይሆን ስለ ጦርነት ብቻ እንዲያስብ ሆኖ በመቀረጹ ነው።
ሦስተኛው፣ ቀደም ሲል በሀገርና ሕዝብ ላይ የፈጸመው ክህደትና ዘረፋ የፈጠረበት ስጋት ነው። አሸባሪው ትሕነግ ከኢትዮጵያና ኢትዮጵያውያን ጉሮሮ የትዬለሌ ንብረት ዘርፎ በውጭ አከማችቷል፤ ሀገርንም ለማፍረስ ጦር መዝዞ ወግቷል። የታሪክ ገጾቹ እንደሚያስረዱትም፤ አሸባሪው የትሕነግ ቡድን ከ1985 ዓ.ም ጀምሮ የተቋቋሙት መሰቦ ሲሚንቶ፣ አልመዳ ጨርቃጨርቅ፣ መስፍን ኢንጂነሪንግ፣ ሱር ኮንስትራክሽን፣ አዲስ መድኃኒት ፋብሪካ፣ ኢዛና ማይኒንግ፣ ትራንስ ኢትዮጵያ፣ አፍሪካ ኢንሹራንስ፣ ሕወሓት የሚዘውራቸው ባንኮች፣ የማዕድን ንግድና፣ ኮንትሮባንድ፣ ሕገወጥ የሰዎች ዝውውር፣ የጦር መሣሪያ ንግድና የዲፕሎማሲ ውንብድና የቡድኑ ዋነኛ የገቡ ምንጮች ነበሩ። ዛሬ ግን እነዚህ ከእጁ የወጡ መስሎ ስለተሰማው እነዚህን ከሕዝብ ጉሮሮ ነጥቆ ያከማቻቸውን ሃብቶች መልሶ የራሱ ለማድረግ በብርቱ ተመኝቷልና ሰላማዊ መንገድ ለዚህ አያበቃኝም ብሎ ስላመነ ወደሰላም ፊቱን ማዞር አይሻም።
አራተኛው፣ የኢትዮጵያን ጥቅም ለውጭ ኃይሎች አሳልፎ የመስጠት የተላላኪነት ሰብዕናው ነው። አሸባሪው ትሕነግ ላለፉት 30 ዓመታት ምዕራባውያን ቁራሽ ያገኝና ይመፀወት የነበረው የተለየ ነገር ስላደረገ አይደለም። ይልቁንም የኢትዮጵያን ጥቅም አሳልፎ በመስጠትና ሉዓላዊነትን ለከፋ አደጋ በማጋለጡ አበጀህ! ተብሎ ነው። ታዲያ ይህን ቡድን ምዕራባውያን ደጋግመው ያሞካሹት የነበረና ጥሩ ተላላኪ ስለመሆኑ በምፀት እየሳቁ ይሰመክሩለት ነበር። ታዲያ በዚህ ስሜት የሰከረው ቡድኑ ከምዕራባውያን ጋር የተስተካከለ እየመለሰው ነገር። ዛሬም የኢትዮጵያ አፍራሽና ጠላት መሆኑን እያወቀውም ቢሆን ያሞካሹት ኃይሎች መልሰው ከሞት የሚታደጉት አድርጎ እያሰበ መሆኑ ነው። በዚህም የተነሳ ድርድሩን በሰላማዊ መንገድ ከመፍታት ይልቅ ራሱን እንደቻለ ሉዓላዊ አገር በምዕራባውያን ሥም እየማለ በመመጻደቅ ጭምር የሰላም ድርድሩን አይፈልግም።
አምስተኛው፣ አገር ካጅነቱ፣ የመከላከያ ሠራዊት ላይ በውድቅት ሌሊት ከጀርባው የፈጸመው ጥቃት እረፍት ስለማይሰጠው ነው። አሸባሪው ትሕነግ ለእኩይ ዓላማው መሳካት ሲል በሰሜን ዕዝ የመከላከያ ሠራዊት ላይ የተፈጸመው ድንገተኛና አሰቃቂ የወንጀል ተግባር ታሪክ ይቅር የማይለው ነው። ወንጀሉ በገለልተኛ ቡድን ይጣራ ቢባል በዓለም አቀፍ የጦር ፍርድ ቤት የሚያስጠይቅ ነው። ይሄን እውነት ባሰበ ቁጥር ደግሞ የሰላም አማራጭ ሕልውናውን በአጭር የሚያስቀርበት ስለሚመስለው የተራዘመ ጦርነትን እንጂ ሰላምን አይፈልገውም።
ስድስተኛው፣ ራሱን ከጦር መሳሪያ አጀብ ውጪ የሚያኖር ስለማይመስለው ነው። አሸባሪው ትሕነግ ከውልደቱ እስከ ሽበቱ ከጦር መሣሪያ አጀብና ጥፋት ውጪ ራሱን አቁሞ አያውቅም። አሁንም በሽብር ጉዞው ውስጥ ከውስጥም በዘረፋ፣ ከውጪም በድጎማ ያገኛቸው በርካታ የጦር መሣሪያዎች እንዳሉት እሙን ነው። በመሆኑም ከጦርነት ይልቅ የሰላም መንገድን ከመረጠ እነዚህን የሕልውናዬ ማስጠበቂያ ብሎ የሚመካባቸውን ትጥቆች ከጥፋት ኃይሎቹ እጅ ይወጣል ብሎ ይሰጋል። ርግጥ ነው በአንድ አገር ሁለት የታጠቀ ኃይል ሊኖር አይገባም፤ ያውም ለሽብር ተግባር የታጠቀ ኃይል። ስለዚህ አሸባሪው ትሕነግ የጥፋት ኃይሎቹ ትጥቅ ከሚፈቱ የትግራይን ወጣት እያሸከመ ወደ እሳት እየማገደ መኖርን ይመርጣል።
እነዚህ እና ሌሎች በርካታ ምክንያቶችን ለሰላም ጠልነቱ መዘርዘር የሚቻልለት አሸባሪው ትሕነግ፤ ከፈጣሪ በላይ ደደቢት በረሃ እና ክላንሽኮቭ የሚያመልክ ቡድን ነው። ታዲያ ይህ ቡድን ሠላም እንደምን ሊሸተው ይችላል። በሠላማዊ መንገድ ከኢትዮጵያ ሕዝብ ጋር ከመኖር ሞቶም ቢሆን ቢዋጋ ይቀለዋል። ዳሩ ግን አሁን የትግራይ ወጣት በየዐውደ ውጊያው የጥይት ማብረጃ መሆን እየመረረው እጁን ከሀገር መከላከያ ሠራዊትና ለጥምር ጦር እየሰጠ ነው። ይሄም ሆኖ ግን አሸባሪው ትሕነግ እያደረገው ካለው እንቅስቃሴ ሰላማዊ አማራጭና እውነተኛ እርቅ የማይፈልግ ቡድን ስለመሆኑ ለመረዳት ይቻላል።
ዶክተር ጀኔኑስ
አዲስ ዘመን ጥቅምት 7 ቀን 2015 ዓ.ም