በትህነግ የሽብር ቡድን ታጣቂዎች ተገደው የተደፈሩ እናቶች፣ በደባርቅና አካባቢው ለተገኘ የኢትዮጵያ ፕሬስ ድርጅት ጋዜጠኛ “ዓላማችን አማራን ማዋረድና ማጥፋት ነው እያሉ ልጆቻችን ፊት ደፈሩን፤” ሲሉ ቅስማቸው ተሰብሮ ነገሩን። አዲስ ዘመን ጋዜጣ ባስነበበው በዚህ ዘገባ፣ የሽብር ቡድኑ ትህነግ ታጣቂዎች በወረራ ይዘው በቆዩባቸው የአማራ እና አፋር አካባቢዎች ህጻናትንና መነኮሳትን አስገድዶ መድፈር ወንጀል መፈጸማቸውን መለስ ብሎ ያስታውሰናል ። በዚህም በርካታ ህጻናት እና እናቶች ከአካላዊ እና ስነልቦናዊ ጉዳት ባለፈ ራሳቸውን እስከማጥፋት ደርሰዋል በማለት ያረዳናል። ሕመማቸውን እንድንታመም ያደርጋል። እኔም በማላውቀው ምክንያት ይህ ዘገባው ውስጤን ዘልቆ ተሰምቶኛል። በዝብዞኛል። አንገብግቦኛል ።
ጋዜጠኛው በስፍራው ተገኝቶ በጋዜጣው ዘገባ ላይ ያጋራንን ለመስማት የሚሰቀጥጥ ግፍ ስንመለከት፣ በእርግጥ በዚህ አረመኔያዊ ድርጊት ማፈር ፣ አንገት መድፋት ከፍ ሲልም መሸማቀቅ ያለበት እነዚህን አረመኔዎች ጥላቻን ፣ ጭካኔንና ነፍጥ አስታጥቆ የላካቸው ሽብርተኛው ትህነግ ፣ ማህበራዊ መሠረቱ የሆነው ደጋፊው ትግራዋይ ፤ ተገደውም ሆነ ፈቅደው ለሽብርተኛው ፕሮፓጋንዳ አስገድዶ ማጥመቅ (ኢንዶክትሬሽን) መሳሪያ የሆኑ ፤ የትግራይ ትምህርት ተቋማት ፣ የትግራይ ሃይማኖት ተቋማት ፣ የትግራይ ልሒቃን ፣ የሽብርተኛው ደጋፊ ዲያስፓራ ነው ወይስ የዚህ ግፈኛ አሸባሪ ሰለባ የሆነው ደጉና ባለ ፈሪኣ ፈጣሪው የአማራ ሕዝብ !? የሚል ጥያቄን ያስነሳል፡፡ ከፍ ብዬ ካነሳኋቸው ጥያቄዎቼ አንዳንዶች የፖለቲካዊ ትክክለኝነት/political correctness/ ሊያስነሱ እንደሚችሉ ብረዳም ለዚህ ሲባል እውነት ልትኮሰምንና ልትመቻመች ስለማይገባ እንደወረዱ ማቅረብን መርጫለሁ ።
በጋዜጣው ወደተገለጸውና አጥንት ዘልቆ ወደሚሰማ ዘገባ ስንመለስ ፤ ዘገባውን እንዲህ የሚል ነበር፡፡ “… በደባርቅ የገጠር አካባቢዎች ሽብር ቡድኑ የትህነግ ታጣቂዎች የአስገድዶ መደፈር ከተፈጸመባቸው ሴቶች መካከል ለዘገባው ሲባል ስማቸውን የተቀየሩት ወይዘሮ ታሪኳ ይነገር አንደኛዋ ናቸው ። ወይዘሮ ታሪኳ የ50 ዓመት አዛውንት ሲሆኑ፤ የሰባት ልጆች እናት ናቸው። የወይዘሮ የታሪኳ የመጨረሻው ልጃቸው ዕድሜ ሶስት ዓመት ሲሆን፤ የመጀመሪያዎቹ ሁለት ተከታታይ ልጆቻቸው እድሜ ደግሞ ጎጆ ለመቀለስ የደረሰ መሆኑን ይናገራሉ።
እንደ ወይዘሮ ታሪኳ ገለጻ፤ ሁሌም ከእንቅልፋቸው ሲነቁ የመጀመሪያ ተግባራቸው ቤተክርስቲያን በመሄድ ጸሎት ማድረስ ነውና ነሃሴ 12 ቀን 2013 ዓ.ም እንደተለመደው ጸሎት ለማድረስ በጠዋት ተነስተው ወደ ቤተክርስቲያን ያመራሉ። ቤተክርስቲያን ጸሎት ላይ እያሉ የሚኖሩበት ቀበሌ በሽብር ቡድኑ መያዙን ይሰማሉ። ጸሎታቸውን አድርሰው እንደጨረሱ ወዲያውኑ ወደቤታቸው ይመለሳሉ። ከሽብር ቡድኑ ጥቃት ራሳቸውን እና ቤተሰባቸውን ለመከላከል በማሰብ ከሰባት ልጆቻቸው ጋር ቤታቸውን ዘግተው ይቀመጣሉ።
የፈሩት ይደርሳል የጠሉት ይወርሳል የሚሉት ወይዘሮ ታሪኳ፤ እንደጦር የፈሯቸው የሽብር ቡድኑ ትህነግ ታጣቂዎች ወደ ቤታቸው በመምጣት የቤታቸውን በር አንኳኩ። ነገር ግን እነወይዘሮ ታሪኳ በሩን አልከፍት ስላሉ ይህን ተከትሎ የሽብር ቡድኑ ታጣቂዎች በሩን በሃይል ገንጥለው ወደ ውስጥ ዘለቁ ።
በወይዘሮ ታሪኳ ቤት የሚገኝን እህልና ውሃ የሚችሉትን ያህል ከበሉ በኋላ ሲጠግቡ አማራ የሚበላው ማግኘት የለበትም በማለት የተረፋቸውን በቤቱ የሚገኝን አህል በሙሉ አወደሙ። ይህም አልበቃ ብሏቸው ቢላዋ ወደ ወይዘሮ ታሪኳ በማቅረብ አስፈራርተው ለመድፈር ሞከሩ። ወይዘሮ ታሪኳ ለቢላዋው እጅ የሚሰጡ አልሆኑም። በመጨረሻም የሽብር ቡድኑ አባላቱ ጉልበት በመጠቀም ለመናገር በሚዘገንን አኳኋን ወይዘሮ ታሪኳን እየተፈራረቁ ከልጆቻቸው ፊት ደፈሯቸው። ይህንንም ሲያደርጉ ‘ሁሉንም አማራ እንዲህ ነው የምናደርገው፤’እያሉና እየዛቱ ነበር ።
የወይዘሮ ታሪኳ የመጀመሪያ ሁለት ተከታታይ ወንድ ልጆችም የእናታቸውን መደፈር ሲያዩ የት እንደሄዱ ሳይታወቅ ከቤታቸው ብን ብለው እንደጠፉና እስካሁንም የት እንደሚገኙ እንደማያውቁ ወይዘሮ ታሪኳ ይናገራሉ። የቀሩት ልጆችም እናታቸው ላይ የተፈጸመውን ወንጀል ለመናገር ወደ አያታቸው እና አጎቶቻቸው ወደሚገኙበት ሰፈር አመሩ። የልጆች አያት እና አጎቶችም ከአምስት ሰዓት በኋላ ወይዘሮ ታሪኳ ቤት ደረሱ። ነገር ግን ወይዘሮ ታሪኳ ከቤታቸው ወለል ራሳቸውን ስተው ወድቀው ነበር።
ዘግይተው የደረሱት የወይዘሮ ታሪኳ የቅርብ ቤተሰቦች እጅጉን ተደናግጠው እና ያዩትን ማመን አቅቷቸው ተጠቂዋ ህክምና እንድታገኝ ለማድረግ የባህላዊ አልጋ (ቃሬዛ) ሰርተው ወደ ሃኪም ቤት ለመውሰድ ተነሱ። ይሁን እንጂ የሽብር ቡድኑ የትህነግ ታጣቂዎች በሰሩት ስራ ከማፈር እና ከመሸማቀቅ ይልቅ የአማራ እናት እዚሁ ነው መሞት ያለባት በማለት ወደ ሃኪም ቤት ሄደው ህክምና እንዳያገኙ ከለከሉ።
የወይዘሮ ታሪኳ ቤተሰቦች ሽብር ቡድኑን እግር ጠብቀው ወደ ዋሻ ወስደው ደበቋቸው። ከአራት ቀን ቆይታ በኋላም የሽብር ቡድኑ የሌሉበትን ቦታ በመምረጥ ለሃኪም ቤት አበቋቸው ። በተፈጸመባቸው ጥቃት አሁን ላይ ዓይነ ምድራቸውን እና ሽንታቸውን መቆጣጠር እንደማይችሉ የተናገሩት ወይዘሮ ታሪኳ፤ ካጋጠማቸው አካላዊ ጉዳት በላይ የደረሰባቸው የስነ ልቦና ጉዳት እጅጉን ከፍተኛ እና መሪር መሆኑን ይናገራሉ። በመሆኑም ተወልደው ከአደጉበት እና ባል አግብተው ሰባት ልጆች ካፈሩበት ቀዬ እና ልጆቻቸው ተደብቀው ለመኖር መምረጣቸውን ይናገራሉ ።
አሁን ላይ የልጆቻቸው ናፍቆት አላስችል እንዳላቸው የሚናገሩት ወይዘሮ ታሪኳ፤ ከሁሉም በላይ ግን የመጨረሻው የሶስት አመት ልጃቸውን ሁኔታ ሲያስቡት ከሆዳቸው ውስጥ የሆነ አካል ገብቶ አንጀታቸውን የሚስበው ያህል ህመም እንደሚሰማቸው ይናገራሉ። ቢሆንም ግን በደረሰባቸው የስነ ልቦና ጉዳት አሁንም ወደቀያቸው እና ቤተሰቦቻቸው መመለስ እንደማይፈልጉ ይገልጻሉ ።…”
ታዲያ አንገት መድፋት ከፍ ሲልም መሸማቀቅ ያለበት እነዚህን አረመኔዎች ጥላቻን ፣ ጭካኔንና ነፍጥ አስታጥቆ የላካቸው ሽብርተኛው ትህነግ ፣ ማህበራዊ መሠረቱና የቡድኑ ደጋፊ የሆነው ትግራዋይ ፣ የትግራይ ትምህርት ተቋማት ፣ የትግራይ ሃይማኖት ተቋማት ፣ የትግራይ ልሒቃን ፣ የሽብርተኛው ደጋፊ ዲያስፓራ ነው ወይስ የዚህ ግፍ ሰለባ የሆነው የአማራ ሕዝብ …!? መልሱን አሁንም እናቆየውና ከአንድ አመት በፊት ሽብርተኛው ትህነግ ለ2ኛ ጊዜ ጦርነት ከፍቶ የአማራንና የአፋርን ክልሎች ወሮ ከቆየ በኋላ በጥምር ኃይሉ ተገርፎ ሲወጣ ፤ ነጻ የወጡ አካባቢዎችን ከተለያዩ ሚዲያዎች የተውጣጡ አመራሮች ከጎበኙ በኋላ የታዘቡትን ለሕዝብ ይፋ ባደረጉበት ወቅት ሙሓዘ ጥበባት ዲያቆን ዳንኤል ክብረት በወቅቱ ሽብርተኛውን ትህነግ እንዲህ ገልጾት ነበር ።
የአሸባሪው ትህነግ የጭካኔና የአረመኔነት ጥግ ላለፉት 30 አመታት ሆነ ዛሬ እልፍ አእላፍ ጊዜ የተጻፈ ዘጋቢ ፊልም የተሰራለት ህልቆ መሳፍርት በሌላቸው የጥቃቱ ሰለባዎቹ የተነገረ ቢሆንም ባልተለመደ ሁኔታ ተዛብቶ ተጠቅሶ አሜሪካንን ሳይቀር መግለጫ እንድታወጣ እንዳስገደደው የሙሓዘ ጥበባት ዲያቆን ዳንኤል ክብረት የሕወሓትንና የደጋፊዎቻቸውን አጥንት ፣ መገጣጠሚያንና መቅኔን ሰርስሮ እንዲገባ አድርጎ የገለጸው የለም ቢባል ማጋነን አይሆንም። በአሸባሪው ትህነግ የጡት አባቶች ዘንድ ባልተለመደ ሁኔታ አቧራ ያስነሳውም የዲያቆን ዳንኤል ንግግር ዘልቆ ነርቫቸውን ስለነካው እንጂ በናዚና በጀርመን በፋሽስትና በጣሊያን ሕዝብ መካከል ልዩነት እንዳለ ሁሉ በአሸባሪው ትህነግና በትግራዋይ መካከል ልዩነት መኖሩ ጠፍቷቸው አይደለም ። ለማንኛውም ሙሓዘ ጥበባት እንዲህ ነበር የታዘበውን የገለጸው፤
“ሕወሓት መልካም የሆኑ ነገሮችን ሁሉ ለማጥፋት የተነሳ ኃይል ነው። ኢትዮጵያን ለማጥፋት የተነሳውም ከመልካም ነገሮች አንዷ ስለሆነች ነው። ቢሆንለት በአለም ላይ ያለን መልካም ነገር ሁሉ ከማጥፋት አይመለስም። ለሰው ልጅ ህልውና አስፈላጊ የሆኑ ነገሮችን ሁሉ ነው የሚያጠፋው። እስካሁን አሸባሪ ሰውን ብቻ ነው የሚረሽነው። ሕወሓት ግን ሰውን እንስሳትንና እፅዋትን እረሽኗል። ይህ በሌሎች ሀገራት የአሸባሪዎች ታሪክ ያልተፈጸመና ያልታየ ነው። ጭና መቄት እፅዋትን ከብቶችን ዶሮዎች ሳይቀሩ ረሽኗል። ቢሆንለት ኢትዮጵያን ምስራቅ አፍሪካን አለምን ከማጥፋት አይመለስም። አለም ያልተረዳው አንዱ ነገር ይህን ነው። ይህ ሀይል ተራ ተቃዋሚ ቡድን አይደለም።መልካም የሆኑ ነገሮችን ሁሉ ለማጥፋት የተነሳ እንጂ። ነሐሴ 13 ፣ 2014 ዓ.ም የደብረታቦር ዕለት የተኮሰው መድፍ አላማ እኮ ለበዓሉ የተሰበሰቡ ሰዎችን መፍጀት ነው። በዚህ በዓል ከምዕመኑ ከካህናቱ ከዲያቆናት መካከል እኮ የትግራይ ተወላጆች አሉ። ለእሱ ሁሉም ቢያልቁ ጉዳዩ አይደለም። ጭና ላይ ሲደመሰስ ከኋላ የነበረው አዋጊ እያዋጋቸው የነበሩትን ሳይነግር ነው ጥሎ የሸሸው። ሰው ቢያልቅ ቢኖር ባይኖር ምንም አይመስለውም። መንገድ ላይ ያየነው ያ ሁሉ የወጣት ሬሳ አያሳዝነውም። ምነው የትግራይ እናቶች፣ የትግራይ አባቶች ማየት በቻሉ። ልጆቻቸውን ምን እያደረጋቸው እንዳለ። አይራራላቸውም እኮ። ለእነዚያ ወጣቶች የማይራራ ህሊናን እንዴት አድርገን ነው የምንረዳው። በጤናማ አእምሮ እሱን ለመረዳት መሞከር በጣም አስቸጋሪ ነው።
በጉዟችን ስድስት ተቋማትን ሲያጠፋ ተመልክተናል። አንደኛ የመንግስት ተቋማትን አውድሟል።እንግዲህ አገር ልመራ ነው ያለ ሀይል እኮ መንግስታዊ ተቋማትን አያጠፋም። አላማው ስልጣን ቢሆን ኑሮ እነዚህ ተቋማት ያስፈልጉት ነበር።አላማው እሱ አይደለም። ሁለተኛ የሀይማኖት ተቋማትን ያጠፋል። ወሎ አፋር መስጊዶችን መዳርሳዎችን አፍርሷል። አብያተ ክርስቲያናትን ያፈርሳል። ካህናትን ከቅዳሴ ሲወጡ ገድሏል። የስልጣን ትግል ውጊያ አይደለም እያደረገ ያለው። አለማው ጥፋት ነው።ሶስተኛ ግላዊ ተቋማትን አፍርሷል። ዳባት ላይ የገበሬውን ደሳሳ ጎጆዎች ሳይቀር በከባድ መሳሪያ አፍርሷል። ቤታቸው ገብቶ ጋን ምጣድ ድስት ይሰብራል። ከዚህ ምንድን ነው የሚያገኘው። በየደረሰበት የግል የተባለውን ነገር ሁሉ አውድሟል ዘርፏል። ይህ ቡድን እርዮተ አለሙ ምንድን ነው። አራተኛው ይህ ቡድን ማህበራዊ ተቋማትን አውድሟል። ትምህርት ቤቶችን ሆስፒታሎችን ጤና ኬላዎችን የእንስሳት ክሊኒኮችን አውድሟል። እድሮችን አፍርሷል። ዘርፏል። አምስተኛ ቤተሰባዊ ተቋማትን ያፈርሳል። ስድስተኛ ስነ ልቦናዊ ተቋማትን ያፈርሳል።
ቤቱን በልተው ጠጥተውበት አስበስለውበት መጨረሻ ላይ ያበሏቸውን ገደሉበት። የሞቱ ጓደኞቻቸውን አምጥተው ቀበሩበት። በኢትዮጵያዊ ሞራል ይሄን እንዴት እንረዳው። እዚያ አካባቢ የሚወለዱ ወጣቶች እንዴት አድርገው ይረዱታል። የገዛ አዋጊዎቻቸውን አንገት ቆርጠዋል እኮ። ጭካኔዋን እንዴት ነው የቻሉበት። ይሄ ቡድን ይሄን የክፋት አቅም ከየት አገኘው። ምንጩ ከየት ነው። ከዚህ በኋላ ስነ ምግባር የሚባለውን ነገር እንዴት ነው ማስተማር የሚችለው። እንዴት ነው ህጻናትን በመድፈር ሽማግሌዎችን በመግደል አላማ ሚሳካው ። ሆስፒታል ከተኙ ሰዎች ጉሉኮስ ነቅሎ ወስዷል። የአካል ጉዳተኞችን ሰው ሰራሽ እግር ነቅሎ ወስዷል። በምን የቅስም/የሞራል/ልዕልና ነው መተንተን የሚቻለው። ይሄ ለሰው ልጅ የኑሮ መስተጋብር በጣም አስቸጋሪ ነው። ይሄ ቡድን መጥፋት ያለበት ለሁሉም የሰው ልጆች ሲባል ነው። ለትግራይ ሕዝብ ሲባል ሕወሓት መጥፋት አለበት። ለኢትዮጵያ ሕዝቦች ሲባል መጥፋት አለበት። ለአለም ሕዝብ ሲባል መጥፋት አለበት።
መቼም ችግር ከአንዲት ቡድንና ከአንድ ሰው ነው የሚነሳው።ከዚያ በኋላ ነው አለምን የሚያዳርሰው።ይህ ቡድን ዝም ብለን ከፈቀድንለት አለምን ከማጥፋት አይመለስም። ሰናይ መልካም የተባለውን በሙሉ ነው ያጠፋው። ይህን ሲያደርግ መጀመሪያ ክፋትን ጽፎ ሰነድ አዘጋጅቶ አስቀምጦ ነው።ድንገት ክስተት አይደለም። አንዳንድ ሰዎች ድንገት ክስተት ይመስላቸዋል። በስምንት ወሩ ዘመቻ ወይም ከስልጣን በመውረዱ ተበሳጭቶ ወይም ተገቢውን ስልጣን አላገኘሁም ብሎ አይደለም። የስነ ልቦና ባለሙያዎችን ብንጠይቅ ድንገት እንዲህ ያለ ጥፋት አይፈጸምም።ክፋትን ጽፏል። አሰልጥኗል። በዚህ በጻፈው ክፋት ሰዎችን አሰልጥኖበታል።ክፋትን ባህሪው አድርጎታል። ጠባዩ እሱነቱ አድርጎታል።ጭና መቄትና ደቡብ ጎንደር ያደረገው ይሄን ነው። እንዲህ አድርጉ ብሎ አሰልጥኖ መመሪያ ሰጥቶ ነው ያሰማራው።”
ታዲያ በበላበት ማዕድ ላይ ፣ ጎኑን ባሳረፈበት አልጋ ላይ የተጸዳዳ ፣ መነኮሳትንና ህጻናትን የደፈረ ፣ ንጹሐንን በጅምላ የገደለ ፣ እናትን ከልጇ ፊት በቡድን የደፈረ ሰዶማዊ፣ የቤት እንስሳትን በጥይት የቆላ ፣ ሞሰብ ገልብጦ የበላ ፣ ቡሀቃ የተሸከመ ፣ አብያተ ክርስቲያናትንና መስጊዶችን ምሽግ ያደረገ ያረከሰ ፣ በቅዱስ ቁራንና በመጽሐፍ ቅዱስ የተጸዳዳ ፣ ፊደል የቆጠረበትን ትምህርት ቤት ፣ የተከተበበትን ክሊኒክ ፣ እናቱ የወለደችበትን ሆስፒታል ፣ ወንድሞቹ የተማሩበትን ዩኒቨርሲቲ ያፈረሰ የዘረፈ ፣ የአርሶ አደር መርፌ ሳይቀር ፣ ወዘተረፈ የሰረቀ ወራዳ ይፈር እንጂ ፤ ትናንትም ዛሬም በከፍታው ላይ የሚገኝ አማራ ፣ አፋር ፣ ኢትዮጵያዊ ለምን ያፍራል?። ለምንስ ይዋረዳል ?። ይሄን ሁሉ ያደረጉትን ሲማርክ እንዴት ተንከባክቦ እንደሚይዝ እያየን ነው ። ሰሜን ዕዝ እንደዚያ ተከድቶና ተጨፍጭፎ እነ አቦይ ስብሐትን ሲማርክ ያደረገውን እኮ አይተናል ። ትናንትም ፣ ዛሬም፣ ነገም ፣ ምንጊዜም በስራው እንዳፈረ ፣ እንዳጠረ፣ እንደተዋረደ ፣ አንገት እንደደፋና እንደተሸማቀቀ የሚኖረው ሽብርተኛው ሕወሓትና ደጋፊው እንጂ ዛሬም በሞራል ልዕልናው በክብር በዙፋኑ የተቀመጠው አማራ፣ አፋርና ኢትዮጵያ አያፍርም ። ጥቁሩ ፋሽስትና ናዚ ሕወሓት በእኩይ ስራው በሀፍረት መሸሸጊያ ይጣ እንጂ ይህ ታላቅ ሕዝብ አንገቱ ቀና እንዳደረገ በክብር ይኖራል ።
ሀገራችን ኢትዮጵያ በጀግኖችና በሀቀኛ ልጆቿ ታፍራና ተከብራ ለዘላለም ትኑር !!!
አሜን ።