እኔነት እና እኛነት፡- የራስ ዕይታ
በዚያች በሥሉሳዊቷ(በሦስታዊቷ) መካከለኛው ምስራቅ የተሠመረቱት ሦስቱ ትልልቅ የሰው ልጆች ሃይማኖቶች፡- ይሁዲ፣ ክርስትናና እስልምና በዶግማና በቀኖና እንዲሁም በመሠረታዊ አስተምህሮዎቻቸው የተለያዩ ቢሆኑም ሦስቱንም የሚያመሳስላቸው አንድ ነገር አለ። እርሱም ይሁዲ፣ ክርስትናም ሆነ እስልምና ሦስቱም በአንድ አምላክ ሁሉን አድራጊነት (በዘመናችን በሃገራችን ያለቅጥ ሥር ሰድዶ በሚገኘው የመንጋ ፖለቲካ ቋንቋ አጠራር “በፈጣሪ አሃዳዊነት”(Monotheism) የሚያምኑና የሚመሩ መሆናቸው ነው።
ይሁን እንጂ በእነዚህ ሦስት ዋና ዋና የዓለማችን ሃይማኖቶች ውስጥ የሚመለኩት አሃዳዊ አምላኮች ሕላዊያቸው አንድነት፣ የሚያመለኩትም “አንድ አምላክ” ብለው ቢሆንም፤ በእያንዳንዱ ሃይማኖት ውስጥ የሚመለከው አምላክ ራሱን የሚገልጸው ግን “እኔ” እያለ ሳይሆን “እኛ” እያለ ነው። የአይሁዱ ያህዌ፣ የክርስትናው እግዚአብሔርም ሆነ የኢስላሙ አላህ ሁሉም “በአንድ አምላክነት” የሚመለኩ ቢሆኑም በየቅዱስ መጽሐፎቻቸው “እኔ” ሳይሆን “እኛ” እያሉ ነው ራሳቸውን ሲገልጹ የሚስተዋሉት።
ሰው የአምላክ የእጅ ሥራ ነውና ይኸው እሳቤ ወደሰው ልጆችም ተላልፎም እንደሆነ አይታወቅም የሦስቱም ሃይማኖቶች የጋራ መነሻ አብራሃማዊው አንድ አምላክ ብቻ ሳይሆን እንደ “ግርማዊ ቀዳማዊ ንጉሠ ነገሥት ዘ ኢትዮጵያ አጼ ኃይለ ሥላሴ” ዓይነት ራሳቸውን “እኛ” እያሉ የሚገልጹ ሰዎችም አልጠፉም። እናም አምላክ አምላክ በመሆኑ የፈለገውን መሆንና ማድረግ ይችላልና፣ አንድም የፈለገውን ቢልና ቢያደርግ አምላክ ነውና ከሳሽም የለበትምና አንድ የሆነው አምላክ ራሱን “እኛ” ብሎ ቢገልጽ ይችላል።
ለሰው ልጅ ግን ከሕግና ከሥርዓት መውጣት ያስጠይቃልና እዚህ ጋር ያለውን ከቋንቋው ሕግ የወጣ ነጠላ እኛ ወይንም በሰው ዘንድ ያለውን “እኔ”ን “እኛ” ብሎ የመግለጽ ሁኔታ ግን “ለምን?” ብለን እንጠይቃለን። ምክንያቱም በሁሉም ማለት ይቻላል፤ በሰው ልጆች ቋንቋዎች ሰዋሰው የመደብ ሕግ መሠረት “እኔ” የሚለው ተውላጠ ስም የሚወክለው አንድን ግለሰብ፤ “እኛ”ደግሞ ከአንድ በላይ የሆኑ ሰዎችን ነው። ስለሆነም አንድ ግለሰብ ራሱን ሲገልጽ “እኔ” እንጅ እኛ ሊል አይችልም። እኛ የሚለው ተውላጠ ስምም ያው ከአንድ በላይ ለሆኑ ሰዎች በመገለጫነት የሚያገለግል በመሆኑ ማናቸውም ከአንድ በላይ የሆኑ ስብስቦች ራሳቸውን “እኔ” ብለው ሊገልጹ አይችሉም።
በሌላ በኩል ግለሰብ ራሱን “እኔ” ከአንድ በላይ የሆኑ ግለሰቦች ደግሞ ራሳቸውን “እኛ” ብለው መጥራታቸው ሕጉን የተከተለና ተገቢም ሆኖ ሳለ ብዙውን ጊዜ “እኔ” የሚለውን አገላለጽ የግለኝነትና የራስወዳድነት መገለጫ አድርጎ የመውሰድ አመለካከት በበርካታ ባህሎች ውስጥ ሲንጸባረቅ ይስተዋላል። ታዲያ ሁለቱም አገላለጾች ማለትም የስብስቦቹ ራሳቸውን “እኛ” ብለው መጥራትም ሆነ የግለሰቦች ይሄንኑ መግለጽ ሕጉን የተከተለ ሆኖ እያለ የግለሰቦቹ ብቻ ተለይቶ ለምን ከግለኝነትና ከራስወዳድነት ጋር ሊዛመድ ቻለ? የዚህ ጽሑፍ ዋነኛ ተጠየቅም ይህ ለምን ሊፈጠር እንደቻለ የራስን ዕይታ ማጋራት ነው።
በእኔ አረዳድ ለዚህ አስተሳሰብ መፈጠር ዋነኛው ምክንያቱ “እኔ” እና “እኛ” በሚሉት ተውላጠ ስሞች ውስጥ የሚገኙት የአባላት ብዛት ናቸው። ይኸውም “እኔ” የሚለው የማይጨምርና የማይቀንስ፣ የማይለዋወጥና ሁሌም ያው የሆነ አንድ አባል ብቻ ያለው መደብ ሲሆን “እኛ” ግን ከአንድ በአንድ ብቻ ከምትበልጠው ሁለት እስከ መጨረሻው ትልቅ ቁጥር ድረስ የሚዘልቅ ብዛት ያላቸው ስብስቦች አባል ሊሆኑ የሚችሉበት የሰማይና የመሬት ያህል ልዩነት ያላቸው የአባላት ብዛቶች አንድ ላይ የሚጠሩበት አስገራሚ መደብ ነው። “ነገር በምሳሌ” እንዲሉ አበው “እኛ” በሚባሉ ስብስቦች መካከል ያለውን ከፍተኛ የሆነ የምጥጥን ተቃርኖ ለማብራራት የሚከተለውን ንጽጽር እንመልከት።
ባልና ሚስት ብቻ የሚገኙበት ሁለት አባላት ያሉት አንድ ቤተሰብ አለ እንበል። በሌላ በኩል ሚሊዮኖች አባል የሆኑበት አንድ ትልቅ አገርን እንውሰድ። እጅግ በሚያስገርም ሁኔታ ግን ሁለቱም ራሳቸውን “እኛ” ብለው ነው የሚገልጹት። አስቡት እንግዲህ ከ “እኔ” በአንድ አባል ብቻ በልጦ የሚገኘው ሚጢጢ ስብስብ ከአንድ በአንድ ስለበለጠ ብቻ ሚሊዮኖችና ቢሊዮኖችም የሚጠቀሙበትን “እኛ” የሚለውን መደብ መጠሪያው ሲያደርግ! እንግዲህ በዚህ ፍጹም የተንጋደደ ሚዛን መለኪያ መሠረት እኔና ሚስቴም፣ ኢትዮጵያም፣ ዓለምም ራሳችንን “እኛ” ብለን መግለጽ እንችላለን ማለት ነው።
ስለሆነም እኛ የዚህ ቤተሰብ አባላት ወይም የዚች ጎጆ ነዋሪዎች፣ እኛ የቀጠና አንድ ነዋሪዎች፣ እኛ የቀበሌ አስራ አንድ ነዋሪዎች፣ እኛ የደጃች ውቤ ሰፈር ነዋሪዎች፣ እኛ ኢትዮጵያውያን፣ እኛ አፍሪካውያን፣ እኛ የዚች ምድር ነዋሪዎች(እኛ የዓለም ሕዝቦች) እያልን ሁለት ሆነንም ሰባት ቢሊዮን ሆነንም “እኛ” የሚለውን መደብ እኩል እንጠቀማለን። በእርግጥ ሁኔታው ሁለትና ቢሊዮን እኩል እስኪሆኑ ድረስ ፍጹም የሆነ “ፍትሐዊነትና እኩልነት” የሰፈነበት ነው። ይህ የሚያስቀና እኩልነት “እኛ” የሚለውን መደብ ያለ ምንም ገደብ መጠቀም ላይ ተገድቦ ቀረ እንጂ! ምክንያቱም በሌላው ሕይወታችንማ ሁለትና ቢሊዮንን እኩል አድርጎ ማየት ይቅርና ሁለት ከራሷ ከሁለት ጋር እንኳን በእኩልነት እንድትኖር የማንፈልግ ክፉዎች ነን።
በእኔ እምነት ፍጹም የሆነ “ፍትሐዊነትና እኩልነት” ያለበት የሚመስለው ይህ በእኔና በእኛ መደቦች መካከል ያለው ያልተስተካከለ የአባላት ብዛት ምጣኔ በተቃራኒው ፍጹም ኢ-ፍትሐዊነት የነገሰበትና ለአያሌ የሰብዓዊ ፍጡር ችግሮች መንስኤ የሆኑ ክፋቶችን የተሸከመ ነው። ከዚህ ቀደም በዚሁ ዓምድ ላይ ያመላከትኩትና “ራስ ጠልነት” በሚል ስያሜ የገለጽኩት እጅግ አደገኛና አውዳሚ የሰው ልጆች ባህሪይ አንደኛው መንስኤውም ቀላል የሚመስለው ይኸው የአንደኛ መደቦች ነጠላና ብዙ ኢ-ፍትሐዊ የአባላት ብዛት ነው።
ሁለት ማሳያዎችን በመጠቀም ሃሳቤን በተጨባጭ አመክንዮ አስደግፌ እይታየን ላጋራችሁ። ጉዳዩን ጠልቀን ስንመረምረው ብሔርተኝነትን ጨምሮ ዓለም ላይ የሚገኙ የሁሉም ኢ-ምክንያታዊና ኢ-ተፈጥሯዊ ራስን ብቻ ወዳድ ቡድንተኝነቶችና ቡድኖች እንዲሁም ለጋራ ዓላማ ተቋቁመው የአንድ ወይንም የተወሰኑ ጥቂት አካላትን ጥቅም ብቻ የሚያስፈጽሙ ድርጅቶች ከዚህ የቋንቋ መደብ ስያሜ ኢ-ፍትሐዊነት ጋር የተገናኙ መሆናቸውን እንገነዘባለን።
ማሳያ አንድ፡- ቡድንተኝነትና ብሔርተኝነት
የእኛን ጨምሮ በዓለም ላይ የተከሰቱና የሚከሰቱ ብሔርተኝነቶች በአጥንትና በደም የሚሰባሰቡት ቆምኩለት ለሚሉት ለዚያ ብሔር ጥቅም አስበው ሳይሆን፤ በግለሰብነት “በእኔነት” ማሳካት የማይችሉትን ራስን ብቻ ወዳድነት (ራስ ጠልነት) የፈጠረው ስግብግብነነት፤ ያልተገባ ጥቅምና ጥቅመኝነት ማሳካት የሚችሉት ከጥቂት መሰሎቻቸው ጋር በመተባበር “በእኛነት” ስም ነው።
ይሁን እንጂ እንዲህ ዓይነቱ ቡድንተኝነት እንደ ቡድን ብዙ (ማኅበር) ይሁን እንጂ የራስን ብቻ ወዳድ (የራስ ጠል) ግለሰቦች የማይረካ ሲኦላዊ ፍላጎትና የማያልቅ ጥቅም (ስግብግብነት) ማስፈጸሚያ ሽፋን በመሆኑ አሁንም ግለሰብ ነው። የአንድ ክፉ ራስ ጠል ግለሰብ ወይንም ሙሉ በሙሉ የዚያን ግለሰብ የራስ ብቻ ተጠቃሚነት ፍላጎት የሚያስፈጽሙ፣ ከግለሰቡ ጋር ያውና አንድ የሆኑ፣ የግለሰቡ “ሃይኮፒዎች” ብቻ የብቻ ተጠቃሚነት ማስፈጸሚያ መድረክ በመሆኑ ወይንም የአባላቱን የብዙኃን የጋራ ፍላጎት የማያስጠብቅ በመሆኑ የብዙዎች አይደለም። በብዙዎች ሽፋን የተቋቋመ የአንድ ግለሰብ ወይንም የጥቂት እርሱን መሰል ግለሰቦች ነው። አንድ ራስ ያለው ብዙ አካል፣ በግለሰብ አዕምሮ የሚያስብ ስብስብ (ቡድን) ነው፣ በ“እኛነት” ስም የሚነግድ “እኔነት” ነው።
እናም ማኅበር ወይንም ማኅበረሰብ ሊባል አይችልም፣ ማኅበረሰብ ለጋራ ዓላማ የተሰበሰበ የግለሰቦች ኅብረት ነውና! ብሔርተኝነት ከሆነም በብሔር ስም የራሱን ፍላጎት ማስፈጸሚያ ግለሰብ ወይንም የብሔር ሽፋን ያለው ግለሰብ ነው እንጂ ብሔርም ብሔርተኝነትም አይደለም። ይህ በብሔር ስም ለግል ጥቅም ብቻ የሚካሄድ ብሔርተኝነት፣ ማኅበራዊነት የሚመስል ግላዊነት (ግለኝነት)፣ በግለኝነት የሚነዳ ወገንተኝነት፣ የጋራ የሚመስልና ለራስ ብዙ የሚመስል ነጠላ፣ ኅብረት የሚመስል ብቻነት (ብቻ ወዳድነት) ነው። እናም ብሔርተኝነት ሊሆን አይችልም። ምናልባት ቡድን የሚለው የተሻለ ይገልጸዋል። ከቡድን ደግሞ መንጋ ይበልጥ ይስማማዋል፣ መንጋ በአንድ (በግል) የሚነዳ ብዙ የሚመስል ነጠላ ስብስብ ነውና!
ማሳያ ሁለት፡- “የተባበሩት” መንግሥታት ድርጅት
በ“እኛነት” ስም “እኔነት” ከሚነገድባቸው የብዙኃን ኅብረቶች መካከል ሌላኛውና ዋነኛ ማሳያ ሆኖ የሚጠቀሰው ደግሞ በአሁኑ ሰዓት 153 ሀገራትን በአባልነት ያቀፈው፤ በተግባር ግን የምዕራባውያንን የግል ፍላጎትና ጥቅም ብቻ የሚያስጠብቀው ግዙፉ የዓለማችን ማኅበር “የተባበሩት” መንግሥታት ድርጅት ነው። ይህ ድርጅት በ153ቱ አባል ሃገራት የዘር፣ የፆታ፣ የቋንቋ ወይም የሃይማኖት ልዩነት ሳይደረግ ለሁሉም ሀገራትና ለሁሉም የሰው ልጆች ሰብዓዊ መብቶች እና መሠረታዊ ነፃነቶች ሊኖር እንደሚገባው በመተዳደሪያ ቻርተሩ ውስጥ በግልጽ ደንግጎ አስቀምጧል። በዚህም በአባል ሀገራት ውስጥ ሰላምና ደህንነት እንዲሰፍን የማድረግ ተልእኮ ተሰጥቷል። ይህንን ተልእኮውን የሚያስፈጽምበትም አባል ሀገራቱ በግልጽ ተለይቶ የተሰጠው ስልጣንና ተግባር ብሎም ዝርዝር የአሠራር ሕግና ደንቦችንም አስቀምጧል።
ይሁን እንጂ ድርጅቱ በግልጽ ወግኖ የሚሠራው ድምፅን በድምፅ የመሻር መብት ለተሰጣቸው ለጥቂት ኃያላን ሃገራት በተለይም ደግሞ ለምዕራባውያን ጥቅም ብቻ መሆኑ ዓለም ያወቀው፤ ፀሐይ የሞቀው ሐቅ ነው። ይህም የድርጅቱን ሥም በከንቱ ለማጠልሸት የሚደረግ የሐሰት የፕሮፖጋንዳ ዘመቻ ሳይሆን በገሃዱ ዓለም የተከሰቱ ነባራዊ እውነታዎችን መሠረት ያደረገና በተለያዩ የዓለማችን ክፍሎች የተፈጠሩ ሁነቶችን በማሳያነት በማቅረብ በተጨባጭ መረጃዎችና ማስረጃዎች ተደግፎ የሚቀርብ እውነት ነው። በዚህ ረገድ በጉልህ ከሚጠቀሱ ዋና ዋና ማሳያዎች መካከልም ከፍልስጤም እስከ እስራኤል፣ ከሶሪያ እስከ የመን፣ ከኢራቅ እስከ አፍጋኒስታን፣ ከሊቢያ እስከ ሶማሊያ በርካታ አገራትን መዘርዘር ይቻላል።
ለአብነት ድምጽን በድምጽ የመሻር ልዩ መብት የተሰጣቸው ኃያላኑ አባሎቹ፤ በተለይም አሜሪካና ምዕራባውያን በመተዳደሪያ ቻርተሩ የተቀመጠውን በሃገራት የውስጥ ጉዳይ ላይ ጣልቃ ያለመግባት ሕግ ጥሰው በርካታ ሃገራትን ሲወሩና ሲያወድሙ የተባበሩት መንግሥታትና ጉዳዩ በቀጥታ የሚመለከተው የድርጅቱ አካል የፀጥታው ምክር ቤት ሕገ ወጥ ድርጊታቸውን ሲቃወምም ሆነ ሲያስቆም አልተስተዋለም። ይባስ ብሎ በሀገራቱ ሰላምና ደህንነት እንዲመለስና የሕዝብ ስቃይና መከራ እንዲያበቃ መደበኛው የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት ጉባኤ በሚካሄድበት ወቅት አባል ሀገራት በተደጋጋሚ የፀጥታው ምክር ቤትን ሲጠይቁ አንድም ምላሽ ሳይሰጥ ለጉዳዩ ጆሮ ዳባ ልበስ ብሎ ሲቀር በገሃድ ተስተውሏል።
በተመሳሳይ መንገድ በአሜሪካና የምዕራባውያን ሕገ ወጥ የጉልበት ጣልቃ ገብነት የመን ወደ ፍርስራሽነት ስትቀየር ዜጎቿ በግፍ ሲያልቁ፣ የቀሩት በዓለም ላይ እንደ ጨው ሲበተኑ፣ ሊቢያ የእርስ እርስ ጦርነት አውድማ ስትሆን፣ ንጹሐን በጥይት በጅምላ ሲያልቁ፣ ሰብዓዊ ፍጡራን ሲሰቃዩ… ምንም አላለም። ጉዳዩ በቀጥታ የሚመለከተው የድርጅቱ አካል የፀጥታው ምክር ቤትና በሥሩ የሚገኘው ዛሬ በኢትዮጵያ ጉዳይ ላይ የሰብዓዊ መብት ተቆርቋሪ ሆኖ በሰብዓዊ መብት ባለሙያዎች ኮሚሽኑ አማካኛነት ላም ባልዋለበት ኩበት ሲለቅም የሚውለውና የሐሰት ሪፖርት እያመረተ የሚገኘው የሰብዓዊ መብቶች ኮሚሽንም ቃል አልተነፈሰም።
ሴቭ ዘ-ችልድረን የተባለው መንግሥታዊ ያልሆነ ሰብዓዊ የተራድኦ ድርጅት በሶሪያ ለሰው ልጆች የተሻለ ሕይወትን የመፍጠር ዓላማ ያላቸው ሰብዓዊ ተቋማት ትምህርት ቤቶች የሰው ልጆች የማሰቃያ ማዕከላት መሆናቸውንና፤ ሕጻናትና ልጆች ለጦርነት ዒላማ መለማመጃ መሆናቸውን የሚያሳይ በማስረጃ የተደገፈ ዘገባ ሲያቀርብላቸው ባላየ አልፈውታል። “እባካችሁ በእነዚህ ልጆች ላይ እየተፈጸመ የሚገኘው ስቃይና በአጠቃላይ በሰው ልጆች ላይ እየደረሰ ያለው ዘግናኝ እውነታ እንዲያበቃ ኃላፊታችሁን ተወጡ” ብሎ የተባበሩት መንግሥታትን ሲማጸንም እነሰብዓዊ መብት ኮሚሽንና የባለሙያዎች ቡድን ጆሮ ዳባ ልበስ ብለውት ቀርተዋል።
ምንም አሳሳቢ ሁኔታ በሌለበት በኢትዮጵያ የውስጥ ጉዳይ ግን የተደበቀ ማንነቱን ግልጥልጥ አድርጎ በሚያሳይ ፍጹም አሳፋሪ ሁኔታ የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት የፀጥታው ምክር ቤት በአንድ ዓመት ውስጥ በተኩላ ተቆርቋሪነት የበግ ለምድ ለብሶ አስራ ሁለት ጊዜ ጉባኤ ተቀምጧል። እነሆ ዛሬም ለምዱን ቀይሮ የሰብዓዊ መብትን ገጽ ለብሶ መጥቷል። የጥቅም ተጋሪው የኢትዮጵያ ብሎም የሰው ዘር በሙሉ ጠላት የሆነው አሸባሪው ትሕነግ ዓለም አቀፍ ሕግጋትን ጥሶ ንጹሐንን ሲያርድና ሲጨፈጭፍ፣ በኢትዮጵያውያን ላይ የዘር ማጥፋት ሲፈጽም፣ ሕጻናትን በይፋ እየመለመለ ለጦርነት ሲማግድ እሰየው ብሎ አልፎ በጥፋት ቡድኑ ወንጀል ገልብጦ ኢትዮጵያን ይከሳል።
የዚህ ምክንያቱ ደግሞ አንድና አንድ ነው፤ በ153 ሃገራት ስም በሌሎች አገራት ላይ እንደለመደው የአዛዦቹን የአሜሪካና የምዕራባውያንን ጥቅም ብቻ በኢትዮጵያም ላይም ለማስፈጸም ነው። ከዚያም የምዕራባውያን ፍላጎትና ውሳኔ ይፈጸምና “የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት ውሳኔ ነው” ተብሎ ይነገረናል። ታዲያ የአንድን ወገን እኩይ የግል ጥቅም ብቻ የብዙዎች ወይንም የጋራ አስመስሎ የሚፈጸምበት ይኼ የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት ሥራ በ“እኛዎች” ስም የሚካሄድ የ“እኔዎች” ንግድ አይደለምን? እናም “የተባበሩት” መንግሥታት ድርጅት፤ የተባበሩት ይሁን እንጂ በ“እኛነት” ስም “እኔ ብቻ ልጠቀም ሌላው ሁልጊዜ ከኔ በታች ሆኖ ይኑር” በሚል በተዛባ ሕግ የሚመሩ፣ በፍትሕ በእኩልነትና በወንድማማችነት የማያምኑ፣ የሰለጠኑ መስለው ያልሰለጠኑ ኋላ ቀር ኃይሎች ብቻ የሚያገለግል በመሆኑ የተባበሩት ወይንም የዓለም መንግሥታት ድርጅት ራሱን ሊፈትሽ፤ ስምና ዓላማውን ሊመስል ይገባል!!!
ምክንያቱም በተለይ አንዳንድ የምዕራቡ አገራት እንደ አሸባሪው ትሕነግ ዓይነት የእነርሱ ዓላማ ደጋፊዎችና የጥቅም ተጋሪዎች ፍላጎት ብቻ ማስፈጸሚያ መድረክ በመሆኑ፤ ወይንም የአባላቱን የብዙኃኑን (የሁሉንም አባል አገራት) የጋራ ፍላጎት የማያስጠብቅ በመሆኑ የተባበሩት የጋራ ድርጅትነት ስያሜውን መሸከም ይከብደዋል። በብዙዎች ሽፋን የአንድ ወገን የግል ጥቅም ብቻ ወይንም የጥቂቶች ጥቅም የሚሳደድበት የጋራ መሳይ የግል ድርጅት ሆኗል። ከዚህ አንጻር የተባበሩት መንገሥታት ድርጅት እንደ ስሙ ሁሉም ተባብረው የሚሠሩበት፣ የሚናገሩበት፣ የሚወስኑበት፣… እንዲሆን አሠራሩ ላይ ስር ነቀል ተሐድሶና ለውጥ ማድረግ ይኖርበታል።
ይበል ካሳ
አዲስ ዘመን ሐሙስ ጥቅምት 3 ቀን 2015 ዓ.ም