ተቃርኗዊ ወግ፤
ሀገራዊ ኢኮኖሚያችን ጨርቁን ጥሎ ካበደ ሰነባብቷል፡፡ የእብደቱ መጠን ሲጨምር እንጂ ሲቀንስ አይስተዋልም፡፡ የወፈፍታው መንስዔ ምን እንደሆነ እቅጩን ነግረው ቁርጣችንን ያሳውቁናል በማለት በተስፋ የምንጠብቃቸው የሙያው ልሂቃንም እንደ ተራው ዜጋ ሁሉ እብደቱ በፈጠረባቸው ጫና መታመማቸውን እንጂ ሀገራዊው መፍትሔ ይህ ነው ብለው “ገዢዎቻችንን” ሊሞግቱልንም ሆነ ሊያረጋጉን አልቻሉም፡፡ “አውሮፓ በኢኮኖሚው ጣጣ ሲያስነጥስ እኛ በኑሮ ኢንፍሉዌንዛ” እየተቀጠቀጥን እስከ መቼ እንደምንኖር ግራመጋባት ብቻም ሳይሆን እህህታው ራሱ የእለት ቀለባችን እስከ መሆን ደርሷል፡፡
ምሑራኑ በየጓዳቸው፣ “በየዝግ ሴሚናሮቻቸው”፣ በየሚያስተምሩባቸውና “በየምሽቱ መሰባሰቢያቸው” ምን የመፍትሔ ሃሳብ ሲመክሩና ሲቀምሩ እንደሚውሉ ሊነግሩን የማይፈልጉት አንድም ባዕድ ባለሀገር አድርገው ስላገለሉን ነው፤ ወይንም የተራው ሕዝብ ቋንቋ ለገለጻ ስለማይመጥናቸው ነው፡፡ እንዘንላቸው ካልንም የቀመሩት ቲዎሪ አልሠራላቸው ብሎም ሊሆን ይችላል፡፡
በአዘቦቱ ቋንቋችን ቢያስረዱንና ሰበበ ምክንያቱን ቢነግሩን ኖሮ ቢያንስ “ሆድ ይፍጀው” በሚለው ብሂላችን ተጽናንተን ማቃሰቱ ሊቀንስልን ይችል ነበር፡፡ አልፎ አልፎ የሚሰነዝሯቸው መላምቶችና ምክንያቶችም ቢሆኑ የምኞታችንን ሀገራዊ የተራራ ጫፍ ይጠቁሙ ካልሆነ በስተቀር ቁልቁል ዝቅ ብለው የዕለት እንጀራ መሸመቻ የጉልቶቻችንን ቁስል ስለማይነካኩ ከኑሯችን ጥዝጣዜ ፋታ ለማግኘት ያለመቻላችን ሊሰመርበት ይገባል፡፡
የአድአ ጤፍን (ወይ መቅበጥ አሉ!) ሰማይ ላይ ያሽቀነጠረው ምንድን ነው? ከአዋሽ ወንዛችን ፀጋ የሚታፈሰው ሽንኩርትና ቲማቲም ለምን ስማቸው እንጂ መልካቸው ጠፋብን? የሸኖ ቅቤና ምስር፣ የማረቆ በርበሬ፣ የላንቴ ሙዝ፣ የባሌና የአርሲ ስንዴ፣ የቡልጋ ቃሪያ፣ የጎጃም ማር፣ ከወልቃይትና ከሁመራ ሰሊጥ ይመረት የነበረው ዘይት፣ የሐረርና የሲዳማ ቡና ወዘተ. ስለምን በወርቅ መስፈሪያ ሊቸረቸሩ ቻሉ? እያልን ስናጉተመትም “በፈረደበት የምርጫ ካርድ አደራ የጣልንባቸው ሹመኞቻችንና ‹ያስተማርናቸው› ጠቢባኖቻችን” ለዩክሬን-ራሽያ ልቅሶ ሙሾ እያሞሹ እንድናላቅሳቸው ይጎተጉቱናል – “የራሷ እያረረባት…” እንዲሉ፡፡
“የደም ወዛችንና” ገበያው ተኳርፈው ጀርባ ለጀርባ ከተሰጣጡ ዓመታት ተቆጥረዋል፡፡ ባዕድነታቸውም ሰፍቶ ተራርቀዋል፡፡ ስለዚህም ሽንኩርት የለመደው ድስታችን፣ ምስር የለመደው ጉርሻችን፣ ጥቁርና ማኛ እያልን ስናማርጥ የኖርነው የጤፍ ሬሽናችን፣ ልጆቻችንን የምንደልልበት የመክሰስ “ብጤሌ” ቂጣ ከደሃው ሕዝብ ማጀት እንኳን ሊገኙ ቀርቶ ከእህል በረንዳ ጆንያም ተራግፈው ገበያው በድርቅ ተመትቷል፡፡ “ምድሪቱ አላበቅል ብላ ይሆን (?)” ብለን ስንጠይቅ እንደ ማኅበረሰባዊ የጅል ባህርይ እየታየ ይሳቅብናል፡፡ በርግጥም ብራችን እንደ ስሙ ብር እያለ መክነፍ የጀመረው ዘንድሮ ሳይሆን አይቀርም፡፡ “ስሙን መላእክት አውጥተውለት ይሆን?”
ይሄ ሁሉ ጫና ያነሰ ይመስል የትራንስፖርቱ በጀት፣ የልጆቻችን ት/ቤት ወጭ፣ የአልባሳቱ ሸመታ ጉዳይ ወዘተ. እያልን በመዘርዘር ብሶታችንን መዘርዘሩ በፈጣሪ ድካም ላይ ሌላ ጫና ማሸከም እየመሰለን የባሰ እንዳያመጣብን እየተማጸንን “በሰላም ያዋልከን በሰላም አሳድረን!” ማለቱን መርጠናል፡፡ አስተዳዳሪው መንግሥታችንም ቢሆን “እንዴት መታገስ አቃታችሁ፣ ለምንስ በተስፋ መኖር ተሳናችሁ?” በሚል ቁጣ ሊገስጸን ስለሚችል “መጀን ለሁለቱም!” እያልን “ኑሮ ካሉት መቃብር ይሞቃል” በሚለው ሀገራዊ ብሂል መጽናናቱ ሳይሻል እንደማይቀር ደምድመናል፡፡
ብራናችንን እንግለጥ፤
“ይህ ሁሉ የኑሮ ሸክም እያንገዳገደን ስለምን ሌላ ቅንጡ ጉዳይ አንስታችሁ እንድናማርር ትጎተጉቱናላችሁ” በማለት ዋነኛውን ርዕሰ ጉዳያችንን እንደ “ቅብጠት” የሚያዩ “ሆደ ባሻዎች” እንደማይጠፉ ብንጠረጥርም ጨክነን ወደ ዋናው የመነሻችን መሪ ሃሳብ እናቀናለን፡፡ ምክንያታችን ግልጽ ነው፡፡ ሆዳችንም ተርቦ፣ አዕምሯችንም በጠኔ ተጠቅቶ ሕይወትን መግፋቱ “በቡሃ ላይ ቆረቆር” እንዳይሆንብን በመስጋት የሚሰማ ጆሮ ካለ ሌላኛውንም ብሶታችንን እንዲያደምጥልን በስልጣነ መንበሩ ስም ለመማጠን ነው፡፡ እነሆ ሀገራዊ ብሶታችን፡፡
በሀገራችን ታሪክ የወርቅና የኅትመት ወረቀት ዋጋ ልክ እንደ ዛሬው ተቀራራቢ ደረጃ ላይ ደርሰው የነበረበት ዘመን ኖሮ ከሆነ “ለጸሎትም ለእውቀትም” ስለሚረዳን የሚያውቁ ቢያሳውቁን ከብሶትም ከስህተትም ልንጠበቅ እንችላለን፡፡ ዛሬ በኢትዮጵያ ምድር መጻሕፍት እናሳትማለን ብለው የሚወስኑ ደራስያን ሊመሰገኑ የሚገባቸው “እስከ ሞት ድረስ ለሙያቸው ክብር ለመሰዋት እንደሚጨክኑ ጀግኖች” ነው፡፡ ይደልዎ! ብለናል፡፡
ከመቶ ገጽ የሚያንስ መጽሐፍ በመቶዎች የሚቆጠር ዋጋ ሲሰላለት ስናስተውል “መሳቁን ይስቃል ጥርሴ መች አረፈ፤ ልቤ ነው በጣሙን እጅጉን ያዘነ” ብለን እንድናንጎራጉር እንገደዳለን፡፡ ስቅስቅ ብሎ ከብዕር ጋር መላቀሱ እጅግም ስለማይበረታታ ብሶትን አምቆ በእህህታ ጊዜውን መግፋት
ይበጃል፡፡ አጽናኝ የሌለበት ልቅሶ መጯጯሁ ስለሚበረታ፡፡
“የኅትመት ዋጋ ናረ!” የሚለው አገላለጽ ትርጉም የነበረው ከዓመታት በፊት ነበር፡፡ ዛሬ ዛሬ “የኅትመት ዋጋ ናረ ሳይሆን ክንፍ አውጥቶ ተሰወረ” ማለቱ ይቀላል፡፡ ለማተሚያ ቤቶች የተነገረው የሚከተለው የሙገሳ ሐተታ እንደትናንቱ በዚህች በእኛይቱ ጨፍጋጋ ጀንበርም “ቁብ” ተሰጥቶት “አሜን!” ይባልለት ከሆነ እርግጠኞች አይደለንም፡፡ ለማንኛውም ፍካሬውን እናስታውስ፡፡
“ይህ ማተሚያ ቤት ነው፡፡ የሥልጣኔ
መገኛ፡፡ በጊዜ ምክንያት እንዳይቃወሱ የጥበቦች ሁሉ መድኅን፣ የወሬ ብቻ ሳይሆን የእውነት ማህደር፣ የማያቋርጥ የንግድ እምቢልታ ነው፡፡ ከማተሚያ ቤት ቃሎች ወደ ሩቅ ይበርራሉ፡፡ ንግግርና ድምጽ ብቻ ሆነው እንዳያልፉ፡፡ ከጊዜ ወደ ጊዜ እንዳይለወጡ ግን ታርመው ለዘለዓለም እንዲኖሩ፡፡ ክቡር ሆይ! አሁን በተቀደሰ ቦታ ይገኛሉ፡፡ ይኼውም በማተሚያ ቤት ነው፡፡” (አርትስቲክ ማተሚያ ቤት ደጃፍ ላይ “በወርቅማ ቀለም” የተጻፈ ማስታወሻ)፡፡ “ቃሎች ወደ ሩቅ ይበራሉ!” የሚለው አገላለጽ ከይዘቱ ጋር ከሚያያዝ ይልቅ ከኅትመት ዋጋ መክንፍ ጋር ቢተያይ መልካም ሳይሆን የሚቀር አይመስለንም፡፡
ወደ ሰማየ ሰማያት እየጎነ ያለውን የኅትመት ዋጋ በሩጫም ይሁን በተማጽኖ ማስቆም የማይቻል ከሆነ የሀገሬ ደራስያን ያላቸው አንድ ብቸኛ መፍትሔ ብራና ፍቀውና ቀለም በጥብጠው ራሳቸው ድጉሱን በማሳመር እንደ ቀድሞ አባቶች የውስጣቸውን የተሰጥኦ ወላፈን እንዲያበርዱ መምከር ብቻ ነው፡፡ ለየበዓላቶቻችን የሚሰውት የበግና የፍየል መንጋ ሌጦ ገዢ አጥቶ በየመንገዱ እየተጣለ ስለሆነ የጥሬ ዕቃ ችግር ይኖራል ተብሎ አይታሰብም፡፡
ለክፉም ለደጉ ከወረቀት ኅትመት ወደ ጥንቱ የብራና ጥበባችን መመለሱ ግድ መሆኑ ስለማይቀር ለብዕረኞቹ ወዳጆቻችን መሠረታዊውን የብራና አዘገጃጀትና የቀለም ቅመማውን እውቀት እንድንጋራቸው መልካም ሆኖ ታይቶናል፡፡
ብራና የሚሠራው ከጥጃ፣ ከበግ፣ ወይንም ከፍየል ቆዳ (አንጋሬ) መሆኑን ልብ ይሏል፡፡ ደራስያን ወዳጆቻችን ከበሬ ቆዳና ሌጦ ጋር እንዳትታገሉ አደራ፡፡ አንጋሬው በውሃ ተዘፍዝፎ ወይንም በርጥቡ ተወጥሮ ፀጉሩ ከላዩ ላይ ሲላጭና ሲጸዳ ወረቀት መሰል የጽሕፈት ሰሌዳ ይወጣዋል፡፡ “ግዛዋ ሳለ ከደጅሽ፤ ለምን ሞተ ልጅሽ?” እንዲሉ፤ ዘዴው ከደጃፋችን ስላለ የደራሲዎቻችን ጽንስ እንዳይጨነግፍ ብልሃቱ ሳይረዳ አይቀርም፡፡
ቀለም የሚቀመመው ደግሞ እንደሚከተለው ነው፡፡ የተለያዩ ቅጠላ ቅጠሎችን፣ የበግ ቀንድና የበሬ ሸኮና፣ የብራናው ፍቅፋቂ፣ ከሰል፣ የእንጆሪ ፍሬ፣ ቀይ አበባ፣ ቀይ አፈር ወዘተ. አንድ ላይ አጅሎና ዘፍዝፎ በማሰንበት ወደሚፈለገው ደረጃ ሲደርስ በግራር ሙጫ በመቀቀል አንጥሮ በማውጣት መጠቀም፡፡ የቀለማቱን ዓይነት ለመወሰንና ዝርዝር አተገባበሩን ለማወቅ ተጨማሪ ንባብ አስፈላጊ ይሆናል፡፡ ከዚያም ብራናውን ዘርግቶ በመቃ ብዕር እየቀሸሩ እንደ ቀደምት አባቶቻችንና እናቶቻችን “የጽሑፍ ቅርስ” ማቆየት ነው፡፡
ቅርሱ ከደራሲዎቹ ዕድሜ በላይ መሰንበቱ እንደተጠበቀ ሆኖ ምናልባትም በሰማይ ቤት ከሀዲስ ዓለማየሁ፣ ከበዓሉ ግርማ፣ ከብርሃኑ ዘርይሁን፣ ከዳኛቸው ወርቁ፣ ከስንዱ ገብሩ፣ ከፊርማዬ ዓለሙና ከሌሎች ነፍሰ ሄሮች ጋር መገናኘቱ ስለማይቀር፤ “ለመሆኑ የዘመናችሁ የኅትመት ደረጃ ከምን ደረሰ?” ብለው ቢጠይቁ የሚከተለውን መልስ አስቦ መዘጋጀቱ አይከፋም፡፡
“ኢትዮጵያ ከወረቀት ጋር ተኳርፋ፣ ከዲጂታሉ ዓለም ጋር ከንፋ፣ ለደራሲያዎቿ ክብር ነፍጋ፣ ለጠፊው ዶላር ቅድሚያ ሰጥታ፣ የወረቀት ዋጋን ከወርቅ ዋጋ ጋር አቀራርባ ስለገፋችን የመጻሕፍት ኅትመት ጉዳይ ጉዳዬ አይደለም በማለቷ ወደ ቅድመ አያቶቻችን ዘመን ወደ ጥንቱ የብራና ጥበብ ለመመለስ ተገደናል፡፡” ብሎ መመለሱ አያሳፍርም፡፡ ዓለም አቀፍ ደረጃውን የጠበቀ ቤተ መጻሕፍት በዋና መዲናዋ ያስገነባች ሀገር ለኅትመቱ ጉዳይ ለምን ቸል እንዳለችም ሪፖርት ማቅረቡ ክፋት የለውም፡፡
ማስረጃ ከተጠየቀም በየትኛውም የዓለም ክፍል ተዘውትሮ የማይተገበረውን የመጻሕፍት ኅትመት ግብዓት የታክስ አወሳሰን በማስረጃ ማሳየት
ይቻላል፡፡ ኢምፖርት/ዲዩቲ ታክስ 10%፣ ሱር ታክስ 10% (በቅርቡ ይህ ታክስ ቀርቶ ከሆነ እናጣራለን)፣ ዊዝ ሆልዲንግ ታክስ 3% ለተጨማሪ እሴት ታክስ 15% (ወደ ምርት ሲለወጥ)፣ በአጠቃላይ ድምር ወደ 43% ገደማ ግብር ከመጻሕፍት ግብዓቶች ላይ መንግሥታችን ይቀርጣል ማለት ነው፡፡
በአንድ አብነት ማሳየት ከተቻለም 61X86 ሴ.ሜ ስፋት ባለው አንድ ሪም (400 ወይም 500 ቅጠል የሚይዝ ፓኬጅ) ዛሬ በሀገር ውስጥ ከብር 5000.00 በላይ ደርሷል፡፡ ከጥቂት ዓመታት በፊት ይህ ዋጋ ከአራት መቶ ብር በታች እንደነበር ጸሐፊው ያስታውሳል፡፡ ይህ ጸሐፊ የአንጋፋው ማተሚያ ቤት ባልደረባ በነበረበት ዘመን የኅትመት ግብዓቶችን ግዢ ሲያዝ የነበረውን ዋጋ ማስታወስ ተረት ስለሚመስል ያለመጥቀሱ ይበጃል፡፡ ወረቀት ከነዳጅ በልጦ በየዕለቱ ማሻቀቡን ሲታሰብ “ወየው ለነገ ያሰኛል፡፡”
ከውጭ ሀገራት ታትመው የሚገቡ መጻሕፍት ግን ከተጨማሪ ታክስና ከታሪፍ ቀረጥ ነፃ ስለሆኑ በሀገር ውስጥ መጻሕፍትን ከማሳተም ይልቅ ውጭ ሀገር አሳትሞ ማስገባት በእጅጉ ይቀላል፡፡ መጻሕፍትን ውጭ ሀገራት ለማሳተም ብልሃቱ የውሃ መንገድ የሆነላቸው እድለኞችና “ምርጥ የሀገሪቱ በኩራን” ግን “እንኮኮ” እየተባሉ መጻሕፍት ከውጭ ሀገራት እንዲያስገቡ ጎዳናው ይጠረግላቸዋል፡፡
ስለዚህ የሀገሬ ደራስያንና ደራስያት ሆይ! “ዝም አይነቅዝም!” በማለት የብዕራችሁን አንደበት ከመዝጋት ባህላዊውንና ጥንታዊውን የብራና ጥበብ በመጠቀም ከተሰጥኦ ምጣችሁ ለመገላገል ሞክሩ፡፡ “የጨነቀው እርጉዝ ያገባል” ይባል የለ፡፡
ቀድሞውንም ቢሆን የዚህች ሀገር ደራስያንና ደራስያት እንባቸውን ከቀለም ጋር እያጣቀሱ ሲጽፉ መኖራቸው እየታወቀ ወረቀትን በወርቅ ሚዛን እየመዘኑ የፈጠራ ሥራዎቻቸውን እንዲያሳትሙ የፈረደችባቸውን ኢትዮጵያን ትዝብት ላይ የሚጥል ክፉ ድርጊት ነው፡፡ ወርቅና ወረቀት ለመዋቢያ ካልሆነ በስተቀር የአዘቦት ቀናት መገልገያዎች እንደማይሆኑ ብዙ ምልክቶች እየታዩ ነው፡፡ ስለዚህም ብራና ፍቆ የመጻሕፍትን ኅትመት ማስቀጠሉ ውዴታ ብቻም ሳይሆን ግዴታ ጭምር ነው፡፡ “የተሸከመው ከብዶታል፤ እንደገና ይጨምሩበታል” አሉ አበው፡፡
ወላጆችም ቢሆኑ በቀጣዩ ዓመታት የልጆቻቸውን የብራና ድጉስ የመማሪያ መጻሕፍት እንደ ባህላዊ “የቆሎ ተማሪዎች” አሸክመው ወደ ትምህርት ቤት መላካቸው ስለማይቀር ከወዲሁ ዝግጅት ቢያደርጉ ይበጃቸዋል፡፡ የብራና አዘገጃጀቱን ጥበብ ወላጆችም በየቤቱ እንዲማሩ አደራ እንላለን፡፡ “ፊርማና ወረቀት ጠፊ ነው ተቀዳጅ፤ መተማመን ብቻ ይበቃል ለወዳጅ” የሚለው የአበው ትንቢታዊ ብሂል በእኛ ዘመን ተፈጽሞ ማየት “ዕድለኛነትም ይሁን እርግማን” ብቻ ከሁለቱ አንዱ ላይ መውደቁ አይቀርም፡፡ የኢትዮጵያ ደራስያን ማኅበርም ለወደፊቱ ስሙ ላይ ማስተካከያ በማድረግ “የኢትዮጵያ የብራና ደራስያን ማኅበር” ወደሚል “ከፍታ” መሸጋገር ግድ ይለዋል፡፡ ይኼው ነው፡፡ ሰላም ይሁን!
(ጌታቸው በለጠ /ዳግላስ ጴጥሮስ)
አዲስ ዘመን ጥቅምት 2 ቀን 2015 ዓ.ም