ድህነት ክፉ ነው፤ ረሃብ ደግሞ ከዚህም በብዙ እጥፍ የከፋ፣ ከክፋትም በላይ ክብርና ማንነትን ለዕለት ጉርስ ዝቅ አድርጎ ማስገዛትን የሚያስከትል
ነው፡፡ ችግሩ እንደ ሕዝብና ሀገር ሲሆን ደግሞ፤ በልቶ የማደር ጥያቄን ለመመለስ ክብርና ሉዓላዊነትን አሳልፎ ወደሚያሰጥ፤ ለረጂ ሀገራትና ተቋማት በርን ክፍት አድርጎ እስከመቀበልና ለእነሱ ጥቅምና ፍላጎት እጅ እስከመስጠት የሚያደርስ አደጋን የሚጋብዝ ነው፡፡ በዚህ ረገድ በርካታ ሀገራት የዜጎቻቸውን በልቶ የማደር ጥያቄ ለመመለስ፤ ከድህነት አረንቋ ለመውጣት ሲሉ ክብርና ሉዓላዊነታቸው ተደፍሮ፣ ሰላማቸው ከእጃቸው ወጥቶ በረጂዎቻቸው ፍላጎትና ጥቅም ላይ ተመሥርተው ለመራመድ ተገድደዋል፡፡ በርካቶችም በድህነት በራቸው በገባ አካል እጃቸው ተጠምዝዞ እንደ ሀገር የመኖር ሕልውናቸው በእነዚሁ ሀገራትና ተቋማት መዳፍ ላይ ወድቆ ይታያል፡፡
ኢትዮጵያም፣ ምንም እንኳን ድህነትን እና ጊዜ ጠብቆ የሚከሰተውን ድርቅና ሌላም ክስተት ተከትሎ እጆቿን ለምጽዋት ስትዘረጋ የኖረች ብትሆንም፤ የዜጎቿን በልቶ የማደር ፍላጎት ለማሟላት በምታደርገው ሂደት ውስጥ የተዘረጋውን እጇን ይዞ ለመጠምዘዝ ለሚደረግ ጥረት ግን በጅ ሳትል ዘመናትን ኖራለች፡፡ ድህነቷን ተጠግተው ሊጠመዝዟትና ሊያንበረክኳት የሚሹ ኃይሎችን እንደየአመጣጣቸው ስትመክትና ስትመልስም ዘመናትን አስቆጥራለች፡፡ ዛሬም ድረስ ይሄንኑ የድህነቷን ጥላ ተጠልለው የዜጎችሽን ሆድ ከሞላን እንዳሻን እንዘዝሽ ለሚሏት ሁሉ፤ ክብር በሆድ አይለወጥም በሚል በእንቢኝ ለክብሬ ቆፍጣና አቋማ ጸንታለች፡፡
ይህ ሂደት ግን እንዲሁ በቀላሉ እንቢ ስለተባለ ብቻ የሆነ አይደለም፡፡ ይልቁንም ብዙ ዋጋ እያስከፈላት የዘለቀ እንጂ፡፡ ድጋፍ ከመከልከል ጀምሮ ጦርነት እስከማስነሳት ደርሶ በሚገለጸው በዚህ እጅ መጠምዘዣ ጫናቸው ላለመንበርከክ የዜጎቿን ውድ ሕይወት ከፍላለች፤ ከሌላት ቀንሳ የገነባቻቸውን የልማት አውታሮችም አጥታለች፡ ፡ ነገር ግን ኩሩና ለክብሩ ሟች የሆነውን ሕዝቧን (በሰሜንም፣ በደቡብም፣ በምስራቅም፣ በምዕራብም ያለውን) ለአንድ ዓላማ እንዲሰለፍ፤ ለክብርና ሉዓላዊነቱ በሙላት መከበር እንቅፋት የሆነበትን ድህነት ለማሸነፍ በሚያስችለው መስመር ላይ በጋራ ለመቆም የሚግባባበትን፤ ተግባብቶም ወደ ተግባር የሚገባበትን ዕድል ፈጥሮላታል፡፡
እናም ሃብት ላይ ተኝቶ ድህነትና ረሃብ ሊሆን የማይገባው የተቃርኖ ዓለም ነውና፤ አገር ያላትን እምቅ አቅም ለይቶና እንደየፈርጁ አልምቶ በመጠቀም ከድህነት መውጣት ይቻላል የሚለውን እምነት በሁሉም ዜጎች ማስረጽ ተቻለ፡፡ ማስረጽ ብቻም ሳይሆን በግብርናው፣ በኢንዱስትሪው፣ በማዕድን፣ በቱሪዝም፣… ዘርፎች ያሉ እምቅ አቅሞችን በመለየት ማልማትና መጠቀም እንደሚቻል በተግባር መግለጥ ተጀመረ፡፡ ለዚህ አንዱ ማሳያ ደግሞ ግብርናው ሲሆን፤ በተለይ ስንዴን አልምቶ ከራስ አልፎ ለሌሎች መትረፍ ሲቻል ስንዴ መለመን አይገባም የሚል እምነት ተይዞ ስንዴን በመስኖና በቆላማ አካባቢዎች በማምረት ጭምር እጅን በአፍ ያስጫነ ውጤት ማምጣት ተቻለ፡፡ በዚህም የአስቸኳይ ጊዜ የምግብ ተደራሽነትን በራስ አቅም ከመደጎም ጀምሮ፤ ከውጪ የሚገባ የስንዴ ምርትን በከፍተኛ ደረጃ ማስቀረት የተቻለበትን እውነት አስመልክቷል፡፡
በዘርፉ የተጀመረው ሥራ የበለጠ እየሰፋና እየተጠናከረ መሄዱ ደግሞ፤ አንደኛ፣ ሰፊ የሥራ እድል መፍጠር አስችሏል፡፡ ይሄ ደግሞ ወጣቱ አቅምና ጊዜውን በአልባሌ ጉዳዮች ላይ ከማዋል ይልቅ ለልማት በማዋል ራሱንም፣ ወገንና አገሩንም የሚጠቅምበትን እድል በመስጠት፤ ለገንዘብ ሲል ራሱንም አገሩንም አደጋ ውስጥ እንዲከትት ከውጪ ሆነው ለሚነዱት የጥፋት ኃይሎች ተገዢ እንዳይሆን አድርጎታል፡፡ ይሄን መልካም ጅምር ማስፋትና ማጽናት ከተቻለ ደግሞ ውጤቱ ከዚህም የሚልቅ ለመሆኑ እሙን ነው፡፡
በሌላ በኩል፣ የስንዴ ልማት ሥራው አገር ከውጪ የምታስገባውን ስንዴ በአገር ውስጥ አምርታ እንድትሸፍን ያስቻለ ሲሆን፤ ይሄም በአንድ በኩል ስንዴን ለመግዛት የሚወጣውን የውጪ ምንዛሪ የሚያስቀር፤ በሌላ በኩል አርሶ አደሩ ለሚያመርተው ምርት ተገቢውን ዋጋ እንዲያገኝ እና ለላቀ ምርታማነት እንዲነሳሳ ያደረገው ሆኗል፡፡ የዚህ አንዱ ማሳያ ደግሞ ስንዴን በራስ አቅም አምርቶ የራስን ፍላጎት ከመሸፈን ባሻገር፤ በመሰል ችግር ውስጥ ለሚገኙ የጎረቤት ሀገራት በሽያጭ ማድረስ የሚቻልበትን እድል ታሳቢ ያደረገ ህልም ተይዞ ተግባራዊ እንቅስቃሴ መጀመሩ ነው፡፡ ይህ ደግሞ በአንድ በኩል የውጪ ምንዛሪን ከማዳን አልፎ የውጪ ምንዛሪን ወደማስገኘት መሸጋገር እንደሚቻል የሚያሳይ ሲሆን፤ በሌላ በኩል ኢትዮጵያ ከተረጂነት ተላቅቃ ራስን መቻልና ለሌሎችም መትረፍ እንደሚቻል ምሳሌነቷን በተግባር የገለጸች አገር በመሆና ከፍ ያለ የገጽታ ግንባታ ስዕል የሚፈጥርላት ነው፡፡
እነዚህ እውነቶች እንደተጠበቁ ሆነው ግን፤ ስኬታማው የስንዴ ልማት ጉዞው በምግብ ራስን ከመቻል፣ የውጪ ምንዛሪን ከማዳን፣ የሥራ ዕድል ከመፍጠርና የውጪ ምንዛሪን ከማስገኘት ከፍ ያለ ትርጉም የሚሰጥ ነው፡፡ ይሄውም ኢትዮጵያ ሉዓላዊነትና ክብሯን በዐውደ ውጊያዎች ብቻ ሳይሆን በልማት መድረኮች ላይም ፈርጥማ በመውጣት ለሉዓላዊነቷ የምታነሳቸውን ክንዶች ዘርፈ ብዙና በኢኮኖሚውም ፈርጥመው የሚገለጹ እንዲሆኑ የሚያስችላት ነው፡፡ በዚህም በጦር ዐውዶች፣ በዲፕሎማሲውና በሌላውም ከፍ ብላ በታየችባቸው መስኮች እንዳደረገችው ሁሉ፤ ድህነትና ረሃቧን ተጠቅመው በርዳታና ድጋፍ ስም እጅሽን እንጠምዝዝ፤ ሉዓላዊነትሽን ተዳፍረን እንዘዝሽና እኛ እንወስንልሽ የሚሏትን ኃይሎች ቆም ብለው እንዲያስቡ፤ አደብ እንዲገዙና፤ ከኢትዮጵያ ጋር የሚኖራቸው ግንኙነት በእጅ ጥምዘዛ ላይ ሳይሆን በጋራ ተጠቃሚነት ላይ የተመሠረተ ትብብር ሊሆን እንደሚገባው የሚገነዘቡበትን አውድ የሚፈጥርላት ነው፡፡
መረጃዎች እንደሚያሳዩት ደግሞ፤ መስኖ በመጠቀም በ2015 በ1ነጥብ3 ሚሊዮን ሄክታር መሬት 52 ሚሊዮን ኩንታል ስንዴ በመስኖ፥ 101 ሚሊዮን ኩንታል በመኸር በድምሩ 153 ሚሊዮን ኩንታል ስንዴ ለማምረት ግብ ተጥሎ እየተሠራ ይገኛል፡፡ ከሰሞኑም ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ፣ በሱማሌ ክልል በመኸር እየለማ ያለውን ስንዴ ከመጎብኘት ጎን ለጎን፤ ሀገራዊ የበጋ መስኖ ስንዴ ማስጀመሪያ ይፋ ባደረጉበት ወቅት የታየውና የተሰማውም ይሄው እውነት
ነው፡፡ እንደ ጠቅላይ ሚኒስትሩ ንግግር፤ የ2015 የበጋ ስንዴ ልማት በይፋ ሲጀመር ኢትዮጵያ እና ኢትዮጵያውያን በስንዴ ራሳቸውን ከመቻል አልፎ ወደ ውጭ ለመላክ የሚችሉበትን አቅም የሚፈጥር ነው፡፡
ይሄ ሊሆን የማይችል የሚመስለው እውነትም በዚህ ዓመት ወደ ተጨባጭ እውነት የሚለወጥ ሲሆን፤ ይህ እንዲሆንና ለሂደቱ ስኬታማነት አመራሩና ባለድርሻ አካላት በቁርጠኝነት ሊሠሩ የተገባ ነው፡፡ ምክንያቱም ሥራው የኢትዮጵያ ታሪክ የሚቀይር እንደመሆኑ፤ ይህ ታሪክ የሚቀየረው ደግሞ በልጆቿ ላብ በመሆኑ ነው፡፡ እየለማ ያለው ስንዴም አስቀያሚ የነበረውን የኢትዮጵያና የስንዴ ታሪክ እጥፋት (ለውጥ) ማሳያ ነው። በዚህ መልኩ ከተሠራ እና ውጤቱን ማስቀጠል ከተቻለ ደግሞ፤ ኢትዮጵያ ከልመና ወደ መስጠት፤ ከመግዛት ወደ መሸጥ፤ ከድህነት ወደ ብልጽግና መሸጋገር ብቻ ሳይሆን፤ በድጋፍ ስም ከሚጫንባት ቀንበር ራሷን ማላቀቅ እና የዜጎቿን ክብር፣ የራሷንም ሉዓላዊነት አስጠብቃ መጓዝ የምትችልበትን ፈርጣማ አቅም ይፈጥርላታል፡፡
በየኔነው ስሻው
አዲስ ዘመን ጥቅምት 2 ቀን 2015 ዓ.ም