እዛ ብቻ አይደለም፤ አፍሪካም አባቶች አሏት። ለዛውም የደለበ ታሪክ ያላቸው፤ ለአፍሪካ ርእይ የሰነቁ፤ ስለ አፍሪካ የወደቁ፤ ስለ አፍሪካም ሲሉ ህይወታቸውን ሳይቀር አሳልፈው የሰጡ፤ ቅኝ ገዢነትነትን አምርረው የተጠየፉና የጸረ ቅኝ አገዛዝ ትግል ያካሄዱ፤ የነጮቹን ”ጨለማዋ አህጉር” ትርክትን ከስሩ ለመገልበጥ ሌት ተቀን የተጉ። አህጉሪቱ ከቅኝ ገዢዎች የግፍ አገዛዝ ነፃ እንድትወጣ በፋና ወጊነት የታገሉ፤ ችጋር፣ እረሃብ፣ በሽታ፣ ድንቁርና … እንዲወገድ የለፉ፤ አስቀድመው የPan-Africanism ፍልስፍናን ያቀነቀኑ፤ የNegritudeን (የጥቁርን ህዝብ የተወሳሰብ የስልጣኔ፣ ባህል፣ ምጣኔ ሀብት፣ ማህበራዊ ዋጋ ያለው ሲሆን የሰብዓዊ መብት ጽንሰ ሃሳብን የያዘ ነው) ርእዮት መሰረት ያስያዙ።
በኒው ዮርክ የኢትዮጵያ አምባሳደር የነበሩት ሀዲስ አለማየሁ ያፈለቁት፣ በቀዳማዊ ኃይለሥላሴ በኩል አልፎ በአፍሪካ መሪዎች ይሁንታን ያገኘውና በአፍሪካ የመጀመሪያው የሆነው ዓለም አቀፍ ድርጅት (የአፍሪካ ኢኮኖሚክ ኮሚሽን)ን በአዲስ አበባ የመሰረቱት (ለቅኝ ገዥዎች አልበገር ያለችውን ኢትዮጵያን ጨምሮ ላይቤሪያ፣ ጋና፣ ሞሮኮ፣ ሱዳን፣ ቱኒዚያና ግብጽ ናቸው) ይህንኑ ራእያቸውን ለማሳካት መሆኑን ማስታወስ ተገቢ ነው።
ይህ ተቋም ሲመሰረት ”የአፍሪካን ኢኮኖሚያዊና ማህበራዊ ለውጥ ለማፋጠንና አንድነታቸውን ለማጎልበት በስራ ዕድል ፈጠራ፣ ቴክኖሎጂ ሽግግር፣ በሰው ኃይል ልማትና በአቅም ግንባታ ስራዎች ላይ ድጋፍ ለማድረግ ያለመ ነው” የሚለው ዋና አላማው እንደሆነም መገንዘብ ጠቃሚ ነው።
ድርጅቱ የምስረታውን 60ኛ ዓመት ሲያከብር ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር አቶ ደመቀ መኮንን እንዳሉት፤ የአፍሪካ ኢኮኖሚክ ኮሚሽን አፍሪካዊያን በኢኮኖሚ፣ በማህበራዊና በሰላም ጉዳዮች ውጤታማ ትብብር እንዲኖራቸው አግዟል። … የአፍሪካ ኀብረት አጀንዳ 2063 እና የ2030 ዘላቂ የልማት ግቦች እንዲፈጸሙ የአፍሪካ ኢኮኖሚክ ኮሚሽን በፖሊሲ የተመሰረተ የፋይናንስ፣ የቴክኒክና የአቅም ግንባታ ድጋፍ እየሰጠ፤ በስራ ዕድል ፈጠራ፣ በአረንጓዴ ልማት፣ ለአፍሪካ ሰላምና የዴሞክራሲያዊ ስርአት ግንባታ፣ በውጤታማ የፋይናንስና የተፈጥሮ ሐብት አስተዳደር እንዲሁም በቀጣናዊ ሰላም ማስፈን የበኩሉን አስተዋጽኦ እያደረገ ይገኛል።
የሚታወቁትን ለመጥቀስ ያህል፣ ”የአፍሪካ አባት” የሚል ማህበራዊ ማእረግን የተጎናፀፉት ቀዳማዊ ኃይለሥለሴ፣ ክዋሜ ንክሩሁማ፣ ጆሞ ኬኒያታ፣ ጋርቬይ፣ የታንዛኒያው አባት ሙዋሊሙ ጁሊዬስ ኔሬሬ፣ ሴዳር ሴንጎር … ወዘተርፈ ሁሉ የዘመናዊት አፍሪካ መስራች አባቶች ናቸው። በመሆኑም፣ ከላይና ከታች የጠቀስናቸውን አፍሪካዊ ተቋማት ትተውልን ሄደዋል።
የአጼ ኃይለሥላሴና ክዋሚ ንክሩሃማን ጨምሮ ሌሎች የአፍሪካ ታላላቅ መሪዎች ባደረጉት ታላቅ ጥረት እንደ ጎርጎሮሲያኑ አቆጣጠር ግንቦት 1963 የ32 ነጻ አገራት መሪዎች በኢትዮጵያ መዲና አዲስ አበባ ላይ በመሰብሰብ የአፍሪካን የመጀመሪያውን አህጉራዊ ተቋም (”የአፍሪካ አንድነት ድርጅት” በሚባል ይታወቅ የነበረውን ማለቴ ነው) ማቋቋማቸውና ተቋሙ አፍሪካን ይታደግ ዘንድ አላማ ይዘው መነሳታቸው በራሱ ከበቂ በላይ ማሳያ ነው። ዝርዝሩ ብዙ ነውና ወደ ጉዳያችን እንመለስ።
ምንም እንኳን፣ አህጉሪቷ በ“ተፋላሚ ወገኖች” ብራንድ ብትታወቅም፣ አንድ ቀን (በቅርቡ) ከዚህ አይነቱ አዙሪት ውስጥ ትወጣለች፣ ከተጣባት ደዌ ትላቀቃለች …. የሚለው የበርካታ አፍሪካዊያን ተስፋ ነው። እውነትም ያ ጊዜ ደግሞ አሁን ይመስላል። ከጊዜዎች ሁሉ ”አሁን” ለአፍሪካ ወሳኝ ጊዜ ነው። አሁን የተደቀነባትን ዘመናዊ ቅኝ አገዛዝ ወይ መቀበል፤ አለያም አሽቀንጥሮ መጣል።
አዎ፣ ዘመናዊ ቅኝ አገዛዝ አይኑን በጨው አጥቦና አፍጥጦ፤ ጥርሱን አግጥጦና ጦሩን ሰብቆ መጥቷል። መምጣት ብቻም አይደለም የአልሞት ባይ ተጋዳይነቱን ከጀመረ ሰንብቷል። በ”የውጭ ጉዳይ ፖሊሲ”ዬ ያልተፃፈ ሕግ አፍሪካን ሊቀራመትና መቅኔዋን ሊመጠምጥ ያለ የሌለ ኃይሉን አሰልፏል። ቢለመን፣ ቢዘከር፤ ቢገሰፅ፣ ቢገፈተር … በፍፁም ሊገባው አልቻለምና ንክች ያባ ቢላዎ ልጅ ብሎ በር ላይ ተገትሯል። ታዲያ የዚህ መፍትሄው ምንድነው?
ከመፍትሄው በፊት፣ ዘመናዊ ቅኝ አገዛዝ አይኑን አፍጥጦ፣ ጥርሱን አግጦ … መጥቷል ስንል ያለ ምክንያትና መረጃ ሳይሆን፤ በርካታ ምክንያቶችንና መረጃዎችን ይዘን፣ ለምሳሌ ያህልም፣ በዚህ በአንድና ሁለት ዓመት ውስጥ አሜሪካ ከ40 በላይ የሚሆኑ አገራት ላይ የኢኮኖሚ ማእቀብ መጣሏ (ኢትዮጵያም ከ”አጎዋ” መታገዷን ልብ ይሏል)፤ እንዲሁም፣ ትንሽ እንኳን ይሉኝታ በሌለው ሁኔታ አገራት ጉዳይ ላይ ጣልቃ የመግባቷ፤ ገብታም (እንደ ለመደችው ሁሉ – ሶሪያ፣ አፍጋን፣ ሊቢያ …ን ያስታውሷል) አፈራርሳ ለመውጣት እያለከለከች መሆኗን ጠረጴዛችን ላይ በማስቀመጥ ነው።
ሰሞኑን የፈረንሳዩ መሪ በ”ፍራንስ 24” ቲቪ መስኮት ብቅ ብለው 14 የአፍሪካ አገራት ቅኝ የገዛኋችሁን ዓመታት ወጪዬ እንደ እዳ ተቆጥሮ እዳችሁን ልትከፍሉኝ ይገባል በማለት ያስተላለፉት መልእክትም እዚህ ጋር ለታሪክም ቢሆን ሊጠቀስ (ምንም እንኳን ጉዳዩ መሳቂያ መሳለቂያ ቢያደርጋቸውም፣ የአፍሪካ አካሄድ የፈጠረባቸው ከብስጭትም ያለፈ ብሽቀትን ያመላክታል) ይገባል።
የዚህ መፍትሄው ያው ሁሌም እምንደሚባለው፤ ታሪክም ልምድም እንደሚያስተምረው አንድነት ጥንካሬ ነው (Unity Is Strength)። ዩኤስ ይህንን ሁሉ ታድርግ እንጂ፣ የአሁኑ ወቅት የአፍሪካዊያን ትብብርና አንድነት፤ የዩኤስን ጫና በጋራ ለመቋቋም እያደረጉት ያለው ርብርብ ተስፋ ሰጪ ነውና አፍሪካ ወደ ዘመናዊ ቅኝ አገዛዝ ዘመን የመግባቷ ጉዳይ በመርፌ ቀዳዳ የመሹለክ ያህል ነውና እዳው ገብስ ነው።
በመሆኑም፣ አሁን ከመቸውም ግዜ በላይ የአፍሪካዊያን አንድነት ያስፈልጋል። ከምን ግዜውም በላይ ለአፍሪካዊ ችግር አፍሪካዊ መፍትሄን ማቀንቀን የግድ ይላል። ከምን ግዜውም በላይ የአህጉሪቷ መሪዎች አፍ ከልብ ሆነው ሊናገሩ፣ ”አይሆንም”፤ ”እምቢ” ሊሉ ይገባል። የተናጠል ጉዞ የትም አያደርስምና “በቃ” ወይንም “ኖ ሞር” ማለት ካለባቸው ጊዜው አሁን ነው። ይህ ካልሆነ፤ ይህን ካላደረጉ… ”መጪው ጊዜ ለአፍሪካ ብሩህ ነው!!!” ማለት አይቻልም።
ሁሉም እንደሚመሰክረው፤ ባለፈው አመት የአሜሪካው ”ዎል ስትሪት ጆትርናል” (ለምሳሌ እንኳን ”U.S.-China Tech Fight Opens New Front in Ethiopia” (ሜይ 23 2021) በሚል ርእስ የወጣውን ፅሁፍ ይመለከቷል) እንደ ዘገበው ሃያላኑ የአፍሪካን ጦርነት ኢትዮጵያ ላይ እያካሄዱ ነው። (ይህንን ማብራራት የሚጠበቅ ስለማይሆን እንዝለለውና ወደ አጠቃላይ አፍሪካ እንመለስ።) እዚህ ላይ አንድ የተለመደ፣ ግን ደግሞ ወሳኝ የሆነ ጥያቄ እናንሳና ለጥያቄው ማብራሪያ እንስጥ። ”ለምን?”
እንደሚታወቀው አፍሪካ ድንግል ነች። ዲያመንዱ ከአፍሪካ ነው፣ ወርቁ፣ ቡናው ….፣ ሁሉ ከአፍሪካ ነው። ታላቁ ተቃርኖ የሚሆነው ድህነቱም ያለው እዚሁ አፍሪካ የመሆኑ ጉዳይ ነው። ይህ ብቻ አይደለም፤ East African Bottling Share Company (EABSC) የሚባለው ዓለም አቀፍ የንግድ ተቋም እንኳን አፍሪካ ምን ያህል ለኮካ ኮላ ምርቶችና ግብይት አዋጪ እንደሆነች ያመለከተ ሲሆን ከአፍሪካም በተለይ ኢትዮጵያን የሚደርስባት እንደ ሌለ ”Africa is an important market for Coca- Cola as it fights a campaign to increase per-capita annual consumption. Nowhere is this truer than in Ethiopia.” በማለት መግለፁንም በሌላኛው ጎኑ ተፈላጊ ይሆናል።
ይህንን ሁሉ ስናይ አፍሪካ እንደ አጠቃላይ፣ በተለይም አገራችን ምን ያህል የውጭ ባለ ሀብቶችን እየሳበች እንደሆነ በግልፅ እንረዳለን። ታዲያ ቤት በኩል፣ የፖለቲካ አለመረጋጋቱ፣ የኋልዮሽ ጉዞው … ወዘተርፈ … በየት በኩል። እናም አፍሪካ ከዚህ መውጣት አለባት የሚለው የዚህ ፅሁፍ ምክረ ሀሳብ ሳይሆን ድሮም ሲባል፣ በመስራች አባቶችም ሲመከር ነበርና በጉዳዩ ላይ ወገብን በመቀነት አስሮ መስራት የአሁኑ ዘመን መሪዎች የመሪነት ድርሻ ይሆናል።
ግራም ነፈሰ፣ ቀኝም ነፈሰ …. አፍሪካ የድሮው አልበቃ ብሎ እንደ ገና ወደ ዘመናዊ ቅኝ አገዛዝ ጭለማ ዘመን ውስጥ መግባት አለባት ብሎ አፍሪካዊያን ፊት ቆሞ የሚናገር ተስፋ የቆረጠ ካልሆነ በስተቀር ደፋር ሰው አይገኝም። ቅኝ መገዛቱ መቀጠል አለበት ብሎ የሚከራከር ማንም አፍሪካዊ የለም። የተፈጥሮ ፀጋዋም ሆነ ሰው ሰራሽ ሀብቷ በባእድ መበዝበዝ አለበት ብሎ የሚያምንም ሰው አይኖርም። ስለዚህ ሁሉም የሚስማማበትን፣ ሰርቶ የመለወጥን ጉዳይ ማንም፣ በተለይም አመራሩ ቸል ሊለው አይገባም። ማለትም፣ የዘመናዊት አፍሪካ መስራች አባቶችን ራእይ ማስቀጠል የግድ ይሆናል ማለት ነው።
እርግጥ ነው፣ አንዳንድ የአፍሪካ ጉዳዮችን ለተከታተለ ጉዳዩ ተስፋ ሁሉ ሊያስቆርጥ ይችላል። እንኳን የዘመናዊት አፍሪካ መስራች አባቶችን ራእይ ለማስቀጠል ቀርቶ እራሷ አፍሪካም ስለ መቀጠሏ ያጠራጥራል። ይህንን ስንል ሟርት አይደለም፤ አንድም በአፍሪካዊነታችን፣ ሁለትም አፍሪካ በመፈንቅለ መንግሥት ላይ መፈንቅለ መንግሥት እሚካሄድባት ጉደኛ አህጉር ስለ መሆኗ ”የአይን ምስክር” በመሆናችን ነው።
ይህ በመንግሥት ግልበጣ ላይ የመንግሥት ግልበጣ ጉዳይ የእሩቅ ታሪክ የሆነና ነገር ለማጣፈጥ እዚህ የተደነቀረ ሳይሆን፤ ሰሞኑን ቶማስ ሳንካራ ሲመራት በነበረች አገር (ቡርኪና ፋሶ) የሆነውና፤ መንግስት ገልብጦ ቁጭ ያለውን አካል ሌላ ገልባጭ መጥቶ ገልብጦት ቁጭ ማለቱ ነው። (ነገሩ አንዳንዴ የልጆች ጨዋታ ሁሉ ይመስላል፤ የዛሬ ልጆች ከዚህ የተሻለ ይጫወታሉ ካልተባለ በስተቀር። የአፍሪካ ህብረትም በሕጉ መፈንቅለ መንግስትን ይኮንን እንጂ በተግባር በፌጦ ተውጧል።)
አፍሪካ ይህ ሁሉ – ከላይ የጠቀስናቸው መልካም አጋጣሚዎችና እድሎች፣ ይህ ሁሉ ተፈላጊነትና ተመራጭነት ይኑራት እንጂ እራሷን በሯሷ ጠልፋ እየጣለች እንጂ ወደ ፊት ስትራመድ ለማየት አዳጋች እየሆነ ነው። ከእድሎቿ ፈተናዎቿ አመዝነው እዚ እሳት፣ እዛ እሳት፣ እዚም እዛም እሳት …. መሆኑ ነው እየታየ ያለው።
ዛሬ አፍሪካ ውስጥ የቱ ጋር ሰላም እንዳለ ፈልጎ ለማግኘት ያስቸግራል። በመሆኑም ከዚህ መውጣት ያስፈልጋል። ድህነትን ተረት ማድረጉ ቢከብድ እንኳን መቀነስ የግድ ይሆናል። 1.4 ቢሊዮን ላይ ያለው የህዝብ ቁጥር በ2050 2.5 ቢሊዮን መድረሱን ከወዲሁ አውቆ መስራት ብልህነት ነው። በግሉ ዘርፍ ያለው ሀብት ቀጫጫ መሆኑን ($2.1 ትሪሊየን) ተገንዝቦ ለማሳደግ መጣር ይገባል። ሙስናው፣ ሰብአዊ መብት ጥሰቱ፣ ስራ አጥነቱ (ከ42 ሚሊዮን በላይ ደርሷል)፤ መፈናቀልና ስደትን …. በአይነትም በመጠንም ከተቻለ መወገድ፣ ካልተቻለ መቀነስ አለባቸው።
ቅጥ የለሹ ፖለቲካ ሊሰለጥን ይገባዋል። እርስ በእርስ መጋደል ለ21ኛው ክ/ዘ የማይመጥን መሆኑን መገንዘብ ጠቃሚ ነው። ከ40 ሚሊዮን በላይ አፍሪካዊያን በከፋ ድህነት ውስጥ መሆናቸውን የመሪዎች ራስ ምታት ሊሆን ይገባል። እንደ አንድ አህጉር የጋራ ራእይ ያስፈልጋል። ለአጀንዳ 2063 መሳካት አፍ ከልብ ሆኖ መስራት ይጠበቃል። ቋንቋችን እንደ መስራች አባቶቻችን ”እኛ አፍሪካዊያን …” እንጂ ”እኔ …”፣ ”እኔ …” ሊሆን አይገባውም። ተቋማት እንደነ ኤዥያን (ASEAN) ሊጠነክሩ ይገባል።
ባጠቃላይ ሲታይ ተስፋ አለን። እንደገና የቀድሞው ዘመን ‹‹አፍሪካን መቀራመት›› አጀንዳ እንደሚመክን ተስፋ አለ። በተለይ ከምስራቁ ዓለም ጋር እጅ ለእጅ የመያያዙ ጉዳይ እየተባለ ባለው መሰረት ከሄደ … ምንም ጥርጥር የለም … አፍሪካ ተስፋ አላት። መጪው ዘመኗም ብሩህ ነው!!! ። እስከዛው ቦብ ማርሌይ Africa Unite ያለውንና ሁሉም የሚስማማበትን እኛም እንደግመዋለን – አፍሪካዊያን እንተባበር።
ግርማ መንግሥቴ
አዲስ ዘመን ሰኞ መስከረም 30 ቀን 2015 ዓ.ም