ሰላም የፍጥረታት ሁሉ ዋስትና ነው። ሕይወት ያለው ሁሉ በሰላም ውሎ ሲያድር ስለነገው መኖር መተማመንን ያተረፋል። ሰላም የነገዋን ጀንበር በድል ያሻግራል፣ የትውልድ ተስፋን ይቀጥላል፣ የሕይወት ትርጉምን ያደምቃል። ብ ዙሀን ያ ለ ሰ ላም ዓ ለም ሁ ሉ ም ንም ስለመሆኑ በአንድ ቃል ይስማማሉ። እውነት ነው። ዓለም ያለ ሰላም ምንም ነች ምንም።
አገራችን ለዘመናት በጦርነት ስትታመስ ቆይታለች። የሰላም ትርጉሙ ባልገባቸው ኃይሎች ጠብ አጫሪነትም ህዝቦቿ ሲያልቁ፣ ንብረታቸው ሲወድምና ለስደት ሲዳረጉ ኖረዋል። ይህ የታሪካችን ደማቁ ጠባሳ ነው። የጦርነት ሀሩር ያሳረፈብን ጉዳት ስማችንን ከርሀባችን ገጽ ቀጥሎ በክፉ ሲያስነሳ፣ ሲያስነብበው ታይቷል።
ኢትዮጵያ ባህር ተሻግረው ከመጡት ጠላቶቿ ባለፈ ከጉያዋ ወጥተው፣ ከዕቅፏ ተነጥለው በወጓት ልጆቿ አይረሴ ታሪኮችን አልፋለች። ጀግንነት ከጥንት የወረሰችው ታሪክ ቢሆንም ስለ ሰላም ባላት አቋም በጎውን እያስቀደመች፣ ክፉ መንገዶችን ስታሳጥር ቆይታለች።
ስልጣን መራሹ የወያኔ ስርዓት ዙፋኑን ‹‹እምቢኝ›› ብሎ ከተቆናጠጠበት ወንበር ከተወገደ ማግስት የመጀመሪያ ምርጫው የጦርነት ሜዳ ሆኗል። ሁሌም ‹‹እሞትልሀለሁ›› ሲል የሚገድለውን የትግራይ ህዝብ ለጦርነት ማግዶም ለሰላም ያለውን ንቀት በግልጽ አሳይቷል።
እነሆ ! የጦርነቱ እሳት ተጭሮ በርካታ ንጹሀን በነዲዱ መቃጠል ከጀመሩ ሁለት ዓመታት ተቆጥረዋል። በነዚህ ዓመታት ለሰላም የተዘረጉ እጆችን ሲያጥፍ የቆየው እኩይ ቡድን ከስልጣን ባሻገር ለሚያልመው ተስፋ ቢስ ዓለም የብዙሀንን ነፍስ እንደ ግብር ጭዳ ማድረጉን ቀጥሏል።
ሰላም ናፈቂው የትግራይ ህዝብ የሚሻውን እፎይታ ከተነጠቀ ወዲህ ልጆቹን ለጦርነት እንዲያዘምት ተገዷል። ስለምን ሲል የመጠየቅ መብቱን የተነፈገው ወገን በጥቂቶች ስግብግብነት ማንነቱ ተሰርቆ የችግሮች ሁሉ ሰለባ ከሆነ ጊዚያት ተቆጥረዋል።
አሁንም ካለፈው ክፋቱ የማይማረው የጥፋት ቡድን ህጻናትን ከእናቶቻቸው፣ ወንዶችን ከባሎቻቸው፣ ተማሪዎችን ከትምህርት ገበታቸው እየነጠለ በጦርነቱ እሳት መማገዱን ይዟል።
እነሆ! ባሳለፍናቸው የጦርነት ዓመታት የለመለሙ ተስፋዎቻችን ከስመዋል። ያደጉ ሰብሎቻችን ተቃጥለዋል። ከከፍታ የደረሱ፣ ትውልድን የሚቀርጹ የትምህርት ተቋሞቻችን ትቢያ አመድ ሆነዋል። ከምንም በላይ ጦርነቱ ተተኪ የሌለውን የሰው ልጆች ህይወት አጭዶብናል። በዚህ አይተኬው ትውልድ ያለጊዜው ባክኗል። ውድ አገራችንም በኢኮኖሚው ማደግ፣ መመንደግ ሲገባት በእጅጉ ከስራለች፤ ኮስምናለችም።
ይህ ሁሉ እውነታ የሰላም አለመኖር ማሳያ ነው። ሁሌም በሰላም ውስጥ ያሉ እሴቶች በክፋት ሀይሎች በተነጠቁ ጊዜ ሕይወት ያለወጉ ይመነዘራል፣ ያለመንገዱ አቅጣጫውን ይስታል። በዚህም የዓለም መሰረት ይናወጣል፣ የፍጥረት ህልውና ይናጋል።
ተደጋግሞ እንደሚነገረው ጦርነት የሰው ልጆች መቅሰፍት ነው። በጦር የተጀመረ መንገድ ኪሳራው የበዛ፣ ጨለማው የደመቀ ይሆናል። በጦርነት መልካም ውጤት አይገኝም። በጦርነት ዕቅድ ዓለም ሰምሮ፣ መልካም ህይወት ተቀምሮ አያውቅም። ጦርነት ያወድማል፣ ትውልድ ይጨርሳል፣ ታሪክን ከቅርስ፣ አገርን ከህዝብ ይነጥቃል። ሰላም ባጣ አገር የሚኖሩ ነፍሶች ዕንቅልፍን አያውቁም፣ ዘርቶ ማጨድ፣ ወልዶ መሳም፣ አስተምሮ ለወግ ይሏቸውን እውነቶችም ፈጽሞ አያልፉባቸውም።
ጦርነት በተጫረባቸው አገራት ያሉ ህዝቦች ዕጣ ፈንታቸው ሞትና ስደት ነው። ማን ከማ ጋር እንደተጋጨ በወጉ የማያወቁ ንፁሀን ጭምር የነፍስ ዋጋ ይከፍላሉ። የስደት መንገድ ይጀምራሉ። በዚህ መሀል ህጻናትና ሴቶች፣ ወጣቶችና አረጋውያን ሰው የመሆን ህልውናቸውን ያጣሉ። ባገራቸው የሚያገኙትን ክብር ተነፍገው የሰው አገር አፈር ይበላቸዋል። ታሪካቸው በበረሀው አሸዋ ይዋጣል። ስምና ዝናቸው በባህሩ ሞገድ ይሰጥማል።
አሁን አገራችንና ህዝቦቿ በሰላም እጦት አየተፈተኑ ነው። የዚህ ክፉ ጽንፍ ጭራም ከአንዳንድ ዓለም አገራት ጋር የነበረውን መልካም ዲፕሎማሲ ሳይቀር በጥቁር ጥላው ሸፍኖታል። ሰላም ወዳዱ የኢትዮጵያ ህዝብ ግን ሁሌም ለሰላም የሚዘረጋው እጁ አይታጠፍም። በተገኘው አጋጣሚ ሁሉ ስለሰላም አብዝቶ ይጮሀል። ድምጹን አጉልቶ ይዘምራል። ሰላም ህይወቱና የመኖር ትልሙ መሆኑን ያውቃልና ከህልሙ ተገናኝቶ፣ ከእፎይታው ለማደር ሌት ተቀን በትኩረት ይተጋል።
ከጦርነቱ ማግስት አንስቶ የሰላም አማራጮች ሲቀርቡለት የቆየው አጥፊ አሸባሪው ትህነግ ቃሉን ከእርኩሰት ቆጥሮ በሰው ልጆች ህይወት ሲቀልድ ቆይቷል። ከሰላም ይልቅ ጦርነትን ምርጫው ሲያደርግም ስለሚጠፋው ክቡር ሕይወትና ስለሚወድመው በርካታ ንብረት አንዳች ስሜት አልነበረውም። በጦርነት ዕልፍ ወገኖች ሲያልቁ፣ ቤት ጎጆ ይናዳል። የትውልድ ተስፋ መክኖ የነገው ሕይወት ይጨልማል።
እንዲህ በሆነ ጊዜ ታሪክ ፈጥኖ ለመጥፋት፣ አገር በውድመት ለመፍረስ ትቃረባለች ። የክፉዎች ጥፍር በሰላ ቁጥር የሚቀደድ፣ የሚቦተረፈው ይበዛል፣ የሚዘረፍ የሚጠፋው ያይላል ። ይህ አጋጣሚ ዳር ሆነው ለሚያዩት ባዕዳን መግቢያ በር ከፋች ነው። ሁኔታውን የሚሹት የቅርብና የሩቅ ጠላቶችም በተፈጠረው ክፍተት ተጠቅመው የፍላጎታቸውን ለማድረሰ ያመቻቸዋል። አንዱን ከአንዱ እያጋጩ በሚያገኙት ውጤትም የረጅም ጊዜ ህልማቸውን ለመፍታት ዕንቅልፍ ይሉትን አይተኙም።
ይህ እውነታ ክፉ ልቦና ካላቸው እሳቤ ጋር ሲዛመድ ትርጓሜውን ይለውጣል። ከሰላም ይልቅ ጦርነትን ‹‹ይሁነኝ›› ለሚሉ ሁሉ የስልጣን ርካባቸውን ለማስፋት ፣ የአምባገነን ታሪካቸውን ለማርዘም ሰፊ ዕድል ይሰጣል። እንዲህ በሆነ ጊዜ ስልጣንን ያለወጉ የተቆናጠጡ ከርሳሞች የህዝብን ለቅሶ ለመስማት ጆሯቸው ይደፈናል። ምርጫቸው ጦርነት ብቻ ሆኖ የሰላም እጆችን ይገፋሉ። ዓለምን በአንድ የሚያስተሳስረውን ፍቅርም አጥብቀው ይረግጣሉ።
ስልጣን ወዳዱ አንጃ ቡድን እስካሁን የተሰጠውን የሰላም መንገድ ላለመቀበል ምክንያቶችን ሲደረድር ቆይቷል። በጦርነቱ በደረሰበት የመጨረሻ ኪሳራ ‹‹ሰላምን እሻለሁ ሲል ቢቆይም ወደ ህዝብ የደቀነውን አፈሙዝ ‹‹ይብቃኝ›› ሲል በተግባር አላሳየም። በተማጽኖው መሀል አስብቶ የሚያርደውን ህዝብ ለአፍታ ለመታደግ ፍላጎት አልታየበትም። አንደበትና ድርጊቱ ፊትና ጀርባ ሆኖ በተቃራኒ ሲጓዝ መክረሙን ድፍን ዓለም የሚያውቀው ሀቅ ነው።
እነሆ ! ሁሌም በአንድ ቃል የምንዘምረለት የሰላም ጥያቄ ቋጠሮው ሊፈታ ጊዜው ደርሷል። ዛሬም ለሰላምና ፍቅር እጁን የማያጥፈው የኢትዮጵያ ህዝብ በደልና ግፉን ለታሪክ ትቶ የሰላም እጁን ለመዘርጋት ተዘጋጅቷል። ከጦርነት እፎይታን፤ ከስደትና መፈናቀል በአገር መኖርን፣ ከክፋት ተግባራት ይልቅ መልካም ዝማሬን የሚሻው የአገራችን ህዝብ ሁሌም ለሰላም፣ ስለሰላም ሲባል ቅድሚያውን ይሰጣል። በህዝቦች አንድነትና ሕብረ ብሄራዊነትም ፈጽሞ አይደራደርም።
አዎ ! ስለሰላም የቀረቡ እጆች ዛሬም በሰፊው ተዘርግተዋል። ይህ ዋጋ የሚከፈለው ስለኢትዮጵያና ሰለሰላም ወዳዶቹ የኢትዮጵያ ህዝቦች ህልውና ሲባል ነው። ያለፈው የጦርነት ጠባሳ፣ ያደረሰው ግፍና መከራ በዋዛ ባይረሳም እኛ ግን ታሪክን ለጊዜው እውነታ እንተዋለን። እኛ ለሰላም የተዘረጉ እጆችን አናጥፍም። የሰላም ዝማሬን በለቅሶ ጩኸት አንቀይርም። ሰላም ታሪካችን ነው። ሰላም መለያችን ሆኖ ይቀጥላል።
መልካምሥራ አፈወርቅ
አዲስ ዘመን መስከረም 30 ቀን 2015 ዓ.ም