የኢሬቻ በዓል ከጥንት ጀምሮ የኦሮሞ ሕዝብ ሲያከብረው የኖረ የምስጋና በዓል ነው ። አባ ገዳ ጎበና ሆላ የቱለማ አባ ገዳና የኦሮሞ አባ ገዳዎች ሕብረት ፀሐፊና የኢሬቻ በዓል ሰብሳቢ እንደሚናገሩት ኢሬቻ የሚለው ቃል በራሱ ምስጋና፤ መስማማት፣ አንድነት፣ እርቅ ፣ማለት ነው። የገዳ ሥርዓት ባለበትና የኦሮሞ ሕዝብ በሚገኝበት ሁሉ ይከበራል።
በኢሬቻ በዓል ውስጥ የሚደረጉ የተለያዩ ሥርዓቶችም አሉ። የኦኮሌ ሥርዓት አንዱ ሲሆን ለመጀመሪያ ጊዜ የወለዱ ከብቶች ይመረቁበታል። ጊደሮች ወተታቸው ተጠራቅሞ፣ ግማሹ ተንጦ፣ ቅቤው ወጥቶ፣ ግማሹ እርጎ፣ ግማሹ አይብ ተደርጎ ቅንጬ ተሰርቶ፣ ዘመድ አዝማድ ተሰብስቦ ከተመረቁ በኋላ ይበላል።
ኢሬቻ ብዙ አይነት ቢሆንም ዋናዎቹ ሁለት ናቸው። ኢሬቻ መልካ (Irecha Melka) እና ኢሬቻ ቱሉ (Irecha Tullu ) ፤ኢሬቻ መልካ ፤በውሃ ዳርቻ ክረምት እንደወጣ ይከበራል። ይበልጡን ምድርን በዝናብ ያጠገበውን አምላክን በምስጋና የመዘከር በዓል ነው። ኢሬቻ ቱሉ ፤በተራራ ጫፍ ላይ በበጋው መሀል ይከበራል። ዝናብን በወቅቱ የሚሰጠውን አምላክ በበጋውም ወራት ለእንስሳቱ መልካሙን ዝናብ እንዲሰጥ እንስሳት እንዳይሞቱ ይለመናል። ይበልጡን የፀሎት በዓል ነው። ቢሆንም…ቡራኬው፤ ምስጋናው፤ ፀሎቱ በሁለቱም ኢሬቻ አይቀርም።
አንዳንድ ሰዎች ከፈጠራ ወሬም ሆነ ከሀሚት ተነስተው እንደሚሉት በአድ አምልኮ ማራመጃና ከክፉ መንፈስ ጋር የሚገናኝ አይደለም። በዓሉ ሲከበር ለተራራው ወይም ለወንዙ አይሰገድም። እነሱን ለፈጠረ ፤ አምላክ ነው የሚሰገደው። በኦሮሞ ባህል ልምላሜ እና ውሃ የአምላክ መንፈስ ማደርያ፤ ንፁህ የአምልኮት ስፍራ ነው ተብሎ ይወሰዳል። ለፀሎት ምቹ እና ሰላማዊ ቦታ ነው የሚል የፀና ዕምነት አለ። እናም በኢሬቻ መልካ በዓል የተፈጥሮን ኡደት ሳያዛባ ያስቀጠለ አምላክ ይመሰገናል። አምላክ ይከበራል፣ አምላክ ይመለካል።
በዓሉ የሚከበረው ታላቁ የወራት አውራ መስከረም ወር ላይ ነው ። በመሆኑም ኢሬቻ በክረምት ወራት ዘመዳማሞች በዝናብ እና በውሃ መሙላት ምክንያት ተራርቀው ሳይገናኙ ክረምቱን ስልሚያሳልፉ ውሃው ሲጎድል እግዚአብሄር ታረቀን፣ ምህረት አደረገልን፣ በውሃው መሙላት ምክንያት የተለያየን ቤተሰቦች እግዚአብሔር እንድንገናኝ አደረገን ብሎ ለፈጣሪው ምስጋና የሚያቀርብበት ከገዳ ሥርዓት አንዱ ነው ማለት ይቻላል። ክረምቱ ካለፈ በኋላ የወንዙ ሙላት ከጎደለ እሩቅ ያሉ ዘመዳማሞች ይገናኛሉ። በሌላ መልኩ ደግሞ የኢሬቻ በዓል ዘመን የሚለወጥበት ቀን ጭምር ነው። ኦሮሞ በእድሜያችን ላይ አዲሱን ዘመን ጨመርክልን ብሎ አምላኩን ያመሰግንበታል።
ኢሬቻ በዓል ዋቄፈና ከተባለውና ከጥንቱ የኦሮሞ ሕዝብ እምነት የፈለቀና ገና ሲወለዱና በዳዴ ከሚሄዱበት ጀምሮ ቋንቋ መናገር ሲጀምሩ ፈጣሪ ለሰው ልጆች የሰጠው ፀጋ ነው ይላሉም አባ ገዳ ጎበና ሆላ። ዋቄፈና የሐይማኖቱ ስም የእምነቱ ተከታይ ዋቄፈታ ተብለው እንደመጠራታቸው እንዲሁም ፈጣሪ አምላክ የሚመሰገንበት በመሆኑ ሐይማኖታዊ በዓልም ነው ኢሬቻ።
“ኢሬቻ ማለት ዋቃ (ፈጣሪ) ማለት ነው የሚሉት የኦሮሞ ታሪክ ምሁሩ ዲሪቢ ደምሴም ይሄን ከክረምት መውጫና ከበጋ መግቢያ ጋር ተያይዞ ለፈጣሪ ምስጋና ማቅረብን የተመለከተ የአባ ገዳውን ሃሳብ የሚጋራ ሃሳብ ያንፀባርቃሉ። ኢሬቻ የፈጠረውን ማመስገን ማለት ነውም ይላሉ። የአንትሮፖሎጂ ባለሙያዎችም ይሄንኑ ሃሳብ ይጋራሉ። ሁሉም ኢሬቻ ማኅበራዊ ደረጃ እና የእድሜ ልዩነት ሳይደረግ በፈጣሪው የሚያምን ሁሉ በአንድነት ወጥቶ ለዘመናት በጋራ ሲያከብረው የኖረ የኦሮሞ ሕዝብ የአደባባይ በዓል ነው። የገዳ ሥርዓት አካልም ነው።
ታሪክ ፀሐፊዎቹና የታሪክ ድርሳናት እንደሚናገሩትም ኢሬቻ የኦሮሞ የገዳ ሥርዓት መገለጫም ተደርጎ ይወሰዳል። የኢሬቻ በዓል ከ6 ሺ 660 ዓመት በፊት መከበር መጀመሩንም ያነሳሉ። ከዚህ ጊዜ አንስቶ በዓመት ሁለት ጊዜም ሲከበር ቆይቷል። የመጀመሪያው ክረምት መውጣትን ተከትሎ በውሃማ አካባቢዎች የሚከበርበት ነው። ሁለተኛው ደግሞ በበልግ ወቅት ግንቦትና ሰኔ ወራት ውስጥ በተራራማ አካባቢዎች ይከበራል። ይሄ አሁን አሁን እየተረሳ መጥቷል።
በዓሉ በአዲስ አበባ መከበር ከጀመረም ዘንድሮ አራተኛ ዓመቱን ይዟል። አዲስ አበባ ከተማ ላይ በዓሉን የማክበሩ ሂደት በ2012 ዓ.ም እንደ አዲስ አለመጀመሩና በተለያዩ ሁኔታዎች ተቋርጦ የቆየ መሆኑ ይወሳል። አንዱ ምክንያት የምስጋና በዓሉን ከበዓድ እምነት ጋር የሚያያይዝ የሰዎች አመለካከት ነበር ይላሉ። ለምሣሌ ቡና አንዳንድ ሰዎች በዘልማድ ቡና ማፍላት፣ ዛፍ ቅቤ መቀባት፣ ስለት ማግባት፣ ሽቶ ውሃ ውስጥ መወርወር ሲደረግበት ስለምናይ በዓድ አምልኮ ነው ይላሉ ። ነገር ግን ይሄ አይፈቀድም ።
በዚህ የተነሳም በዓሉ እውነተኛ ታሪክና ቱፊቱን በሳተ ትርጓሜ ምክንያት መከበር እንዳቆመ ይነገራል። በዓሉ በቢሾፍቱ ሆራ አርሰዲ ኃይቅ መከበር ከጀመረ በኋላም የጥፋት ኃይሎች አይን ማረፊያ በመሆን የግጭትና ሁከት ማእከል ለማድረግ ብዙ ተሞክሯል። ሩቅ ሳንሄድ በ2008 ወይም የዛሬ ሰባት ዓመት አካባቢ በዓሉ ሲከበር በነበረበት ወቅት የተፈጠረው ሁከት ጥሩ ማሳያ ነው። ሁከቱ መንግሥትን በተቃወሙ ወጣቶችና በመንግሥት ኃይሎች መካከል ግጭት በመፈጠሩ ወይም ልዩ የፖለቲካ ፍላጎት በነበራቸው የጥፋት ኃይሎች መሆኑ አያጠራጥርም።
የጥፋት ኃይሎቹ በሁከቱ በተኩስ፣ በአስለቃሽ ጭስ፣ በመረጋገጥ እና ገደል ውስጥ በመግባት በርካታ ፈጣሪያቸውን ለማመስገን የወጡ የበዓሉ ታዳሚዎች ሕይወት እንዲያልፍ አድርገዋል። የውጭና የሀገር ውስጥ ሚዲያዎች ዘግበውት እንደነበረው በሁከቱ ምክንያት የበዓሉ አከባበር ሥነስርዓት ተስተጓጉሏል።
የምስጋና በዓሉ ከዚህ በኋላ በነበሩት ዓመታት በቢሾፍቱ ሆራ አርሰዲ ኃይቅ ሲከበር እንዲሁም ባለፉት ሦስት ዓመታት በአዲስ አበባ ሲከበር የጥፋት ሃይሎች ያቀዱት አለመደገሙ ያስደስታል። ምክንያቱ ደግሞ አንደኛው በዓሉ በከተማዋ አስተዳደር ብርቱ ጥንቃቄ ተደርጎ በመከበሩ ነው።
ሁለተኛው ሕዝቡ ለፈጠራ ወሬዎችና ለአሉባልታ ወይም ልዩ የፖለቲካ ፍላጎት ላላቸው ክፍሎች ጆሮውን ባለመስጠቱ ነው። ሦስተኛው ምክንያት በዓሉን መላው ሕዝብ በዓሌ ነው ብሎ በመቀበሉ ነው። ለዚህ በአዲስ አበባ ባሉ ሁሉም ክፍለ ከተሞች ሕብረተሰቡ በነቂስ አደባባይ ወጥቶ ያከበረው መሆኑ በምሳሌነት ይነሳል። የሀገር ውስጥና የውጭ ቱሪስት መስህብ እንዲሁም የክልሉና የሀገሪቱ የማይዳሰስ ቅርስ ገቢ ከመሆኑ አንፃርም ፋይዳው ቀላል አልነበረም።
ለአብነት የኦሮሚያ ክልል ባህልና ቱሪዝም ቢሮ ምክትል ኃላፊ አቶ ሁንዴ ከበደ እንደሚናገሩት በ2014 ዓ.ም በአዲስ አበባ በተከበረው ኢሬቻ ሆራ ፊንፊኔ ወደ አምስት ሚሊዮን የሚጠጉ የሀገር ውስጥ ቱሪስት ተካፍለዋል። ይህ ለቱሪዝም ገቢ መጎልበት ከፍተኛ ፋይዳ አለው።
ከኢሬቻ ጋር ተያይዞ በቢሾፍቱ የተከበረው ሲደመርበት ገቢው ምን ያህል ከፍተኛ እንደሚሆን መገመት አያዳግትም። በአሁኑ ወቅት የኢሬቻ በዓል መከበር እየተጠናከረ ከኢትዮጵያ ባሻገር በተለያዩ የዓለም ክፍሎች ውስጥ የሚገኙ የኦሮሞ ብሔር አባላት በዓሉን በድምቀት ያከብሩታል።
በሆራ አርሰዲ ሐይቅ በየዓመቱ በዓሉ ሲከበር በሚሊዮን የሚቆጠሩ የሀገር ውስጥና የውጭ ቱሪስቶች ይታደማሉ። ለምሳሌ በ2010 ዓ.ም ከተማዋን የጎበኙ የአገር ውስጥና የውጭ ቱሪስቶች ቁጥር ከ2006 ዓ.ም ጋር ሲነፃፀር ከ260 ሺህ ወደ 343 ሺህ 861 አድጓል። ገቢው በቁጥር ቢጠቀስ በገቢ ደረጃም ከአራት እጥፍ በላይ ብልጫ አለው። ዘንድሮ መስከረም 21 ቀን 2015 በሚከበርበት በሀገራችን ዋና መዲና እንዲሁም ነገ መስከረም 22 ቀን 2015 በሚከበርበት ቢሾፍቱ ምን ያህል የሀገር ውስጥና የውጭ ቱሪስቶች እንደሚታደሙበት፤ ከነዚህም ምን ያህል ገቢ እንደሚገኝ አስቦ ማክበር ያለው ፋይዳ ቀላል አይሆንም። መልካም በዓል!
ሰላማዊት ውቤ
አዲስ ዘመን መስከረም 23 ቀን 2015 ዓ.ም