ትምህርት የሁሉ ነገር መሰረት ነው ሲባል ለአገር እድገት ከሚጫወተው ሚና እና ለሰው ልጅ አስተሳሰብ አድማስ መስፋት ከሚያበረክተው አስተዋጽኦ ጋር በማያያዝ ነው፡፡ በመሆኑም ከአገራት እድገትና ለውጥ ጋር ትምህርት እድገትም እየተለዋወጠ መጥቷል፡፡ በኢትዮጵያም ከአፄ ምኒልክ ዘመነ መንግሥት አንስቶ ዘመናዊ ትምህርት እንደተጀመረ ቢነገርም በቤተ እምነቶች አካባቢ ግን ማንበብና መፃፍ ከዚያም በፊት በስፋት ይካሄድ እንደነበር የታሪክ ድርሳናት ያመለክታሉ፡፡
ከ1900 በኋላ ደግሞ ዘመናዊ ትምህርት “ሀ” ብሎ በመጀመሩ ጥቂት ህፃናት የዘመናዊ ትምህርት ማግኘት ችለዋል፡፡ ይህም የተጀመረው በዳግማዊ ምኒልክ ትምህርት ቤት ነበር፡፡ ይህም ትምህርት ቤቱን በዘመናዊ ትምህርት ታሪክ ፋና ወጊ አድርጎታል፡፡ ቀጥሎም እስከ 1925 ዓ.ም ድረስ ባሉት ዓመታት በመላው አገሪቱ ሃያ የሚሆኑ ትምህርት ቤቶች ሊከፈቱ ችለዋል፡፡ ይሁን እንጂ የተማሪዎች ቁጥር ከስምንት ሺ የሚበልጥ አልነበረም፡፡
በአፄ ኃይለሥላሴ ዘመን በትምህርት ዘርፍ በርካታ ሥራዎች የተሠሩበትና ትምህርት ቤቶችም የተስፋፉበት በተቃራኒው ደግም በርካቶች ከትምህርት ገበታ በተለያዩ ምክንያቶች የተገለሉበት ዘመን ነበር፡፡
በደርግ ዘመነ መንግስትም የትምህርት ስርዓቱ በኃይለሥላሴ ዘመን በነበረው የቀጠለ ቢሆንም የራሺያ ኮሚኒዝም የተቀላቀለበት ነበር፡፡ ይህም ሆኖ ደርግ በአገሪቱ የተማረ የሰው ኃይል ለማፍራት በሚያስችል መልኩ ሲሰራ መቆየቱ ይነገራል፡፡ ለምሳሌ በመጀመሪያ ደረጃ ትምህርት ቤቶች ኑሮ በዘዴ፣ እርሻና እደ ጥበብ ነክ ነገሮች በካሪኩለም ተቀርፀው ይሰጡ ነበር፡፡
ከዚህም ባለፈ አንድ ተማሪ የሁለተኛ ደረጃ ትምህርቱን አጠናቆ ሲወጣ የቀለምም የሙያም እውቀት እንዲይዝ የሚደርጉ ትምህርቶች ይሰጡ ነበር፡፡ ከከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ተምረው የሚወጡ ተማሪዎችም መንግስት በሚመድባቸው ቦታ ሄደው የማገልገል ግዴታ ነበረባቸው፡፡ ይህም የተማረው ሀይል በሁሉም የአገሪቱ ክፍሎች ህዝቡን የሚያገለግልበት ዕድል በመፍጠሩ ለውጥ እንዲመጣ አድርጓል፡፡
የደርግ ዘመነ መንግስት በህዝባዊ ትግል ከወደቀ በኋላ አገሪቱን ማስተዳደር የጀመረው ኢህአዴግ አዲስ የትምህርት ስርዓት ቀርፆ ወደተግባር አስገብቷል፡፡ በዚህም ቀደም ብለው የነበሩት ትምህርቶች እንዲቀሩ አድርጓል፡፡ የመማሪያ መፅሐፍትም መንግስት በሚፈልጋቸው መልኩ የፓርቲውን የፖለቲካ ርዕዮተ ዓለም እንዲያስፈጽሙ በሚያስችል መንገድ የተቃኙ በመሆናቸው የትምህርት ጥራት በከፍተኛ ደረጃ እንዲወድቅ አድርጓል፡፡
ከዚህም ባሻገር ብዛት ላይ እንጂ ጥራት ላይ ባለመተኮሩ የትምህርት ጥራት ይበልጥ እንዲዘነጋ አድርጎት ቆይቷል፡፡ ከዚህም ባለፈ የመምህራን ትምህርት አሰጣጥ ትኩረት የተሰጠው ባለመሆኑ ብቁ ባለሙያዎችን ማፍራት አልተቻለም፡፡
ስለሆነም በኢህአዴግ ዘመን የነበረውን የትምህርት ስርዓት ለማሻሻል አዲስ ስርዓተ ትምህርት ተቀርፆ ወደ ሙከራ ትግበራ በ2014 ዓ.ም ተገብቷል፡፡ በአዲሱ ሥርዓተ ትምህርት የአደረጃጀት ለውጥ ተደርጓል፡፡ በዚህም የነበረው አደረጃጀት ቅድመ መደበኛ ሁለት ዓመት፣ አንደኛ ደረጃ ከአንደኛ እስከ ስድስተኛ ክፍል ስድስት ዓመት፣ መካከለኛ ደረጃ ሰባት እና ስምንተኛ ክፍል ሁለት ዓመት፣ እንዲሁም ሁለተኛ ደረጃ ከዘጠነኛ እስከ አስራ ሁለተኛ ክፍል አራት ዓመት እንዲሆን ተደርጓል፡፡
በ2015 ዓ.ም የትምህርት ዘመን ከቅድመ መደበኛ እስከ ስምንተኛ ከፍል አዲሱ ስርዓተ ትምህርት ሙሉ በሙሉ ተግባራዊ እንደሚሆን ትምህርት ሚኒስቴር አስታውቋል፡፡ በዘጠነኛ እና አስረኛ ክፍል ደግሞ የሙከራ ትግበራ በተመረጡ 80 ትምህርት ቤቶች የሚካሄድ ይሆናል፡፡
ይሄ አሰራር ቀድሞ የነበረውን የትምህርት አሰጣጥ የሚቀይረው ሲሆን ተማሪዎች በቂ የሆነ እውቀት ይዘው እንዲወጡ የራሱን አሻራ ያሳርፋል ተብሎ ይጠበቃል።እዚህ ጋር መስተዋል ያለበት ነገር አዲሱን የትምህርት ስርዓት በአግባቡ የተረዱ መምህራንን ማብቃት ወሳኝ ነገር መሆኑ ነው፡፡ መምህራን በስነ ምግባርና በእውቀት ማጎልበት ከተቻለ ውጤታማ ተማሪዎችን ማፍራት ይቻላል፡፡ ይህ ስራ ደግሞ ከአዲሱ የትምህርት ስርዓት ይጠበቃል፡፡
በአገሪቱ በሁሉም ክልሎች በሚገኙ ትምህርት ቤቶች መስከረም ዘጠኝ ቀን 2015 ዓ.ም ተከፍተው የመማር ማስተማር ሥራ ጀምረዋል፡፡ በልዩ ልዩ እና አስገዳጅ ምክንያቶች ሰኞ መስከረም ዘጠኝ ቀን 2015 ዓ.ም ትምህርት የማይጀምሩ ትምህርት ቤቶች እንደመኖራቸውም መጠን ተገቢውን ክትትልና ድጋፍ በማድረግ የመማር ማስተማር ሥራ እንዲጀምሩ እየተደረገም ይገኛል፡፡
በአጠቃላይ የትምህርት አጀማመሩ በተሳለጠ መልኩ ለማከናወን ያግዝ ዘንድ 34 ሺህ ትምህርት ቤቶች ለአገልግሎቱ ዝግጁ መደረጋቸውን እና ለዚህም 16 ነጥብ ሶስት ሚሊየን ተማሪዎች መመዝገባቸውን ከትምህርት ሚኒስቴር የተገኘው መረጃ ያሳያል፡፡
ከአዲሱ ስርዓተ ትምህርት ጋር በተያያዘም የዘጠነኛ እና አስረኛ ክፍል አዲሱ ስርዓተ ትምህርት የሙከራ ትግበራ በሁሉም ክልሎች እና ከተማ መስተዳድሮች እንዲሁም በተመረጡ የሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤቶች ውስጥ በ2015 ዓ.ም እንደሚጀመር የተጠቀሰ ቢሆንም ስራው ከሙከራ ትግበራነት ባፋጣኝ መውጣት ካልቻለ የተዘበራቀ ትምህርት አሰጣጥ ሊፈጥር ይችላል፡፡ ለምን ቢባል በሙከራ ትምህርቱን የጀመሩትና ቀደም ብሎ ያለውን እየተማሩ ያሉት ተማሪዎች ወጥ የሆነ እውቀት ስለማያገኙ ነው፡፡
የሙከራ ትግበራ ከሚካሄድባቸው ትምህርት ቤቶች ለተውጣጡ መምህራን ስርዓተ ትምህርቱን የማስተዋወቅ የአሰልጣኞች ስልጠና እየተሰጠ የሚገኝ ሲሆን፤ አዲሱ የስርዓተ ትምህርት ዝግጅት በርካታ ደረጃዎችን አልፎ ለሙከራ ትግበራ የደረሰ መሆኑን ትምህርት ሚኒስቴር ጠቅሷል፡፡
በስርዓተ ትምህርት ዝግጅቱ ላይ የተመረጡ የመማር ማስተማር፣ የልህቀት ማዕከላት ዩኒቨርሲቲዎች እና ካምብሪጅ ዩኒቨርስቲ በአማካሪነት መሳተፋቸው ለትምህርት አሰጣጡ ጉልህ ድርሻ ይኖረዋል፡፡
ይህ ሥርዓተ ትምህርት አገር በቀል እውቀትን፣ ግብረገብነትን፣ ሳይንስና ቴክኖሎጂን የተላበሰ እንዲሆን ተደርጎ የተዘጋጀ ሲሆን፤ በዚህ የሙከራ ትግበራ ወቅት ከመምህራንና ከባለድርሻ አካላት ብዙ ግብዓቶች ተሰብስበው፤ ወላጆችና ሌሎችም አስተያየት እንዲሰጡበት በድረ ገፅ እንዲለቀቅ ተደርጓል። በሙከራ ትግበራው ወቅት የሚመጡ አስተያየቶች ተካተው በ2016 ዓ.ም ወደ ሙሉ ትግበራ ይገባል፡፡ የሚሰጠው ስልጠናም መምህራን የመምህሩን መምሪያና የተማሪውን መጽሐፉ እንዲተዋወቁ ይረዳቸዋል።
በአዲሱ የትምህርት ስርዓት ውስጥ ሌላው ሊተኮር የሚገባው በሁሉም ክልሎች የሚሰጠው ትምህርት ወጥነት ያለው እንዲሆን ማድረግ ላይ ነው፡፡ ቀደም ብሎ በነበረው የትምህርት ስርዓት በክልሎች ውስጥ የሚሰጠው ትምህርት የተለያየ በመሆኑ በአንድ ጉዳይ ላይ መግባባት እንዳይመጣ ማድረጉ የሚታወስ ነው። በዚህም ትውልዱ የአገር ፍቅር እንዳኖረው መሰረት ጥሏል፡፡ አሁንም ይህ ሁኔታ እንዳይደገም ማድረግ ይገባል፡፡
በአዲሱ የትምህርት ስርዓት ውስጥ የተጨመሩ የትምህርት አይነቶችን ለማስተማር ብቁ የሆነ መምህር ማፍራት ላይ ትምህርት ሚኒስቴርም ሆነ የክልል ትምህርት ቢሮዎች ጠንክረው መስራት አለባቸው፡፡
በተጨማሪም ከፍተኛ የትምህርት ተቋማትም በመምህርነት የሚያሰለጥኗቸው ባለሙያዎች በቂ እውቀት ይዘው እንዲወጡ በአግባቡ ኃላፊነታቸውን ሊወጡ ይገባል፡፡
አዲሱ ባይከዳኝ
አዲስ ዘመን መስከረም 15 ቀን 2015 ዓ.ም