ለደጋጎች ግብረ መልስ፤
“የዓለም ሥልጣኔ መሠረት የተቀረጸው በብዕር ቀለም ነው። የዓለማችን የጥፋትና የጦርነት ታሪኮች የተበጠበጡትም በብዕር ቀለም አማካይነት ነው።” ዘመን ያሸበተው ይህ ዝነኛ “አረጋይ” ብሂል የተሸከመውን የገዘፈ እውነት በተመለከተ በብዙ አቅጣጫ መፈተሽ ይቻላል። መልካም ጥበባትን፣ ምርምራቸውን፣ እውቀታቸውንና ግለ ታሪኮቻቸውን በአግባቡ ሰንደው እና ወደ ሌሎች ቋንቋዎች ተርጉመው በጽሑፍ ላቆዩልን ባለ ወርቃማ አእምሮዎች (Beautiful Minds እንዲሉ) ታሪክ ባለመታከት ሲያመሰግናቸው እንዲኖር አደራችንን እናስተላልፋለን።
ምሥጋናችንን ለማቅረብ ግድ ያለን የኖሩበትን ዕድሜ አስልተው ብቻም ሳይሆን ከፊታቸው ላለው ትውልድና ዘመን ጭምር ግድ ብሏቸው እውቀታቸውን ያለስስት፣ ጥበባቸውን ያለንፍገት ላስተላለፉልን ደጋጎች ብቻም አይደለም። ዛሬም በእኛይቱ ጀንበር መሰል የጽሑፍ ቅርሶችንና ሰነዶችን በማቆየቱ ሕያው ተግባር አድካሚ ኃላፊነታቸውን በትጋት እየተወጡ ያሉ በርካታ “የአፍቃሬ በጎነት” ባለ ብእሮች በዓለማችን ላይ እንደ ከዋክብት እያበሩ ስላሉ “በእጅ የያዙት ወርቅ ከምንትስ ይቆጠራልን” ብሂል እንዳያስተርትብን እነርሱንም “አሹ!” ብሎ ማበረታታቱ ግድ ይላል። ብዕራቸው ይለምልምልን፤ አክብሮታችንም ይድረሳቸው።
በእሾህ ብዕር ደም ጠቃሾች፤
ብዕራቸውን ለእውነት፣ ቀለማቸውንም ለውበት ያዋሉ ጸሐፍት የመብዛታቸውን ያህል፤ በአንጻሩም በተቃርኖ የቆሙ የእሾህ ብዕረኞችንም ዓለማችን “አምጣ ወልዳለች።” ምድራችን ሰላም አግኝታ እፎይ እንዳትል በጽሑፋቸው አማካይነት እየደነቋቆሉ እንደምን እያስነከሷት እንዳሉም እለት በእለት የምናስተውለው ሐቅ ነው። እውነትን አዛብተው፣ ታሪክን አፋልሰው፣ አምባገነንነትን ሰብከውና ሁከትን ቀስቅሰው በሰው ልጆች እልቂት ደስ በመሰኘት “በዋንጫቸው ውስጥ ደም እየሞሉ ቺርስ!” በመባባል በፌሽታ የተሳከሩ የዓለማችን ፀሮች ቁጥራቸውም ሆነ ሥራዎቻቸው ተዘርዝሮ የሚጠናቀቅ ባለመሆኑ “ትዝብታችንን በማውረስ” ጊዜ ይግለጠው ብሎ ማለፉ ይቀላል።
ሰፊውን ምልከታችንን ሰብሰብ አድርገን በአገራዊ መሰል ችግሮቻችን ዙሪያ ትኩረት መስጠቱ ይበጅ ስለመሰለን ስለኛዎቹ “የቤት ውላጅ የእሾህ ብዕረኞች” ጥቂት ሃሳቦችን እንፈነጣጥቅ። ሕወሓት የአገሪቱን ሀብት አጋብሶ ለማዳከም በኋላም ለአካባቢ መሬቶች ቅርምትና ለጦርነት ዝግጅት ዳር ዳር ከማለቱ ቀደም ብሎ በትጋት ሲሰራ የኖረው በእሾህ ብዕረኞቹ አማካይነት የክፋት ሴራውን በማስረጽ ውጊያ መክፈት ነበር። እንደ እውነቱ ከሆነ ይህ ስትራቴጂው በሚገባ ግቡን እንደመታለት በውጤቱ ማረጋገጥ ይቻላል።
ሕወሓት ከውልደት እስከ እድገቱ፣ ከልጅነት እስከ ጉልምስናው የኖረውና ምናልባትም አብሮት ሊቀበር የሚችለው “ከእኔ ወዲያና ከእኛ ወዲያ ላሳር” የሚለው ትዕቢቱና ትምክህቱ በዋነኛነት የሚጠቀስለት “ሌጋሲው” እንደሆነ ለማመን አይከብድም። ይህንን የክፋት አስተሳሰቡን ሲዘራና ሲበትን የኖረው የእሾህ ብዕር አስጨብጦ ባሰለፋቸው “ሠራዊቱ” አማካይነት ነበር። ዛሬ ዛሬ ደግሞ የዕሾህ ብዕረኞቹን ፈለግ የሚከተሉ የማሕበራዊ አሜክላዎችን በዓለም ዙሪያ በትኖ ይህንኑ አገርንና ሕዝብን የማተራመስ፣ የማድማትና በታሪክ እውነታዎች ላይ የመዘባበት ተልዕኮውን አጠናክሮ ገፍቶበታል። ከጦር ሜዳው ባልተናነሰ ፍልሚያ ጎን ለጎን የተከፈተብን ጦርነት ቀደም ሲል በብዕር ዛሬ ደግሞ በማሕበራዊው ሚዲያ መሆኑን አንባቢው ልብ ይበል።
“ብዕራቸውን ለከፋፋይነት” በመጠቀም የመጻሕፍት ገጾቻቸውን ኢትዮጵያን ለማሳነስ ቢቻልም ለማዳከም በትጋት ሲሰሩ የኖሩት ጥቂት የማይባሉት የዘመናችን አፍቃሬ ሕወሓት ጦማሪዎች “የደረሷቸው” በርካታ ጥራዞች የተለወሱት በዘመን ተሻጋሪ ከፋፋይ መርዞች ቀለማቸው እየተበጠበጠ ነበር። ለማሳያነት እንዲረዳም ሁሉንም መሰል መጻሕፍት ሊወክል የሚችለውን አንድ መጽሐፍ ብቻ ለማሳያነት እንጥቀስ።
የመጸሐፉ የተሳከረ ርዕስ “ዘረኛው ማነው? ኢትዮጵያዊያን ፍረዱ! ሁለት ሺሕ ዓ.ም ሚሊኒዬም – ኢትዮጵያ ” የሚል ሲሆን ደራሲው በተለያዩ ርዕሶች የጻፏቸው ሌሎች ጠቃሚ መጻሕፍትም መኖራቸውን ሳናስታውስ አናልፍም። ይኼኛው መጽሐፍ ግን በመልካም አዝመራ ውስጥ የበቀለ እንክርዳድ መሆኑን የምንተቸው መልካሞቹን በመዘንጋት ያለመሆኑ ይታወቅ።
መጽሐፉ በወቅቱ “አንቱታን ባተረፉ” የግዜው ሹመኞች ልዩ ትኩረት ተሰጥቶትና አድናቆት ተችሮት በተመረቀበት ዕለት በቦታው በመገኘት የዓይን እማኝ ለመሆን እድል አግኝተን ነበር። በመጽሐፉ ላይ የተሰጡትን ግምገማዎችም ልብ ተቀልብ ሆነን ተከታትለናል። ይዘቱንም ከዳር እስከ ዳር ለማንበብ አልሰነፍንም። በዚሁ የመጽሐፍ ምረቃ ላይ የተገኘው ሌላው የሙያ ባልደረባችን የመጽሐፉን ገጾች ገለጥ እያደረገ ይዘቶቹን በመቃኘት ላይ እያለ፡- “ይድረስ ለትምክህተኛ ሁሉ፤ እንደ መግቢያ” የሚለውን መንደርደሪያ እንዳየና “ዘረኝነት ሲባል ምን ማለት ነው?” የሚለውን የምዕራፍ 3 ክፍል ፈጠን ብሎ ካነበበ በኋላ በድፍረት የተገለጹት ክፉ ሃሳቦች እጅግ አስቆጥተውት “በእምባ ቀረሽ” ቁጭት እየተብሰከሰከ ፈጣሪን ለፍርድ የተማጸነው እዚያው አጠገቤ እንደተቀመጠ ነበር።
የዚህ መጽሐፍ አስኳል ሃሳብ የሚከተለው ነው። “ሕወሓት – ኢሕአዴግ ዘረኛ የተባለው የክልል መንግስታትን ቋንቋን መሠረት አድርጎ በመስራቱ ነው? ወይንስ ሌላ ተጨማሪ ያልተለመደ ባሕሪ ጨምሮበታል? ለምንስ አስፈለገ? በድሮው እንደነበር ቢቀጥል አይሻልም ነበር ወይ? ይህ አካሄድ ዘረኝነትን ያስፋፋል፣ ያጋጫል፣ ያራርቀናል፣ ያጣላናል፣ አገሪቷ ወደማትወጣው አዘቅት ሊከታት ይችላል፤ የሚሉ ወገኖች አሉ። ዕውነት ግን ያጣላል፣ ያራርቃል፣ ወይንስ ያቀራርባል፣ ያፋቅራል?” በማለት መደላድሉ ከተመቻቸ በኋላ ጸሐፊው የአገሪቱን በርካታ ብሔረሰቦች ስም በጥላቻ እየጠቀሱና በተለይም በአንደኛው የትግራይ ተጎራባች ክልል ላይ ጫን በማለት “የጭቃ ጅራፋቸውን” እንዴት እንደሚያጮኹ ገጾቹን ገልጾ ማንበብ ይቻላል፤ (ከገጽ 85 ጀምሮ)።
መጽሐፉ ገና ከመግቢያው ጀምሮ የአገሪቱን ቀደምት መሪዎች፣ የታሪክ ባለሙያዎች፣ የታላላቅ ሰዎች ንግግሮችንና ቀደምትና የወቅቱን ደራስያን በስምና ሥራዎቻቸውን እየጠቀሱ ደራስያኑን እያንቋሸሹ የሚሰድቡበትን ቋንቋና ገለጻ ደግሞ ማስታወሱ “ከሰደበኝ መልሶ የነገረ ገደለኝ” መርህን መጣስ ስለሚሆን ወደ ጥልቅ ይዘቱ በመግባት መሄሱ እጅግም ረብ አይኖረውም።
መቼም የሕወሓት ግልጽና ድብቅ ተልዕኮ አገሪቱን እንዴት አሽመድምዶ ዛሬ ለደረስንበት መከራ እንደዳረገን በብዙ ማስረጃዎች እያመላከትን ባለመሰልቸት ስንጽፍ መክረማችን ይታወሳል። በተለይም የዘመን ተሻጋሪነት ባህርይ ባለው የጽሑፍ ጥበብ ታሪክን እያዛቡና እውነታን እያጣመሙ የሕዝቦችን የአብሮ መኖር ተፈጥሯዊ ባህርይ በእሾሃማ ብዕር በማጠር ከትውልድ ትውልድ የሚተላለፍ ወንጀልን መፈጸም ይቅር የማያሰኝ ተግባር መሆኑ ለማንም ይጠፋል ተብሎ አይታመንም።
ሕወሓት ይሉት “የሞት መላዕክ” በአገሪቱ ታሪክ፣ በነባራዊ እውነታዎችና በሕዝቦች ሥነ ልቦና ላይ ሲፈጽም የኖረው የከፋ በደል ከመላው ሕዝብና በተለይም ከአብዛኛው የትግራይ ሕዝብ አዕምሮ ውስጥ ተጠርጎ እስኪወጣ ድረስ ምን ያህል ጥረትና ዓመታት እንደሚያስፈልግ ለግምት እንኳን አዳጋች እንደሆነ መገመት አይከብድም።
በተደጋጋሚ በዕብሪት በወረራቸው አካባቢዎች ቀብሯቸው የሄደው አውዳሚና ተቀጣጣይ ፈንጂዎችን በተመለከተ፤ ክብር ለመከላከያ ሠራዊታችን የመሃንዲስ ባለሙያዎች ይሁንና ጥንቃቄ በታከለበት ወታደራዊ ግዳጅ የጊዜ ጉዳይ ካልሆነ በስተቀር ከተቀበሩበት ቦታ እየተለቀሙ መጽዳታቸውና መክሸፋቸው የማይቀር ነው። ነገር ግን በአጠቃላይ በአገሪቱ ዜጎች በተለይም በትግራይ ሕዝብ አእምሮ ውስጥ በተበከለ የፕሮፓጋንዳ ጦርነት የታጨቀው ክፉ አስተሳሰብ በምን ያህል ዘመናት ታጥቦ እንደሚጸዳ ለመገመትም ሆነ ለማሰብ በእጅጉ ይፈትናል።
የፈተናው ክብደትና ውስብስብነት የሚናቅ ባይሆንም የአገሪቱ የታሪክ ባለሙያዎችና ደራስያን እስከ ዛሬ በህትመት ዘዴ ተሰራጭተው በሕዝብ አእምሮ ውስጥ የተነሰነሱትን መርዛማ የሕወሓት ታሪኮችና ትርክቶች በእውነታና በማስረጃ ለመሞገት ቁርጥ ውሳኔ በማድረግ ወደ ሥራ ሊገቡ ይገባል። ለዚህ ተልእኮ ተፈጻሚነትም መንግሥትና ያገባናል የሚሉ ተቋማት የታሪክ ተመራማሪ ምሁራኑንና ደራስያንን በቅርበት ሊያግዟቸውና ሊያደፋፍሯቸው ይገባ ይመስለናል።
በፈራ ተባ እየታለፈ ያለው የታሪክ ውይይትና ክርክር ጉዳይም ከምንም በፊት ትኩረት ተሰጥቶበት ወደ ተግባራዊ ዘመቻ መግባት እስካልተቻለ ድረስ ጓያ እንደሰበረው ምስኪን ሰው “በቆይ ብቻ” እየፎከሩ ጊዜ ማባከን በዚህ ጸሐፊ እምነት ድክመት ብቻ ተብሎ የሚታለፍ ሳይሆን ታሪክንና እውነትን ከመበደል ተለይቶ ሊታይ አይገባውም።
ከጥቂት ዓመታት በፊት በርካቶቹ ዩኒቨርሲቲዎቻችን የታሪክ ክፍላቸውን በመዝጋት የመምህራኑን ልብና መንፈስ ሲሰብሩና ተማሪዎች የታሪክ ትምህርትን ልክ እንደ አንድ አስፈሪ መንፈስ እንዲሸሹት ባደረጉበት ወቅት በዚሁ ጋዜጣ ላይ የመረረ ጩኸታችንን ማስተጋባታችን አይዘነጋም። ያ ቸልተኝነት የሚያስከትለው ውጤት በቅርብ የሚገለጽ ሳይሆን ከዓመታት በኋላ ፍሬ አፍርቶ መመልከታችን አይቀርም።
አሁንም ቢሆን ጊዜው አልመሸም፤ “የኢትዮጵያ ታሪክ ስንል የቱን ማለታችን ነው?” የሚለው ጉንጭ አልፋ መከራከሪያ ጥርት ብሎ ወደ እውነቱ መቃረብ ይኖርበታል። በቃል ሙግት ብቻ የሺህ ዓመት ዕድሜ አለው የምንለውን ታሪካችንን “በአሉ ተባባሉ” እያጎላን ጮክ ብለን በመናገር፤ በጽሐፋችን ግን አይናፋርነታችን ጠንክሮ “እነ አከሌ ምን ይሉናል?” የምንል ከሆነ ጠቡ ከታሪክና ከእውነታ ጋር ብቻም ሳይሆን ህሊናንም ይጨምራል። እትትት እያሰኘ ድፍረታችንን ቆፈን ካስያዘው ፖለቲካ ተላቀን ነፃ እስካልወጣን ድረስ ቸል ያልነው የታሪክ እውነታ እንደሚፈርድብንም ማሰቡ አይከፋም። ለዩኒቨርሲቲዎቻችንና የትምህርት ሥርዓቱን ለሚመሩ ሹመኞች ቀደም ሲል የሰጠነውን ማሳሰቢያ ደግመን ማስታወሱ አግባብ ይመስለናል።
ሕወሓት የራሱን ትርክት በራሱ የእሾህ ብዕረኞች እያጣደፈ ይጽፍና ያጽፍ የነበረው በፌዴራል ከፍተኛ የትምህርት ሥርዓቱ ላይ ይህንን መሰል መሰሪ ስልት ለመተግበር እንደነበር ዛሬ በሚገባ እውነቱ እየተገለጠ መጥቷል።
ብዙ የታሪክ ምሁራንና ደራስያን ያፈጠጠውን የሕወሓት ተንኮልና ሴራ እያስተዋሉ “ምንትስን ምን አገባው ከእርሻ” በሚል ፈሊጥ ራሳቸውን ሸሽገውና ሰውረው “ክፉን ቀን እንደ ቅዝምዝም ዝቅ ብለው ለማሳለፍ” መሞከራቸው ፀሐይ የሞቀው እውነታ ነው። ቀላሉ ማሳያ በኢትዮጵያ ብሔረሰቦች ታሪክ ላይ ደፈር ብለው በየሚዲያው የምናስተውላቸውን ጥቂት ተመሳሳይ ሰዎች ብቻ በማየት እውነቱን ማረጋገጥ ይቻላል።
ሕወሓትና ብዕረኞቹ በዚህ ጉዳይ ብርቱ መሆናቸውን ባንመሰክር ከእውነት እንጋጫለን። ሀሰተኞች ገንነው ሲወጡ እውነትን የያዙት ለምን ዓይናፋር ሆነው “ከራስ በላይ ነፋስ” በሚል ፍልስፍና ሕይወታቸውን ለመምራት እንደወሰኑ ምክንያቱን ለመግለጽ “እነርሱን መሆን” ግድ ይላል።
በመጨረሻም፡- “እሾህን በእሾህ” እንዲሉ በውሸት ሲተረክ የኖረውን የሕወሓት ትርክት ለማርከስ ጊዜውም ሆነ አመቺው ወቅት አሁን ስለሆነ የዘርፉ ምሁራንና የአገራችን ደራስያን ያሸለበውን ብዕራቸውን ቀስቅሰው እውነቱን እየገላለጡ በውሸት የተበከለውን የሕዝባችንን አዕምሮ በተለይም የትግራይ ወገኖቻችንን ሥነ ልቦና ሊፈውሱ ውዴታ ብቻ ሳይሆን የዜግነት ግዴታ ጭምር ነው። ሰላም ይሁን!
በ(ጌታቸው በለጠ /ዳግላስ ጴጥሮስ)
gechoseni@gmail.com
አዲስ ዘመን መስከረም 12 ቀን 2015 ዓ.ም