ዓለም አቀፉ የሴቶች ቀንን የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት ዕውቅና ችሮት በይፋ መከበር ከጀመረ አርባ አምስት ዓመታት ገደማ ሆኖታል። ለዚህ በዓል መሠረት የሆነው እንቅስቃሴና ትግል ከተጀመረ ግን አንድ ክፍለ ዘመን ተሻግሯል። በተለይ ከእንቅስቃሴው ጋር በተገናኘ ሁልጊዜም ከፍተኛ ትግል የፈጸሙ ብሎም በምርጫቸው ኢትዮጵያዊ የሆኑ፣ ሕይወታቸው ካለፈም በኋላ እዚሁ የተቀበሩ አንዲት ሴት አሉ። እአአ በ1914 የሴቶችን መብት ለማስከበር ሰላማዊ ሰለፍ ይመሩ ስለነበር ለእስራትም ተዳርገዋል።
እኚህ ሴት ሲልቪያ ፓንክረስት ናቸው። እሳቸውና አጋሮቻቸው የታገሉለት ዘርፈ ብዙው የሴቶች ጥያቄ በዋናነት በሶሻሊስት አገሮች በየዓመቱ ሲከበር ቆይቶ ሲልቪያ ፓንክረስት ካለፉ በኋላም በተባበሩት መንግሥታት ድርጅት በየዓመቱ ‹‹የሴቶች ቀን›› ተብሎ እየተከበረ ይገኛል። በዛሬው እትማችንም ከብዙ አስርት ዓመታት በፊት በዚህ ወር ከዚህ ዓለም በሞት የተለዩት ነገር ግን ዛሬም ድረስ ታሪክ የማይዘነጋቸውን እኚህን ሴት እናስታውሳለን።
ሲልቪያ ፓንክረስት የተወለዱት ሚያዝያ 27 ቀን 1874 ዓም በእንግሊዝ አገር ማንችስተር በተባለው ከተማ ነው። ለሲልቪያ ፓንክረስት የወደፊት ሕይወት ላይ ደማቅ አሻራን ያኖሩት አባታቸው ዶክተር ሪቻርድ የእንግሊዝ ሌበር ፓርቲ ንቁ ተሳታፊ፣ ለድሆች ተሟጋችና መብታቸውን ለተነፈጉ ሁሉ ድምጽ ነበሩ። እናታቸው ኤምሊ ፓንክረስትም ሴቶች በእንግሊዝና በአውሮፓ ፖለቲካና ምርጫ ውስጥ ንቁ ተሳትፎ እንዲኖራቸው ትልቅ ሚና የተጫወቱና ብርቱ ትግል ያደረጉ ሴት ነበሩ።
ሲልቪያ በማንቸስተር የስነ-ጥበብ ትምህርት ቤት (Manchester School of Art) የስዕል ትምህርት ተምረዋል:: በመቀጠልም እአአ በ1900 ወደ ለንደን የሮያል የስነ-ጥበብ ትምህርት ቤት (Royal College of Art) በማቅናት ተጨማሪ ትምህርት መማር ችለዋል:: እአአ በ1902 የሞዛይክ ስነ ጥበብ (Mosaic) ለማጥናት ወደ ኢጣሊያ ቬኒስ ከተማ ሄደው እንደነበርም ታሪካቸው ያስረዳል::
እአአ ከ1906 ጀምሮ እናታቸው ኤመሊን ፓንክረስት ያቋቋሙትን ‹‹የሴቶች ማህበራዊና ፖለቲካዊ ህብረት›› የተባለውን እንቅስቃሴ በመቀላቀል ከእናታቸውና ከእህታቸው ጋር መስራት ጀመሩ:: ሲልቪያ በወቅቱ ለሴቶች እኩልነት ሲታገሉ እንደነበሩት ሌሎች ሴቶች ሁሉ በተደጋጋሚ ለእስር ተዳርገዋል:: እአአ ከየካቲት 1913 እስከ ነሐሴ 1914 ድረስ ለስምንት ጊዜያት ያህል እስር ቤት ገብተዋል:: በእስር ቤት እያሉም የረሀብ አድማ ያደርጉ ነበር::
ሲልቪያ የአባታቸውንና እናታቸውን አርአያ በመከተል ዕድሜ ዘመናቸውን ሁሉ ለሰው ልጆች መብትና ነጻነት በመታገል አሳልፈዋል። በ1928 ዓም ወራሪው ፋሽስት ኢጣሊያ የኢትዮጵያን ህዝብ በመርዝ ቦምብ ሲፈጅና የፍትህ ያለህ እያለ በሚጮኽበት፣ ኢትዮጵያውን አርበኞች በዱር በገደል ለአገራቸው ነጻነት ደማቸውን በማፍሰስ ላይ በነበሩበት ጊዜ ሲልቪያ ፓንክረስት ማንንም ሳይፈሩ የፋሽስት ወራሪውን ኃይል ግፍን በግልጽ በአደባባይ በመቃወም ድምጻቸውን ለዓለም ሁሉ ህዝብ ያሰሙ የነጻነት አርበኛና የጭቁን ህዝቦች አለኝታ ነበሩ።
የኢጣሊያ ወታደሮች አዲስ አበባን ከያዙበት ከ1928 ዓም ጀምሮ በእንግሊዝ ‹‹The New Times and Ethiopian News›› የተባለውን ጋዜጣ አቋቁመው ያለ ማቋረጥ በየሳምንቱ በማሳተም ለኢትዮጵያውያን ነጻነት፣ ክብርና ሉዓላዊነት ድምጻቸውን አሰምተዋል። በዚህ ጋዜጣም ፋሽስት ኢጣሊያ በኢትዮጵያ ህዝብ ላይ እያደረሰ ያለውን ግፍ በመግለጽ በዓለም አቀፍ ደረጃ ተሰሚነትን ሊያገኙ ችለው ነበር።
ሲልቪዮ ኮሪዮ ከተባለ ጣሊያናዊው ጋር ግንኙነት መስርተው እአአ በ1927 ዓም ሪቻርድ የተባለ ወንድ ልጅም ወልደዋል:: ይህ ልጅ በኋላ የኢትዮጵያን ታሪክ በማጥናትና በማስተማር ልክ እንደ እናቱ የኢትዮጵያ ባለውለታ የሆነው ፕሮፌሰር ሪቻርድ ኬይር ፔቲክ ፓንክረስት ነው::
ሲልቪያ ፓንክረስት ለኢትዮጵያ የሚያደርጉት ትግል በኢጣሊያ መባረር ብቻ አልተገደበም:: የፋሺስት አስተዳደር ከኢትዮጵያ ከተወገደ በኋላም እንግሊዝ የኢትዮጵያ የበላይ ጠባቂ (ሞግዚት) ለመሆን የሸረበችውን ሴራ ሲልቪያ ተቃውመዋል:: ኤርትራ ከኢትዮጵያ ጋር እንድትዋሃድም ደጋግመው አስገንዝበው ነበር:: ከጸረ-ፋሺስት ትግሉ ባሻገር የኢትዮጵያ ፓርላማ እንዲሻሻልና ኢትዮጵያዊያን ሴቶች በአገራቸው የፖለቲካ፣ ኢኮኖሚና የማህበራዊ ጉዳዮች ላይ ያላቸው ተሳትፎ እንዲጠናከር የሚያሳስብ ደብዳቤ ለቀዳማዊ አጼ ኃይለ ሥላሴ ጽፈዋል።
ከኢትዮጵያ የረጅም ዘመን ሥልጣኔ፣ ታሪክ፣ ባህል፣ የህዝቦቿ የነጻነት ተጋድሎና ኩራት እጅግ የተማረኩት ሲልቪያ ፓንክረስት ከነጻነት በኋላ በቀሪው ዕድሜያቸው በሩቅ የሚያውቋትን ኢትዮጵያን በአካል በመገኘት ስለ ኢትዮጵያ ለማጥናት ሲሉ በ1948 ዓም ከወንድ ልጃቸው ከሪቻርድ ፓንክረስት ጋር ወደ ኢትዮጵያ መጡ።
በኢትዮጵያም ውስጥም ‹‹Ethiopian Observer›› የተባለውን መጽሔት በማዘጋጀት በየወሩ ያሳትሙ ነበር። በወቅቱ ኢትዮጵያ ከእንግሊዝ ጋር የነበራትን ግንኙነት በተመለከተ፣ በኢትዮጵያና በኤርትራ በኩል ስላለው ታሪካዊ ግንኙትና ፖለቲካዊ ቀውስ ሰፊ የሆነ ጥናትና መልካም ተሳትፎ ያደርጉ እንደነበር በዘመኑ ካስነበቧቸው ጽሑፎች መረዳት ይቻላል። የአዲስ ዘመን ጋዜጣ መስከረም 18 ቀን 1953 ዓም እትሙ በሲልቪያ ፓንክረስት የቀብር ሥነ ሥርዓት የአገር ግዛት ሚኒስትር የነበሩት ራስ አንዳርጋቸው መሳይ ለእኚህ የኢትዮጵያ ወዳጅ ያደረጉትን ንግግር እንዲህ ዘግቦት ነበር።
‹‹ሚስስ ሲልቪያ ፓንክረስት በኢትዮጵያ ገና ብዙ ለማገልገል ከፍ ያለ ምኞት ስለነበራቸው በዛሬው ቀን የቀጠሩን እዚህ ሳይሆን ሌላ ስፍራ ነበር። በእውነት እላችኋለሁ፣ የኢትዮጵያ ህዝብ መከራ፣ ግፍና ስደት አልቆ ውጤቱ እስኪደርስ ድረስ ሚስ ሲልቪያ የሠሩት ሥራ በሽማግሌ ጉልበታቸውና ላባቸው ብቻ ሳይሆን ጤናቸውን እስኪያጡ፣ ርስታቸውን ሽጠው እስኪደኸዩ፣ በግል ገንዘባቸው ጭምር ለኢትዮጵያ የሠሩ ሰው ናቸው። ስለዚህ ታላቋ እንግሊዛዊት ሚስ ሲልቪያ ፓንክረስት የኢትዮጵያ ወዳጅ፣ እውነተኛዋ ኢትዮጵያዊ አርበኛ መባል የሚገባቸው ናቸው››።
ክቡር ራስ አንዳርጋቸው ንግግራቸውን በመቀጠልም ‹‹ወዳጃችን ሲልቪያ ፓንክረስት ሆይ 25 ዓመት ሙሉ ያለ ዕረፍት የዕድሜዎን ሸክም ሳያስቡ በእውነትና በታማኝነት የረዱዋቸው የኢትዮጵያ ንጉሠ ነገሥትና ሕዝብ አሁን በዙሪያዎ ቆመው ያለቅሱልዎታል። ወዳጆችዎ አርበኞችና ስደተኞች እዚሁ ባጠገብዎ ቆመዋል። ያንንም የመከራ ዘመን ያስባሉ።
ታሪክዎ ከታሪካቸው በደም ቀለም ተጽፎ ሕያው ሆኖ ይኖራል። እርስዎም በዚህች በኢትዮጵያ ምድር ላይ በሰላም አርፈው እንዲኖሩ የግርማዊነታቸው መልካም ፈቃድ ስለሆነ እንደ ኢትዮጵያዊት ዜጋ ቆጥረን በክብር እናሳርፍዎታለን። እግዚአብሔር በምድር ላይ ሳሉ የሠሩትን በጎ ሥራ ሁሉ ቆጥሮ በሰማይ ቤት የክብር ቦታ እንዲያድልዎ እንመኛለን›› በማለት ነበር እኚህ ታላቅ የኢትዮጵያ ባለውለታ በጥልቅ ሐዘን ስሜት ውስጥ ሆነው የተሰናበቷቸው።
ግርማዊ ቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴም በሚስ ሲልቪያ ፓንክረስት የቀብር ዕለት ባደረጉት ንግግራቸው ደግሞ ‹‹ሚስስ ሲሊቪያ ፓንክረስት ኢትዮጵያን ለማገልገል ቆርጠው ከተነሱበት ጊዜ ጀምሮ የመጨረሻው ድል እስኪገኝ ድረስ ያደረጉትን የአሳብና የሥራ ተጋድሎ ሰፊ የታሪክ መስመር የያዘ ነው። ምኞታቸውና እምነታቸው የማይበገር የምሪት ምሽግ ነበር።
የመንፈሳቸው ጽናት በፊታቸው የተጋረደውን እንቅፋት አስወግዶ ለማለፍ የተለየ ሥልጣን ነበረው። የኢጣሊያ ፋሽስት ጦር በዓለም መንግሥታት የተከለከለ የመርዝ ጢስ እየጣለ ሰላማውያኑን ህዝብ ሴቱንና ሽማግሌውን ህጻኑን ለመጨረስ ስለተነሳ ይህን ግፍ ለዓለም ሸንጎ ለማሰማት ወደ ጄኔቭ መሄዳችንን ሲከታተሉ የቆዩት ሚስስ ሲልቪያ በዓለም ላይ ከዚህ የባሰ ምን በደል ይድረስ በማለት ለእውነተኛው ፍርድ በመቆርቆር ተነሱ።
ፋሽስቶች የኢትዮጵያን ህዝብ ያለ ፍርድ ፈጁት። ሚስስ ፓንክረስትም የጽሁፍና የፎቶግራፍ ማስረጃዎች እያሰባሰቡ ዓለም ይህን ሰምቶና አይቶ ካልፈረደ ለራሱ ወዮለት እያሉ ጮኹ። የኢትዮጵያን አርበኞች ተስፋ ለማስቆረጥ ፋሽስቶች በመርዝ ጢስና ቦምብ ያደረጉባቸውን የጭካኔ ውጊያ ሴቱንና ህጻኑን ያለ ምክንያት እየሰበሰቡ በመትረየስ መፍጀታቸውን ማስረጃ አቀረቡ››።
‹‹ሚስስ ፓንክረስት በባሕርያቸው እውነተኛ ፍርድ ለማግኘት ሲታገሉ፣ የዚህችን ጥንታዊ አገር ታሪክ፣ ሥልጣኔና ቅርስ የህዝቦቿን ጀግንነትና ፍቅር እየማረካቸው ሄደ። ከኢትዮጵያና ከህዝቦቿ ጋር በፍቅር የወደቁት ሲልቪያ ፓንክረስት ለሀገራቸው ነጻነትና አንድነት ክቡር ህይወታቸውን ከከፈሉት ኢትዮጵያን አርበኞች የሚደመሩ ናቸውና በዚህ በቅድስት ሥላሴ ካቴድራል ያርፉ ዘንድ በጎ ፈቃዳችን ሆኗል።›› በማለት ነበር እኚህን ታላቅ የኢትዮጵያ ወዳጅ መቼም ቢሆን በኢትዮጵያ ታሪክ ውስጥ ሥራቸው ሲታወስ እንደሚኖር በትልቅ አድናቆትና አክብሮት የተሰናበቷቸው።
ሚስስ ፓንክረስት በሁለተኛው የዓለም ጦርነት ባሎቻቸውን ያጡትን ባልቴቶችና እንዲሁም ድኃ አደግ የሆኑትን ልጆች በመሰብሰብ ከፍ ያለ ዕርዳታ አድርገዋል። ትምህርት ቤትና ክሊኒኮችንም ከፍተው ገቢው ለሠራተኞች በተለይም ለመርከበኞችና ለወታደሮች ሚስቶች ጉዳይ እንዲውል በማድረግ ራሳቸው ጸሐፊ በመሆን ታላቅ ሥራ ሠርተዋል። በአምስቱ ዓመት የፋሽስት ወረራ ዘመን ማቲዎቲ የሚባለው የፋሽስት ተቃዋሚ ድርጅት መሥራችና ዋና ጸሐፊ ነበሩ።
በኢትዮጵያ ጉዳይ ላይ ሰፊ የሆነ ጥናትና ምርምር ያደረጉም ሴት ናቸው። በኢትዮጵያ ላይ ከጻፏቸው መጻሕፍት መካከልም፤ የኢጣሊያ ጦርነት ወንጀል በኢትዮጵያ፣ የእንግሊዝ አመራር በኢትዮጵያ፣ የኢትዮጵያ ህዝቦች መብታቸውና ዕርምጃቸው፣ ኢትዮጵያና ኤርትራ፣ ‹‹The Cultural History of Ethiopia›› የሚጠቀሱ ናቸው።
እንግሊዛዊቷ ሚስስ ሲልቪያ ፓንክረስት በ1953 ዓም በወርሀ መስከረም በመስቀል በዓል ዕለት አርፈው የቀብራቸው ሥነ ስርዓት በቅድስት ሥላሴ ካቴድራል የተፈጸመው በማግስቱ መስከረም 18 ቀን ነበር።
አቤል ገብረኪዳን
አዲስ ዘመን መስከረም 8/2015