ኢትዮጵያ ልጆቿ በዓለም አቀፍ፣ በአህጉራዊ እና ክፍለ አህጉራዊ ተቋማት፣ መድረኮች፣ ወዘተ አንጸባራቂ ሆነው እንዲታዩ ጽኑ ፍላጎት አላት:: የልጆቿ በእነዚያ ተቋማት፣ መድረኮች፣ ወዘተ መታየት የእሷም መታየት ነውና እምነቷ ትክክል ነው::
ይህ ዓይነቱ ሁኔታ እንዲፈጠር አገሮች አጥብቀው ይሠራሉ፤ ይህን አጋጣሚ ማባከን የሚፈልግ አገር የለም፤ የአገራቸው ጥቅም ማስጠበቂያና ገጽታ መገንቢያ፣ የዲፕሎማሲ ግንኙነታቸው ማጠናከሪያ፣ ወዘተ አድርገው ይጠቀሙበታል:: አይደለም የዓለም አቀፍ ድርጅት መሪ በእነዚያ ታላላቅ ተቋማት የሚገኝ ተራ ሠራተኛም ቢሆን፣ ለአገርና ሕዝብ ያለው ፋይዳው ከፍተኛ ነው::
ለእዚህም ሲባል አገሮች ብቻም ሳይሆኑ አህጉራትና ክፍለ አህጉራት የራሳቸው ሰው በዓለም አቀፍ ድርጅቶች መሪነት ስፍራ ላይ እንዲቀመጥ ሲሉ ብዙ ዋጋ ይከፍላሉ:: በየአገሮቹ በመዘዋወር የምረጡኝ ቅስቀሳ ያደርጋል:: ለሎቢስቶች (አግባቢዎች) ከፍተኛ ገንዘብ እየተመደበ ይህ ሥራ እንደሚካሄድ ይነገራል:: ለዚህ የሚከፈለው ዋጋ ለአገር ለአህጉርና ክፍለ አህጉር ሲባል የሚደረግ ነውና ተገቢ ነው::
ኢትዮጵያም የዓለም ጤና ድርጅት ዋና ዳይሬክተር ዶክተር ቴድሮስ አድሃኖም ለዓለም ጤና ድርጅት ዋና ዳይሬክተርነት ዕጩ ሆነው በቀረቡ ጊዜ እንዲመረጡላት ብዙ ደክማለች:: ኢትዮጵያ ብቻ ሳትሆን የአፍሪካ ህብረት አገሮችም ይህንኑ አድርገዋል:: ለእዚህም ሎቢስቶችን ለመቅጠርና ለመሳሰሉት ብዙ ዋጋ እንደከፈለች በወቅቱ ሲነገር ነበር:: የአፍሪካ አገሮች ድምጽ ከጎናቸው እንዲቆም በአህጉሪቱ የተለያዩ አገሮች በመዘዋወር ብዙ ተሠርቷል:: ይህ መሆኑ ትክክል ነው::
በዚያን ወቅት በዶክተር ቴድሮስ ላይ በአገር ውስጥ ከኤችአይኤድስ ኪት ግዥ ጋር በተያያዘ ቅሬታ የሚያሰሙ አካላት እንደነበሩ አስታውሳለሁ:: ያ ቅሬታ ጠንካራ መረጃዎች ያሉት ሆኖም፣ በግዥው የአገር ሀብት ተመዝብሯል እየተባለም፣ ዶክተሩ ለዓለም ጤና ድርጅት እንዳይወዳደሩ ሆን ተብሎ የታቀደ ተግባር ነው ተብሎ ሳይስተናገድ ቀርቷል ይባላል::
ዛሬ ላይ ቆመን ስንመለከተው ደግሞ በወቅቱ በአገሪቱ አድራጊ ፈጣሪ የነበረው አሸባሪው ትህነግ አግባቢዎችን (ሎቢስቶችን) ለማሰማራት አያሌ የኢትዮጵያ ሕዝብ ገንዘብ እንዲወጣ አድርጓል ይባላል:: ለአገር ታስቦ ከሆነ ይህም ባልከፋ:: ለማናቸውም ተብሎ ከሆነ ግን በእጅጉ ያነጋግራል:: እንደ አገርና አህጉር ሰውዬውን የዓለም ጤና ድርጅት ኃላፊነት ላይ ለማስቀመጥ የተደረገው ርብርብ የሚደነቅ ነው::
ያ ሁሉ ተደክሞም ዶክተር ቴድሮስ የዓለም ጤና ድርጅት ዋና ኃላፊ ተደርገው ተመረጡ:: ዶክተሩ ለኢትዮጵያ ምን ዋሉላት ተብሎ ሲታሰብ ግን ያሳዝናል:: የዋለላቸውን የኢትዮጵያን ሕዝብ እጅ ነክሰው፣ አገሪቱን ለማፍረስ ከሚጣጣረው አሸባሪው ትህነግ ጋር ሆነው እየሠሩ ናቸው:: የኢትዮጵያን አጀንዳ ከፍ አድርገው ያሳያሉ፣ የኢትዮጵያን ገጽታ ይገነባሉ የተባሉት ዶክተሩ፣ ኢትዮጵያውያንን በአሰቃቂ ሁኔታ እየጨፈጨፈ ካለው ቡድን ጋር ሆነው መሥራታቸውን ቀጥለውበታል:: የቡድኑ ቃል አቀባይ እስኪመስሉ ድረስ ።
አጀንዳቸው ሁሉ የአሸባሪው ትህነግ ጉዳይ ሆኗል:: ቡድኑ እንደሚያደርገው የትግራይ ሕዝብ በረሃብ አደጋ ውስጥ ነው፣ የመንግሥት ኃይሎች ትግራይ ውስጥ የዘር ጭፍጨፋ አካሄዱ፣ መሠረታዊ አገልግሎት ተቋማት ባለመኖሩ ሳቢያ ከቤተሰቦቼ ጋር መገናኘትም ሆነ ገንዘብ ልልክላቸው አልቻልኩም፣ ወዘተ እያሉ መክሰሳቸውን ቀጥለዋል::
ቡድኑ በሚቆጣጠራቸው አካባቢዎች የሚገኙ የኢትዮጵያ ሕፃናት፣ እናቶች፣ አዛውንቶች በአጠቃላይ ሕዝቦች ጉዳይ ለዶክተሩ ጉዳያቸው አይደለም፤ የአማራ ክልልና አፋር ክልሎችን ያን ያህል ወርሮ ባሰቃየበት ወቅት፣ እነዚያ ሁሉ ንጹኃን ኢትዮጵያውያን በጅምላ ጭፍጨፋ ሲገድሉ ዶክተሩ የተነፈሱት የላቸውም፤ እነዚያ ሁሉ የጤና ተቋማት ሲፈርሱ፣ ሲዘረፉ ለእሳቸው ምናቸውም አልነበረም:: በሚሊዮኖች የሚቆጠሩ ዜጎች የክረምት ዶፍ በሚወርድበት ወቅት ከቀዬቸው ተፈናቅለው በየድንኳኑና በየትምህርት ቤቱ ተጠልለው አሳራቸውን ሲያዩ ያሉት አልነበራቸውም::
በአሸባሪው ትህነግ ተላላኪዎች እነ ሸኔ በመላ ኦሮሚያና በአንዳንድ የአማራ ክልል አካባቢዎች ስንትና ስንት ንጹኃን ዜጎች በአሰቃቂ ሁኔታ ሲጨፈጨፉ እሳቸው ያሉት የለም:: ዝምታቸው የቡድናቸውን ድል እያጣጣሙ ነው ያሰ ኛቸዋል::
ቡድኑ በሚሠራቸው ድራማዎች በቀጥታ በመተወን የትግራይ ሕዝብ ተራበ፣ መድኃኒት አጣ፣ መሠረተ ልማት ፈረሰበት፣ ስልክ ባንክ መብራት ውሃ ተቋረጠበት ሲሉ ነው የሚሰሙት:: መሠረተ ልማት አውዳሚው፤ ማህበራዊ አገልግሎቶች እንዳይቀርቡ ዋነኛው እንቅፋት ትህነግ መሆኑን ስረ መሠረቱን ጠቅሰው ትንፍሽ አላሉም፤ ጦርነቶቹን ሁሉ የሚጀምራቸው እሱው እንደሆነም እያወቁ የጦርነት ጀማሪው የኢትዮጵያ መንግሥት ነው ከሚለው ቡድን ጋር መወዛወዛቸውን ቀጥለዋል::
የእናት አገርን ውለታ መካድ ይሏል እንዲህ ነው:: ያጎረሰን እጅ መንክስ ማለት እንዲህ ነው:: ሰውየው ቀንደኛ የኢትዮጵያ ጠላት መሆን የጀመሩት አገራዊ ለውጡን ተከትሎ ነው:: በታላቅ ዓለም አቀፍ ኃላፊነት ላይ ተቀምጦ በለውጡ ላይ አኩርፎ ትግራይ የመሸገውን ትህነግ መደገፍ ቀንደኛ የኢትዮጵያ ጠላት መሆን ነው::
አገራቸውን በአጠቃላይ አፍሪካን በተለያየ መልኩ ፕሮሞት ያደርጋሉ፤ ተጠቃሚም ያደርጋሉ ተብለው የተጠበቁት ዋና ዳይሬክተሩ፣ ኢትዮጵያን ካላፈረስኩ እያለ ለሚደክመው ቡድን፣ በሰው ልጅ ላይ አሰቃቂ የተባሉ ግድያዎች እየፈጸመ ያለው ትህነግ ዋና ቃል አቀባይና ጠበቃ ሆነው እየሠሩ ናቸው:: ዓለም በአደራ የሰጣቸውን የዓለም ጤና ድርጅትነት ታላቅ ቦታ የአሸባሪው ትህነግ ቃል አቀባይ ቢሮ አድርገውታል:: የሚመሩት ድርጅት በእሳቸው መጥፎ ተግባር የተነሳ በዓለም ጤና ድርጅት የሕወሓት ቢሮ ቢባል አያስኬድም ተብሎ አይታሰብም:: እኔ ያስኬዳል እላለሁ::
በግላቸው ቡድኑን ቢደግፉ ብዙም ችግር ላይኖረው ይችላል ተብሎ ይታሰብ ይሆናል:: ከያዙት ቦታ እና አሸባሪ ቡድኑ በሰው ልጅ ላይ እያደረሰ ካለው እኩይ ተግባር አኳያ ሲታይ ግን ይህን ቡድን ደግፈው ሽንጣቸውን ገትረው ከጎኑ መቆማቸው በእጅጉ ኃላፊነት የጎደላቸው ያሰኛቸዋል::
ቡድኑ መንግሥትን በኃይል ለመጣል የሞከረ፣ የአገርን ሉአላዊነት ለአመታት ሲያስጥብቅ የኖረውን የሰሜን እዝ በመካድ ከጀርባው የወጋ ጨፍጫፊ ነው፤ ሕፃናትን እናቶችን አቅመ ደካሞችን የሚጨፍጨፍ የሚያስጨፈጭፍ እንደመሆኑ ከዚህ ቡድን ጋር ላይ ታች ማለት በራሱ ከጨፍጫፊዎቹ፣ ከከሀዲዎቹ፣ ያስመድባል::
አብረኸው የምትውለው የምታድረው ሰው፣ አብረኸው የምትሠራው ሰው አገር እያወከ ያለ ከሆነ ከእሱ ጋር የሚኖርህን ግንኙነት በልኩ ማድረግ የግድ ነው:: አለበለዚያ ከኑግ ጋር የተገኘ ሰሊጥ አብረህ ተወቀጥ ይመጣል፤ እያወቁ የሌባ ዕቃን ማስቀመጥ ወይም ለሌባ መንገድ መምራት ሌባ አያሰኝም ተብሎም አይወሰድም:: እያወቁ አብሮ መስረቅ ውስጥ ከተገባ ደግሞ ሙልጭ ያለ ሌባ መሆን ነው::
ጓዶቻቸው ኢትዮጵያ መፍረስ አለባት፤ እናፈርሳታለን ይላሉ፤ እሳቸውም ኢትዮጵያውያንን በአሰቃቂ ሁኔታ ሰጨፈጭፉ ከማውገዝ ይልቅ ጭፍጨፋው የተፈጸመው በመንግሥት ነው እያሉ ዓለም አቀፉ ማኅበረሰብ በኢትዮጵያ ላይ ማዕቀብ እንዲጥል ሌላም ሌላም እርምጃ እንዲወሰድ ሲወተውቱ ከቆዩት መካከል ናቸው፤ አሁንም እየወተወቱ ናቸው:: በትግራይ ለተፈጠረው ቀውስ ሙሉ በሙሉ ተጠያቂው ትህነግ ሆኖ ሳለ እሳቸው ትህነጎች በሀሰት የሚያሰራጩትን መረጃ ይዘው መንግሥትን መክሰስን ሥራቸው አድርገውታል::
የዓለም ጤና ድርጅትን እየመሩ ለአንድ አሸባሪ፣ ጦረኛና ገዳይ ቡድን በመወገን ነጋ ጠባ የሚያሰራጩት መረጃ ያን ትልቅ ተቋም የአሸባሪ ትህነግ ቅርንጫፍ ቢሮ የማድረግ ያህል ነው። እውነታው የተቋሙን የመተዳደሪያ ቻርተር የሚጻረር፤ የሰውየው የኃላፊነት መዝቀጥ የቱን ያህል እንደሆነ የሚያሳይ ጭምር ነው::
ዘካርያስ ዶቢ
አዲስ ዘመን ነሐሴ 27 /2014