የከፍተኛ ትምህርት አግባብነት እና ጥራት ኤጀንሲ ስሙን ቀይሮ የትምህርት እና ስልጠና ባለስልጣን ሆኗል።ለምን ስሙን ቀየረ? ስሙን በመቀየር ብቻ የቁጥጥር ስራውን በተገቢው መልኩ መፈፀም ያስችላል ወይ? የጥራት ችግር ያለው በመላው አገሪቱ ሆኖ የግል ከፍተኛ ትምህርት ተቋም ላይ ብቻ ለምን ትኩረት ይደረጋል? የመንግስት ተቋማትንስ ለምን አልታዩም? እንዲሁም በባለስልጣን ስራ ላይ የባለስልጣናት ጣልቃ ገብነት እስከምን ድረስ ነው? በሚሉና በሌሎችም ተያያዥ ጉዳዮች ላይ የባለስልጣኑን የኮሙኒኬሽን ጉዳዮች ዳይሬክቶሬት ዳይሬክተር አቶ ታረቀኝ ገረሱ ጋር ቆይታ አድርገናል ።መልካም ንባብ።
አዲስ ዘመን፡- የከፍተኛ ትምህርት አግባብነት እና ጥራት ኤጀንሲ ስሙን ቀይሮ የትምህርት እና ስልጠና ባለስልጣን ተባለ ።ስም መቀያየር ለትምህርት ጥራት ቁጥጥርም ሆነ ክትትል ምን ፋይዳ አለው? ይልቅ ቁጥጥር እና ክትትሉ ላይ ማተኮር አይሻልም?
አቶ ታረቀኝ፡- መጀመሪያ ስለተቋሙ ሥራ እናንሳና ከዛ ወደ ስም ስያሜው መቀየር እንነጋገራለን። ተቋሙ መጀመሪያ የከፍተኛ ትምህርት አግባብነት እና ጥራት ኤጀንሲ በሚል የተቋቋመው በ1995 ዓ.ም ነው። ከዛ ጀምሮ በአገሪቱ ውስጥ ያሉ የከፍተኛ ትምህርት ተቋማት የሚሰጡትን ትምህርት እና ስልጠናዎችን አግባብነት እና ጥራታቸውን የማረጋገጥ ሥራ ዓላማን ይዞ ሲሠራ ነበር።ይሁንና ሌሎችም የተለያዩ ዋና ዋና ሥራዎችን ሲያከናውን ነበር።
የከፍተኛ ትምህርት የጥራት ኦዲት ሥራን ሲያከናውን ቆይቷል።የዕውቅና ፈቃድ አሠጣጥ ላይም ሲሠራ ነበር።የትምህርት ማስረጃዎችን ህጋዊነትን የማረጋገጥ እና የአቻ ግመታ ሥራም ሲሠራ ቆይቷል፡፡
እነዚህን ሥራዎች ሲሠሩ በጥራት ኦዲት ዙሪያም የተሠሩ ሥራዎች አሉ። በዛን ጊዜ እስከ 2011 ወደ 90 የሚደርሱ የከፍተኛ ትምህርት ተቋማትን ጥራት ኦዲት አካሒደናል።የጥናት ኦዲት ሲደረግ አስር መስፈተርቶች አሉ።
አዲስ ዘመን፡- ይቅርታ ላቋርጦት።የትምህርት ጥራት ችግር እንደሚታወቀው በሁሉም ዘንድ አለ።እዚህ ላይ እናንተ የግሎቹን የከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ላይ እንጂ የመንግስትን ተቋማትን ጥራት አትከታተሉም እየተባላችሁ ትታማላችሁ።ይህንንም አያይዘው ይመልሱልኝ።ለምን የመንግስት የትምህርት ተቋማት ላይ ቁጥጥር አታደርጉም?
አቶ ታረቀኝ፡- አይ ጥራት ላይ የምንሰራው እና የምናየው ሁለቱም ላይ ነው። የግልም ሆነ የመንግስት ከፍተኛ የትምህርት ተቋሞችን እናያለን። ነገር ግን የመንግስቶቹ የትምህርት ተቋማት ልክ እንደኛ ኤጀንሲ ሁሉ የሚቋቋሙት በአዋጅ ነው። ኤጀንሲው በአዋጅ የተቋቋሙ ተቋማትን ለመቆጣጠር የተሰጠው ስልጣን ላይ ክፍተት ነበር። ነገር ግን በሁለቱም ላይ ይሠራል። እውቅና እና ፍቃድ ግን የሚመለከተው የግሎቹን ብቻ ነው።
በእርግጥ የመንግስቶቹን ለመቆጣጠር የአዋጅ ክፍተት ብቻ ሳይሆን ተቋሙ ራሱ ከውስጥ ችግር ነበረበት።ማለትም አደረጃጀት ፈጥሮ መቆጣጠር ላይ ድክመት እንደነበረበት አይካድም።
አዲስ ዘመን፡- ድክመት ነበረበት ሲሉ እስኪ በደንብ ያብራሩት ? ተቋሙ ድክመት የነበረበት በምን በኩል ነበር?
አቶ ታረቀኝ፡- የአደረጃጀት ችግር ነበር። አደረጃጀቱ አሁንም ድረስ አላለቀም።ሌላው የባለሞያ ቁጥር ነው። ከተቋሙ ሥራ እና ተልዕኮ አንፃር የባለሞያው ቁጥር እጅግ በጣም ትንሽ ነው።ከ15 የማይበልጡ ባለሞያዎች ብቻ የሚኖሩበት ጊዜም ነበር።ባለሞያ ቢቀጠርም ወዲያው ይለቅ ነበር። ምክንያቱም እውነቱን ለመናገር የመስሪያ ቤቱ ሁኔታ በአጠቃላይ ጥሩ አልነበረም።
አዲስ ዘመን፡- መስሪያ ቤቱ ጥሩ አልነበረም ሲሉ? ምን ማለት ነው?
አቶ ታረቀኝ፡- አዎ! በግልፅ ለመናገር የመልካም አስተዳደር ችግር ነበር። ለዚህም ብዙ ማስረጃዎች አሉ።በተጨማሪ የአመራር ቁርኝነት ችግር ነበር።ይህንን ስል በፊት ምንም የተሠራ ነገር የለም ማለቴ አይደለም።ብዙ ተቋማት የጥራት ኦዲት ተደርገዋል። እስከ 2011 ዓ.ም 90 አካባቢ የሚሆኑ ተቋማት ፍቃድ እና እውቅና ተሰጥቷቸው እየተሠራ ነበር።የአቻ ግመታ ሥራም ሲሠራ ነበር።
የትምህርት ማስረጃ የማጣራት ሥራም ሲሰራ ነበር።የመጀመሪያ የሆኑ መሠረታዊ ሥርዓት የመዘርጋት ሥራ ተሠርቷል።ነገር ግን የተቋቋመበትን ዓላማ ግብ ለመምታት ግን ችግሮች እንደነበሩ አይካዱም።ይህንን ህዝቡ ያውቀዋል።
የግል ከፍተኛ የትምህርት ተቋማት ጥሩ የሚሠሩ እንዳሉ ሁሉ ምን ያህል ሰርተፍኬት የሚሸጡ እንዳሉ ይታወቃል።ከዛ አንፃር እውቅና እና ፈቃድ መስጠት ብቻውን በቂ አይደለም። አንዳንዴ ለሪፖርት ግብዓት ብቻ ማስታወቂያ ላይ የምናወጣቸው ነገሮች ነበሩ።ሁለት እና ሶስት ተቋም ብቻ ተቀጣ ብለን በዓመት የሆነች ነገር አውጥተን ከሪፖርት አናልፍም ነበር።
እውቅና እና ፈቃድ ከመስጠት ውጪ ቀጣይነት ያለው ክትትል አይካሔድም ነበር። ክትትል ማድረግ አንዱ የተቋሙ ሥራ ነው። በዛ ውስጥ ሰሞኑን እንዳደረግነው ድንገተኛ ግምገማ ማድረግ ነው።ዓመቱን ሙሉ ቁጭ ብሎ አንድ ጊዜ ብቻ የሚካሔድ መሆን የለበትም። በየጊዜው የህብረተሰቡንም ጥቆማ መስማት አለብን። ጥቆማም ባይመጣ ራሱ ተቋሙም ማቀድ አለበት። እንዲህ ዓይነት ሥራዎች አይሠሩም ነበር።
ሌላው የሥርዓት ማነስ ነው።እነዚህ ከፍተኛ የትምህርት ተቋማት አመሰራረታቸው ራሱ በትክክለኛ አካሔድ ላይ የተመሰረተ አይደለም።ትክክለኛ ከትምህርት ጋር የተገናኘ የሥራ ፈቃድ ራሱ አልነበራቸውም።
አዲስ ዘመን፡- ምን ማለት ነው ? የሥራ ፈቃዳቸው ምን ነበር?
አቶ ታረቀኝ፡- ሲቋቋሙ ራሱ የሆነ የችርቻሮ ወይም የጋራዥ ፍቃድ ይዘው የተቋቋሙ ነበሩ።አንድ አካል የትምህርት ሥራ ላይ ለመሳተፍ ከፈለገ በዛ ላይ የተለየ ዕውቀት ሊኖረው ይገባል። የትምህርት ዓይነቱ ራሱ በየትኛው ላይ ይሳተፋል? ለምሳሌ በጤና ወይስ በቢዝነስ የሚለው መለየት አለበት። ነገር ግን እስከ 2011 ዓ.ም ድረስ ያለው ሁኔታ በምንም ዓይነት ከትምህርት ጋር የማይገናኝ ፈቃድ የነበራቸው ለምሳሌ የአስመጪ እና ላኪ ፈቃድ ይዘው የትምህርት ማስተማሪያ ተቋም ኮሌጅ ይከፍቱ ነበር፡፡
አዲስ ዘመን፡- እነዚህን ለመዝጋት አትችሉም ነበር?
አቶ ታረቀኝ፡- ተቋሙ ራሱ ባለቤቱ ማን ነው? የሚለውን መጠየቅም አይቻልም ነበር።ዜጋ እየተማረበት ኮሌጅ ተነስቶ ቢጠፋ እንኳ መያዣ እንኳን የለውም ነበር።ሁለት ተቋማት እኮ ጠፍተዋል።ዘመን ሊደርሽፕ ኤንድ ዴቨሎፕመንት ማኔጅመንት ኢንስቲትዩት በሚል ቀበና አካባቢ የተከፈተው ኮሌጅ እና ሴንተራል ጤና ኮሌጅ ተነስተው በቀላሉ ተማሪ በትነው ጠፍተዋል።እስከዚህ ድረስ ቀላል ሆኖ ነበር።
ሌላው እስከ አሁን የተከማቸው የትምህርት ማስረጃ የማጣራት ሥራ እጅግ በጣም ትልቅ ጉዳይ ነው።እጅግ በጣም የተከማቸ እና ውሳኔ የሚያስፈልገው ነው።ብዙ ተጣርቶ ተለይቶ ቁጭ ብሏል። በመቶ ሺህ የሚቆጠር የትምህርት ማስረጃ ተጣርቷል።በዛ ጊዜ ግን ማስረጃ ማጣራት ላይ ይህን ያህል ትኩረት ተሰጥቶ እየተሰራ አልነበርም።ለእዚህ አንዱ የአመራር የቁርጠኝነት ችግር ነው።
ሥርዓቱ እያለ ያለመወሰን ችግር ይስተዋል ነበር።የሰው ሃይል እጥረትም ቢኖር በተቻለ አቅም ወስኖ መስራት ያስፈልጋል።እነኚህ ሁሉ ነገሮች የዛኔ ያልተከናወኑ የተጠራቀሙ ሥራዎች ነበሩ። ሌላው ከተቋም ህጋዊነት ጋር ተያይዞ ዞረን እየሠራን ያለነው በታሪክ ለመጀመሪያ ጊዜ የተፈፀመ ነው።ድንገተኛ ግምገማ በማድረግ ችግር ያለባቸውን በዙር እየገለፅን ነው።
ከ2011 ዓ.ም ጀምሮ በአዲስ አበባ እና በአዲስ አበባ ዙሪያ በህገወጥ ተቋማት ላይ እርምጃ እየተወሰደ ነው። በ2011 ዓ.ም ወደ 46 የግል ተቋማት ላይ እርምጃ የተወሰደ ሲሆን፤ በየጊዜው የግል እና የመንግስት ተቋማት የትብብር ስልጠና መስጠት የለበትም ቢባልም አሁንም ድርጊቱን የሚፈፅሙ አሉ። ከኢቢኤች ጋር የገጠመን ችግርም ተመሳሳይ ነው። የከሰሰን በውሸት ነው። እውቅናም ሆነ ፍቃድ የለውም።
ከሌሎችም ጋር እየተካሰስን ነው።ድንገተኛ ግምገማ እየተካሔደ ህብረተሰቡም ጥቆማ ሲያመጣ እየተሠራ ነው።በዚህ ዓመት በ2014 ብቻ 305 ካምፓሶች ላይ እርምጃ ወስደናል። በዙር እየገለፅናቸው ነው።አሁን ሶስተኛው ዙር ላይ ነን።
አዲስ ዘመን፡- የምትወስዱት እርምጃ ምንድን ነው? ተቋሞቹን መዝጋት ነው?
አቶ ታረቀኝ፡- አይ እንደየደረጃው ነው።ፕሮግራም መዝጋት አለ፤ ካምፓስ መዝጋት አለ፤ አለፍ ሲል ደግሞ ተቋሙን መዝጋትም ይኖራል።ይህ አዲስ አበባ ላይም አለ።
አዲስ ዘመን፡- በተቋም ደረጃ እንዲዘጋ እርምጃ የሚወሰድበት ወይም የተወሰደበት ምን ያህል ነው?
አቶ ታረቀኝ፡- መረጃው ገና ይጠራል።ነገር ግን ቢያንስ በአዲስ አበባ ብቻ ሶስት ይሆናሉ።ወደ ፊት እነማን እንደሆኑ እንገልፃለን። እንዲህ አይነት ሥራ በፊት አይሠራም ነበር። ያ የተከማቸ ሥራ አሁን እየተሠራ ነው።ቀደም ብሎ የተነሳው ወደ ስም ቅየራው ለመሔድ እነዚህ የተጠራቀሙ ሥራዎችን ችግር መፍታት አንድ ጉዳይ ነው።
በሌላ በኩል ደግሞ የአገሪቱ የቆዳ ስፋት እና የሕዝብ ብዛትም ሲታይ በዚህ በአንድ ተቋም ብቻ ሥራውን ስኬታማ ማድረግ አይቻልም።የትምህርት ጥራትን ለመሥራት የሚቋቋም ተቋም ገለልተኛ መሆን አለበት። ይሔ ችግር አሁንም ቀጥሏል። በአዋጅ ተጠሪነቱ ለትምህርት ሚኒስቴር ነው።
በ2011 ዓ.ም የተደረገው በፊት የነበረውን የባለሞያ እጥረት ማለትም ከ15 የማይበልጠውን በተለይ የኢትዮጵያን በሙሉ ጥራት የሚያዩ የጥራት ኦዲት ላይ የሚሰሩ ባለሞያዎች ቁጥር ከ10 የበለጠ አልነበረም። እውነት ለመናገር በዛ ጊዜም መንግስት ባለሞያ እንዳይቀጠር አልከለከለም። ነገር ግን የአመራር ቁርጠኝነት አልነበረም። አሁን ግን የተደረገው የለውጥ አመራሩ ሲመጣ ማለትም ዶክተር አንዷለም አድማሴ እንደተሾሙ በአንድ ጊዜ ወደ አርባ የሚሆኑ ባለሞያዎች ተቀጥረዋል።
በፊት ተሳስሮ የነበረውን መስፈርት በማቅለል ዜጎች ተቀጥረው ሚናቸውን እንዲወጡ ማለትም ይሔን ያሕል ዩኒቨርስቲ ያስተማረ በሚል ከፍ ያደረጉትን መስፈርት በመቀነስ እና ሲቪል ሰርቪስን በማስፈቀድ በአንድ ጊዜ 42 ባለሞያዎችን መቅጠር ተችሏል።ከዛ በኋላ የሆነው አደረጃጀቱ እንዲህ መሆን የለበትም፤ ብዙ አዳዲስ ክፍሎች ያስፈልጋሉ በመባሉ አደረጃጀቱ ተስተካክሎ ቀርቦ እየተጠየቀ ነው።
አሁን የተሻለ ሁኔታ አለ። ስሙም ከኤጀንሲ ወደ ባለስልጣን ሲቀየር የመቆጣጠር ሃላፊነቱ ይጨምራል። ከዚህም በተጨማሪ በፊት የከፍተኛ ትምህርት እና አግባብነት ኤጀንሲ ነበር። አሁን ግን ትምህርት እና ስልጠና ባለስልጣን ተብሏል። ሃላፊነቱ አሁን ሰፍቷል። በፊት በከፍተኛ ትምህርት ላይ ብቻ ነበር።አሁን ከፍተኛ ትምህርት ብቻ ሳይሆን ቴክኒክና ሞያ እንዲሁም አጠቃላይ ትምህርትን ይመለከታል። ይህንን ሁሉ አጠቃሎ እንዲይዝ የሚመጥነውን ስያሜ ተሰጥቶታል፡፡
በአዲስ መልክ ተቋማት ሲቋቋሙ የሚደረገው መስራት የሚችሉበትን የሰው ሃይል አደረጃጀት እንዲኖር ከስራ ባህሪያቸው ጋር የተመጣጠነ የሰው ሃይል እና አደረጃጀት እንዲኖራቸው ማድረግ ያስፈልጋል። አሁን ስለአደረጃጀቱ አስተያየት እየተሰጠበት ነው።እርሱ ሲያልቅ ውጤቱ የሚታይ ይሆናል።እናም ስሙ ሲቀየር ሃላፊነቱ የሰፋ መሆኑን መታወቅ አለበት።
ምክትል ዋና ዳይሬክተር በፊት አንድ ብቻ ነበር፤ አሁን ግን ሶስት ናቸው። ይህ የሆነበት ምክንያት በየዘርፉ እንዲመሩ በማሰብ ነው። ይሄ አደረጃጀቱ ሲያልቅ ይፋ ይሆናል። በዛ መልኩ ሥራቸውን ለመስራት በሚያስችላቸው መልኩ እንዲደራጅ ተደርጓል። የስም ለውጡም ከዚሁ ጋር የተያያዘ ነው።
አዲስ ዘመን፡- እስኪ ያለፈውን ትተን የአሁኑን እናንሳ። ከ2011 ዓ.ም ጀምሮ ተቋሙ ምን ያህል በነፃነት እየሠራ ነው? ቁጥጥር እናድርግ ስትሉ አመራሮቹ ጣልቃ የሚገቡበት ሁኔታ እያጋጠማችሁ አይደለም? እናንተ ራሳችሁ ከአድሎ ምን ያህል የፀዳችሁ ናችሁ?
አቶ ታረቀኝ፡- ትክክል ነው። መጀመሪያ ለውጥ የሚመጣው ከውስጥ ነው። በውስጥ በኩል ችግር አለ።ከ2011 በኋላም ካለፈው የቀጠለ የውስጥ ሰራተኞች ሳይቀሩ ከግል ተቋማት ጋር ድርሻ ያላቸው እና የጥቅም ግንኙነት የነበራቸው ነበሩ። በቅድሚያ የተደረገው በግልፅ ቁጭ በማለት ከተቋሙ ሰራተኞች ጋር ውይይት በማካሔድ ችግር መፍታት ተጀምሯል።
በእርግጠኝነት ለመግለፅ ቢያስቸግርም ሌላም አለ።እንደሃሜት በአንዳንድ ኮሌጆች ላይ እርምጃ ላለመውሰድ ሰበቡ ከጀርባ ሰው አላቸው ይባል ነበር። ነገር ግን ከውስጥ ቁርጠኝነት ካለ መስራት ይቻል ነበር።
አዲስ ዘመን፡- ይህችን ነገር ግልፅ ያድርጉልን፤ ማለትዎ አንድ ተቋም ላይ ከጀርባ ሰው አለ በሚል ሰበብ ተቋም ላይ እርምጃ አይወሰድም ማለትዎ ነው?
አቶ ታረቀኝ፡- በእርግጥ እንደዚህ ሲደረግ አላየሁም።ነገር ግን እኔ የማውቀው መረጃ እርምጃ ሲወሰድ የትም ቦታ ሔደው ቅሬታ አሰምተው ውሳኔዎችን ያስቀለብሱ ነበር። ለምሳሌ ተጠሪነታችን ለትምህርት ሚኒስቴር ነው። ትምህርት ሚኒስቴር ሄደው ቅሬታ ሲያሰሙ የሚለወጡ ውሳኔዎች ነበሩ። አሁንም ከ2011 ዓ.ም ጀምሮ ግፊቶች አይኖሩም ማለት አይደለም። ነገር ግን ጣልቃ አትግቡብን እያልን በመሆኑ የውጪ ግፊቱ ቀንሷል።
የአሁኑን አመራር ለማሞገስ አይደለም።ከ2011 ዓ.ም ጀምሮ ጣልቃ አትግቡብን በማለት እና በመጋፈጥ እየሠራን ነው። ከዛ ውጪ የገንዘብ አቅም ያላቸው ተቋማት አሉ። ለምሳሌ ኢ ቢ ኤች የሚባል አለ። የፍትህ አካላትን እና አመራሮችን በገንዘብ ሊገዛ ይችላል። የሚደግፈው አመራር ሊኖራቸው ይችላል። ነገር ግን ልናጣራ ስንል ዕውቅና እና ፈቃድ እንደሌለው አወቅን። በዚህ ጊዜ ፕሬስ ኮንፈረስ አዘጋጅቶ ሕዝብን ሲያታልል ነበር። ይህ ተቋም በፍርድ ቤት ከመክሰስ አልፎ ካሳ እስከ መጠየቅ ደርሷል። ለእዚህ ድፍረቱ አመራር ከጀርባ ስላለው ሊሆን ይችላል።
ይህ ድርጅት ከውጪ የመጣ መንግስታዊ ያልሆነ የእርዳታ ድርጅት ነው። ከጅማ ዩኒቨርስቲ ጋር የትብብር ስልጠና ይሰጣሉ። ለዚህ ፈቃድ የላቸውም።ጅማ ዩኒቨርስቲ የሚሠራው በመንግስት በጀት ነው።ነገር ግን ይህ ተቋም አብሮ ሲሠራ የሚጠቀሙት በጀት እንዴት እና በማን ነው? የሚለው ያጠያይቃል። ይሔ ሳይታይ ስልጠና አትስጡ ተብለው ተከልክለው ነበር። እንዴት ተከለከልን ብለው መጥተው ለማስፈራራት ሞከሩ።
እነዚህ አካላት ከጀርባ ሰው አላቸው።እኔም በእነርሱ ዙሪያ መረጃ እንዳልሰጥ ተከልክዬ ነበር።ወደ ተቋማችን የበላይ ሀላፊ በመደወል እኔም መረጃዎችን እንዳልሰጥ ተደርጎ ነበር። አመራሩ ቁርጠኛ ስለነበር ‹‹እኔን ጠይቁኝ›› ብሎ መረጃውን እንድለቅ ተፈቅዶልኛል። አቅጣጫ የሰጠውና ያንን መልዕክት የላከ አመራር ነበር። በአመራሮች ተመክተው መመሪያን የሚጥሱ መኖራቸው አይካድም።
አዲስ ዘመን፡- ስለዚህ አመራሮች ጣልቃ ለመግባት የሚሞክሩበት ሁኔታ ቢኖርም እናንተ ግን ተፅዕኖውን ተቋቁማችሁ እየሠራችሁ ነው ማለት ይቻላል?
አቶ ታረቀኝ፡- ቁርጠኝት ያልኩት ይሔንን ነው።ከ2011 ዓ.ም ጀምሮ ተከሰናል፤ ብዙ ታግለናል።ለማንም ወደ ኋላ አላልንም።አንዱ ችግር ደግሞ የፍትሕ አካላት የሚፈጥሩት ነው።እውነት ለመናገር ምክንያታቸው ምን እንደሆነ አይታወቅም፤ ወይ በገንዘብ ተታለዋል፤ አልያም ጥቅም የሚገኙበት ሁኔታ አለ።ውሳኔ ቶሎ አይሰጡም።አንዳንድ ውሳኔያቸው አድሏዊ ነው።ብዙ ተጨባጭ መረጃዎችም ቀርበው ፍትሓዊ ውሳኔዎች እየተሰጡ አይደለም።
የአገራችን የፍትህ አካላትን በሚመለከት እንግለፅ ካልን ብዙ ተጨባጭ መረጃዎች ቀርበው ፍትሃዊ ውሳኔ እየተሰጠ አይደለም። ሕግ ጥሶ ከመስሪያ ቤቱ ጋር ተካሰን ውሳኔው አንድ መቶ ብር ብቻ መሆኑ አስገራሚ ነው።እንደዚህ ዓይነት በጣም ማሾፍ የሚመስሉ የፍርድ ውሳኔዎች አሉ። ሌሎች ደግሞ ብዙ እስከ አሁን ውሳኔ ያልተላለፈባቸው አሉ። ነገር ግን የፍትሕ አካላቱ ቢያግዙንም ሆነ በወቅቱ ምላሽ ቢሰጡ ሁሉም ተቋማት ምላሽ ይሰጡን ነበር።
በሌላ በኩል ደግሞ በእርግጥ አመራሮችን ተመክተው መስሪያ ቤቱ የሚያስተላልፋቸውን ውሳኔዎች ላለመቀበል የሚያንገራግሩ ተቋማት አሉ። በተጨማሪ በውስጥ በኩል ያለው ችግር ሲታይ ድርሻ ነበራቸው የሚባሉ የነበሩት አምስት አካባቢ የሚሆኑት ባለሞያዎች ለቀዋል።አሁን ሙሉ ለሙሉ ጠርቷል ማለት አይቻልም። ይህን ስል አሁን ድርሻ ያላቸው አሉ ለማለት አይደለም።
አዲስ ዘመን፡- ከላይ ወደ 300 የሚደርሱ ተቋማት ላይ እርምጃ እንወስዳለን ብላችኋል።እንዴት ይህ ሁሉ ተቋም እስከ አሁን ሲሠራ ቆየ? ለምን በፊት ከሥር ከሥር እርምጃ አልተወሰደም?
አቶ ታረቀኝ፡- ከላይ እንደገለፅኩት የተከማቸ ችግር ነበር።አንደኛው የተቋማችን የራሱ የአመራር ቁርጠኝነት ማነስ ሲሆን፤ ሌላው ሥራዎች ቀጣይነት ባለው መልኩ ካለመሰራታቸው ባሻገር የሰው ሃይል ችግርም ነበር። ስለዚህ በፊት በአግባቡ ያልተሠራ የተጠራቀመ ችግር ከ2011 ዓ.ም ጀምሮ እየተሠራ ነው። ከ2011 ዓ.ም ጀምሮ አመራሮች ቁጭ ብለው ተወያይተው ወደ ሥራ ገብተዋል። ነገር ግን ከተቋማትም ጋር መደጋገፍ የለም።
ተጠሪ ተቋም እንደዋና መስሪያ ቤት መደገፍ ባለበት ልክ እየደገፈ አይደለም። ከሪፖርት ግምገማ ባለፈ ሕገወጥ ተቋማት ሲበዙ እና ሲያስቸግሩ ድጋፍ በሚያስፈልግበት ሰዓት መስሪያቤቱን እያገዙት አልነበረም።አሁን የሌለው የሳይንስ እና ከፍተኛ ተቋማት ሚኒስቴር ሲቋቋም በወቅቱ የነበሩ አመራሮች ጥሩ ሠርተዋል።ሰራተኛውን አግኝተው ከአመራሩ ጋር ያለው ችግር ምንድን ነው? ብለው ተወያይተው ተደጋግፈዋል። የወቅቱ ሚኒስትር ፕሮፌሰር ሒሩት ወልደማርያም በሰፊው ድጋፍ ሲያደርጉ ነበር።
ቁጭ ብለን ከተወያየን በኋላ አዲስ አበባ እና በአዲስ አበባ ዙሪያ ድንገተኛ ምርመራ በማድረግ በ2011 ዓ.ም ወደ 46 ሕገ ወጥ ተቋማት ተገኙ። እነዚህን ከ2011 በፊት ቀድሞ ማስቆም ይቻል ነበር። የመንግስት ተቋማትንም ክትትል በማድረግ እርምጃ ተወስዷል። ውሳኔዎች ተሰጥተዋል። አንዳንድ ክልከላዎች ተደርገዋል።
አዲስ ዘመን፡- የመንግስት ተቋማት ላይ ምን ያህል እርምጃ ወሰዳችሁ?
አቶ ታረቀኝ፡– የመንግስት ተቋም ዙሪያ በ2012 ዓ.ም አካባቢ የትብብር ስልጠና የሚሰጡ ተቋማት ነበሩ።የግል ተቋማት ከመንግስት ተቋማት ጋር በትብብር ስልጠና መስጠት አይቻልም፤ ተብሎ የተከለከለውን ማስተግበር ተችሏል። መመሪያው የወጣው በ2006 ዓ.ም ነበር።ነገር ግን መተግበር የተጀመረው በ2012 አካባቢ ነው።እዛ ላይ በዝርዝር ቢታይ አብረው በትብብር መስራታቸው ብዙ ችግር ነበረበት።ከዚህ ባለፈ አዋጁን ለማስተግበር ብዙ ሠርተናል ለማለት እቸገራለሁ፤ ብዙ ይቀረናል።
ቀጥሎ ለምን አሁን 300ዎቹ ላይ እርምጃ ተወሰደ? ለሚለው በ2014 ዓ.ም በስፋት የተሠራው በፊትም ሲታቀድ የነበረ ሥራ ነው። ወደ 82 የሚሆኑ ማስጠንቀቂያ የተሰጣቸው ናቸው። አዲስ አበባ ላይ 106 ተቋማት ከማስጠንቀቂያ እስከ ተቋም መዝጋት እርምጃ የተወሰደባቸው አሉ። ፕሮግራም የተዘጋባቸው፣ ካምፓስ የተዘጋባቸው ወይም ተቋም የተዘጋባቸው አሉ።በክልል በመጀመሪያ ዙር ወደ 95 ተቋማት ይፋ አድርገናል። በመቀጠል 104 ተቋማትን ይፋ አድርገናል። 300 ካምፓሶች ላይ እርምጃ ተወስዷል።
ይህ እርምጃ ሲወሰድ ተጠራቅሞ የመጣ በፊት የተለመደ ከ1995 ዓ.ም ጀምሮ ምን ያህል ህገወጥ የትምህርት ማስረጃ ሊኖር እንደሚችል መገመት ከባድ ነው።ሌላው የአደረጃጀት ችግር ነው።ተቋሙ መስራት በሚችልበት መልኩ እንዲደራጅ ብዙ ጊዜ ጥያቄ ቀርቧል። ሚኒስቴር መስሪያቤቱም ተገቢውን ድጋፍ አልሰጠም። የሚመለከታቸው አካላትም አልወሰኑበትም።ስለዚህ እየተጓተተ መጥቶ፤ አሁን ትኩረት ተሰጥቶት የተሻለ ሁኔታ እየተፈጠረ ነው።
በ2011 ዓ.ም ላይ እኛ ጋር መረጃ ያለው 75ሺህ ተመራቂ እና ተማሪ ብቻ ነበር። ተቋማቱን የምታስተምሩትን እና ያስተማራችሁትን ተማሪ መረጃ አምጡ ብለን ማስገደድን ማንም አልከለከለም። ይህም የውስጥ የራሳችን ችግር ነው።አሁን ግን በአራት ዓመት ውስጥ አንድ ነጥብ አንድ ሚሊየን መረጃ ተሰብስቧል፤ አሁንም ገና ነው።አሁን የከፍተኛ ትምህርት መረጃ አስተዳደር ስርዓት ተዘርግቷል። እዛው ሆነው በተቋማቸው ቶሎ መረጃ እንዲያስገቡ ይደረጋል። ሌላው ከዚህ በፊት ያልነበረው የኦን ላይን ትምህርት መመሪያ ኢትዮጵያ ውስጥ አልነበረም። አሁን ግን መመሪያ ተግባራዊ እየተደረገ ነው።
በተጨማሪ የግል ተቋማት ራሳቸው ተሳትፈው ያፀደቁት የሥነ ስርዓት መመሪያ አለ።እርሱ ነገር ሲጓተት መጥቶ አሁን ገና ተግባር ላይ ይውላል።በፊት አንድ ተቋም ምን ሲያጠፋ ምን ይቀጣ? የሚለው ግልፅ አልነበረም። ይህም የተጀመረው ቆይቷል። ተግባራዊ እንዲሆን የተደረገው ግን አሁን ነው። ይሔ በፊት ምን ያህል ብዙ ችግር እንደነበረና ምን ያህል እንዳልተሰራበት ያሳያል።
ከ2011 ጀምሮ ከተጨመረው የተወሰነ ባለሞያ ውጪ አሁንም ገና አደረጃጀቱ አልተቀየረም።ደመወዝ አከፋፈሉም ተመሳሳይ ነው፡፡ ሆኖም ባለን ዓቅም ብዙ ነገር እየሠራን ነው።
አዲስ ዘመን፡- አሁን የትምህርት ጥራት ላይ እየሠራን ነው ብትሉም ዛሬም ችግሩ አልተቀረፈም።ማሳያው አንዱ ሲኦሲን የሚያልፈው ቁጥር ውስን መሆኑ ነው።ሲ ኦ ሲን በተመለከተ ምን ይላሉ?
አቶ ታረቀኝ፡– ሲኦሲ 2003 እና 2004 አካባቢ የተጀመረ ነው። ሲጀመር ጥራትንም ለማረጋገጥ ነው። የኛ ተቋም ዲግሪ ለመማር ማለትም ከቴክኒክ እና ሙያ የተመረቁ ሌቭል 4 ሲኦሲ ማለፋቸውን ያረጋግጣል።አንዱ ድንገተኛ ግምገማ ሲደረግ የተማሪዎች ፋይል በድንገት ሲታይ፤ በዚህ ዙሪያ ሰፊ ችግር መኖሩ ታይቷል። ተማሪው ራሱ ከተቋሙ ጋር ተስማምቶ ማሟላት ያለበትን መስፈርት በቀጣይ አሟላለሁ ብሎ ቃል ገብቶ እንደሱቅ ዱቤ ሌላ ጊዜ እናመጣለን ብለው ስምምነት ተፈራርመው የሚማሩ እና የሚያስተምሩ መኖራቸው ታውቋል።
ተቋሙ በዚህ ምክንያት ለሚደርስ ኪሳራ ሃላፊነቱን ላለመውሰድ ተማሪን ያስፈርማል። ተቋሙ ብቻ ሳይሆን ዜጋውም ወደ ስህተት ይገባል። ከሲኦሲ ጋር በተያያዘ ብዙ ተቋማት ችግር ውስጥ የሚሆኑበት ሁኔታ አለ።ብዙ ተመራቂዎች እስከ ላይ አመራርም ድረስ ማለት ነው።
አዲስ ዘመን፡- ተቋሙ በትክክል ሀላፊነቱን ቢወጣ የጥራት ችግር ይህን ያህል የተወሳሰበ አይሆንም ነበር የሚሉ አሉ ለዚህ ምን መልስ አላችሁ።
አቶ ታረቀኝ፡- ሲኦሲውም አንዱ የጥራት ማስጠበቂያ መንገድ እኮ ነው።ሲኦሲውን እንዲያልፉላቸው ተማሪዎቻቸውን ያበቃሉ።ይሔም አንዱ መንገድ ነው። የእኛ ሚና ጥራትን ከማስጠበቅ አኳያ የጥራት ኦዲት የሚባል አለ።ነገር ግን ተቋማት የሚሰጣቸውን ግብረመልስ ተግባራዊ ባያደርጉ ቅጣት የለውም። ራሳቸውን እንዲቀይሩ ምክር ብቻ ይሰጣል። ክትትል ብቻ ይደረጋል።
አሁን የጥራት ኦዲት ራሱ አስገዳጅ እንዲሆን እየተሠራ ነው።እዚህ ላይ ድክመት አለ።አደረጃጀቱ ይህንን ሊያሰራ በሚችል መልኩ ይሆናል። ሌላው ውሳኔዎች እንዳይቀለበሱ ይሠራል።በእርግጥ የተጠሪነት ጉዳይም አንድ ነገር ነው። ተቋሙ በዚህ መልኩ በአዋጅ ስለተቋቋመ እርሱን መንካት አንችልም።
አዲስ ዘመን፡- ስለነበረን ቆይታ በዝግጅት ክፍሉ ስም አመሰግናለሁ።
አቶ ታረቀኝ፡- እኔም አመሰግናለሁ።
ምህረት ሞገስ
አዲስ ዘመን ነሐሴ 11 /2014