በወጣቶች ተወዳጅ ከሆኑ ድምጻውያን አንዱ ነበር። ሙዚቃዎቹ ከመዝናኛት ባለፈ ጠቃሚ ጭብጥ ያላቸው ናቸው በሚል በሀያሲያን ዘንድ ይደነቃል። ነገር ግን ይህ ባለ ታላቅ ተሰጥኦ አርቲስት ከዚህ ዓለም በሞት የተለየው ገና በዘመኑ እኩሌታ ላይ ነበር። ይህ በጊዜ የተቀጠፈ አበባ ስሙ ኢዮብ መኮንን ይባላል። ከዚህ ዓለም በሞት የተለየንም በዚህ በያዝነው ወር ነሐሴ 12 ቀን 2005 ዓ.ም ነው። ዛሬ የዚህን ተወዳጅ ድምጻዊ የሕይወት ታሪክ በአጭሩ እንዳስሳለን።
ድምጻዊ እዮብ መኮንን ዘውዴ ከአባቱ ከአቶ መኮንን ዘውዴ ይመኑ እና ከእናቱ ወይዘሮ አማረች ተፈራ የምሩ ጥቅምት 12 ቀን 1967 ዓ.ም በጅጅጋ ከተማ ጭናቅሰን ገብርኤል አካባቢ ተወለደ። እድሜው ለትምህርት ሲደርስ የአንደኛ ደረጃ ትምህርቱን በጅጅጋ አንደኛና መለስተኛ ሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤት፤ ከፊል የሁለተኛ ደረጃ ትምህርቱን ደግሞ ከወላጅ አባቱ ጋር ወደ አስመራ በመሄድ የተከታተለ ሲሆን፤ ቀሪውን የሁለተኛ ደረጃ ትምህርቱን ደግሞ ወደ ጅጅጋ በመመለስ ተምሯል። በ1991 ዓ.ም. በአጋጣሚ ወደ አዲስ አበባ የሚያመጡ ፈቃደኛ ሰዎች በማግኘቱ እራሱን ያስተዳድርበት የነበረውን የፎቶግራፍ አንሺነት ሥራን ትቶ፣ በ24 ዓመቱ ወደ አዲስ አበባ በመምጣት ካዛንቺስ አካባቢ በሚገኘው የያኔው ፋልከን ክለብ ድምጻዊነቱን “ሀ” ብሎ ጀመረ።
በኢዮብ የሙዚቃ ሕይወት ውስጥ የሬጌ ንጉሱ ቦብ ማርሌይ እና የኦሮምኛ ሙዚቃ ንጉሱ አሊ ቢራ ተጽእኖ ከፍ ያለ ነው። በተለይ አሊ ቢራ ለእዮብ ወደ ሙዚቃ መግባት ትልቅ አስተዋጽኦ አለው። “ልጅ እያለሁ ወደ ትምህርት ቤት ስሄድ ብዙውን ጊዜ የመስማት እድል አጋጥሞኝ የነበረው የአሊ ቢራን ሙዚቃ ነበር” ብሏል በአንድ ቃለ መጠይቁ ላይ። በዚህ መልኩ የተጀመረው የኢዮብ የሙዚቃ
ሕይወት አዲስ አበባ ከመጣ በኋላ በክለቦች በመጫወት እያደገ ሄዷል። በተለይም ዛየን ባንድ ውስጥ የነበረው ተሳትፎ ከፍተኛ ነበር።
ከዚያም እዮብ የመጀመሪያ አልበሙን አወጣ። ወቅቱም በኢትዮጵያ ሚሊኒየም ሰሞን ነበር። አልበሙ እንደቃል የሚል ስያሜ ያለው ሲሆን ነገር ግን አዘፋፈኑ ከተለመደው የኢትዮጵያ ሙዚቃ አካሄድ ለየት ያለ በመሆኑ መጀመሪያ ላይ ለመደመጥ ጊዜ ወስዶበት ነበር። “ለሰባት ወራት ገደማ አልተደመጥኩም ነበር” ይላል። እንዲያውም የሙዚቃው አለመደመጥ ወደ ሌላ ሙያ እንዲያተኩር ገፋፈቶት እንደነበር ይናገራል። ከዚያ ግን ጸጥታው እየተገፈፈ የኢዮብ ሙዚቃዎችም የህዝብን ጆሮ መያዝ ጀመሩ። ከዚያ በኋላ ያለው ታሪክ ነው። ኢዮብ ብዙዎች ጆሮ ላይ ታትሞ ቀረ። እስከዛሬም አልወጣም።
ኢዮብ ሙዚቃን ለማህበረሰብ ግንባታ ማስተማሪያነት መጠቀም አላማ አድርጎ የሚሰራ ሰው ነው። “በኔ ሙዚቃ ሰዎች እንዲስቱ አልፈልግም” ይላል። ይህ አላማው በሙዚቃውም ሆነ በሙዚቃ ማጀቢያ ቪዲዮም ውስጥ ይታያል። የሚያውቁትም ሰዎች እዮብ በስራዎቹም ሆነ በአኗኗሩ ቁጥብ እንደሆነ ይናገራሉ። የመጀመሪያ አልበሙ ተወዳጅ በሆኑ ሙዚቃዎች የተሞሉ ናቸው። በተለይም እንደ ነቅቻለሁ ፤ ነገን ላየው ፤ ደብዝዘሽ ፤ ይዘባርቃሉ፤ ያሉት ሙዚቃዎች ዛሬም ድረስ እንደ አዲስ የሚደመጡ ሆነው አሉ።
የኢዮብ ሁለተኛ አልበም ከመጀመሪያው አልበም ከ10 ዓመት በኋላ ነበር የወጣው። ይህኛውም አልበም እንደመጀመሪያው በአድማጩ ዘንድ እጅጉን ተወዶለታል። የአልበሙ መጠሪያ እሮጣለሁ የሚል ሲሆን ጠንካራ የሆኑ መልእክቶችን ያዘሉ ተወዳጅ ሙዚቃዎች ስብስብ ነው። ይህ አልበም ለየት የሚያደርገው እዮብ ከዚህ ዓለም በሞት ከተለየ በኋላ የወጣ መሆኑ ነው። በሕይወት ሳለ ሁለተኛ አልበሙን መሥራት እንደጀመረ ስለተገለጸ፣ ብዙዎች የአልበሙን መለቀቅ በጉጉት ይጠብቁ ነበር። ካለፈ በኋላም ሙዚቃዎቹ እንደሚለቀቁ ከተገለጸ ቆየት ብሏል። ታኅሣሥ 25 ቀን 2009 ዓ.ም. ገበያ ላይ የዋለው አልበሙ በቅንብር ዳግማዊ አሊ፣ ሚካኤል ኃይሉና ካሙዙ ካሳ በግጥምና ዜማ ምዕራፍ አሰፋ፣ ኃይሉ አመርጋ፣ ዓለማየሁ ደመቀ፣ ሙሉቀን ዳዊት፣ ኤርሚያስ ታደሰና ሌሎችም ባለሙያዎች ተሳትፈውበታል። ማስተሪንጉ በአበጋዝ ክብረወርቅ ሺኦታ ተሠርቷል። አልበሙ ፕሮዲውስ የተደረገው በይሳቃል ኢንተርቴመንት ሲሆን፣ በቮካል ሪከርድስ ተከፋፍሏል።
እዮብ ተወዳጅ ስራዎችን በማቅረቡ የተነሳ በሕይወት እያለ በአገር ውስጥም ሆነ ከአገር ከውጭ ፈላጊዎች በዝተውበት የነበረ ሲሆን በየቦታው የሙዚቃ ዝግጅቶች ነበሩት። አድናቂዎቹ በበኩላቸው የእሱን አዳዲስ ስራ ለመስማት እየጠበቁም ነበር። ነገር ግን ያ ባለብዙ ተስፋ ጥበበኛ ሳይታሰብ አደጋ ገጠመው። የነበረውን ሁኔታ አንድ ሰው በሚከተለው መልኩ አስፍሮታል
“ነሐሴ 5 እንደ ሁልጊዜውም እዮቤ ቅዳሜ ምሽቱን ተረኛ በሆነበት የቬላ ቬርዴ ክለብ ሲሰራ አምሽቶ እጅግ በተዳከመ ገፅታ ወደቤቱ ገባ፣ ባለቤቱ ጋደም ብላ እየጠበቀችው ነበር እዮቤ እንደወትሮው እቤት እንደገባ ሶፋ ላይ አረፍ ማለትን አልመረጠም ነበር እንደደከመው ለባለቤቱ ነግሯት ወደመኝታ ቤት አመራ ማግስቱን በጠዋት ተነሳና ወደ ሀኪም ቤት አመራ፣ በዛም ጤነኛ እንደሆነና እረፍት ብቻ እንዲያደርግ ተመክሮ ተመለሰ::
ነሐሴ 7 እዮቤ ዛሬም በጠዋት ነበር የተነሳው። ምክንያቱ ደግሞ የልጁ የትምህርት ቤት ምዝገባ ቀን ስለነበረ ነው። ልጁ ኬቨን ወደ ትምህርት ቤት ስለሄደ እዮቤ ቁርሱን በላላና ኦንላየን ጊታር ይማር ስለነበር ለፕቶፑን ከፍቶ ጊታሩን ጨብጦ ለመማር ዝግጁ ቢሆንም ኔትወርኩ ጥሩ አልነበረም። ደጋግሞ ቢሞክርም አልሆነም። ይሄኔ ኔትወርኩ ጥሩ እስከሚሆን ለምን የኬቨንን የትምህርት ቤት ክፍያ ከፍዬ አልመጣም የሚል ሀሳብ አሰበ። ወዲያው ተነሳና ለባብሶ የሚወዳትን ሳይክሉን እያሽከረከረ 4:30 ላይ ከቤት ወጣ፣ ክፍያውን ከፍሎ ተመለሰና በሩ ላይ ሲደርስ እዮብ ግማሽ አካሉ ከበደው አልታዘዝለት አለው። በቆመበት በተደገፈው በር ስር ሽርተት ብሎ ወደቀ። አካባቢው ላይ የነበሩ እዮብ ያቀርባቸው የነበሩ ወጣቶች ተሯሩጠው መጥተው አፋፍሰው ወደቤት ይዘውት ገቡ። ታክሲ ተጠራና ጉዞ ወደ አያት ሆስፒታል። እዛ ደርሰው መጠነኛ ምርመራ ከተደረገለት በኋላ ለተሻለ ህክምና ወደ ቅዱስ ገብርኤል ሆስፒታል አመሩ። በመንገዳቸው እዮብ ስልኩን አወጣና ለጓደኛው ኦሪዮን እንድትደውል ስልኩን ለባለቤቱ ሰጣት። ኦሪዮንና እነእዮብ እኩል ቅዱስ ገብርኤል ደረሱ። ሀኪም ካየው በኋላ ወደ ሲቲ ስካን ክፍል መግባት አለበት ተባለ። እዮቤ ደቂቃዎች በሄዱ ቁጥር እየተዳከመ መጥቷል። ወደ ሲቲ ስካን ክፍል ከኦሪዮን ጋር እየሄደ የሕይወቱን መጨረሻ በጤነኛ ቃላት እንዲህ አለው……. “ለፈጣሪ ፀልዩልኝ”
እዮብ ልክ ከሲቲስካን እንደወጣ ነገሮች በፍጥነት መቀያየር ጀመሩ። እዮብ ያወራል ግን የሚናገረው ነገር ጥርት ብሎ አይሰማም። ቅዠት ነገርም ይመስላል። በፍጥነት ወደ IC ክፍል እንዲገባና እንዲተኛ ተደረገ፣ ቤተሰቦቹ ከውጭ ሆነው ሁኔታውን ሲጠባበቁ መሸ:: አመሻሽ ላይ በብዙ ልመና ገብተው እንዲያዩት ተፈቀደላቸውና ገብተው ሲያዩት አይኑን ገርበብ አድርጎ በዛ በሚያምር ግርማ ሞገሱ ጋለል ብሎ ተኝቷል:: ሊያዋሩት ሞከሩ መልስ አይሰጥም፣ ሀኪሙ እንደምታዩት እዮብ በጥልቅ እንቅልፍ ውስጥ ነው ያለው መልስ አይሰጥም፣ ህክምናውን ለማድረግ የግድ እስኪነቃ መጠበቅ አለብን አለ። መንገደኛው እዮቤ ግን ላለመንቃት ወደ ማንቀላፋት ነበር !
እዮብ መኮንን ነሐሴ 5 የገጠመው አደጋ ነሐሴ 12 ቀን 2005 ዓ.ም ነፍሱ ከስጋው እንድትለይ አደረገ።
እዮብ ባለጠንካራ ስብእና ሰው ነው። ለዚህ ማሳያ የሚሆኑ የደራሲ በእውቀቱ ስዩምን ምስክርነት እንስማ። “ከጥቂት ዓመታት በፊት አንድ የበጎ አድራጎት ትርኢት ላይ ለመሳተፍ፣ ከዘፋኞች ጋር ወደ ደሴ ተጉዤ ነበር። የተሣፈርንበት አውቶብስ ጉንጫቸውን በጫት አሎሎ በወጠሩ ዘፋኞች ተሞልቷል። ዘፋኞቹ ሲሻቸው ይተራረባሉ፣ ሲሻቸው ይጮሃሉ፣ ይጨፍራሉ። የአውቶብሳችን ሽማግሌ ሹፌር ሳይቀር፣ አልፎ አልፎ መሪውን እየለቀቀ በማጨብጨብ፣ በ ‹‹ቅወጣ›› ከዘፋኞች እንዳማያንስ በማሳየት ላይ ነበር። በጫቱም፣ በጭፈራውም የሌለበት ድምጻዊ እዮብ መኮንን ብቻ እንደሆነ ተመለከትሁ። በእርጋታ ተቀምጦ፣ በአውቶብሱ መስኮት አሻግሮ የሚሮጡ የግራር ዛፎችን ይመለከታል።›› ልዩነቱ ግልጽ ነበር።
ድሮ ድሮ፣ እዮብ መኮንን አቤሴሎም የሚዘናፈል ረጅም ጸጉር ያለው ጎልማሳ ነበር። ድንገት ጸጉሩን ተሸለተ፣ ከጸጉሩ ጋር የጥንት ባህርይውን አራገፈ። ጭምት፣ መንፈሳዊና በመጽሐፍ ቅዱስ ፍቅር የነደደም ምዕመን ሆነ።
በተገናኘን ቁጥር፣ እዮብ ስለእምነት እንድንወያይ ይፈልጋል። ብዙ ጊዜ እምነት የሚያጠብቅ ሰው አንዳች ችግር ይኖርበታል ብዬ አስብ ነበር። እዮብ ግን እጅግ መልካም ሊባል በሚችል ሕይወቱ፣ ይሄንን አመለካከቴን ውድቅ አድርጎብኛል።
የዛሬ ሳምንት ገደማ ኢዮብ ዘፈን በመሥራት ላይ ነበር። እና ለአንድ ዜማው ግጥም እንድሠራለት ጋበዘኝ። ከዚህ በፊት የሞከርኳቸው የዘፈን ግጥሞች ስለከሸፉብኝ ግብዣውን ለመቀበል አመነታሁ። ግን ደሞ ወዲያው፣በኢዮብ ድምጽ ግጥሜ ተዘፍኖልኝ ለማየት ጓጓሁ። ውሀ ልማት አካባቢ፣ ሌክስ ፕላዛ ሕንጻ ሥር መኪናው ውስጥ ቁጭ ብለን ዜማዎችን ማድመጥ ጀመርን። ዘፈኑ ውስጥ ያሉት ሐሳቦች አብዛኞቹ ወደ መዝሙር ያዘነብላሉ። እዮብ ዘፈኑን ለፈንጠዝያ ሳይሆን ለስነምግባር ግንባታ ሊጠቀምበት ፈልጓል። አንድ በጣም ልብ የሚበላ የሶማሌ ዘፈን አስደመጠኝ።
‹‹ሶማሊኛ ትችላለህ እንዴ?››
‹‹አዎ፣ትግርኛም አውቃለሁ!››
‹‹የት ተማርከው?››
‹‹አስመራ፣ የወታደር ልጅ መሆኔን አትርሳ››
ከዘፈን ውጭ ምን ታደርጋለህ?
‹‹ኦን ላይን፣ ጊታር እየተማርሁ ነው። ቆይ ላሳይህ››…ላፕቶፑን ለኮሰና ጥቂት አስጎበኘኝ። ከዛ ከመኪናው ስወርድ የመኪናው እጀታ ስለማይሠራ ወርዶ ከውጭ ከፈተልኝ። እዮብ ብዙ ብሮችን መቁጠር የሚችል ልጅ እንደሆነ መገመት ይቻላል። ይሁን እንጂ እንኳን መኪናውን የመኪናውን እጀታ ማስቀየር አልፈለገም። ምናልባት፣ ዓመት በአልን ጠብቆ ልብስ የሚቀይር ብዙ ሰው ባለበት አገር ውስጥ፣ መኪና መቀያየሩን እንደ ኃጢአት ቆጥሮት ይሆናል።
ከጥቂት ቀናት በኋላ ልኡል የተባለ ዘፋኝ ጓደኛዬ፣ የእዮብን በድንገት መውደቅ ሲነግረኝ ወደ ቅዱስ ገብርኤል ሆስፒታል ሄድኩ። ዘፋኞችና አዘጋጆች መጠበቂያው ክፍል ላይ ተደርድረው ይተክዛሉ። ዘሪቱ፣ ዳግማዊ አሊ፣ እቁባይ በርሄ፣ እጃቸውን አገጫቸው ላይ ጭነው፣ ተቀምጠዋል። የእዮብ ባለቤት ወዲያ ወዲህ እየተንቆራጠጠች ታነባለች።
ዛሬ ደግሞ ይሄው ሞቱን ሰማሁ። ኢዮብ!!! በጠፈሩ ውስጥ፣ ያለግብ ከሚዞሩ ኮረቶች፣ ያለ ምክንያት ከሚበሩ ኮከቦች በቀር ምንም የለም ብዬ እንደማምን ታውቃለህ። ይሁን እንጂ ለዛሬ እንኳ፣ የኔ እምነት ከሽፎ ያንተ እምነት እውነት እንዲሆን እመኛለሁ። በምድር ለገጠመህ መራራ እጣ ሰማያዊ ካሳ (ጉማ) እንድታገኝ እመኛለሁ።
ከጊዜው ቀድሞ ስለተለየን ተወዳጅ ድምጻዊ ሳሙኤል ወልደየስ የተባለ ሰው በ2011 ዓ.ም የሬጌው ንጉስ በኢትዮጵያ የሚል መጽሀፍ የጻፈለት ሲሆን በቀጣይ ሳምንት እሁድ እዮብን የሚዘክር መርሀ ግብር በሀገር ፍቅር ቴአትር መዘጋጀቱም ተሰምቷል።
አቤል ገ/ኪዳን
አዲስ ዘመን ነሐሴ 8 /2014