የኢፌዴሪ ባህል እና ስፖርት ሚኒስቴር በቅርቡ ክብር ለጥበብ በሚል ስያሜ የኪነ ጥበብ ባለሙያዎች ሲሸልም ከዚህ ቀደም ባልተለመደ መልኩ ዲጄዎችን የሽልማቱ አካል አድርጓል። በዚህ ዘርፍ ለሽልማት ከበቁ ሶስት ዲጄዎች መካከል ዋነኞቹ የዛሬ የዝነኞች ገፅ እንግዶቻችን ጆርዳን እና ቤክ ግዕዝ የኤሌክትሮኒክ ሙዚቃ ኘሮዲውሰር፣ ዲጄ እና ኦዲዮ ኢንጂነር ናቸው።
የመድረክ ስማቸው ጆርዳን እና ቤክ ግእዝ ሲባል የመታወቂያው ደግሞ ዮርዳኖስ እና ቤካ ጊንቦ ይባላል። ሁለቱም ወጣቶች ናቸው። ሁለቱም ልባቸውን ተከትለው ላለፉት 9 አመታት ባልተሄደበት መንገድ የተጓዙ እና ስኬት ላይ የደረሱ ወጣቶች ናቸው። ያልተሄደበት መንገድ ደግሞ ኤሌክትሮኒክስ ዳስስ ሚዩዚክ የሚባለው ዘመናዊ የሙዚቃ ዘርፍ ነው። ሁለቱ ወጣቶች እዚያ ላይ ከመድረሳቸው እና ለመሞከር ከመድፈራቸው በፊት ግን ቀድመው በሙዚቃ ፍቅር ወድቀው ነበር።
ቤክ ግዕዝ ‹‹የሙዚቃ ህይወቴ ከትምህርት ቤት ነበር የጀመረው›› ይላል እሱና ሙዚቃ እንዴት እንደተዋወቁ ሲገልጽ። ያኔ ገና ትምህርት ቤት እያለ የውጭ ዲጄዎችን ስራ ይከታተል ነበር። ቀስ በቀስም ስራቸውን እየወደደው እና በዚህ የሙዚቃ ስልት እጅጉን እየተሳበ መጣ። የጆርዳን የሙዚቃ ህይወት የጀመረው አንጋፋ የውጭ ሀገር ዲጄዎችን በመመልከት ሲሆን የዲጄዎች ስራም ይስበው ነበር። በሁለቱም ውስጥ የተጸነሰው ይህ ፍላጎት ቀስ በቀስ እያደገ ሄዶ ሁለቱም ወደ ዲጄነቱ አዘነበሉ። ይህ ሲሆን ግን አይተዋወቁም ነበር። ከዚያም እድሜ ለቴክኖሎጂ ተመሳሳይ ዝንባሌ ኖሯቸው በተለያየ ቦታ ይኖሩ የነበሩት እነዚህ ሁለት ወጣቶች በፌስቡክ ተገናኝተው ማውራት ያዙ። ወቅቱም 2005 ዓ.ም ነበር። ጆርዳን እና ቤክ ግዕዝ ዝንባሌያቸው ተመሳሳይ ስለነበር ለመግባባት ብዙ ጊዜ አልወሰደባቸውም።
በወቅቱ በሀገሪቱ አንደዚህ አይነት የሙዚቃ ስልት ላይ የሚያተኩር ባለሙያ አልነበረምና የመጀመሪያዎቹ ሆነው ፈር ቀደዱ። ይህንን የሙዚቃ ስልት በሀገር አቀፍ ደረጃ ተቀባይነትን እንዲያገኝ እና ኢትዮጵያዊ ቀለም እንዲኖረው የውጪውን ኤሌክትሮኒክ ሚዩዚክ ከሀገርኛ ስልተ ምት እና ቅኝት ጋር በማጣመር ነበር ራሳቸውንም አድማጩንም ከስልቱ ጋር ያላመዱት። ይህንን የሙዚቃ ስልት በእጅጉ ለማስተዋወቅ አዳዲስ ሙዚቃዎችን ለአድማጭ ማቅረብ ጀመሩ።
የመጀመሪያ ስራቸውም ጸዳል የሚል ስያሜ ተሰጠው። ስራውም ተወዳጅነትን አገኘ። በመቀጠል ከስቱዲዮ ስራቸው ባለፈ በትላልቅ የኮንሰርት መድረኮች በአደባባይ ስራቸውን ያቀርቡ ዘንድ እድል ተፈጠረ። ያ አጋጣሚ የያዙት መንገድ ሲመኙት የነበረው እንደነበር እንዲገነዘቡ አደረጋቸው። ‹‹በራስህ ሙዚቃ ህዝብ ሲደሰት ፊት ለፊት ማየት ትልቅ ደስታን ይሰጣል›› የሚሉት ጆርዳን እና ቤክ ግዕዝ ይህ ሞራል ግስጋሴያቸውን አፋጠነው። በ2008 ዓ.ም የመጀመሪያቸውን ኮሌክሽን ሲዲ የተለያየ ሀገርኛ እና የምዕራባውያን ስልተ ምት እና ቅኝት በማጣመር የኤሌክትሮኒክ ሙዚቃን ለአድማጭ አደረሱ። ነገር ግን የታተመው 50 ፍሬ ሲዲ ብቻ ነበር። እንዲያም ሆኖ ስማቸው በከተማው ቀስ በቀስ እየገነነና እየታወቁ ከነሱ ጋር አብሮ ለመስራት የሚፈልገውም ሰው እየጨመረ መጣ። በተለይ አንድ ላይ እና ፀዳል የተሰኘው ስራቸው በየቦታው እየተደመጠ እና በተለይም ወጣቱ እጅጉን እየወደደው ነበር። ለዚህ ምስከራቸው የሆነው ደግሞ ወደ ቢሾፍቱ ፤ አዳማ ፤ አርባ ምንጭ ፤ ባህር ዳር እና ጎንደር ለኮንሰርት በሄዱበት ወቅት ህዝቡ ያሳያቸው ስሜት ነበር።
ከዚያን በኋላ ከዝነኞቹ አርቲስቶች ጋር አብሮ የመስራት እድሉ እየሰፋ መጣ። አብረዋቸው ከሰሩት አርቲስቶች መካከልም ሳሚ ዳን (ሀያል) ሪሚክስ ፤ አቡሽ ዘለቀ (ማሎ ኢንተሎ) ፤ ጃኪ ጎሲ (አሮድዮን) ሪሚክስ ፤ ያሬድ ነጉ እና ሚኪ ጎንደርኛ (ሸጌ) እንዲሁም አዳዲስ ሙዚቀኞችን ከማብቃት አንፃር እዮቤድ፣ ዊሀ እና ቤን ይጠቀሳሉ። ጆርዳን እና ቤክ ግዕዝ ከስድስት ወር በፊት ‹ለ› የተሰኘ ግማሽ አልበም ያወጡ ሲሆን የአልበሙ መጠሪያም በስፋት እየተዘጋጁበት ላለው ራእይ የተሰኘ አልበማቸው መንደርደሪያ እንዲሆን በማሰብ ነው። ‹‹በኤሌክትሮኒክስ ሙዚቃው ዘርፍ አሁን ላይ ስልቱን ከማስተዋወቅ ባለፈ አትራፊ የመሆን እቅድ የለንም›› የሚሉት ሁለቱ ወጣቶች የአድማጫቸውን ስብጥር ለማስፋት ሲሉ የሀገርኛን የሙዚቃ ቅኝት እና የሙዚቃ መሳሪያ ከውጪው ስልት ጋር በማዳቀል አዳዲስ ስልት ለመፍጠር እና ለሁሉም የሚስማማ ሙዚቃ በመፍጠር ላይ ናቸው።
በቅርቡ የሚወጣው ራእይ የተባለው አዲሱ አልበማቸው በዚህ መልኩ የተቃኘ ሲሆን አብረዋቸው የሚሰሩትም በአብዛኛው አዳዲስ ወጣቶች ናቸው። በዚህ መልኩም ለዘመኑ ወጣቶች ይመጥናል ያሉትን ስራ በቅርቡ ለማድረስ ዝግጅት ላይ ናቸው። በሌላ መልኩ በመድረክ ስራቸው ከጆርካ ፤ ኮረንቲ ፌስቲቫል፤ ኢ ኤም ኤል እና ሌሎች ጋር አብረው የሰሩ ሲሆን በትልልቆቹ የምሽት ክለቦችም ተጋባዥ ዲጄ በመሆን ስራዎቻቸውን ያቀርባሉ።
ሄኖክ በሪሁን
ጠቢባን በየጊዜው ይወለዳሉ። እነ እገሌን አይተን ከነሱ ኋላ እነሱን የሚያክል አይፈጠርም ባልንበት አንደበት አዲስ ከያኒ ይወለድና የቀድሞውን መወድሳችንን ያስረሳናል። በዚህ ሂደት የኢትዮጵያ ብሄራዊ ቲያትር በየጊዜው አዳዲስ ድንቅ ከያኒያንን አይቷል። አሁን ላይ ካሉት ድንቅ ከያኒያን መካከል ደግሞ አንዱ ተዋናይ ሄኖክ በሪሁን ነው። ሄኖክ የደሴ ልጅ ነው። የትውልድ ጊዜው ደግሞ ግንቦት 22 ቀን በ1978 ዓ/ም ነው።
ሄኖክ ደሴ ይወለድ እንጂ እድገቱ ግን አዲስ አበባ ነው። የተማረውም 4 ኪሎ በሚገኙት በዳግማዊ ሚኒሊክ 1ኛና 2ኛ ደረጃ ት/ቤት ነው። የኪነ ጥበብ ጉዞው የጀመረውም እዚያው ዳግማዊ ምኒሊክ ሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤት ነው። የሁለተኛ ደረጃ ተማሪ በነበረበት ጊዜም በድራማና ሥነ-ጽሁፍ ክበብ ውስጥ ይሳተፍ ነበር። ያኔ ነው በመምህራኑ እገዛ ውስጡ የታመቀው የኪነት ጸጋ የታወቀለት እና እንዲያድግ እድል የተመቻቸለት። ወጣቱ ተዋናይ ይህንን ሲረዳ የዳግማዊ ምኒሊክ ት/ቤት 1ኛ ደረጃ ተማሪ በነበረበት ወቅት የአማርኛ ቋንቋ መምህሩ የነበሩት መምህር ሂርጶ ተማሪዎቻቸው አጫጭር ድራማ እንዲሰሩ፣ የልብ- ውለድ መጽሐፍ እንዲያነቡ፤እርስ በእርሳቸው አስተያየት እንዲሰጣጡ ያደርጉ ስለነበር በዚህ ውስጥ ሄኖክ በሪሁን በንቃት ይሳተፍት ነበር። ገና በልጅነቱ መምህር ሂርጶ ተሰጥኦውን እንዲያውቅና የነፍሱ ጥሪ ከሆነችው ኪነ- ጥበብ ጋር እንዲገናኝ ስላደረጉት ዛሬም ድረስ በክብር ያስታውሳቸዋል።
ከሁለተኛ ደረጃ ትምህርቱም በኋላ በተለያዩ አጋጣሚዎች አጫጭርና ረጃጅም ኮርሶችን ወስዷል። ከተከታተላቸው ኮርሶች መካከል እነ አርቲስት አለማየሁ ታደሰ ባቋቋሙት “ሆሊላንድ የጥበብ አካዳሚ” ከ1996- 1997 ለአንድ ዓመት ተኩል የተከታተለው የትወና ትምህርቱ ለሙያው መጎልበት ትልቅ መሠረት እንደሆነ ይገልጻል። ይህን ከመሳሰሉ አጫጭርና ረጃጅም ኮርሶች በኋላም በከፍተኛ ትምህርት ተቋም የቲያትር ጥበብን ምርጫው በማድረግ በአዲስ አበባ ዩንቨርሲቲ የመጀመሪያ ዲግሪውን ይዟል። ሁለተኛ ዲግሪውንም በሲኒማ (ፊልም ፕሮዳክሽን) አግኝቷል።
የኢትዮጵያ ብሔራዊ ቲያትር ለተዋናይ ቅጥር ባወጣው ማስታወቂያ መሠረት ሄኖክም በትምህርት ዝግጅቱና በዝንባሌው መሠረት ተወዳድሮ በማሸነፉ በ2004 ዓ/ም ወደ ቲያትር ቤቱ በመቀላቀል ዛሬም ንቁ ተዋናይ ሆኖ በማገልገል ላይ ይገኛል።
ከቲያትር ቤቱ የተገኘው መረጃ እንደሚያመለክተው ከሆነ በቲያትር ቤቱ በቋሚ ቅጥር ከመቀጠሩ በፊት በተጋባዥነት “ህንደኬ” ተብሎ በሚታወቀው ተውኔት ላይ ሲሰራ የቆየ በመሆኑ ቲያትር ቤቱን በቅጥር ከተቀላቀለ በኋላም ይህንኑ ተውኔት ሲጫወት ቆይቷል። ከተሳተፈባቸው ተውኔቶች ውስጥ አልቃሽና ዘፋኝ (በትምህርት ቤት) አቤቶ እያሱ(በሜጋ አንፊ ቲያትር)፣” የቴዎድሮስ ራእይ”፣ “አብሮአደግ “፣ “የቃቄ ውርድወት “፣ “የአሻ ልጅ” ፣ “ሚሥጥሩ”፣የሚጠቀሱ ሲሆን አጭርና ረጅም ሀገራዊ ጉዞ በማድረግ አሳታፊ ተውኔቶች ከአዲስ አበባ ውጪም አቅርቧል። ለማንኛውም ተዋናይ የመድረክ የቲያትር ትወና ከባዱ ነገር ግን አስደሳቹ ሲሆን ሄኖክ የተሳተፈባቸው ቲያትሮች ደግሞ ታላላቆቹ ተዋንያን የሰሩባቸው እና ህዝብም የወደዳቸው ናቸው። በመሆኑም በነዚህ ተውኔቶች ላይ ተሳትፎ መስራቱ የሄኖክ የከያኒነት ህይወት ገና በአፍላነቱ ምን ያህል በፈጣን መስመር ላይ እንደተጓዘ አመላካች ነው።
ነገር ግን ሄኖክ የሚታወቀው በቲያትር መድረኮች ብቻ አይደለም። መልከ ቀናው ተዋናይ በቴሌቪዥን ተመልካቾች ዘንድም ታዋቂ እና ተወዳጅ ነው። በሀገራችን ለመጀመሪያ ጊዜ ለረጅም ጊዜ በታየው “ገመና “በተጨማሪ “የቤት ስራ” ፣ “ውርስ” ፣ “ህልሞች” እና “ሠንሰለት” ፡የተባሉ ታዋቂ የቲሌቪዥን ድራማዎችን በተዋናይነት ከተሳተፈባቸው ውስጥ የሚጠቀሱ ናቸው። “ሴቶቹ “የተባለ ተከታታይ ድራማና እንዲሁም አጫጭር ፊልሞች ላይ እና “የራሄል መንገድ” ፣የተባለ የሙሉ ግዜ ፊልም ላይ በዳይሬክተርነት ሰርቷል። በቅርብ የሚለቀቁ “ትስስር” ፣”ራኬብ” በሚባሉት ድራማዎች ላይም ሄኖክን እናገኘዋለን።
“የልደቴ ቀን”በተሰኘ ፊልም በረዳት አዘጋጅነትና በትወና እንዲሁም ፕሮዳክሽን ማናጀር በመሆን የሰራ ሲሆን ይህ ወጣት ተዋናይ በጥቅሉ ከ 15 በላይ ረጃጅምና አጫጭር አማርኛ ፊልሞችን እና ሁለት (Sweetness in the Belly እና Mandela’s Gun) የተባሉ አለማቀፍ ፊልሞች መስራቱን የብሄራዊ ቲያትር መዝገቡ ያሳያል።
ተዋናዩ በተለያዩ ክበረ-በዓላት ላይ የቀረቡ አጫጭር እና ረጃጅም ድራማዎን በማዘጋጀትና በመተወን፣የተውኔት ጽሁፎችንና ተውኔቶችንም በመገምገም እና በማስተባበር አገልግሏል። ሄኖክ በሪሁን አዲስ አበባ ዩንቨርሲቲ እና ማርች ፕሮጀክት ትብብር ያሳትመው በነበረው “ life one one” በተሰኘ እያዝናና የሚያስተምር በተውኔት መልክ በፎቶና በጽሁፍ እየተዋዛ በሚዘጋጅ የመጽሄት ተውኔት ላይም ለ3 ዓመት ያክል ተሳትፏል።
ሄኖክ ከሀገር ውስጥ ስራው አልፎም በዓለም አቀፍ ደረጃ በተዘጋጀና ከፊሉ ቀረጻ እዚሁ ኢትዮጵያ ውስጥ በነበረው በቀድሞው የደቡብ አፍሪካ ፕሬዚዳንት በነበሩት በኔልሰን ማንዴላ ታሪክ ላይ በሚያጠነጥን እና የሆሊዩውዱ ዳይሬክተር በጃን ኤርቪን በተዘጋጀው “ማንዴላስ ጋን “ ፊልም ላይ ለመስራት በተወዳደረው መሰረት በመመረጡ በተዋናይነት የመሳተፍ ዓለም አቀፍ እድል አጋጥሞት ተሳትፏል ።
ሄኖክ በሪሁን የኢትዮጵያ ብሔራዊ ቲያትር የሙያ ፍቅሩ ላላቸው ወጣቶች በየወቅቱ በሚሰጠው ኮርሶች ላይ በማስተማር ተሳትፎ ከማድረግ ባሻገር በአዲስ አበባና ከአዲስ አበባ ውጪ ላሉ ወጣቶች እንዲሁም በግሉ ለአንደኛና ለሁለተኛ ደረጃ ተማሪዎች ዕውቀቱንና ልምዱን አካፍሏል። በማካፈልም ላይ ይገኛል።
ተዋናዩ በ2008 ዓ/ም የኢትዮጵያ ኢንተርናሽናል ፊልም ፌስቲቫል ላይ ምርጥ ተዋናይ ለመሸለም በተደረገ ዝግጅት ምርጥ 5 ውስጥ በእጩነት ገብቶ የነበረ ሲሆን በቅርብ በነበረው የአውሮፓ ፊልም ፌስቲቫል 2022 (Addis in the time of coved 19 OR City portrait of addis) በሚል ባዘጋጀው አጭር ዶክመንተሪ ፊልም ቀርቦ ተሸላሚ መሆኑን ቲያትር ቤቱ ይገልጻል።
አቤል ገ/ኪዳን
አዲስ ዘመን እሁድ ሐምሌ 17 ቀን 2014 ዓ.ም