ሙሉ ስሙ አርቲስት ብዙነህ ተስፋ ይባላል። የተወለደው አዲስ አበባ ሳሪስ ሰፈር ነው።እናቱ ወይዘሮ ካሰች ብርሃኑ ሲባሉ አባቱ ደግሞ አቶ ብርሃኑ ይባላሉ። ገና የ9 ወር ጨቅላ እያለ አባቱን በሞት ያጣው ብዙነህ ያደገው በአጎቱ ቤት መገናኛ አካባቢ ነበር። አራት ዓመት ሲሞላው ግን ወደ እናቱ ቤት ወደ ሳሪስ ተመለሰ። ኑሮ በእናቱ ቤት ቀላል አልነበረም። እንጀራ እና ፓስቲ በመሸጥ ነበር ኑሮቸውን የሚገፉት። ትምህርቱን በፍሬሕይወት ቁጥር አንድ እና ስብስቴ ነጋሲ የተማረው ብዙነህ የኑሮ መክበድ ግን በውስጡ ያለውን ተሰጥኦ እንዲታፈን አላደረገውም። ገና ልጅ እያለ ከመኪና ባትሪ የሚወጡ ቀላጮችን በመጠቀም የሽቦ መኪናዎችን ለመሥራት ይሞክር ነበር። የሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤት ተማሪ እያለም የተለያዩ ስዕሎችን እየሳለ ለጓደኞቹ ያሳይ ነበር፡፡
1983 ላይ የሁለተኛ ደረጃ ትምህርቱን ሲጨርስ እና ከፍተኛ የትምህርት ተቋምን ሲቀላቀል ምርጫው የሆነውም የስነ ጥበብ ትምህርት ቤት ነበር። በወቅቱ የስነ ጥበብ ትምህርት እንደ ቁምነገር ስለማይወሰድ የብዙዎች ምርጫ አልነበረም። በዚያ ዘርፍ የተመደቡ ተማሪዎችም ምርጫቸው ቀለም ቅብ መማር ነበር። ብዙነህ ግን ብቸኛው በገዛ ፈቃዱ የሐውልት እና ቅርጻ ቅርጽ ተማሪ ሆኖ ትምሀርቱን ጀመረ። እርግጥ ወደ ስነ ጥበብ ትምህርት ቤቱ ለመግባት ያደረገው ሙከራ ቀላል አልነበረም። ለመጀመሪያ ጊዜ የሞከረው የ10ኛ ክፍል ተማሪ እያለ ነበር። ነገር ግን አልተሳካም።ለሁለተኛ ጊዜ ሞክሮም አልተሳካም። ለሶስተኛ ጊዜ ሲወዳደር ደግሞ የተወዳደረው ከሌሎች 1200 ተማሪዎች ጋር ነበር። በዚህ ውድድር ላይ ግን ቀንቶት ሁለተኛ ደረጃን በማግኘቱ ትምህርት ቤቱን ተቀላቀለ። ደስ አለው። በብዙ መከራ ያሳደጉት እናቱም ደስታው ደስታቸው ነውና ባላቸው አቅም ቲማቲም ገዝተው ለልጃቸው መለስተኛ የደስ ደስ ድግስ አዘጋጁለት። ትምህርቱም ተጀመረ ፤ ከአራት ዓመት በኋላም በማዕረግ ተመረቀ። ከዚያ በኋላ ያለው ዘመን ዛሬ በየቦታው የምናያቸውን አስደናቂ ሐውልት እና ቅርጻ ቅርጽን የማምረት ዘመን ሆነ፡፡
የመጀመሪያ ዋጋ ያገኘበት የቅርጽ ሥራው እንስራ የያዘች ሴት ቅርጽ ነበር። ለዚህ ሥራውም በወቅቱ አራት መቶ ብር ተከፍሎት ነበር። ታሪኩም አስገራሚ ነው። የሚማርበት ትምህርት ቤት አንድ ቀን አንድ ሰው ጎራ ይላል። የሰውየው ስም መላኩ አብዲሳ ይባላል። አንድ ሐውልት የሚሠራ ሰው ፈልጌ ነበር ብሎ የትምህርት ቤቱን ጥበቃዎች ይጠይቃል። ጥበቃዎቹም ብዙነህን ይጠሩና ትሞክራለህ ወይ ይሉታል። ፈራ ተባ እያለ እሺ ይላል። የመጀመሪያ ሐውልቱንም ይሰራል፡፡
ገና የሶስተኛ ዓመት ተማሪ እያለ የመጀመሪያ ሥራውን የሠራው ብዙነህ በዚያ የጎረምሳ ድፍረት ከአንድ ጓደኛው ጋር ሂልተን ሆቴል ላይ ኤግዚቢሽን አቅርቦ ነበር። በወቅቱ ትምህርት ቤቱ የብዙነህን እና ጓደኛውን ተግባር ክፉኛ ኮንኖ ከምርቃታቸው በፊት እንዲህ አይነት ተግባር ቢያደርጉ እንደሚባረሩ ቤተሰቦቻቸውን አስፈርሞ ነበር፡፡
ብዙነህ ገና ተማሪ እያለ የአጼ ቴዎድሮስን ሐውልት ለመሥራት ፍላጎት ነበረው። በዚህም የተነሳ ሐውልቱን አሁን ቴዎድሮስ አደባባይ በሚሰኘው ቦታ ላይ ለመሥራት ፍላጎት ነበረው። ለዚህም ተገቢውን እንቅስቃሴ አድርጎ በወቅቱ የከተማው ከንቲባ በሆኑት አቶ አሊ አብዶ እንዲሠራ ተፈቀደለት። ፍቃዱን ለማግኘት ግን ሶስት ዓመት ፈጅቶበት ነበር። የሆነ ሆኖ ፈቃዱ ተገኝቶ ሥራው ሊጀመር ሲል አቶ አሊ ከሥራ ወርደው የአቶ አርከበ አስተዳደር ይመጣል። ብዙነህም ከንቲባው ቢሮ ይጠራል። ሐውልቱን መሥራት እንደማይችል እና እነሱ በቴዎድሮስ ምትክ የሴባስቶፖልን ሐውልት ለማስቀመጥ እንዳቀዱ ይነግሩታል። በቀላሉ እጅ የማይሰጠው ብዙነህ ይሟገታል። ይህን ያህል ሐውልት የመሥራት ፍላጎት ካለህ መስቀል አደባባይ ላይ የፈለግከውን ያህል ቦታ እንሰጥሀለን የእኛን ታጋዮች ሐውልት ሥራ ይሉታል።እሱ ግን ፍላጎቱ የአጼ ቴዎድሮስን ሀውልት መሥ ራት እንደሆነና የነሱን ሀሳብ እንደማይስማማበት ይናገራል።ይሄኔ ስብሰባው ላይ የነበሩት ሕላዌ ዮሴፍ ሲጋራቸውን እያጨሱ ወደ ብዙነህ ጠጋ በማለት ለጊዜው ምንነቱን በማያውቀው ነገር ጭንቅላቱን መትተውታል፡፡
ከዚህ በኋላ ስቱዲዮውን ዘግቶ የታክሲ ሹፌር ሆኖ ኑሮውን ቀጠለ።ከዚያ በኋላ ደግሞ ጥበብ አገረሸችበትና የታላላቆቹን ኢትዮጵያውያን ጥላሁን ገሰሰ እና ኃይሌ ገብረስላሴን ሐውልት ለመሥራት ያቅዳል።ሄዶ ጥላሁንን ያናግረዋል።ጥላሁንም ስለ ቴዎድሮስ ሐውልት ውዝግብ ሰምቶ ስለነበር ከብዙነህ ጋር ለመግባባት ብዙም አልተቸገረም።እቅዱም በጊዜው ተፈጽሞለታል፡፡
በኢትዮጵያ የመጀመሪያውን (Art Foundry) የነሐስና አልሙኒየም ማቅለጫ (ለጥበብ-ሥራ) ብቻ የከፈተው ብዙነህ በዚህም ለበርካታ ለሠዓሊያን እና ለቀራፂያን የስነ ጥበብ መምህራኖችን ጨምሮ አገልግሎት ይሰጥ ነበር:: ዝናው ሲናኝ ትምህርት ለምኔ ያላለው ይህ ጥበበኛ በ2003 ዓ.ም በአዲስ አበባ “አለ” የሥነ-ጥበብ እና ዲዛይን ትምህርት ቤት በባችለር ዲግሪ ተመርቋል።
ብዙነህ የትዳር አጋሩን ወይዘሮ ጽጌረዳ ተክሌን ያገኘው ከሩብ ክፍለ ዘመን በፊት ገና የስነ ጥበብ ትምህርት ቤት የ2ኛ ዓመት ተማሪ እያለ ነው።እሷ በወቅቱ በዳግማዊ ምኒሊክ ትምህርት ቤት የ9ኛ ክፍል ተማሪ ነበረች።እሱ ደግሞ ከምኒሊክ ጀርባ ያለው የስነ ጥበብ ትምህርት ቤት ተማሪ ነበር።ጽጌረዳ አይኑ ውስጥ የገባችውም በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ የስነ ጥበብ ተማሪዎች እንደተለመደው 4 ኪሎ ቁጭ ብሎ ፈጣን ንድፍ ሊሠራ አይኑን ሲያማትር ነበር።አይኑ ውስጥ የገባችውን ቆንጆ ማግኘቱ ግን ቀላል አልነበረም።ኮስታራ የነበረች ሲሆን እሷን ለማግኘት ብዙ ደጅ መጥናት እና ስእለት መሳል አስፈልጎት ነበር፡፡
አራት ዓመታት በጓደኝነት ከቆዩ በኋላም ትዳር መሥረተው እስከዛሬም አብረው አሉ።የአብፋና ፤ አብያለው ፤ የአብጥበብ እና ራእይ የተሰኙ አራት ልጆች አሏቸው። ዛሬ ላይ ለደረስኩበት ከፍታ ዋነኛ ባለቤት ናት የሚላት ባለቤቱ ለሙያ እድገቱ ከፍተኛ ድርሻ አላት። ዛሬ ላይ ብዙነህ ታዋቂ የሆነበት የማንነት ስቱዲዮንም ሲያቋቁም ዋነኛዋ ሰው እሷ ነበረች።ይህ ለሁለት አስርተ ዓመታት የዘለቀ ተቋም ከ25 በላይ የሥዕል ፍላጎት ያላቸውን ታዳጊዎች ፣ ወጣቶች መሠረታዊ አሳሳልና የቅርፃ ቅርፅ ስልጠና ሰጥቷል።ከፊደል ጋር በተያያዘ በሀገር ቤት ከባለቤቱ ፅጌሬዳ ጋር በመተባበር የራሳቸውን ዲዛይን በማሳለጥ (Amharic development) በሚል በማነፅ ለግዕዝ ፊደል የበኩላችንን አስተዋፅኦ አድርገዋል ። ብዙነህ ወደ አሜሪካ ከተጓዘም በኋላ አሜሪካ ኮሎራዶ ግዛት ማንነት የጥበብ ስቱዲዮን መልሶ በማቋቋም የሐውልትና ቅርፃ ቅርፅ አገልግሎት እየሰጠ ይገኛል። በተያያዥ ዓለም ፀሐይ ወዳጆ የጥበብ መድረክ በሚል መሥራች አባል ሆኖ መሥርቷል ።
ብዙነህ በሀገር ቤት በነበ ረበት ጊዜ በርካታ ሥራዎች ሠርቷል።በሀገር ቤት ቆይታ ከተሠሩ ሥራዎች በጥቂቱ ለማስታወስ የአፄ-ቴዎድሮስ ምስለ-ሐውልት በጎንደር አየርማረፊያ እና በከተማው ዋና አደባባይ ላይ የቆሙ ሁለት ሐውልቶች (በነሐስ እና በፉይበር) ፤ የአፄ-ዮሐንስ ሐውልት በአክሱም ከተማ( የነሐስ ሐውልት) ፤የራስ-አሉላ አባነጋ ሐውልት በመቀለ (ነሐስ ሐውልት) ፤በመርሐቤቴ ከተማ የጀርመናዊው ዜጋ ካርል ሄንዝ በም (የሠዎች ለሠዎች ድርጅት መሥራች)የነሐስ ሐውልት ፤ የክብር ዶ/ር አርቲስት ጥላሁን ገሠሠን ፤የአርቲስት ዘነበች ታደሠን (ጭራ ቀረሽ) ፤ የአርቲስት ሙናዬ መንበሩን (በአገር ፍቅር ቲያትር ቤት) ፤ኮሜዲያን አለባቸው ተካ ፤ኮሜዲያን አብርሃም አስመላሽ ፤ የስፖርት ጋዜጠኛ ደምሴ ዳምጤ ፤ጋዜጠኛ ግዛው ዳኜ ፤ (የሠላም አምባሳደር) ሐኪም ማሞ (ታዋቂው የባህል መድሐኒት ቀማሚ እና ሐኪም) ፤ አርቲስት፣ ክራሪስት አስናቀች ወርቁ ፤የኮሪያ ዘማቶች የሰማዕታት ሐውልት በአፍንጮ በር 6ኪሎ ፤ በሐረር ከተማ 5ቱን የጀጎል በሮች የሚጠቁም – የአደባባይ ሐውልት ፤በአዲስ አበባ የቦብ ማርሌ ሐውልት ፤በኢሊባቦር ጎሬ ከተማ የአቡነ ሚካኤል በነሐስ የተቀረጸ 3 ሜትር ሐውልት ፤ በአዲስ አበባ ስላሴ ቤተ ክርቲያን ግቢ የፓትሪያርክ አቡነ ጳውሎስ የነሐስ ሐውልት፣ የፓትሪያርክ አቡነ ተክለ ሐይማኖት ሐውልት፣ የጀነራል ሐየሎም አርአያ ሐውልት በመቀሌ፣ የሺህዎች እናት አበበች ጎበና (በ5 ኪሎ ሙዚየም) show case (Art)፤ የክብር ዶ/ር አርቲስት አሊቢራ (በኦሮሚያ ሙዚየም) show case Art የጀነራል ታደሰ ብሩ (በኦሮሚያ ሙዚየም)፤ የአትሌት አበበ ቢቀላ (በኦሮሚያ ሙዚየም) ሰርቷል፡፡
ብዙነህ በእናት ሀገር እንደተለመደው ሰዎች ከሞቱ በኋላ ሳይሆን ገና ሳይሞቱ ሐውልታቸው ገና በሕይወት እያሉ መሠራት አለበት ብሎ የሚያምን ሲሆን በዚህም የተነሳ በሕይወት እያሉ በርከት ያሉ ሰዎችን ሐውልት ሠርቷል፡፡
አቤል ገ/ኪዳን
አዲስ ዘመን ሐምሌ 3 ን 2014 ዓ.ም