ክረምትን ተከትለው በአዲስ አበባ ከሚከሰቱ ተደጋጋሚ አጋጣሚዎች መካከል የኤሌክትሪክ ኃይል መቆራረጥ ዋነኛው ነው። ዝናብ ጠብ ባለ ቁጥር የሚቋረጠው የኤሌክትሪክ አገልግሎት ሰኔ ግም ማለቱን ተከትሎ በየአካባቢው የነበረ ተለምዶውን እያስቀጠለ ነው። በኤሌክትሪክ መቆራረጥ በተደጋጋሚ አቤቱታዎች ከሚቀርብባቸው መካከል በዋናነት ጀሞ 1 እና ጀሞ 2 የጋራ መኖሪያ ቤቶች፣ አስኮ፣ ብርጭቆ እና አራት መንታ ፣ ሃያት እና ፈረንሳይ ተጠቃሽ ናቸው። እንዲሁም በሌሎች የተለያዩ አካባቢ እና መንደሮች ተደጋጋሚ የኃይል መቆራረጥ እያጋጠመ ስለመሆኑ ጥቆማ ሰጪዎቻችን አቤቱታ በማቅረብ ላይ ናቸው። የቀረበውን አቤቱታ ይዘንና የራሳችንንም ትዝብት አክለን ወደ አዲስ አበባ ኤሌክትሪክ አገልግሎት ብቅ ብለናል። የአገልግሎቱ የኮሙኒኬሽን ሥራ አስኪያጅ አቶ በቀለ ክፍሌ ጋር ከኤሌክትሪክ መቆራረጥና ሌሎች ተያያዥ ጉዳዮች ጋር ያደረግነውን ቃለመጠይቅ እንደሚከተለው አቅርበነዋል።
አዲስ ዘመን፡- አዲስ አበባ ላይ የኤሌክትሪክ አገልግሎት መቆራረጥ የተለመደ ቢሆንም፤ መሻሻል አሳይቶ ነበር። ሆኖም ከአንድ ዓመት ወዲህ እጅግ ተደጋጋሚ የኃይል መቆራረጥ እያጋጠመ መሆኑን እና በፍጥነት የኃይል መቆራረጥ ችግርን በመፍታት በኩል ክፍተት እንደሚታይ በመጠቆም ነዋሪው አቤቱታ እያቀረቡ ነው። በእርግጥ ከአንድ ዓመት ወዲህ በተለይ በክረምት ኃይል በስፋት የተቋረጠበት የተለየ ምክንያት ይኖር ይሆን ?
አቶ በቀለ፡- በእኛ በኩል የተለየ መቆራረጥ አለ የሚል እምነት የለንም። ክረምት በመሆኑ የተለመደ መቆራረጥ ያጋጥማል። በጥገና ክፍል ያለው የቴክኒክ ክፍሉ መደበኛ ሥራው ጥገና ነው። የቴክኒክ ክፍሉ ክረምት ላይ የቅድመ መቆራረጥ ሥራን ይሠራል። ስለዚህ ከፕሮጀክት እና ከመልሶ ግንባታ ቀጥሎ ጥገና ላይ በመደበኛነት እየሠራን መሆኑ መታወቅ አለበት። በዋናነት እንዳይቆራረጥ የተለያዩ ሥራዎችን በመሥራት ላይ እንገኛለን ስንል በተለይ የፓወር ቻይና ካምፓኒ 600 ኪሎ ሜትሩን ጨርሶ መሥራቱን ማሳወቅ ያስፈልጋል።
አዲስ ዘመን፡- ግልፅ አይደለም። ካምፓኒው የዘረጋው ነባር መስመሮችን ነው ወይስ አዲስ መስመር ዘረጋ ? በደንብ ያብራሩት።
አቶ በቀለ፡- 600 ኪሎ ሜትሩን ግልፅ ለማድረግ ቅድሚያ መታወቅ ያለበት፤ የኃይል መቆራረጥ ማለት ከኃይል ማከፋፈያ ጣቢያው ወጥቶ ወደየሠፈሩ የሚሔድ ለየትራንስፎርመሩ የሚሰጥ ኃይል እዛ ላይ ተቋረጠ ማለት ነው። መልሶ ግንባታ ያስፈለገበትም ምክንያት አዲስ አበባ የኤሌክትሪክ መስመር ሲዘረጋ በዛ ጊዜ የነበረውን የኤሌክትሪክ ፍላጎት መሠረት አድርጎ ኔትወርክ ተዘርግቷል። ትራንስፎርመር ተቀምጧል። አሁን አርጅቶ የሚታየው እና ለመውደቅ ያዘነበለው ምሰሶ ያኔ ለነበረው ፍላጎት በቂ ቢሆንም አሁን ግን ከምሰሶ ማርጀት በተጨማሪ ኬብሎቹም አሁን ያለውን የኃይል ፍላጎት የመሸከም አቅም የላቸውም።
ነባሩ የመሸከም አቅም እንዲኖረውና የማኅበረሰቡን ፍላጎት ዕድገትን መሠረት በማድረግ ይሠራ ስለተባለ ያንን መሠረት በማድረግ እየተሠራ ነው። ይህ ማለት አዲስ አበባ ላይ ወደ 138 ማከፋፈያ ጣቢያዎች አሉ። እነዚህ ማከፋፈያዎች ለአዲስ አበባ ብቻ ሳይሆን በአዲስ አበባ ዙሪያ ላሉ ለኦሮሚያ ልዩ ዞኖች ለሰበታ፣ ለሱሉልታ ወይም ሌሎች አቅራቢያዎችንም ያካተተ ነው። እነዚህ ማከፋፈያዎች በተጨማሪነት የመሐል ከተማውንም ይይዛሉ።
600 ኪሎ ሜትር ተሠራ የምንለው እነዚህን መስመሮች በማጠናከር ነው። እነዚህ ላይ የመልሶ ግንባታ ሥራ ተሠራ ማለት እንጨቱን ወደ ኮንክሪት፤ ኬብሉንም በመቀየር አቅሙን የማሳደግ ሥራ ተሠርቷል ማለት ነው። ይሔ ሲሆን ንፋስም ሆነ የኃይል መጠን መጨመር ችግር አይፈጥርም። ስለዚህ የኃይል መቆራረጥ ይቀንሳል። በሌላ በኩል ከቅርብ ጊዜ ወዲህ መቆራረጥ ሲታይ የነበረው ቀድሞ 600 ኪሎ ሜትር ሲሻሻል ስለነበረ ነው። በመቀጠል በአፍሪካ ልማት ባንክ የሚሠራ ሁለተኛው ምዕራፍ የ400 ኪሎ ሜትር ሥራ ተጀምሯል።
አዲስ ዘመን፡- 600 ኪሎ ሜትር ሸፍነናል ሲሉ የአዲስ አበባ አካባቢ መስመር ታድሶለታል የሚባለው የትኛው አካባቢ ነው?
ከ138 መስመሮች መካከል ትልልቅ ችግር ያለባቸው መስመሮች እየተመረጡ ሥራው ይሠራል። ካሉን ማከፋፈያዎች ተነስተው ወደየመንደሩ ይሔዳል። ነገር ግን ካለው ፍላጎት አንፃር እየተሠራ ያለው በቂ አይደለም። በአንድ ጊዜ ሙሉ ለሙሉ ሥራውን ለማጠናቀቅ ከተፈለገ ደግሞ ከፍተኛ ገንዘብ ይፈልጋል። አሁንም የሚሠራው በብድር ነው። በሀገርም ሆነ በተቋም ደረጃ ያለው አቅም የሚታወቅ ነው። ስለዚህ የኃይል መቆራረጥ አለ። ነገር ግን በእኛም በኩል ችግሩን ለማቃለል እየሠራን ነው።
አዲስ ዘመን፡- የኤሌክትሪክ መቆራረጥ በሚያጋጥምበት ጊዜ ፍጥነት ያለው ጥገና ለምን አይደረግም?
አቶ በቀለ፡- ሁለት ምክንያቶች አሉ። አንደኛው ኤሌክትሪክ የሚቋረጠው እንደሚታወቀው በብልሽት ምክንያት ነው። የብልሽቱ ምክንያት እና የት ቦታ ላይ እንደተቋረጠ ሊታወቅም ላይታወቅም ይችላል። መስመሩ የተቋረጠበትን ምክንያት ለማረጋገጥ እያንዳንዱን መስመር የሲኒ መሰንጠቅ ድረስ ማየት ሊያስፈልግ ይችላል። እስከ 100 ትራንስፎርመር ድረስ የተቋረጠበትን ለማወቅ የሚፈለግበት ሁኔታ ሊያጋጥም ይችላል። የሥራው ሂደት መዘግየትን ሊያስከትል ይችላል።
አዲስ ዘመን፡- ኃይል ሲቋረጥ ምክንያቱን ወዲያውኑ የሚያሳውቅ ቴክኖሎጂ የለም እንዴ?
አቶ በቀለ፡- በእርግጥ በአዲስ መልክ የሚሠራው ሥራ የቱ ጋር ችግር እንዳጋጠመ ይጠቁማል። ከዚህ በኋላ በታደሱት መስመሮች ላይ ቢሮ ቁጭ ብሎ ኃይል የቱ ጋር እንደተቋረጠ ይታወቃል። የጥገና ክፍል ቡድኑ ሔዶ ይሠራል። ፕሮጀክቱ ይሔንንም ያካትታል። ማበዳደሪያ እና ሌሎች አስፈላጊ የሆኑ ነገሮችንም ይዟል። ብልሽት ሲያጋጥም ኃይል ሲቋረጥ መስመሮች ሁሉ አይቋረጡም። ሁሉም መስመሮች የሚቋረጡት በብልሽት ምክንያት ወይም ጥገና ሲካሔድ ለጥንቃቄ ሲባል ብቻ ነው። ይህ ሲባል የፕሮጀክት ሥራውም ሲሠራ ኃይል ይቋረጣል። ያለበለዚያ ሥራውን መሥራት አይቻልም። ለጥንቃቄ ጥገና ስናደርግም እናቋርጣለን።
አዲስ ደንበኞች ሲመጣ እነርሱን ለመቀላቀል ወደ ስምንት መስመሮች በየቀኑ ለ30 ደቂቃ እና ለአንድ ሰዓት እናቋርጣለን። ይሄ ማለት አዳዲስ ደንበኞች ትራንስፎርመር ካልተቋረጠ ማገናኘት አይቻልም። ነገር ግን ከኋላ ቀድሞ ሥራው ከተጨረሰ በኋላ ለማገናኘት ብቻ ኃይል የሚቋረጠው ለ30 ደቂቃ ነው። ይሔ መደበኛ ነው። ሌላው ለጥገና ተብሎም ይቋረጣል። ለምሳሌ ብልሽት ከተገኘ በኋላ ብልሽቱ ረዥም ከሆነ ለማስተካከል እና ለመሥራት ሲባል ይቋረጣል። የመሬት ውስጥ (የአንደር ግራውንድ) መስመር ላይም አንዳንድ ቦታዎች ላይ ለምሳሌ ሃያት አካባቢ ብልሽቱ የቱ አካባቢ እንደተፈጠረ ለማወቅ እና ጠግኖ ወደ አገልግሎት ለማስገባት ጊዜን ይጠይቃል። ስለዚህ በዚህ ጊዜ ኃይል ይቋረጣል።
አዲስ ዘመን፡- በዋናነት በአዲስ አበባ የኤሌክትሪክ አገልግሎት መቋረጥ አሰቃይቶናል የሚሉት የጀሞ 1 እና የጀሞ 2 የጋራ መኖሪያ ቤቶች ናቸው። ሌሎችም የአስኮ እና ብርጭቆ አካባቢ ነዋሪዎችም አራት መንታ አካባቢም በተደጋጋሚ ኃይል ይቋረጣል ይላሉ። በዋናነት በእነዚህ አካባቢዎች ላይ ኃይል የሚቋረጥበት ምክንያት እና ችግሩ የቀጠለበት ሰበብ ምንድን ነው? በእነዚሁ አካባቢዎች በቅርብ ርቀት አገልግሎት ሳይቋረጥ እነርሱ ጋር ለምን ተደጋጋሚ ኃይል ይቋረጣል?
አቶ በቀለ፡- ይሔ የአገልግሎት አሰጣጡ ባህሪ ነው። ለምሳሌ ሁለት ጎረቤታሞች ቢኖሩ የአንዱ ቤት በርቶ የሌላው ቤት ሊጠፋ ይችላል። ትራንስፎርመር ሲመጣ ሶስት ፌዝ ይይዛል። ጭነት ከበዛ በተደጋጋሚ ፊውዟ ትቃጠላለች። የአንዱ ቤት መስመር ከዛች በተደጋጋሚ ከምትቃጠል ፊውዝ ላይ የተወሰደ ሊሆን ይችላል። ሌላኛው ደግሞ ጭነት ካልበዛበት መስመር የተወሰደ ከሆነ አንዱ ቤት የኤሌክትሪክ አገልግሎት ኖሮ አንደኛው ቤት ላይኖር ይችላል። ይሔ ትልቅ ቅሬታ ይፈጥራል። ጭነት አንዱ ላይ እንዳይበዛ የማቻቻል ሥራ እየሠራን ነው።
በሌላ በኩል ከ138ቱ መስመሮች መካከል አንዱ ተደጋጋሚ የኔትወርክ ብልሽት ሊያጋጥመው ይችላል። ሌላኛው ደግሞ በመልሶ ግንባታ የተጠገነለት ሊሆን ይችላል። ስለዚህ አንድ ቤት ወይም አንድ አካባቢ የኤሌክትሪክ ኃይል ኖሮ ሌላው ጋር አለመኖር ያጋጥማል። ከዛ ውጪ ሆን ተብሎ ኃይል እንዲቋረጥ አይደረግም። ሥርዓቱ ራሱ ሆን ብሎ ለማቋረጥ የሚስችል አይደለም። በዋናነትም ኃይል የሚቋረጠው ከእኛ አይደለም። ሲቋረጥ የሚቋረጠው ከኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ ኃይል ነው። የእኛ ሥራ ከኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ ኃይል የገዛነውን ማከፋፈል ነው። ሲቋረጥ የሚቋረጠው ከእነርሱ ጋር መሆኑን ሕዝቡ ማወቅ አለበት። የእኛ መስመር ችግር ሲያጋጥመው የእነርሱ ኃይል ይቋረጣል።
አዲስ ዘመን፡- በኃይል ሻጮቹ ምክንያት ኤሌክትሪክ የሚያቋርጥበት አጋጣሚ የለም?
አቶ በቀለ፡- እነርሱ ከማከፋፈያ ጣቢያ ቀጥሎ ትራንስሚሽን አላቸው። ዋናው ከማከፋፈያ ጣቢያ ከተቋረጠ አበቃ ማለት ነው። ነገር ግን እነርሱ መስመሮችን ያወጡልናል፤ እንደኛ ፍላጎት የማከፋፈያ ጣቢያ ማስፋፊያ ይሠራሉ። እኛም ከእነርሱ ወስደን ለሕዝቡ እናደርሳለን። እነርሱ አካባቢ ምንም ችግር የለም። የኤሌክትሪክ ኃይል አለ። ከሌለ ለሕዝብ የኤሌክትሪክ እጥረት መኖሩ ይነገራል። እጥረት ካለ መኖሩን የሚናገረው የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ ኃይል ነው። የእኛ ሥራ የገዛነውን ማከፋፈል ነው።
አዲስ ዘመን፡- በሰሜኑ ጦርነት ብዙ የኤሌክትሪክ አገልግሎት መስጫዎች ወድመዋል። ያንን ለማስተካከል እና ወደ ነበረበት ለመመለስ የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ ኃይልም ሆነ የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ አገልግሎት ብዙ ሥራዎችን ሠርተዋል። እዚህ ላይ በመጠባበቂያነት ለጥገና በሚል የተያዙ ግብዓቶች በሙሉ ወደ ተጎዳው አካባቢ ሔደዋል ሲባል ነበር። አሁን ተደጋጋሚ የኃይል መቋረጥ ከጦርነቱ ጋር የተያያዘ ነው ማለት ይቻላል? ምክንያቱም አዲስ አበባ ላይ የኤሌክትሪክ ኃይል እየተቋረጠ ነው የሚባለው ክረምት ስለሆነ ብቻ ሳይሆን ክረምቱ ከመግባቱ በፊትም በስፋት ይቋረጥ ነበር። አሁንም ይኸው ቀጥሏል። የግብዓት እጥረት አለ?
አቶ በቀለ፡- እንደተባለው በአዲስ አበባ ደረጃ ለጥገና የግብዓት እጥረት አላጋጠመም። በእርግጥ በተቋም ደረጃ ግብዓቶች ወደ ወደሙ አካባቢዎች ሔደዋል። ሌላው ከኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ ኃይል ያን ያህል ከባድ ችግር አላጋጠመንም። ነገር ግን ጀሞ አካባቢ አንድ የእነሱ ፓወር ትራንስፎርመር ተቃጥሏል። ለሁለት ወር ብዙ መከራ ሆኖ ነበር። ምክንያቱም ትራንስፎርመሩ ሰባት መስመሮችን የያዘ ነበር። ሰባቱን መስመሮች ከሌላ ቦታ በማበዳደር ሲሰጥ ነበር። በዚህ ምክንያት ሕዝቡ ሲሰቃይ እንደነበር አይካድም። በማበደርም ኤሌክትሪኩን የምንሰጠው ለአራት ሰዓት ብቻ ነበር።
አዲስ ዘመን፡- ከማበዳደር እና በሰዓት ከመስጠት ይልቅ በአዲስ መተካት አይሻልም ነበር?
አቶ በቀለ፡- መተካት ያለባቸው እነርሱ ናቸው። የተቃጠለባቸው የእነርሱ ሲሆን ተክተው ኃይል መስጠት ያለባቸውም እነርሱ ናቸው። እኛ ግን ደንበኞቻችን ኤሌክትሪክ እንዳያጡ ከሰበታ የሚገኘውን ከአንፎ እና ከሌሎችም ንዑስ ጣቢያዎች ኃይል በማበደር ከፍተኛ ጥረት በማድረግ አሁን የደረሰበት ደረጃ ላይ ደርሰናል። ጀሞ ላይ አየር ጤናን ጨምሮ ሰባት መስመር ማለት በጣም ብዙ ነው። ያንን ሁሉ በማበዳደር ተክተናል።
አዲስ ዘመን፡- አሁን እነርሱ ተክተዋል?
አቶ በቀለ፡- ለጊዜው መረጃ የለኝም። በእኛ በኩል ግን በማበዳደር ችግሩን አቃለነዋል። ከመካኒሳ ከአንፎ እያልን ለማሟት ሞክረናል። አሁን በአጠቃላይ ችግሩ ተቃሏል።
አዲስ ዘመን፡- አሁን ጀሞ ብቻ አይደለም፤ ከላይ እንደገለፅኩት አስኮ እና ሌሎችም አካባቢዎች ላይ ተመሳሳይ ችግር አለ። ሰዎች ደግሞ አሁን ላይ በኤሌክትሪክ በኩል ጥገኞች ናቸው? ሥራቸው ከኤሌክትሪክ ጋር የተቆራኙ ሰዎች ከፍተኛ ችግር እያጋጠማቸው ነው። እዚህ ላይ ምን ይላሉ?
አቶ በቀለ፡- አስኮ አካባቢ ብርጭቆ እና አራት መንታ አካባቢ አንደርግራውንድ መስመር ብልሽት አጋጥሞ ነበር። ሃያት ፣ ቃሊቲ ፣ ቡልቡላ እና ሌሎችም አካባቢዎች ላይ ግራውንድ ኬብል ሲበላሽ ኃይል ይቋረጣል። የት አካባቢ እንደተበላሸ አይታወቅም። ያ ግራውንድ ኬብል እስኪገኝ መከራ ነው። ኮልፌ አካባቢም ከፍተኛ ጭነት ያለበት እና በጣም የምንቸገርበት አንድ መስመር አለ። እነዚህ ችግር ያለባቸው አካባቢዎች ላይ ትኩረት ይሰጣል። የተለየች ትንሽ አካባቢ ላይ ከሆነ ቅርብ ላለው ማዕከል ሔዶ መንገር ነው። እንዲህ አይነት ችግር ይኖራል። ትራንስፎርመሩ ጭነት በዝቶበት ፊውዝ ሊቃጠል ይችላል። ይህ በአስቸኳይ ጥገና ይስተካከላል።
አዲስ ዘመን፡- የአዲስ አበባ ነዋሪ ቁጥር ከዕለት ወደ ዕለት እየጨመረ ነው። የነበረው ሕዝብም ቢሆን ፍላጎቱ እንደጨመረ ለማወቅ ጥናት አያስፈልግም። ብዛት ያላቸው የጋራ መኖሪያ ቤቶች ለመኖሪያነት እየተዘጋጁ ነው። ለዚህ ሁሉ ፍላጎት የሚመጥን ሥራ እየሠራችሁ ነው?
አቶ በቀለ፡– በዋናነት መሥመሮቹ አሉ። መስመሮቹን ለማሳደግ የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ ኃይል ተለዋጭ መስመሮችን አዘጋጅቶልናል። ለምሳሌ ኮዬ ፈጬ እና ቡልቡላን የመሳሰሉ ብዛት ያላቸው የጋራ መኖሪያ ቤቶች ባሉባቸው አካባቢዎች ላይ ሥራ ተጀምሯል። ኮዬ ፈጬ ብቻውን ትልቅ ከተማ ነው። ባለው ኔትወርክ ውስጥ መግባት አይችልም። ለብቻው ከዛ ጋር አንድ በጣም ትልቅ ማከፋፈያ ጣቢያ ቆሞለታል። ስለዚህ ኃይል ከዛ ይወጣል።
በሌላ በኩል በየአካባቢው አጋዥ ትራንስፎርመር እየሠራን ነው። ፍላጎት ሲያድግ ትራንስፎርመር አብሮ ይጨምራል። ወደ ማከፋፈያ ጣቢያ የሚሔደው መስመር ከቻለ ቻለ፤ እርሱ እያለ የሚያድገውን ፍላጎት ብቻ ከስር ከስር እየጨመሩ መቀጠል ነው። ኔትወርኩ ላይ ቀጫጭን ሽቦዎች ከሆኑ በመደበኛነት የማሻሻል ወደ ወፍራም የመቀየር ሥራ ይሠራል። ከፍላጎት ዕድገቱ ጋር እኩል ለመሔድ እና ያለውን ለማሻሻል አሠራር ተዘርግቷል። ነገር ግን የአቅም ጉዳይ ችግር ነው።
አዲስ ዘመን፡-አቅም ሲሉ የገንዘብ አቅም ማለትዎ ነው?
አቶ በቀለ፡- ታዲያስ ገንዘብ ካለ ምን ችግር አለ። ሁሉንም መሥመር መለወጥ ይቻላል። በብድርም በምንም እያስለወጥን ያለነው ለዚሁ ነው። ገንዘቡ ካለ ከፍላጎቱ ጋር እኩል መሔድ አያዳግትም። ኅብረተሰቡ ምን ያህል እንደሚፈልግ ይነበባል፤ ፍላጎቱ ሲጨምር አጋዥ ትራንስፎርመር ከጎን ይቀመጣል። አሁን ኃይል አነሰ ሲባል፤ ኃይል አንሰጥም ይባላል። ምክንያቱም መሥመሩ መሸከም ስለማይችል ይፈነዳል በሚል ስጋት ነው። ነገር ግን አጋዥ ትራንስፎርመር እየተቀመጠ ከሆነ አዲስ አበባ ላይ ችግሩ እየተቃለለ ይሔዳል። ያለበለዚያ መስመር ላይ ችግር ሲኖር ኃይል ይቋረጣል። በዋናነት ኃይል የሚቋረጠው ከኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ ኃይል ነው። መልሰው ቢለቁትም የቴክኒክ ጉዳይ ስለሆነ መልሶ መስመሩ አይሸከመውም በድጋሚ ይቋረጣል። በዚህ ጊዜ በደንብ ፈልጋችሁ ሥሩ ይባላል።
አዲስ ዘመን፡- አዳዲስ የጋራ መኖሪያ ቤቶች አሉ። ለጋራ መኖሪያ ቤቶቹ የኤሌክትሪክ አገልግሎት የምትሰጡበት አሠራራችሁ እንዴት ነው?
አቶ በቀለ፡- እኛ የኤሌክትሪክ አገልግሎት የምንሰጠው ሙሉ ለሙሉ ሥራቸው ለተጠናቀቁ የጋራ መኖሪያ ቤቶች ነው። ልክ እንደየካ አባዶ በመሬት ውስጥ ለውስጥ (አንደርግራውንድ) ላይ መስመር እንዘረጋለን። ቤቶቹ ካለቁ ትራንስፎርመር አስገብተን ቆጣሪ እንለጥፋለን። የጋራ መኖሪያ ቤት ላይ ብቻ የሚሠራ የፕሮጀክት ቢሮ አለ። እርሱ ከአዲስ አበባ ቤቶች ጋር በጋራ በማቀድ ምን ያህል እንደሚያስፈልግ ታውቆ ይሠራል።
አንዳንዴ የምንቸገረው የመንገድ ግንባታው ካላለቀ ነው። ለምሳሌ ኮዬ ፈጬ ላይ የተቸገርነው መንገዱ አላለቀም። ሰው ተቸግሯል፤ መሠረተ ልማቱ ባያልቅም ይገባል። ስለዚህ ጊዜያዊ መፍትሔ በማሰብ ከላይ መስመር እንዲዘረጋ እየተሠራ ነው። በተረፈ የቤቱ እና የመንገድ ግንባታው ከተጠናቀቀ መስመር ለመዘርጋትም ሆነ ቆጣሪ ለመለጠፍ ምንም ዓይነት ችግር የለብንም። አልፈን ተርፈን ከውጪ ትራንስፎርመር ተክለን ለመስጠት እና ሌላ ወጪ ለማውጣት ሁሉ ፈቅደን እየሠራን ነው።
አዲስ ዘመን፡- ከኃይል መቆራረጥ ጋር ተያይዞ ብዙ ሰዎች የኃይል ማነስ ያጋጥማቸዋል። እንደውም ለእኛ በቂ ኃይል ሳይኖር ለሌላ አገር ተሸጠ የሚሉ ሀሜቶች አሉ። እዚህ ላይ ምን ይላሉ?
አቶ በቀለ፡- እኛ ኃይል ጠይቀን ያጣንበት ጊዜ የለም። የኃይል ችግር ካለ በሀገር ደረጃ መነገሩ አይቀርም።
አዲስ ዘመን፡- የጥሬ ዕቃ ችግር የለባችሁም? የውጪ ምንዛሪው ችግር እናንተን አልነካም?
አቶ በቀለ፡- ከኬብል ጋር ተያይዞ ያለውን ችግር ለማቃለል ግለሰቦች ኬብል እንዲገዙ አድርገናል። ትራንስፎርመር ደግሞ አምራቾች አሉ። የምንገዛው ከእነርሱ ነው። ኬብል አምራቾች ኢትዮጵያ ውስጥ በዝተዋል። ስለዚህ ይህን ያህል ችግር አለ ማለት አይቻልም። ምሰሶም ሆነ ቆጣሪ አለ። ጊዜያዊ ካልሆነ በቀር ከባድ የጥሬ ዕቃ ችግር የለም። ትራንስፎርመር የሚፈልግ ካለ ራሱ ይገዛል እኛ እንገጥማለን።
አዲስ ዘመን፡- አሮጌ መስመር ማደስን በሚመለከት ምን ይላሉ? በእርግጥ እየታደሰ ነው?
አቶ በቀለ፡- የ600 ኪሎ ሜትር እድሳት አልቆ ትልቅ እፎይታን ሰጥቷል። አሁን ደግሞ የ400 ኪሎ ሜትር ተጀምሯል። ወደ ፊት ይቀጥላል። ከስር ከስር በራስ አገዝ ቢሠራም፤ በሶስተኛ ወገን በተቋራጭ እየሠራን መሆኑ ትልቅ ውጤት እያስገኘ ነው። ራሳችን ካልሠራን ስንል ኅብረተሰቡ በብዛት በመንገላታቱ የኮንትራት ማኔጅመንት ቢሮ ለሦስተኛ ወገን ሥራውን እየሠጠ በፍጥነት በቀላሉ እየተሠራ ነው። እኛ ዕቃ እናቀርባለን ተቋራጩ ሥራውን ያጠናቅቃል።
አዲስ ዘመን፡- ዕድሳቱ ምን ያህል አስተማማኝ ነው? ግራውንድ ታደርጉታላችሁ ወይንስ ምን ይሆናል?
አቶ በቀለ፡- ግራውንድ መሠረት ልማት ይፈልጋል። ከመስቀል አደባባይ እስከ ቦሌ ሙሉ አንደርግራውንድ ነበረ። ነገር ግን የመንገድ ሥራ አበላሸው፤ ስለዚህ ሙሉ ለሙሉ አወጣነው። የፈረንሳይ መንገድም በተመሳሳይ ፈርሷል። ስለዚህ ያለቀለት መንገድ ይፈልጋል። አሁን የተቸገርነው ይኸው ነው። አንደኛው መንገዶች ባለስልጣን ሥራውን ለሶስተኛ ወገን ይሰጣል። እነርሱ ሳያማክሩን ወደ መንገድ ቁፋሮ ሲገቡ መስመር ይቋረጣል። የሆነ ቦታ ይፈነዳል። በትክክል የተበላሸበትን ማወቅ ራሱ መከራ ይሆናል። መከራችንን የበላነው በዚህ ነው። በጥገና ምክንያት ሰዎች ይሰቃያሉ።
አዲስ ዘመን፡-የተለያዩ የመሠረተ ልማት አውታሮችን የሚያቀናጅ ተቋም ተቋቁሞ ነበር። በሥራ ላይ የምትሠሩት በቅንጅቱ መሠረት ነው?
አቶ በቀለ፡- ተቀናጅቶ ለመሥራት ይሞከራል፤ ነገር ግን ችግሩ መንገዶች ለሦስተኛ ወገን ሲሰጡ ችግር ይፈጠራል።
አዲስ ዘመን፡- የኤሌክትሪክ አገልግሎት የዋጋ ማስተካከያ ተደርጓል። ሠራተኛው ምን ተጠቀመ? ደመወዝ ጥቅማጥቅም እና በተለይ በሥራ ላይ አደጋ ሲደርስ የሚሰጠውን ካሳ በሚመለከት ምን ለውጥ መጣ?
አቶ በቀለ፡- ማስተካከያው የተደረገው ከግዢው ጋር ተያይዞ ነው። የጥሬ ዕቃ ዋጋ ጨምሯል። ለአራት ተከፋፍሎ ታሪፉ ጭማሪ ተደርጓል። አሁን አልቋል። የአገልግሎት አሰጣጣችንን እና የግዢ ሥርዓታችንን እኩል ለማድረግ ብቻ ነው።
አዲስ ዘመን፡- የተቋሙ ሠራተኞች ደመወዝ በሚመለከት ምን ለውጥ አለ?
አቶ በቀለ፡- ተቋሙ ሠራተኛ ማኅበር አለው። ማኅበሩ ይደራደራል። ያለውን የኑሮ ውድነት ማዕከል በማድረግ በየዓመቱ ጭማሪ ወይም ማስተካከያ አለ። ጉዳቱ ላይ ኢንሹራንስ አለ። ነገር ግን ቀድሞ መጠንቀቅ ላይ ትኩረት አድርገን እየሠራን ነው። ራሱን የቻለ ክፍል ተከፍቷል። በቸልተኝነት አደጋ እንዳይደርስ ዕቃዎችን የሚያሟላ ክፍል አለ። ነገር ግን በማስተማር እና በመከላከል ካልሆነ ውጤቱ ብዙ አይሆንም። መስመር ሲበጠስ ስለማይታይ አደጋ ይደርሳል፤ ምክንያቱም እሳቱ ሽቦ ላይ አይታይም ሲነካ ይገድላል። ዋናው ነገር ጥንቃቄው ነው።
አዲስ ዘመን፡- በመጨረሻ የሚሉት ካለ ዕድሉን ልስጥዎት።
አቶ በቀለ፡- ተቋሙ ሕዝቡ ያለውን ፍላጎት ለሟሟላት ዕቅድ አለው። በዕቅዱ መሠረት እየሠራን ነው። ሌላው ፍጆታቸውን በጊዜ የማይከፍሉ በአግባቡ ይክፈሉ። ምክንያቱም በክፍያ ምክንያት አገልግሎት ማቋረጥ ለተቋማችንም ለተገልጋዩም ኪሳራ ነው። ለፍጆታው ቶሎ በተገቢው ጊዜ ከተከፈለ አገልግሎቱ የበለጠ የተቀላጠፈ ይሆናል። ሌላው በየአካባቢው የኃይል መዋዠቅ የሚያጋጥመው በኃይል ስርቆት ምክንያት ነው። ስለዚህ እንጀራ ቤቶች እና ብረት መበየጃዎች በመሳሰሉት የሥራ ቦታዎች የኤሌክትሪክ ስርቆት አለ። እዚህ ላይ ኅብረተሰቡ መጠቆም አለበት።
አዲስ ዘመን፡-ስለነበረን ቆይታ እጅግ አመሰግናለሁ።
አቶ በቀለ፡- እኔም በጣም አመሰግናለሁ።
ምህረት ሞገስ
አዲስ ዘመን ሰኔ 29 /2014