በ1952 ዓ.ም ታህሳስ 6 ቀን ከእናቱ ከወ/ሮ አምሳለ ዘለቀ እና ከአባቱ ከአቶ አለሙ ወልደማርያማ አዲስ አበባ እንጦጦ ቁስቋም ማርያማ አካባቢ ተወለደ:: የመጀመሪያ ደረጃ ትምህርቱን እቴጌ ጣይቱ ብጡል አንደኛና መለስተኛ ሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤት አጠናቀቀ:: ከዚያ በኋላ ወደ ተፈሪ መኮንን ትምህርት ቤት በመግባት ሁለተኛ ደረጃ ትምህርቱን አጠናቀቀ:: የከፍተኛ ደረጃ ትምህርቱንም በአስመራ ዩኒቨርሲቲ ተከታትሏል:: የሰለሞን የኪነ ጥበብ ህይወት ግን የጀመረው ገና የሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤት ተማሪ እያለ በትምህርት ቤት በሚያቀርባቸው መነባንቦች እና ድርሰቶች ነበር::
ከዚያም በኋላ ወደ አስመራ ክፍለ አገር መሄዱ ለኪነ ጥበብ ህይወቱ ትልቅ እመርታ ሆነ:: በወቅቱ አስመራ ከፍተኛ የፖለቲካ ነውጥ የምታስተናግድ ከተማ የነበረች ቢሆንም በዚያ ነውጥ መሀልም ሆኖ ትልልቅ ስራዎችን መስራት ችሏል:: ከሰራቸው ስራዎች መካከል ደደቧ ወላንሳ፤ ብእሬ፤ እምቧሶራ፤ ሰው ማለት ቀይ ባህር እና መሰል ስራዎቹ ተጠቃሽ ናቸው::
ሰለሞን ህይወቱን በሙሉ የተለከፈበትን የኪነ ጥበብ ስራ የሰራው ግን ወደ አዲስ አበባ ተመልሶ እነ ድርብ ወርቅ ሰይፉ፤ ሰራዊት ፍቅሬ እና መሰል ታላላቅ አርቲስቶችን ያፈራው አፍለኛው የቴአትር ክበብን ከመሰረተ በኋላ ነው:: የክበቡ መሪ እንዲሆን ከተመረጠ በኋላ ከምክትሉ ሰራዊት ፍቅሬ ጋር በመሆን አቅማቸው እና ተሰጥኦቸውን ለማስፈተሽ ወደ ቤተሰብ መምሪያ ሄዱ:: አቅማቸው ተፈትሾም የቤተሰብ መምሪያ የወጣቶች ፕሮጀክት ውስጥ እንዲሳተፉ እድሉ ተሰጣቸው:: ዘመን ተሻጋሪ የሆኑላቸውን እና እስከዛሬ የሚሞገሱባቸውን ስራዎች መስራት የቻሉትም እዚያ ነው:: በተለይም የሰለሞን ብእር ቀለም መትፋትን አላቆም አለ:: ለቁጥር የሚያታክቱ ድርሰቶችም ተፈጠሩ:: በስራዎቻቸውም መላው ኢትዮጵያን አካለሉ::
ሰለሞን ኮሜዲን በመጻፍ ቀዳሚ የሌለው ሰው ነው ብንል ማጋነን አይሆንም:: ህይወቱ ከህዝብ ጋር የተሳሰረ በመሆኑም በማንኛውም ጉዳይ ላይ ለመጻፍ ሲነሳ ተቸግሮ አያውቅም:: የሱን ጽሁፍ ወደ ትወና ለመቀየር ደግሞ አፍለኛው ውስጥ የነበሩ በርካታ ወጣት ተዋንያን ዋነኛ ጉልበቶቹ ነበሩ:: ፍራሽ ሜዳ፤ ከዳንኪራ ጀርባ፤ የሁለት አለም ሰዎች፤ በድሉ፤ አዙሪት፤ እና መሰል ስራዎች በወቅቱ ሰለሞን እና የአፍለኛው አጋሮቹ በጋራ ሰርተዋቸው ቴአትር ቤቶች በተመልካች እንዲጨናነቁ ያደረጉ ነበሩ:: ሳንካ እና ከል ጸዳል ደግሞ የሬድዮ አድማጩን ጆሮ ተቆጣጥረው ነበር:: ከነዚህ በኋላ ነበር ታሪካዊው ሸምጋይ የሬድዮ ድራማ የተሰራው:: አብዬ ዘርጋው በሚሊየኖች የሚቆጠሩ ኢትዮጵያውያን በሬድዮ ድራማ ፍቅር ይጥሉ ዘንድ በሰለሞን ብእር በአፍለኛ ቡድን ትወና ተከሰቱ::
በአብዬ ዘርጋው የእሁድ ጠዋት ተከታታይ ድራማ ላይ ደራሲው ሰለሞን በድራማው ማጠናቀቂያ ታሪክ ላይ ዋናውን ካራክተር አብዬ ዘርጋውን እንዲሞቱ በማድረጉ በርካታ የድራማው አድማጮች በጣም ተቆጥተው ሰላማዊ ሰልፍ አድርገዋል:: ያን ጊዜ አቡነ ጴጥሮስ በሚገኘው የኢትዮጵያ ሬዲዮ ጣቢያ በመሄድ በሩ ላይ ‹‹አብዬ ዘርጋውን ደራሲው ከሞት ያስነሳልን›› በማለት በከፍተኛ ድምፅ በመጮህና በሬዲዮ ጣቢያው ስልክ እና ፖስታም በቁጣ በርካታ አድማጮች መልዕክት በማስተላለፍቸው ‹ተጠናቋል› የተባለውን ድራማ ጠቢቡ ሰለሞን ለአድማጮቹ ባለው ክብር የተነሳ በሚያስገርም ጥበባዊ ለዛ እና ጨዋነት አስመስክሯል:: ጎርፍ ወስዷቸው ሞተዋል ያላቸውን አብዬ ዘርጋውን ከወንዝ ዳር እንደተገኙ አድርጎ ከሞት አንስቶ አድማጮች በድጋሚ በድራማው እንዲዝናኑ ያደረገ ታላቅ ደራሲ ነው።
ሰለሞን እውነተኛ ደራሲ ነው:: ከመጻፍ ውጭ ሌላ የሚያስደስተው ነገር የለም:: በ80ዎቹ እና በ90ዎቹ ወደ ኢትዮጵያ የቴአትር ሰው በሙሉ ከሰለሞን ጋር ያልሰራ አይገኝም:: ሰለሞን አለሙ በአብዬ ዘርጋው ገኖ ይታወቅ እንጂ ከ500 በላይ ድራማዎችን መጻፉ ተመስክሮለታል:: ሰለሞን የአንድ ወንድ ልጅ አባት ነበር::
ዜና እረፍቱ ከተሰማ በኋላ ብዙ ወዳጆቹ ሀዘናቸውን የገለጹ ሲሆን የጥቂቶቹ እነሆ፡-
“1970ዎቹ መጨረሻ ኤርትራ ክፍለ አገር የዱቄት ፋብሪካ ሠራተኛ ሆኖ በሄደበት ወቅት “አታ ግደፈኒ”፥ “አማን” የሚሉ ግጥሞችን በማቅረብ ይታወቃል። በዚያን ጊዜ ከሁለቱም ወገኖች ይፈለግ እንደነበረ አጫውቶኛል:: የተዋወቅሁት 1977 ዓ.ም ሽሮሜዳ አቶ ጃለታ ጃፈሮ ቤት ነው:: ከልጆቻቸው ጋር አብሮ አደግ ነው:: አብዬ ዘርጋውን እና ሌሎች ቀደምት ሥራዎቹን ይፅፍ የነበረው እዚህ ነበር:: ደደብዋ ወላንሣ የሚል ግጥሙንም 1980 ዎቹ መጀመሪያ ላይ ራስ ትያትር ሲያቀርብ አስታውሳለሁ።
ወንድሜ ሠለሞን አለሙ ነፍስ ይማር! (ዶ/ር ሰለሞን ዓሊ- የኢትዮጵያ ቀይ መስቀል ማኅበር ፕሬዚዳንት)
“ሰለሞን ሕይወቱን ለኪነ ጥበብ አሳልፎ የሰጠ፣ ዘመኑን በሚገባ ሰርቶበት፣ ሺሖችን ያፈራ፣ ሚሊዮኖች በሬዲዮ ድራማ ፍቅር እንዲወድቁ ምክንያት የሆነ አርቲስት! አገሩን፣ ወገኑን፣ ሕይወት ራሱን ጠንቅቆ የተረዳ ደራሲ ተዋናይ እና ገጣሚ ነበር::
(ደራሲ ዳንኤል ወርቁ) ይህ ሰው ሐገሩን የሚወድ፣ ለራሱ ሃሳብና እምነት የታመነ ብእረኛ ነው::
ለእውነት፣ ለፍቅር፣ ለፍትህና ለሰላም የላቀ ቦታ አለው:: ልበስሱ ነው:: ህይወቱን ሙሉ ለሚወደውና ለሚያከብረው ሙያ እየሰጠ የነበረ ሰው ነው:: ሰለሞን አለሙ ይባላል:: ደራሲ፣ አዘጋጅና ተዋናይ ነው:: ብዙዎች በተለምዶ “አብዬ ዘርጋው ” እያሉ በሚጠሩት “ሸምጋይ” በተሰኘው ተከታታይ የሬዲዮ ድራማ ያውቁታል:: የራሱ የአፃፃፍ ይትበሃል (style) ያለው ፀሐፊ ነው:: በሰው ልጅ ማህበራዊ ህይወት ላይ አተኩሮ የሚፅፍ ታላቅና ጠንካራ ፀሐፊ ነው::
ሰለሞን ለሰናይ ምግባርና ለስነምግባር የቆመ ነው:: ለራሱ ሃሳብና እምነት የታመነ ብእረኛ ነው:: የእኩይ ድርጊቶች ጠላት ነው:: እውነት ብቻ ናት የብዕሩ ማዕከል:: ህይወቱ እውነት ናት:: ብእሩም ከህይወቱ የሚቀዳ ነው:: ሰለሞን በስራዎቹ ማህበራዊ ሃያሲ ደራሲ ነው ማለት እችላለሁ:: በርካታ በህዝብ ክብርና ፍቅርን ያጎናጸፉ የጥበብ ስራዎች አሉት::
በሐምሌ 1983 ዓ.ም በቤተሰብ መምሪያ የተገናኙት ሰለሞን እለሙ፣ ሠራዊት ፍቅሬ፣ አዜብ ወርቁ፣ ድርብወርቅ ሰይፋ፣ ፍሬህይወት መለሰ ሆነው በጋራ በከፈቱት “አፍለኛው” በተሰኘው የትያትር ቡድን ውስጥ ሰለሞን በጻፉቸው በርካታ ድርሰቶች አማካኝነት ብዙ ሰርተዋል::
ሰለሞን አለሙ 500 የሬዲዮ ድራማዎችን ፅፎአል:: እንደዛሬው ተከታታይ የቴሌቪዥን ድራማዎች በሌሉበት ዘመን 13 ተከታታይ የቴሌቪዥን ድራማዎችን ፅፎ አዘጋጅቷል:: እንዲሁም 6 ትያትሮችን ጽፎ አዘጋጅቷል፣ ተውኗል:: በሌሎች ፀሐፊያን በተሰሩ የቴሌቪዥን ድራማዎችና ቲአትሮች ላይም ተውኗል::
ሰለሞን በርካታ መነባንቦችንም ለመድረክ አብቅቷል:: በተለይ በእሁድ ረፋድ ላይ በኢትዮጵያ ሬዲዮ ለ70 ሳምንት ሲተላለፍ የቆየውና በመላው ኢትዮጵያን ዘንድ ተወዳጅ የነበረው ” ሸምጋይ” ወይም (አብዬ ዘርጋው) የተሰኘው የሬዲዮ ድራማው ዛሬ ድረስ በብዙ ኢትዮጵያዊያን የሚታወስ ድራማ ነው:: ሠራዊት ፍቅሬ፣ አዜብ ወርቁ፣ ድርብወርቅ ሰይፋ፣ ፍሬህይወት መለሰ የዚህ ድራማ ፈርጥ (ጌጦች) ነበሩ:: ሰለሞን ትላንትም ዛሬም ይፅፋል::
(ጋዜጠኛ ይትባረክ ዋለልኝ) በእውቁ የኪነ ጥበብ ባለሙያ ጸሀፌ ተውኔት ሰለሞን አለሙ ህልፈተ ህይወት የተሰማኝን ሀዘን ስገልጽ ጥልቅ በሆነ የሀዘን ስሜት ነው:: ለቤተሰቡ፤ ለመላው የሙያው አድናቂዎች፤ እና ወዳጅ ዘመዶቹ በሙሉ መጽናናትን እየተመኘሁ ፈጣሪ ነፍሱን በአጸደ ገነት እንዲያሳርፈው ከልብ እመኛለሁ::
(ድምጻዊ ቴዎድሮስ ካሳሁን) ፀሐፊ ተውኔቱን፣ ደጉን፣ ሰው ወዳዱን፣ ተጫዋቹን ሰለሞን ዓለሙን ከእድሜዬ ከግማሽ በላዩን ያህል አውቀዋለሁ። በየጊዜው የምንደዋወልና በአካል የምንገናኝ አንሁን እንጂ ስንገናኝ ይበልጡን በእሱ ምክንያት ልብ የሚያሞቅ ወዳጅነት ይኖረናል። ሰለሞን መታመሙንና ወደመጨረሻ ላይም ያለ ኦክስጂን የማይንቀሳቀስ መሆኑን አውቃለሁ። ችግር ላይ እንደነበረም አውቃለሁ። ግን ዛሬ ነገ ስል አልጠየቅኩትም። በአቅሜ ያህል እንኳ አልደረስኩለትም። ብዙ ጊዜውን በህክምና ያሳለፈ እንደመሆኑ ገንዘብም ይቸግረው ነበር። አልደገፍኩትም። ገንዘብ አጥቼ ወይም ወዳጅነታችን የማያሰጥ ሆኖ ሳይሆን ቸልተኛ ሆኜ ነበር።
የግንኙነት ስፋቱን ያህል ሰዎች እየሄዱ አይጠይቁትም ስለነበር እናቱ ” ደጉ ልጄ ምነው ወዳጅ ራቀው ? ” ብለው ሊያስቡ ይችላሉ። እኔም እንዲህ እንዲያስቡ ካደረጓቸው ሰዎች መሀል አንዱ ነኝ። ወዳጄ ወድቆ ቤት ሲውል ለራሴ አድልቼ የምችለውን ያህል እንኳ ጊዜ አልሰጠሁትም። ” እንዴት ያደርግሀል ? ” አላልኩትም። ” ምን ይቸግርሀል ? ” አላልኩትም። ” እስቲ ይቺን ያዛት ለአንዳንድ ነገር እንኳ ትሆንሀለች ” እንኳ አላልኩትም። ” አይዞህ ሰሌ ” አላልኩትም። ሰው እንዳለው፣ ወዳጅ እንዳለው እንዲሰማው አላደረኩትም። እንደውም አደባባይ ተወጥቶ ቢለመንለት ያስፈልገው ይሆን ነበር፤ ምናልባት። እሱ ከችግሩ ጋር ሲሆን እንዲደረግለት ፈልጎ ይሆን ነበር፤ ምናልባት። ይህን ሁሉ ማድረግ ሲገባኝ አላደረኩም። ታዲያ የእኔ ቀብሩ ላይ መገኘት ጥቅሙ ምንድነው ? ለማን ነው ? ለምንድነው ?
ሰለሞን ዛሬ የለም። ብሔድም ብቀርም አያየኝም። በሚያየኝ ሰዓት፣ ሰው በሚፈልግ ሰዓት፣ ደውሎ ሳይቀር ጠይቆኝ ባለ ሰዓት፣ ሰው በራበው ሰዓት፣ ወዳጅ በናፈቀው ሰዓት እኔ ከጎኑ አልተገኘሁም። ሁሉም ነገር ካለፈና ምንም ማድረግ በማልችል ሰዓት የሚያሳምም ፀፀት ተሰምቶኛል። ምንም ማድረግ አይቻልም። ይህን እንኳ ነግሬ ላገኘው አልችልም። ሄዷል። አምልጧል። በቃ ያ ደግ ሰው ሳጥን ውስጥ ገብቷል። አብቅቷል። ቀብሩ ላይ የመገኘት አንዳች የሞራል ብቃት የለኝም። ብገኝና ለታይታ ባለቅስ፣ ባለቀ ሰዓት ቤቱ ተገኝቼ ወዳጅ ብሆን ራሴን ይበልጥ እታዘበዋለሁ። እጠላዋለሁ። በሕይወት ላይ፣ በእውነት ላይ የዘሞትኩ ያህል ይሰማኛል። እኔ ድራማ እጽፋለሁ እንጂ ድራማ የሆነ ሕይወት አልኖርም። ወንድሜን ድጋሚ አልክደውም። የመጀመሪያው ይበቃዋል። ሰዎች ሰው በፈለገ ሰዓት ዛሬ ከጎኑ ተገኙ። ነገ በማንም እጅ የለችም። ነገ ፀፀት ነው ያለው። ወንድሜ ሰለሞን ዓለሙ ደህና ሁን። ነፍስህ በሰላም ትረፍ። (ጋዜጠኛ ቴዎድሮስ ተክለ አረጋይ)
ሰለሞን አለሙ የአቅሙን ያህል ሳይሆን፣ የማህበረሰቡን ፈቃድና የአገሩን አቅም ያህል ሰርቶ እንዳለፈ ይሰማኛል:: ከአመት በፊት ይመስለኛል የሆነ ቦታ ተገናኝተን በቁም ሰላምታችን መሀል፣ ይህንኑ አንስቼለት፣ ተቀምጠን ለመጨዋወት እንድንደዋወል ተነጋግረን ነበር:: . . . ይኸው ዛሬ አረፈ:: . . . ያልታደለ ማህበረሰብ በጎተራ ከተሰጣቸው (ከያዙለት) ላይ በእፍኙ እየቆነጠረ፣ ምንም ያልተሰጣቸውን (ያልያዙትን) ባዶ ቁና በአካፋ ይቧጥጣል:: . . . አቧራው የሚበዛው ለዛ ነው! (ዶ/ር በድሉ ዋቅጅራ)
አቤል ገ/ኪዳን
አዲስ ዘመን ሰኔ 26/2014