ኢትዮጵያ የተፈጥሮ፣ ሰው ሰራሽና ሰፊ የባህል ሃብት ካላቸው አገራት ተርታ ትመደባለች። አገሪቱ የሰው ዘር መገኛም ናት፡፡ የብዝሃ ባህልና እምቅ የቱሪዝም ሃብት ባለቤት ከመሆኗ አንፃር ከዘርፉ ብዙ ትጠቀማለች ተብሎ ይጠበቃል። ይሁን እንጂ እንዳላት የተፈጥሮ፣ የታሪክና የብዝሃ ማንነት ሃብት ከቱሪዝም ዘርፍ እዚህ ግባ የሚባል ጥቅም እንዳላገኘች ይገለጻል።
ይህ ብቻም አይደለም፤ ዓለማችን ላይ በጎብኚዎች መዳረሻነት ከሚታወቁት አገራት ተርታም መሰለፍ አልቻለችም። እነዚህ አገሮች በባህላዊ ተፈጥሯዊ፣ ታሪካዊ እሴቶቿ በብዙ እጥፍ የምታስከነዳቸው አገራት ሃብቶቻቸውን የመጠበቅ፣ የማስተዋወቅና ምቹ መሰረተ ልማት በመገንባት የመንከባከብ ተግባር በመስራታቸው ብቻ ቱሪዝምን የኢኮኖሚ አንቀሳቃሽና የጀርባ አጥንት እንዲሆን አስችለውታል።
ወደ አገራችን ስንመጣ ግን ይህ የተገላቢጦሽ ሆኖ እናገኘዋለን፡፡ “በእጅ የያዙት ወርቅ እንደ መዳብ ይቆጠራል” እንዲሉ አገሪቱ የቱሪዝም ዘርፉን እሴቶች በሚገባ በመረዳት ከዚያም ተጠቃሚ ለመሆን የሚጠበቅባትን ያህል ሳትሰራ ቆይታለች፡፡ እንዲያም ሆኖ ግን የአገሪቱን የቱሪዝም መስህቦች የጎበኙ የውጭ ቱሪስቶች በደብዛዛውም ቢሆን ስለድንቅ የቱሪዝም ሀብቶቿ ድምፃቸውን ከፍ አድርገው በመደነቅ ምስክርነታቸውን ሲሰጡ ይሰማል። ይህ ነው የሚባል የአገር ውስጥ ጎብኚ ባይኖርም፣ በአገራቸው የቱሪዝም ሃብት ኮርተው ዙሪያ ገባውን በመቃኘት ዓለም ትኩረት እንዲሰጠው የሚሞግቱም የአገር ውስጥ ጎብኚዎች አልጠፉም። ከቅርብ ጊዜ ወዲህ ደግሞ መንግስት ዘርፉን በሚገባ መጠቀም የሚያስችሉ ስራዎችን እየሰራ ይገኛል፡፡
ቱሪዝምና መዳረሻ ስፍራዎች በማልማት፣ በማስተዋወቅ ጎብኚዎችን በመሳብ እንዲሁም አዳዲስ መዳረሻዎችን በመፍጠር ከሃያላኑ ተርታ የሚያሰልፍ ጠንካራ ኢኮኖሚና እጅግ ተወዳጅ አገርን በመፍጠር ብልጽግናን ማረጋገጥ እንደሚቻል ታምኖበት እየተሰራ ነው። በአዲስ አበባ የቱሪስቱን ቆይታ ሊያራዝሙ የሚችሉ የግዙፍ ፓርኮች ግንባታዎች ተካሂደዋል፤ በገበታ ለአገር ፕሮጀክት ደግሞ በኮይሻ፣ በወንጪና በጎርጎራ ግዙፍ ተግባሮች እየተከናወኑ ናቸው፡፡ መንግስት አገሪቱን ከብልጽግናው ማማ ላይ በክብር ለማስቀመጥ የቱሪዝም ዘርፉን ከኢኮኖሚው ዋና ዋና ምሰሶዎች አንዱ ዘርፍ አርጎ አስቀምጦ እየሰራ ይገኛል።
መንግስት የቱሪዝም መዳረሻዎችን ከማልማት፣ የመስህብ ስፍራዎችን ከማስተዋወቅና መሰል ዘርፉን የሚያንቀሳቅሱ ተግባራት ላይ ከመሳተፍ ባሻገር የግሉ ዘርፍ፣ ባለሃብቶች እና ሌሎች ከቱሪዝም ጋር ተያያዥ ትስስር ካላቸው አካላት ጋር እንዲሰራ ይጠበቃል። በዋናነት በእቅዱ የያዛቸውን ፕሮጀክቶች እነዚህ አካላት በቀጥታም ይሁን በተዘዋዋሪ እንዲደግፉ በሩን ክፍት ከማድረግ ባሻገር በግል ተነሳሽነት ለአገሪቱ ቱሪዝም የሚጠቅሙ እቅዶችና አዳዲስ ፕሮጀክቶች ሲኖሩ በሙሉ አቅም በመደገፍ እውን እንዲሆኑ ምቹ ሁኔታ እንዲፈጥር ይጠበቃል።
ከዚህ አንፃር በኢትዮጵያ ውስጥ በቱሪዝም ዘርፍ የመንግስትና የግሉ ዘርፍ ተቀናጅቶ በመስራት በኩል ጎልቶ የሚታይ ሁኔታ እንደሌለ አንዳንድ የዘርፉ ባለሙያዎች ይናገራሉ። የግሉም ዘርፍ አዳዲስ የቱሪዝም ፅንሰ ሃሳቦችን በማምጣትና በማስፋፋት የድርሻውን ከመወጣት አኳያ እዚህ ግባ የሚባል ስራ ሲከውን እንደማይታይ ይነገራል። በእርግጥ በሆቴልና ሆስፒታሊቲው ዘርፍ የግል ባለሃብቶች የማይናቅ አበርክቶ እንዳላቸው ግን የሚካድ አይሆንም።
የዝግጅት ክፍላችን በዛሬው የባህልና ቱሪዝም አምዳችን በግል ጥረት ለቱሪዝም ዘርፉ የበኩሉን አበርክቶ ለማኖር የሚጥር የአንድ ግለሰብ ፕሮጀክትን በመዳሰስ ይህን መሰል ጥረቶች በጥቅሉ ስለሚኖራቸው ፋይዳ ይዳስሳል። እግረ መንገዱንም መንግስትና የግሉ ዘርፍ ቅንጅት አስፈላጊነትን በመዳሰስ ለቱሪዝም ዘርፉ ያለውን ፋይዳ አንመለከታለን። ይህ ወጣት በግል ተነሳሽነት በምዕራብ ጎጃም ዞን ደጋ ዳሞት ወረዳ የሚገኘው ማራኪው ሙሉ ኢኮ-ሎጅ መስራችና ከማህበረሰቡ ጋር በቅንጅት የቱሪስት መስህብ እንዲሆን ጉልህ ድርሻ መጫወት የቻለ ነው።
ጥቂት ስለ ሙሉ ኢኮ ሎጅ
ሙሉ ኢኮ ሎጅ በዓይነቱ የተለየ በየትኛውም ሁኔታ ተፈጥሮን ማዕከል አድርጎ የተሰራ እና አገር በቀል እውቀትንና የማህበረሰቡን ወግና ባህል ለሌሎች ማስተዋወቅን እና ተጠቃሚ መሆንን ታሳቢ ያደረገ ነው። የዚህ ሃሳብ ጠንሳሽና ልምድና ዕውቀቱን ለተወለደበት ማህበረሰብ በማካፈል ህዝቡ ተጠቃሚ እንዲሆን ያደረገው ወጣት አብይ ዓለም ኑሮውን በጀርመን አገር ባደረገበት ጊዜ ከቀሰመው ልምድ በመነሳት ሎጅ ማልማት ውስጥ እንደገባ ይገልፃል።
የሙሉ ኢኮ ሎጅ በጮቄ ተራራ አካባቢ ይገኛል። መረጃዎች አንደሚያመለክቱት፤ የጮቄ አካባቢ የመሬት አቀማመጥ 86 ከመቶ ተራራማ 1 ነጥብ 5 ከመቶ ሸለቋማ ና 12 ነጥብ 5 ከመቶ ሜዳማ ነው፡፡ የጮቄ የተፋሰሱ የታችኛው ክፍል ማለትም የአባይ ወንዝ እና መሰል አካባቢዎችን ተከትሎ ሸላቋማ ሲሆን፣ በዚህ አካባቢ እንደ ሾላ፣ ሉል፣ ክትከታ፣ ግራር፣ ቅላባና አምብስ በመሳሰሉ እፅዋቶች የተሸፈነ ነው፡፡ የመካከለኛው ክፍል ተራራማና ተዳፋታማ ሲሆን፣ ይህ አካባቢ በዋናነት በአስታ የተሸፈነና አልፎ አልፎ በአዕምጃና በሌሎች የተሸፈነ ነው፡፡
የጮቄ የላይኛው አካል በአብዛኛው ሜዳማ ሲሆን ይህም በጅብራ፣ ግምይና አሸንግድየ ተክሎች የተሸፈነና አካባቢው ከፍተኛ የሆነ የግጦሽ ጫና ያለበት ነው፡፡ ከጠጠር ወደ ድጓ ፅዮን ሲጓዙ ግምይና ጅባራ የበዛበትን ድልዳላማ መሬት አልፈን የምናገኘው የፍልፈል ሜዳ ከፍተኛ ቦታን እናገኛለን፡፡ ይህ ቦታ ለቱሪስት ማረፊያነት ማገልገል የሚችል ሲሆን የአካባቢውን ገፅታ ለመመልከት የሚያስችል ከፍተኛ ቦታ ነው፡፡
የጮቄ ተራራ ልዩ ውበትና ተፈጥሮአዊ ፀጋ መላበሱ እንደተጠበቀ ሆኖ የአፍሪካ የውሃ ማማነቱን ሊቀንስ የሚያስችሉ ድርጊቶች ሲፈፀሙበት ይታያል፡፡ ለምሳሌ ልቅ ግጦሽ፣ የደን መጨፍጨፍና ብርቅዬ የዱር እንስሳት መመናመን፣ በአካባቢው ባሉ አርሶ አደሮች በእርሻና በመኖሪያ ቤት መወረር ይታይበታል፡፡ ስለሆነም ቀጣይ ይህንን ቦታ ከነውበቱ ለማስቀጠልና ለማልማት ከመንግስትም ሆነ በየደረጃው ካለው ማህበረሰብ ትልቅ ትኩረት ሊሰጠውና የልማት ፕሮጀክት ሊነደፍለት እንደሚገባ ባለሙያዎች ምክረ ሃሳባቸውን ይሰጣሉ፡፡
የሙሉ ኢኮሎጅም ይህንን የአፍሪካ የውሃ ማማ እየተባለ የሚጠራ ቦታን ተጎራብቶ የሚገኝ ነው። የኢኮ ሎጁ መስራችና በአካባቢው የሚኖሩ ማህበረሰቦችንም ይህን መሰል መስህብነቱን የሚቀንሱ እንቅስቃሴዎች እንዲገደቡ፣ የቱሪስት መዳረሻነቱ እንዲጨምር፣ ከዚህም በላይ በአገር በቀል እውቀትና በራስ ማንነት ላይ የተመረኮዘ የኑሮ ዘይቤ ቀጣይነት እንዲኖረው እየሰሩ ይገኛሉ። የማህበረሰብ አቀፍ ሎጁ በደብረማርቆስ በደምበጫ በኩል 37 ኪሎ ሜትር ገባ ብሎ የሚገኝ ሲሆን፣ ተራራማና ለእይታ እጅግ ማራኪ በሆነ ወደ 3ሺህ 50 ሜትር ከፍታና አቀማመጥ ላይ እንደሚገኝ የኢኮ ሎጁ መስራች አብይ ይናገራል።
እንደ ማህበረሰብ አቀፍ ሎጁ መስራች ገለፃ፤ በአካባቢው ሰፊ የተፈጥሮ፣ የባህልና ያልተበረዘ የአኗኗር ዘይቤ ቢኖርም በሚፈለገው መንገድ የቱሪስት መዳረሻ ሳይሆን ለረጅም ጊዜ ቆይቷል። እርሱ ኢትዮጵያን ለጎብኚዎች በሚያሳየው “የቱሪስት ጋይድ” ስራ ላይ ተሰማርቶ ስለነበር ያንን አጋጣሚ በመጠቀም ከእምቅ ሃብቱ ነዋሪው ተጠቃሚ የሚሆንበትን ስልት መቀየስ ችሏል። በዚህም በርካታ ጎብኚዎች በስፍራው እየተገኙ ውብ ተፈጥሮውንና ማራኪ የኑሮ ዘይቤውን ከነዋሪው ጋር በቀጥታ ተገናኝተው እንዲያጣጥሙ እድሉን እንዲያገኙ ማድረግ ችሏል።
“ቱሪዝም አለ ህብረተሰብ ተሳትፎ ዘለቄታ የለውም” የሚለው አብይ አለም፤ በኢኮ ሎጁ በዋናነት ማጉላት የፈተፈለገው ያንን እንደሆነ ይናገራል። በተለይ ከ85 በመቶ በላይ አርሶ አደር የሆነውን የኢትዮጵያ ህዝብ ማሳተፍ ሳይቻል ስለ ቱሪዝም እድገት ማሰብ እንደማይቻል በማንሳትም ይህንን ለማሳካት በሎጁ ጎብኚዎች በሚገኙበት ወቅት የአካባቢው አርሶ አደር ባህሉ የሆነውን ቆሎውን፣ ዳቦውን፣ ባህላዊ መጠጡንና መሰል ከእለት ተእለት ኑሮው ጋር የሚገኘውን ነገር በማቅረብ እንግዶቹን እንዲቀበል ይደረጋል።
በዋናነት ቱሪስቱ የአካባቢው ማህበረሰብ ቱባ ባህል ከራሱ ከአርሶ አደሩ ጋር በቆየበት ጊዜ ሁሉ እንዲኖረው በማድረግ የሚተገበር ማህበረሰብ ተኮር ቱሪዝም እንደሆነም ይናገራል። በተለይ በዚህ ማህበረሰብ አቀፍ ኢኮ ሎጅ ውስጥ ጎብኚዎች የኢትዮጵያውያንን እንግዳ ተቀባይነት እንዲመለከቱ እድሉን ከመፍጠር ባሻገር የገቢ ምንጭ እንዲፈጠርላቸውም የተሻለ አማራጭ እንደሆነ ይናገራል።
የአካባቢው ማህበረሰብ በሎጁና በዙሪያው ባሉ መኖሪያ አካባቢዎች ከጭቃ፣ ከቀርከሃና ከሳር ክዳን የሚሰሩ የተዋቡ ቤቶችን ጎብኚዎች በቀጥታ በጋራ እንዲሰሩና ልምዱን እንዲካፈሉ በማድረግ ያመቻቻሉ። የድሮ ባህላዊ ቤት አሰራር እንዳይጠፋና የማህበረሰቡ ቱባ የአኗኗር ዘዬ እንዳይበረዝ የበኩላቸውን ድርሻ ይወጣሉ።
ከዚህ ባሻገር በእሳት ዳር ጨዋታ ከሩቅ አገር ለሚመጡ የውጪ አገር ጎብኚዎች የማህበረሰቡን የጨዋታ ወግ፣ ዘፈንና ባህላዊ ውዝዋዜ በማሳየት ከምንም ነገር በላይ ቱሪስቱ ተዝናንቶና በድጋሚ ለመምጣት እቅድ ይዞ እንዲሄድ ለማድረግ እንደሚጥሩም የሎጁ መስራች አቶ አብይ ይናገራል።
“ይህን የመሰለ ውብ የእንግዳ አቀባበል ቱሪስቶች ከተደረገላቸው በኋላ ቀጣይ የሚሄዱት በአካባቢው ነዋሪ ወደሆኑ አርሶ አደር ቤት ነው” የሚለው የኢኮ ሎጁ መስራቹ፣ በዚህም ቱሪስቶቹ አርሶ አደሩ የሚኖረውን የእለት ተእለት ኑሮ በጋራ እንዲካፈሉ ይደረጋሉ። እርሻ ማረስ፣ ማጨድ፣ ከብት ማሰማራት እንጨት መልቀምም ሆነ ማንኛውንም ነዋሪው በየእለቱ የሚያከውናቸውን ተግባራት በቀጥታ ተሳትፎ እንዲከውኑ ይደረጋል። ለቤት መስሪያ ጭቃ ከማቡካት ጀምሮ ለውቂያ የደረሰ እህል እስከ ማበራየት ከጎብኚዎቹ ይጠበቃል።
ፅንሰ ሃሳቡን ለማስረፅ
የሙሉ ኢኮ ሎጅ ማህበረሰቡንና ጎብኚዎችን በቀጥታ በማገናኘት ቱሪስቱ ማራኪ ቆይታ እንዲያደርግ ከማድረጉም ባሻገር አዲስና በዓይነቱ ለየት ያለ የቱሪዝም ፅንሰ ሃሳብ እንዲተዋወቅ እድሉን ያመቻቸ ነው። ከሁሉም በላይ ግን የማህበረሰቡ ባህል እንዳይበረዝ፣ ወግና ስርአቱን እንዳይለቅ በተለይ ደግሞ እንግዳ ተቀባይነቱን የሚታወቅበትን ማንነቱን እንዳይሸረሸር ትልቅ እገዛ የሚያደርግ ፅንሰ ሃሳብ ነው። ይህ ማህበረሰብ ተኮር የቱሪዝም እንቅስቃሴ ልክ በደቡብ ጎንደር አውራምባ ማህበረሰብ ማህበረሰቡ ጠንካራ የስራ ባህልና ንቁ ዜጎችን ፈጥሮ አካባቢውን ባህሉንና ኑሮውን በእውቀት እንዲመራ እድሉን እየፈጠረ የሚገኝ ነው።
በተለይ መንግስት አዳዲስ የቱሪዝም ዘርፎችን ለማስተዋወቅ፣ መዳረሻ ስፍራዎችን ለማልማት፣ ማህበረሰቡን ያካተተ ቱሪዝምና በዚያ ላይ የተመሰረተ ጠንካራ ኢኮኖሚ ለመገንባት የሚያደርገውን ጥረት አጋዥ እንደሆነ በቀላሉ መገንዘብ ይቻላል። ጎብኚዎች ወደ ኢትዮጵያ በሚመጡበት ወቅት ያለ እረፍት ከአንዱ ስፍራ ወደ ሌላኛው ባዝነውና ይህ ነው የሚባል ቁምነገር ሳይጨብጡ ቆይታቸውን ከሚጨርሱ መሰል ስልቶችን በመንደፍ አንድ አካባቢ ላይ በቂ የቆይታ ጊዜ እንዲኖራቸው ለማድረግ ሎጁ ትልቅ ምሳሌ መሆን የሚችል ነው። በተለይ መሰል የቱሪዝም ፅንሰ ሃሳቦችን በሁሉም የአገሪቱ አካባቢዎች ማስፋትና ከዚያም ሁሉም ባለድርሻ አካል ተጠቃሚ እንዲሆን ማስቻል አስፈላጊ እንደሆነ እናምናለን።
ዳግም ከበደ
አዲስ ዘመን ሰኔ 26/2014