‹‹ለረጅም ዓመታት በሰሜኑ የሀገራችን ክፍል ሲካሔድ የነበረው የርስ በርስ ጦርነት ያስከተለውን የኢትዮጵያውያን ህይወት መጥፋትና ከኑሮ መፈናቀል ለማስቀረት በልዩ ልዩ መልክ ጥረት ሲደረግ ቆይቷል። ሆኖም ችግሩ አልተቃለለም። ይልቁንም ወደ ባሰ ደረጃ እየተሸጋገረ በመሔድ ላይ ይገኛል። ስለዚህ ደም መፋሰስ እንዲቆምና ሰላምም እንዲሰፍን በልዩ ልዩ ወገኖች የሀገሪቱ ፕሬዚዳንት ከስልጣን መውረዳቸው እንደሚበጅ የታመነበት ስለሆነ ይህንኑ በማመዛዘን ፕሬዚዳት መንግሥቱ ኃይለማርያም ከስልጣቸው ወርደው ከኢትዮጵያ ውጪ ሔደዋል።››
ግንቦት 13 ቀን 1983 ዓ.ም ይህ ታሪካዊ ዜና በኢትዮጵያ ሬድዮ ተነበበ።ዜናው የኢትዮጵያን የፖለቲካ መስመር ሙሉ ለሙሉ የቀየረ ዜና ሲሆን ይህን ዜና ያነበበው ሰውንም በኢትዮጵያ የጋዜጠኝነት ታሪክ ውስጥ ስሙ እንዲመዘገብ ያደረገ ነው።የዜናው አንባቢ ዳርዮስ ሞዲ ነው።የዛሬው ጽሁፋችን በያዝነው ሳምንት ከሞተ 7ኛ ዓመቱ ላይ የሞላውን ይህን ታሪካዊ ጋዜጠኛ ያስታውሳል፡፡
ልጅነት
ዳርዮስ የሚለው ስም ምንጩ በመጽሀፍ ቅዱስ የታወቀው ዝነኛ የፋርስ ንጉስ ነው።አባቱ ከህንድ ተነስተው እንግሊዝ ኖረው ፤ ጀርመን ከርመው ፤ በመጨረሻ ኢትዮጵያ የመጡት እና ለ46 ዓመታት ኢትዮጵያ ውስጥ ከኖሩት ፎቶግራፈር ሞዲ ጉስታቭ እና ኢትዮጵያዊ ከሆኑት እናቱ ወይዘሮ አማረች መኩሪያ ታህሳስ 12 ቀን 1939 ዓ.ም ነው የተወለደው።ቦታውም በአዲስ አበባ አባቱ ፎቶ ቤት ከፍተው ከሚሰሩበት ራስ መኮንን ድልድይ አካባቢ ነው፡፡
ዳርዮስ የትምህርት ህይወቱን በእንግሊዝ ትምህርት ቤት ተጀመረ።ከዚያም የሁለተኛ ደረጃ ትምህርቱን በዳግማዊ ምኒልክ ትምህርት ቤት የተከታተለ ሲሆን፤ ከዚያም ወደ አዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ገብቷል።የዩኒቨርሲቲ ትምህርቱ ግን እንደታሰበው አልሄደም።የዩኒቨርሲቲ ጓደኛው የነበረው ጥላሁን ግዛው መገደል ዳርዮስ እና ሌሎች 11 ተማሪዎች በ1962 ዓ.ም ትምህርት እንዲያቋርጡ አደረጋቸው።ከዚያ በኋላ የዳርዮስ የህይወት መስመር ተቀየረ።ለሁለት ዓመታት ያህል ስራ አጥቶ ቤቱ ተቀመጠ።ተቀጥሮ ለመስራት አይመቸው እንጂ በግሉ የትርጉም ስራዎች እየሰራ የቀጠለው ዳርዮስ በ1964 ዓ.ም በብስራተ ወንጌል ሬድዮ ጣቢያ በጓደኛው ጥቆማ ተቀጠረ።ረጅሙ የጋዜጠኝነት ህይወትም ተጀመረ፡፡
ጋዜጠኝነት
የዳርዮስ የጋዜጠኝነት ህይወት የተዋበ ነው።ለሶስት አስርት ዓመታት የቆየው የጋዜጠኝነት ህይወት ዳርዮስ ድንቅ የዜና ሰው መሆኑ የተረጋገጠበት ነበር።ዳሪዮስ ሞዲ ለሬዲዮ የተፈጠረ ምሉዕ በኩልዔ የሆነ ጋዜጠኛ ነበረ። ተሰምቶ የማይጠገብ፣ እያነበበ የሚስረቀረቅ የሬዲዮ ሞገድን የሚገዛ ባለግርማ ድምፅ የታደለው ዳሪዮስ ሞዲ፣ ከዜና ባህሪው ተነስቶ አነባነቡን የሚከተል እንከን አልባ ዜና አንባቢ ነበር። መንግሥታት በተለዋወጡ ቁጥር የሚሉት ጎልቶ ይደመጥላቸው ዘንድ የሚዲያው ልሳንና የድምፅ ሞገድ ዳሪዮስ ነበር። እንደየጊዜው የአዳዲስ ምዕራፍ መሸጋገሪያ ድልድይ ድምፅ ሆኖም አገልግሏል።
እስከ ዛሬ ድረስ በኢትዮጵያ ሚዲያ ስራ ውስጥ እንደ ዳሪዮስ አይነት የትርጉም ጌታም አልተገኘም። በዳሪዮስ ዘንድ በይመስለኛል እና ይሆናል በሚል አቻ ትርጉም አይገኝም። የቀደምት አባቶቹን መዝገብ እየፈተሸ፣ ለዘመናዊው ዓለምም እንዲስማማ የራሱንም የትርጉም መንገድ እየፈለገ የሚማስን የቃላት ዲታ እና ታላቅ ሙያተኛ ነበር። የራሱን ትርጉም የሕዝብ ቋንቋ ማድረግ የቻለ፣ የቋንቋ ምሁራንም ደግመው ደጋግመው የሚመሰክሩለት የትርጉም መምህር ነበር። አማርኛ፣ አፋን ኦሮሞ፣ እንግሊዝኛ፣ ጀርመንኛ፣ ፈረንሳይኛ፣ ጣሊያንኛ የመተርጎም ብቃት ያመነጨውም ካልተቋረጠ የንባብ ብቃቱ ነው።
በብስራተ ወንጌል ሬዲዮ ጣቢያ የጀመረው የሬዲዮ ጋዜጠኝነት ሕይወቱ በኢትዮጵያ ሬዲዮ እና በኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት ለ30 ዓመታት ቢቀጥልም ይከፈለው የነበረው ደመወዝ የሰውየውን አስደናቂ ችሎታና የሙያ ልቀት የሚመጥን ቀርቶ ለወር አስቤዛ የማይበቃ ነበር። እንዲህም ሆኖ ህይወት ለዳሪዮስ ሬዲዮ ነው። ጡረታም ወጥቶ የናፈቀውን ሬዲዮ ለተወሰነም ጊዜ ቢሆን በሸገር እና በሬዲዮ ፋና ቀጥሎበት ቆይቷል።
ዳሪዮስ ሞዲ ወር ጠብቆ ከሚያገኘው ከሶስት አሃዝ ባልበለጠ ደመወዝ ራሱን እና ቤተሰቡን ለማስተዳደር ቢቸገርም ያን ወርቃማ ድምፁን ግን ለማስታወቂያ በማዋል ገንዘብ ሊሰራበት ግን ፈቃደኛ አልነበረም። ‹‹ዜና ላይ የሚሰማ ድምፅ እንዴት ሆኖ ሸቀጥ ይተዋወቅበታል›› ሲል ይሞግታል። ይህ በራሱ የሙያውን ሥነ-ምግባር መጣስ ነው ሲል ለሙያው መርህ እና ልዕልና አጥብቆ ይከራከራል።
ዳሪዮስ በርካታ አድናቂዎችን አፍርቷል።ዳርዮስ ከቀደሙ የሙያ አባቶቹ አሃዱ ሳቡሬ፡ አሰፋ ይርጉ ብዙ እንደተማረ በዚህም ለንደን ሳይሆን ሎንዶን፡ ዋሺንግተን ሳይሆን ዋሽንግቶን ብሎ በመዘገብም ይታወቅ ነበር። ጋዜጠኛው ከሙያ አባቶቹ ያገኘውን ለራሱ ሳያስቀር ለተተኪዎቹ በማስተማር ብንያም ከበደ፣ ነጋሽ መሃመድ፣ ብርቱካን ሐረገወይን፣ ሳምሶን ማሞ ዓይነቶቹን ሙያተኞች ምሳሌ ሆኗቸዋል።
ብዙዎች በርሱ ድምጽ ተማርከው የጋዜጠኝነቱን ዓለም ተቀላቅለዋል። ከነርሱም አንዱ የሆነው ዓለምነህ ዋሴ ስለ ዳሪዮስ ሞዲ አስተያየቱን ሲሰጥ እንዲህ ብሎ ነበር።‹‹ ዳሪዮስ ሞዲ ድምጹ ቀጭን ነው።ግን ሚስጢራዊ ነው።ማንኛውንም ሞገድ አሳብሮ የሚችል ነው። ዳሪዮስ ልክ እንደ ድምጹ ሚስጢራዊ ነው።ድብቅ ነው። ማህበራዊ ህይወት ውስጥም እንደሆነ ዳሪዮስ የለበትም። ሽሽግ ነው››፡፡
ዳሪዮስ አዋቂ ነው። በጣም ብዙ ነገሮችን ያውቃል። የራሱ ጨዋታና ቀልዶች አሉት። በተረፈ በአለባበሱም ሆነ በማህበራዊ ህይወቱ ይሄን ያህል የሚታወስ አይደለም።ዳሪዮስን የምታስታውሰው ለምሳሌ ዜና ተረኛ ከሆነ ከአንዲት አሮጌ ታይፕራይተር ፊት ለፊት ተቀምጦ እዛ ፊልተሩ ጋር የደረሰች ሲጋራ ከንፈሩ ላይ ለጉሞ የውጪ ዜናዎችን ሲተረጉምና ሲተይብ ነው።ዳሪዮስ ከፍተኛ የትርጉም ችሎታ አለው።ቃላትን መፈብረክም ይችልበታል።ዛሬም ድረስ በሬድዮ የምንሰማቸው ሙያዊ ቃላት በርካቶቹ የዳሪዮስ ፍብረካ ውጤቶች ናቸው፡፡(ኢትኦጵ መጽሔት፡ ቅጽ 1- ቁጥር 12፤ ግንቦት 1992 ዓም)
የአሜሪካ ድምጽ ራዲዮ ባልደረባ የሆነው አንጋፋው ጋዜጠኛ አዲሱ ሰለሞን ስለ ዳርዮስ ሲናገር ዳርዮስን ችኮ ነው ይለዋል።ችኮ የሚለውም ዳርዮስ ፈጽሞ መልመጥመጥ የማያውቅ ጽኑ የአቋም ሰው በመሆኑ ነው።በዚህም የተነሳ ብዙ ችግሮች አጋጥመውታል።በብስራተ ወንጌል ሬድዮ የጀመረው ስራ በኢትዮጵያ ሬድዮ ቀጥሎ ከዚያም ኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት የተጠናቀቀ ሲሆን ጡረታ ከወጣ በኋላም በሌሎች ጣቢያዎች ለተወሰኑ ጊዜያት ሰርቷል፡፡
ታሪከኛው ዳርዮስ
የዳርዮስ የስራ ህይወት አስገራሚ ታሪኮች አሉት፡፡
ጥቂቱን እንመልከት፤-
HUMAN IMMUNO DEFICIENCY VIRUS (HIV) የሚለውን ቃል ሕዝብ ሊረዳው በሚችለው ቃል በራሱ መንገድ ተርጉሞ ‹‹ቅስመ ተፈጥሮ መከላከያ ሰባሪ በሽታ›› ብሎ ለመጀመሪያ ጊዜ ሕዝብን ስለ በሽታው ያስተማረውም ይሄው ሙያተኛ ነበር፣ ለዚህ ውለታው ግን ሽልማት ቀርቶ ምሥጋና አላገኘም።ይብሱን ‹‹ያልተገቡ ቃላትን በመጠቀም›› በሚል ከደመወዙ ሠማንያ ብር ተቀጥቷል። በ1978 ዓ.ም ደግሞ አንድ ዜና በሚያነብበት ወቅት የፕሬዚዳንት መንግስቱን ማእረግ አዛብቶ በመጥራት ለሁለት ቀን ታስሮ የቆየ ሲሆን በኋላ ላይ ጠበቃ አቁሞ ተከራክሮ ወደ ስራው ተመልሷል፡፡
ዳሪዮስ ሞዲ ላመነበት ነገር እስከ መጨረሻው ድረስ በአቋሙ ፀንቶ የመቆየት ብቃት ያለው ጋዜጠኛም ነበር። ይህንን ፀባዩን የሚያሳይልን ደግሞ በአንድ ወቅት የተከሰተው ሁኔታ ነው። ጉዳዩ፣ አንድ ሰው የማይወዳቸው ምክትል ሚኒስትር ከስራ ቦታቸው በእድገት ይቀየሩና ወደ ሌላ መስሪያ ቤት ይዘዋወራሉ። ታዲያ በዚህ ወቅት ሰራተኛው መዋጮ አድርጎ የአሸኛኘት መርሃ ግብር ያደርጋል። ዳሪዮስ ግን አስገራሚ ነገር ፈፀመ። ለምክትል ሚኒስትሩ መሸኛ ከሰራተኛው ገንዘብ ሲዋጣ አምስት ሳንቲም ከደመወዜ ላይ የሚቆርጥ ብሎ ሞልቷል፡፡
ዳርዮስ ለልጆቹ አስገራሚ ስም በማውጣትም ይታወቃል።ሰባት ልጆች ያሉት አንጋፋው ጋዜጠኛ ለልጆቹ ካወጣቸው ስሞች መካከል ቼጉቬራ ፣አምጸሽ ተነሺ ፣ ትግል ነው ተነሳ ፣ዳርዮስ (ዳግማዊ ዳርዮስ) ፣ማንዴላ (ዮሴፍ) ተጠቃሽ ናቸው፡፡
የትዳር ህይወት
ዳርዮስ ከእድሜ ዘመን ባለቤቱ ወይዘሮ መሰረት ሀይሌ ጋር ጋብቻ የመሰረተው ገና ስራ እንደያዘ ነው።ገና ስራ በያዘበት ወር 1964 ዓ.ም የመጀመሪያ ደመወዙን እንዳገኘ ውብ ከነበረችው ባለቤቱ ከመሳይ ጋር ጋብቻ ፈፀመ። ይህ እስከ ህይወታቸው ፍጻሜ የዘለቀ ትዳር ሰባት ልጆች እና በርካታ የልጅ ልጆችን አፍርቷል።በዚህ ለ43 ዓመት በቆየ ትዳር ውስጥ ከሚጠቀሱ ነገሮች አንዱ ዳርዮስ በ43 ዓመት ትዳር ውስጥ አንድም ቀን ቢሆን ከቤቱ ውጪ አድሮ አለማወቁ ነው።
ነገር ግን ቤትም ቢሆን ዳርዮስ ብዙ ጊዜውን የሚያሳልፈው በማንበብ ነው።ከንባብ ቀና የሚለው ለጥቂት ጊዜያት እንደሆነ የሚያውቁት ይናገራሉ።ማህበራዊ ኑሮ ላይ እምብዛም ነው።በአንድ ወቅት ለኢትኦጵ ጋዜጣ በሰጠው አስተያየት ‹‹እኔ ፎርማል ነገር አልወድም።ለምሳሌ ሰርግ ተጠርቼ አልሄድም።ደስ ካለኝ ደግሞ ባትጠራኝ እንኳ በሰርግህ ላይ ልገኝ እችላለሁ›› (ኢትኦጵ መጽሔት፡ ቅጽ 3- ቁጥር 36፤ ግንቦት 1994ዓ.ም)
ከዚያ ባለፈ ዳርዮስ ለውሻ የተለየ ፍቅር ያለው ሲሆን፤ ኮክ ለሚባለው ፍሬ ያለው ጥላቻ ደግሞ ብዙዎችን የሚያስገርም እና የሚያስደነግጥ ነው።ሀኪም ቤት መሄድ ብዙም የማይመቸው እና ለራሱ መድኃኒትን ከመጻህፍት ውስጥ አገላብጦ የሚፈልገው ዳርዮስ የጡረታ ዘመኑ የተመቸ አልነበረም።የልብ ህመም ያሰቃየው ነበር።ከዚያም የባለቤቱ ሞት ክፉኛ ጎድቶት ነበር።ባለቤቱ ካረፈች ከ4 ወራት በኋላ ሰኔ 13 ቀን 2007 ዓ.ም ታምሞ ወደ ሆስፒታል የገባው ዳርዮስ በማግስቱ እቺን ዓለም ዳግም ሳያይ እስከመጨረሻው አሸለበ፡፡
አቤል ገ/ኪዳን
አዲስ ዘመን ሰኔ 19/2014