ብስራት በተለያየ መልከኛ እርሳሶች ስዕል እየሳለ አባቱ ፊት ይንደፋደፋል። አጠገቡ አብሮት የሚጫወተው የፈረንጅ ውሻ ዝም ብለህ ተቀመጥ የተባለ ይመስል የብስራትን ድርጊት በተመስጦ ያስተውላል።
የብስራት አባት ጋሽ ተፈራ ርዕሱ የተሸፈነ መጽሐፍ እያነበቡ ከብስራትና ከውሻው ራቅ ብለው ተቀምጠዋል። ሁሉም በራሳቸው ተመስጦ ውስጥ ወድቀዋል፤ ብስራት በሚሞነጫጭረው ስዕል ላይ፣ ቡቺ ምኑም በማይታወቅ ደመነፍሳዊ ተመስጦ ውስጥ፣ ጋሽ ተፈራ በሚያነቡት መሳጭ ታሪክ ውስጥ ራሳቸውን ጥለዋል።
ታዳጊው ብስራት ሳያስበው ወደ አባቱ ቀና አለ። የጀመረውን ሳይጨርስ ሀሳቡን ለሌላ ነገር የማይገብር የሕፃን አዋቂ ዓይነት ነበር፤ ዛሬ ግን በአባቱ ሀሳቡ ተሰረቀ። አባቱን እያስተዋለ ብዙ ቆየ። ማንንም እንደዛ አይቶ፣ በማንም እንደዛ ተመስጦ አያውቅም።
የሁልጊዜ የነፍሱ መመሰጫ በቴሌቪዥን የሚያያቸው የአሻንጉሊት ፊልሞች ነበሩ። ዛሬ ግን በአባቱ ተመሰጠ፤ በልጅነት ነፍሱ ውስጥ የሚያስገርም ትንሽዬ ግርምት ተጸነሰ። አባቱ አሁን የሚያነቡትን መጽሐፍ ይዘው ለዘላለም አይቷቸዋል። በልጅነት አእምሮው ቆጥሮ ለማይደርስበት ጊዜ ሳሎንና፣ መኝታ ቤት፣ በረንዳና፣ ሰገነት ላይ አይቷቸዋል።
የማያልቅ መጽሐፍ ሆኖ ነው ወይስ የማያልቅ ታሪክ ይዞ? የማይገባ ፍልስፍና ተጽፎበት ወይስ ከራስ የሚያጣላ አፍዝ አደንግዝ አርፎበት? አንዱንም አያውቀውም ብቻ ነጋ ጠባ ከእንቅልፉ ሲነቃና መሽቶ ወደ ማደሪያው ሲያዘግም እንዲሁም ደግሞ በሰንበት ከአባቱ ጋር ሲሆን አባቱን ከዚህ መጽሐፍ ጋር ነው የሚያገኛቸው። ሲያድግ ለአባቱ ከሚያቀርብላቸው ጥያቄዎች ውስጥ አንዱ ለምን ይሄን መጽሐፍ ደጋግመው ያነባሉ የሚል ነው። ያኔ ከአባቱ አፍ የሚሰማው መልስ ሁሌም ሲያስደንቀው የሚኖር ይመስለዋል። ግን የዚህን መጽሐፍና የአባቱን ቁርኝት ለማወቅ እስኪያድግ መጠበቅ አላስችል ብሎት አሁኑኑ መጠየቅ ፈለገ። የሚሞነጫጭረውን ስዕል ወደ ጎን ብሎ ወደአባቱ ተንደረደረ።
‹አባ! አለ..አባቱ ፊት ሳይዛነፍ ቆሞ።
‹አባቱ ከሚያነቡት መጽሐፍ ላይ ተገተው ቀና አሉ። ሕፃን ሆኖ አልተረዳውም እንጂ ፊታቸው አጠገባቸው የቆመውን ሰው ሲቆጣ ነበር። ማንም ከዚያ መጽሐፍ ላይ፣ ከዛ ታሪክ ላይ፣ ከዛ ተመስጦ ላይ እንዲያነቃቸው አይሹም። በሕይወታቸው ምህረት የሌላቸው ለሁለት ነገር ነው ከዛ መጽሐፍ ላይ ላነቃቸውና አገራቸውን ኢትዮጵያን በክፉ ላየባቸው።
‹አባ ይሄ ምንድነው? አለ ብስራት ወደ መጽሐፉ በእጁ እየጠቆመ።
ምን እንደሚሉት ግራ ገባቸው። ሊያወርሱት ከሚፈልጉት ታላቅ እውነት ውስጥ አንዱና ዋነኛው ይሄ መጽሐፍና የዚህ መጽሐፍ ታሪክ ነው። አሁን ቢነግሩት የማይገባው ብዙ ነገር አለ..ሲያድግ ሁሉንም ሊነግሩት አስበው ነበር ግን ድንገት ጠየቃቸው። እስከሚያድግ ከሚጠብቁ እየነገሩት ቢያድግ ጥሩ እንደሚሆን በማሰብ ሊነግሩት ከወንበራቸው በመመቻቸት ጉሮሯቸውን አጸዳዱ።
‹የምነግርህን ነገር ለማመንና ለመቀበል፣ በዛ እውነት ውስጥ በታማኝነት ለመኖር ዝግጁ ነህ? ሲሉ ጠየቁት።
ራሱን በአዎንታ ነቀነቀ።
‹እንግዲያውስ ይሄ መጽሐፍ አንተና ታሪክህ ነው። በየቀኑ የምታነበው፣ በየቀኑ የምታስበው፣ በየቀኑ የምትደነቅበት፣ በየቀኑ የምትመሰጥበት፣ በየቀኑ የምትኮራበት አንተና ታሪክህ ነው። ዘመንህን ሙሉ የምታነበው፣ ዕድሜህን ሙሉ የምትገልጠው፣ እስካለህ ድረስ የምታመሳጥረው አንተና ታሪክህ ነው። አሁን ላይ የምነግርህ ነገር ብዙም ላይገባህ ይችላል፤ ግን እየነገርኩህ እንድታድግ፣ እየነገርኩህ እንዳረጅ እፈልጋለሁ።
አልገባውም። በአባቱ ንግግር ትንሽ ነፍሱ ተፈተነች። አባቱ ዛሬ ገና አባቱ አልመስልህ አሉት። እንደዛሬ በማይገባው ቋንቋ የማይገባውን ነገር፣ በማይገባው ፊት ነግረውት አያውቁም።
ግራ እንደገባው ሲያውቁ ‹‹ልጄ አሁን አይገባህም፤ ግን እንዲህ እየተደናገርክ በልጅነትህ ውስጥ ታሪክህን እንድታበቅል እሻለሁ። ብዙዎች አድገው ኢትዮጵያ ማናት? ብለው ግራ ሲጋቡ አንተ ለራስህም ሆነ ለሌሎች ጥያቄ የሚሆን ብዙ መልስ ታገኛለህ። መደናገርህን አትጥላው። ከዚህ ሁሉ ግርታ በኋላ የምትደርስበት እውነት ስሩ የጠለቀ፣ ግንዱ የፈረጠመ፣ ቅርንጫፉ የትየሌለ የሆነ ነው። ከዛም አንተ በሌሎች ዛፍነት ውስጥ ዋርካ ይወጣሀል፤ ሌሎች አንተን ለማጥላት አቅም ሲያጡ ታያለህ።
ይህ መጽሐፍ ይሄን ሁሉ የሚሰጥህን የኢትዮጵያውያንን ታሪክ የያዘ ነው። በሳይንሱም፣ በሃይማኖቱም ብትሄድ ፊተኝነት የእኛ ነው። ዓለምን የፈጠሩ እጆች የእኛ ናቸው። አድዋ በተባበረ ክንድ ታሪክህን ሲነግርህ በእዚህ መጽሐፍ ውስጥ ታገኘዋለህ። ለዛ ነው ዘመኔን ሙሉ ሳነበው የምታየኝ» ሲሉ ወደ ጉያቸው ስበው አቀፉት።
‹አባ ሳድግ ምንድነው የምሆነው?›
‹ስታድግ መሆን የምትፈልገውን አንተ ነህ መወሰን ያለብህ። እኔ በምትሄደው መንገድ አንተን መምራት ነው ድርሻዬ።
‹እኔ ግን..እንዳንተ መሆን ነው የምፈልገው…
‹እንደ እኔ ምን?
‹እንዳንተ ወንድ፣ እንዳንተ አባት፣ እንዳንተ ሰው፣ እንዳተ..
‹እንደ እኔ ከመሆንህ በፊት መጀመሪያ ራስን መሆን ይቀድማል። ምናልባት ራስህን ስትሆን ከኔ የተሻለውን አንተን ልታገኘው ተችላለህ። እንዳባት የምመክርህ መጀመሪያ ራስህን ከዛም እኔን እንድትሆን ነው›። ሲል ጉንጩን ሳመው። አጥብቆ ሲያየው ቆይቶ ‹ምትፈልገውን ለመሆን ጠንካራ ልብና አእምሮ ያስፈልግሃል።
‹ጠንካራ ልብና አእምሮ እንዴት ነው የሚገኘው? ልጁ የአባቱን ጎስቋላ አይኖች ሽቅብ እያስተዋለ ጠየቀ።
‹ጠንካራ ልብና አእምሮ የሚገኘው በጠንካራ ተስፋና ትጋት ነው። እጆችህን መስራት ስታስለምዳቸው፣ አእምሮህን ማሰብ ስታስተምረው፣ ልብህን ማፍቀር ስታለማምዳት፣ ነፍስህን ከኩነኔ ስታርቃት የኔ ጠንካራ ልብና አእምሮ ትሸምታለህ። ሰው ጠንክሮ ከሠራ መሆን የሚፈልገውን ሁሉ ይሆናል። የመከኑ ህልሞች፣ የራቁ ተስፋዎች በጠንካራ ትጋት ስላልፈለግናቸው የተሰወሩ ናቸው። አንተም ተስፋህን እንዳታርቅ፣ ህልምህን እንዳታዘገይ በትጋትና በትህትና የተገነባ ሰውነት ያስፈልግሀል›። ሳም አደረገው።
‹እኔ ግን እንዳንተ ነው መሆን የምፈልገው..› አለ ብስራት ለማኩረፍ በቃጣው ፊት።
‹እንደ እኔ መሆን ከፈለክም ከላይ በነገርኩህ የጥበብ መንገድ ላይ መራመድ ግድ ይልሀል። ወደ ከፍታ የሚያደርስህን የስብዕና ካባ መደረብ ይኖርብሀል። ካለ ዝቅታ የሚመጣ ከፍታ የለም፣ ካለ ጉስቁልና እፎይታ የማይታሰብ ነው፤ ወደ ፊት መሄድ ስታስብ በሕይወትህ ሁሌም ይሄን አስታውስ። ከሁሉ በላይ ደግሞ ሰው ሁን።
‹አሁንም እኮ ሰው ነኝ..
‹አዎ አሁንም ሰው ነህ ግን በአእምሮና ልብ ስትልቅ በአንተ ውስጥ የሚፈጠር ሌላ ሰው አለ።
ብስራት ግራ ገብቶት ዝም አለ።
‹ይሄን እውነት የምትደርስበት ነፍስህን ፍትህ፣ ልብህን ፍቅር፣ አእምሮህን ጥበብ ስታስተምራቸው ነው። ይሄን እውነት የምትረዳው በሰዎች ህመም መሰቃየት ስትችልና ራስህን ለሌሎች ስታብቃቃ ነው። ይሄን እውነት የምትረዳው ራስህን ስትሆን፣ ታሪክንህ ስታጠና፣ በዙሪያህ ያሉትን ስታፈቅርና የፈጠረህን ስትፈራ ነው› አሉት።
በትረ ሙሴ (መልከ ኢትዮጵ)
አዲስ ዘመን ግንቦት 5/2014