እስራኤል እንደ አገር ከቆመች ወዲህ ከአረብ አገሮች ጋር የተለያዩ ጦርነቶችን ተፋልማለች። በተለይም እ.ኤ.አ በ1967 የተካሄደው የስድስቱ ቀን ጦርነት ተብሎ የሚታወቀው ውጊያ በታላቅነቱ ይነሳል። በዚህ ጦርነት እስራኤል የጎላንን ኮረብታ ከሶሪያ ከመረከብ አንስቶ ጋዛ ሰርጥን፣ ዌስት ባንክና የግብፅን የሲናይ ልሳነ ምድር በእጇ ማስገባት ችላለች። ይህን መሪር ፅዋ ለመጠጣት የተገደዱትና እ.ኤ.አ በ1970 ፕሬዚዳንት ጋማል አብዱል ናስርን ተክተው ግብፅን መምራት የጀመሩት አንዋር ሳዳትም፤ የሲናን ምድርን ለማስመለስ እልህ አስጨራሽ ፍልሚያን ገጥመዋል።
ምንም እንኳን አለን የሚሉትን ኃይል ተጠቅመው ቢፋለሙም ቦታዋን ከእስራኤል መንጋጋ በማስለቀቅ ፍላጎታቸውን ማሟላት አልተቻላቸውም። እናም ጦርነት የፈለጉትን ሊሰጣቸው ባይችልም ለሰላም ስምምነት እጅን መዘርጋት ምርጫቸው በማድረግ ወደ እስራኤል አቅንተዋል፤ ስለሰላምም እጃቸውን ዘርግተዋል። በኋላም እ.ኤ.አ በ1979 በአሜሪካ ፕሬዚዳንት ጂሚ ካርተር አማካኝነት በካምፕ ዴቪድ በተከናወነ ስነ-ስርዓት ከዘመኑ የእስራኤል ጠቅላይ ሚኒስትር ሜኒያሂም ቤጊን ጋር የሰላም ስምምነት ተፈራርመዋል።
በስምምነቱ መሰረት እስራኤል በስድስቱ ቀን ጦርነት ወቅት የያዘቸውን የሲናይ ልሳነ ምድር ለግብጽ መመለስ ስትስማማ፤ ግብጽ ደግሞ ለእስራኤል በአጋርነት እውቅና የሰጠች የመጀመሪያ አረብ ሀገር ሆናለች:: ይህ የእስራኤልና የግብፅ ስምምነት በተለይም የፕሬዚዳንት ሳዳት ተግባር ታዲያ ሁለት አይነት ምልክታን ማስተናገድ ግድ ብሎታል። በርካቶች የሳዳትን ተግባር አቆለጳጵሰው ስማቸውን ጠርተው ሲያወድሱ፤ የአረብ አገራቱ በአንፃሩ ሰውዬውን በከሃዲነት ፈርጀዋቸዋል።
ግብጽ የራሷን መሬት ማስመለሷና ለእስራኤል እውቅና መስጠቷን የተቃወሙ እስላማዊ ጽንፈኞች ከሁለት ዓመት በኃላም የሳዳትን ህይወት ነጥቀዋቸዋል። ሰውዬው ስለሰላም የተጓዙት መንገድ የኋላ ኋላ ውድ ህይወታቸውን ቢያስከፍላቸውም አገራቸው በአንፃሩ ላለፉት አራት አስርት ዓመታት በልሳነ ምድሩ ሉዓላዊነቷን አፅንታ ዘልቃለች።
እስራኤልም ብትሆን ከስምምነቱ የምትፈልገውን አግኝታለች። በሰጥቶ መቀበል መርህ በተደመደመው ስምምነት መሰረትም አገራቱ ያለፉትን አራት አስርት ዓመታት ተከባብረውና ተፈራርተው ዘልቀዋል። ወቅታዊ የቀጣና ተፅዕኖ ፈጣሪነታቸውም ከሁሉም ገዝፎ መታየት ችሏል። ድንበር ተጋሪ ጎረቤታሞቹ አገራት ምንም እንኳን በየፊናቸው በከፍታ ማማ ላይ ቢቀመጡም፤ የእርስ በእርስ ሁለንተናዊ ግንኙነት ሲፈተሽ ግን ከአንዳንድ ጉዳዮች በስተቀር ከጋራ ይልቅ ተናጥልን ምርጫው ያደረገ ሆኖ ይስተዋላል።
በቴል አቪቭ ዩኒቨርሲቲ የዲፕሎማሲ ፕሮግራም መምህር የሆኑት ዶክተር ዮአቭ ጄ ቴኒንባውም የሁለቱ አገራት ያለፈ አርባ ዓመት ግንኙነት በይፋዊ ወዳጅነት መርህ ላይ ባይንተራስም፤ እርስ በእርስ ጀርባ ለመሰጣጣት ያልደፈረ ስለመሆኑ ይስማሙበታል። በተለይ ለቀጣናው ሰላም ሽብርተኞችን በመከላከል ረገድም ተባብረው በጋራ መስራታቸው ውጤታማ እንዳደረጋቸው የሚጠቁሙት ፀሐፊው፤ ይሁንና ከቅርብ ዓመታት ወዲህ ፅንፈኛ አሸባሪ አንጃዎች በሲና በረሃ እንዳሻቸው ለመፈንጨት ሲውተረተሩ እንደሚስተዋል ይገልፃሉ።
እነዚህ ፅንፈኛና አክራሪ ሽብርተኞች ምንም እንኳን በአብዛኛው የጥቃት ኢላማቸውን ወደ ግብፅ ያነጣጠሩ ቢሆንም፤ እስራኤልም በጥቁር መነፅራቸው ኢላማ ውስጥ ናት የሚሉት ፀሐፊው፤ ይህ በራሱ ከቅርብ ዓመታት ወዲህ በአገራቱ መካከል ያለውን የጋራ ደህንነት ጥበቃ ይበልጥ መጠናከር እንዳለበት የሚያስጠነቅቅ ቀይ መብራት ሆኖ መቆየቱን ያነሳሉ።
በእርግጥ በተለይ በግብፁ ፕሬዚዳንት በአብዱል ፈታህ አልሲሲ ዘመነ መንግሥት የእስራኤልና ግብፅ ግንኙነት በተለይ በሲና በረሃ የሚስተዋለው የሁለቱ አገራት የፀጥታ ጥበቃ ጥምረት የተሻለ ደረጃ ላይ መሆኑ ይታያል። ይህም በመሪዎች ደረጃ ሳይቀር ማረጋገጫ የተሰጠበት ነው። በዳግም ምርጫ በሰፊ ድምፅ ልዩነት ሲያሽነፉ በሲናይ በርሃ የሚንቀሳቀሱ አንጃዎችን በማንኮታኮት ለዓመታት የዘለቀ የፀጥታ ስጋት ለማስወገድ ቃላቸውን የሰጡት ፕሬዚዳንት አልሲሲ፤ ከወራት በፊት የአሜሪካው የዜና አውታር ሲ.ቢ.ኤስ ቴሌቪዝን ጋር ባደረጉት ቆይታ፤ ከእስራኤል ጋር የመሰረቱት አጋርነት ጥብቅና ጥልቅ ስለመሆኑ ተጠይቀውም «በትክክል ሲሉ» መልሰዋል።
በእርግጥም ምንም እንኳን አሁን ላይ ሁለቱ አገራት አንፃራዊ በሚባል ሰላምና ዶሞክራሲ ልዕልና ላይ ቢቀመጡም፤ በመካከለኛው ምስራቅ ቀጣናው የሚስተዋለው ነውጥ ግን ሰላማቸውን ሙሉ በሙሉ እንዳያረጋግጡና የዛፍ ላይ እንቅልፍ እንዲተኙ አስገድዷቸዋል። በአሁን ወቅት በሲና በርሃ ከሚንቀሳቀሱት አንጃዎች በተጓዳኝ የሃማስ የሽብር ቡድን ለሁለቱም አገራት ከባድ ራስ ምታት ነው። በተለይ እስራኤልና ሃማስ ሁለቱ በጋዛ ሰርጥ የሚያደረጉትን ፍልሚያ እጅጉን ከባድ ነው።
እስራኤል ቡድኑ ድንበሬን ጥሶ በመግባት በታጣቂዎቹ አማካኝነት ጥቃት እየፈጸመ ነው›› በማለት ትኮንናለች። አለፍ ሲልም ከባድ የተባለ የአፀፋ እርምጃን ትወስዳለች። ይህን በእስራኤልና በሃማስ መካከል የተፈጠረ ውጥረት ለማርገብና ሁለቱን ወገኖች ወደ ጠረጴዛ ድርድር ለማምጣት ታዲያ ከግብፅ በላይ የሚታተር የለም። ሁለቱ አካላትም በግብፅ መንግሥትና በተባበሩት መንግሥታት ድርጅት አማካይነት ከአንድም ሁለት ሶስት ጊዜ የተኩስ አቁም ስምምነት ላይ ደርሰዋል። ምንም እንኳ ስምምነቶቹ ዘለቄታ ባይኖራቸውም ካይሮ ግን ሁለቱን ወገኖች በማደራደሩ ተግባር ደከመኝ ብላ አታውቅም። አገራቱ ከድንበር ዘለል የፀጥታና ድህንነት ጥበቃ ጥምረት በተጓዳኝ ከቅርብ ዓመታት ወዲህ በመሰል የእርቅ አውራጅነት ሚና መተማመናቸውን የተመለከቱ በርካታ የፖለቲካ ተንታኝና መገናኛ ብዙሃንም ከአድናቆት ባለፈ አፋቸውን ሞልተው ለመተቸት ቃላት እንዲያጥራቸው አስገድዷል።
አገራቱ በዚህ ዓመት ይባስ በሎ ከፀጥታና ድህንነት ባለፈ በኢኮኖሚም ዘርፍ ለመተባባር ፍላጎት ማሳየታቸውንና ይህንም በተግባር ማስመስከራቸው የሚታወስ ሲሆን፤ ድንበር አቋራጭ የተፈጥሮ ነዳጅ ማስተላለፊያ መስመር ዝርጋታም የትስስራቸው መረብ ሆኗል። በተለይ ግብፅም በካይሮ በተካሄደው የተፈጥሮ ጋዝ ጉባኤ ላይ የእስራኤሉን የኃይል ሚኒስትር መጋበዟ ይህም እ.ኤ.አ 2011 ጀምሮ የመጀመሪያው መሆኑም ግንኙነቱን በኢኮኖሚም ለማስተሳሰር ይበልጥ ተጠቃሚ የመሆን ፍላጎት እንዳላት ምስክር እንደሚሰጥ ባለሙያዎች ሲናገሩ ተደምጠዋል።
ይህ ሁሉ የአገራቱ ለእርስ በእርስ ትስስር መጎልበት ታዲያ አሁን ላይ በእስራኤልም በኩል ማረጋገጫን ማግኘት ችሏል። ከቀናት በፊት የእስራኤል ፕሬዚዳንት ሩውቨን ሪቭለን በእየሩሳሌሙ በሃብሪው ዩኒቨርሲቲ የሄሪ ትሩማን የጥናት ኢንስቲትውት ባዘጋጀው መድረክ ላይ ይህንኑ መስክረዋል። በአገራቱ የተደረሰው ሰላም በመካከላቸው ያለውን ጦርነት ብቻም አለማስቀረቱን የጠቆሙት ፕሬዚዳንቱ፤ ከሲውዝ ካናል ወደ ስራ መግባት አንስቶ በርካታ ማህበራዊ፣ ኢኮኖሚያዊና ፖለቲካዊ ለውጦች እንዲመጡ ምክንያት መሆኑንን አስረድተዋል። «በአገራቱ መካከል የተደረሰው የሰላም ስምምነት ከዓመት ዓመት ራሱን እያረጋገጠ መጥቷል» ያሉት ፐሬዚዳንቱ፤ ይህም ውስብስብ የደህንነትና የፅጥታ ችግሮች በተለይ በእስራኤልና በሃማስ የጋዛ ፍጥጫ መንፀባረቁንም ጠቁመዋል።
ፕሬዚዳንቱ፣ ምንም እንኳን በአገራቱ መካከል የተፈረመው የሰላም ስምምነት በጋራ ትብብር ስራዎች ጎልበቶ ቢታይም፤ አሁንም ቢሆን አገራቱ ለእርስ በእርስ የህዝቦች ግንኙነት ድንበራቸውን ክፍት እንዲያድረጉ የማድረግ አቅም እንዳልኖረው ሳይጠቁሙ አላለፉም። ይህን በመሪዎች ሳይቀር የተረጋገጠ የትብብር ትስስር መጎልበት የተመለከቱ ታዲያ መጪው ጊዜ በሁለቱ አገራት መካከል መልካም የሚሰማበት ስለመሆኑ እንዲገምቱ አስገድዷቸዋል።
አንዳንዶች በአንፃሩ፤ የለም ምንም እንኳን በሰላምና ድህንነት ረገድ ሁለቱ አገራት ውጤታማ የሚባል ጥምረት ስለመመስረታቸው ባይካድም አሁንም ቢሆን «በህዝብ ለህዝብ ግንኙነት ረገድ የእየሩሳሌምና ካይሮ ግንኙነት ድካማ ነው» ሲሉ ተደምጠዋል። በእየሩሳሌሙ በሃብሪው ዩኒቨርሲቲ የሄሪ ትሩማን የጥናት ኢንስቲትውት ታዲያ ይህን የሁለቱን አገራት ወቅታዊ ወዳጅነት ትስስር በሚመለከት አንድ ጥናት በማጥናት መረጃውን ይፋ አድርጓል።
ለጥናቱ ግኝት ይረዳው ዘንድ ለ400 እስራኤላውያን እንዲሁም 100 አረብ እስራኤላውያን ባቀረበው ጥያቄም ከአስተያያት ሰጪዎቹ መካከልም 82 በመቶ እስራኤላውያን የሁለቱ አገራት ሰላም መሆን ከምንም በላይ ዋጋ እንዳለው መናገራቸውን አመላክቷል። በሁለቱ አገራት የእርስ በእርስ ወዳጅነት በሚመለከትም፤ 66 በመቶው አገራቱ በቀዝቃዛው ሰላም ላይ መሆናቸውን ሲናገሩ፤ 64 በመቶው በአንፃሩ ግብፅ የእስራኤል ወዳጅም ጠላትም አይደለችም የሚል አቋም መያዛቸውን አመላክቷል።
የአገራቱ ግንኙነት ቀጣይነት በሚመለከትም፤ 54 በመቶ እስራኤላውያን በሁለቱ አገራት መካካል ያለው ግንኝነት በቀጣይ ይሻሻል የሚል እምነት እንደሌላቸው የታወቀ ሲሆን፤ 12 በመቶው በአንፃሩ ሁለንተናዊ ግንኙነቱ ይበልጥ እንደሚጠናከር እምነት ይዘዋል። 15 በመቶው ግንኙነቱ እያደር እንደሚቀዘቅዝ ሲገልፁ፤ 5 በመቶው ደግሞ የአገራቱ ስምምነት ፈራሽ ስለመሆኑ ተንብየዋል።
በህዝብ ለህዝብ ግንኙነት ረገድ የእየሩሳሌምና ካይሮ ግንኙነት በሚመለከትም በሰራው ጥናትም፤16 በመቶው ግብፅን መጎብኘታቸው ሲታወቅ፤ 22 በመቶው ወደ ግብፅ የመሄድ ፍላጎት እንዳላቸው ተመላክቷል። ቁጥራቸው ከፍ ያሉትና 64 በመቶውም ትናንትም አለመሄዳቸውን ነገም የመሄድ ፍላጎት እንደሌላቸው ጥናቱ አመላክቷል።
አዲስ ዘመን መጋቢት 10/2011
ታምራት ተስፋዬ