በገዳ ስርዓት ውስጥ አንዱና ትልቅ ግምት የሚሰጠው ነው። የኦሮሞ ህዝብም ባህሌ ብሎ የሚኖረው፣ የሚያምንበት፣ የሚያከብረውና የሚተዳደርበት እንደሆነ ይነገርለታል የሲንቄ ባህላዊ ስርዓት። ሲንቄ ሀደ ሲንቄ (የሲንቄ እናቶች) የሚይዙት እና በቁመታቸው ልክ የሚዘጋጅ ቀጥ ያለ እንዲሁም የተስተካከለ «ሃሮሬሳ» ከሚባል ዛፍ የሚዘጋጅ ዘንግ ነው።
ይህንን የኦሮሞን ባህላዊ ስርዓት በበቂ ሁኔታ ያጠናና ለትውልድ ያስተዋወቀ ባለመኖሩ ከኦሮሞ ማህበረሰብ ውጪ በአብዛኛው ህዝብ ዘንድ አይታወቅም። ይሁን እንጂ አሁን አሁን አንዳንድ ሥራዎች ተጀምረዋል። ባህልና ቱሪዝም ሚኒስቴር ከኦሮሞ ባህልና ቱሪዝም ቢሮ ጋር በመቀናጀት የተለያዩ ጥናቶችን አድርጎ እያጠናቀቀ መሆኑን ሰምተናል። ይህንን አስመልክቶም የተለያዩ መረጃዎችን እያጣቀሱ የነገሩን የባህልና ቱሪዝም ሚኒስቴር የሴቶች፣ወጣቶችና ሕፃናት ዳይሬክተር ወይዘሮ ወይንሸት ሃይለማርያም ናቸው።
ሲንቄ ምንድነው? ወይዘሮ ወይንሸት ባህሉ በስፋት በሚተገበ ርባቸው ጉጂ፣ ምዕራብ አርሲ፣ ባሌና ቦረናን ያካተተ ጥናት ተጠንቶ እንደተጠናቀቀ ገልጸው፤ የሲንቄ ስርዓት ከሚሰጠው ጠቀሜታ አንፃር በክልል ደረጃ ብቻ የሚወሰን ሳይሆን አገራዊ ብሎም ዓለም አቀፋዊ መሆን እንደሚገባው ይናገራሉ። ሲንቄ ( ሲንቆ) ያገቡ እናቶች የሚይዙት ቀጥ ያለ በትር ነው። የሲንቄ እናቶች ሴት ልጃቸውን በሚዳሩበት ጊዜ እንደ ትልቅ ስጦታ በውርስነት የሚሰጡት ይህን ዘንግ ወይም ልምጭ ነው፤ የበትሯ መገኛ «ሃሮሬሳ» ከሚባል የዛፍ ዝርያ ሲሆን፤ ዛፉ ወይም ተክሉ የተመረጠው በተምሳሌትነት እንደሆነም ይናገራሉ።
እንጨቱ አይነቅዝም፤ ይህም የእናቶች የሰላምና የእርቅ ሂደት የማያረጅና ብል የማይበላው መሆኑ ማሳያ ነው። ቀጥ እንዲል የተደረገበት ምክንያት ደግሞ እናቶች በትክክለኛውና ፍትሐዊ በሆነ መንገድ በቀጥታ ለሰላምና ለችግር መጓዛቸውን ለመግለጽ እንደሆነ ነግረውናል። የሲንቄ እናቶች ባህላዊ ስርዓት በዓላማ ደረጃ የተለያዩ ተግባራትን ያካተተ እንደሆነ የሚያነሱት ወይዘሮ ወይንሸት፤ ሲንቄን የያዙ እናቶች ግጭት ይፈታሉ፤ ሴቶችን ወደ ውሳኔ ያመጣሉ፤ መብታቸውን ያስከብራሉ፤ወንዶችን በተለያየ አጋጣሚ ይመርቃሉ።
አምላክ ለምድሪቱ ዝናብና በረከት ይሰጥ ዘንድም ይለምናሉ። በተለይም አባቶች ወደ ጦርነት ሲጓዙ መልካም ዕድል እንዲገጥማቸው በሲንቄ ምርቃት ይሸኛሉ። የሲንቄ እናቶች ለሰላም የሲንቄ እናቶች በትራቸውን ይዘው ግጭት እንዴት ያበርዳሉ ከተባለ ደግሞ አንድ ማሳያ እናንሳ። በሌሎች አካባቢዎች በሰፈር ላይ ግጭት ሲፈጠር ሴቶች መጀመሪያ የሚያደርጉት የድረሱልኝ ጥሪ ማሰማት ነው፤ ከቻሉ ይገላግሉ ይሆናል።
ካልሆነ ወደ ፖሊስ ያመራሉ። በሲንቄ ባህላዊ ስርዓት ግን የተለየ ነው። ግጭቱ ቦታ ከወንድ ቀድመው በመድረስ መፍትሕ ያበጃሉ። አንዷ ሴት እልል ካለች ብዙ ሴቶች ሲንቄውን ይዘው በመምጣት ያጅባታል። ከዚያ ግጭቱ መሀል ይገባሉ። በቦታው ሲንቄዋን አስቀምጠውም (ተክለው) ይዘምራሉ። በአንድነት ለምን ይህንን ታደርጋላችሁ እያሉም ይገስጿቸዋል። በወቅቱ አንዲት ሴት ወደ ግጭቱ ቦታ እልል እያለች ስትጓዝ መሀል አትገቢም የሚላት አይኖርም። ይልቁንም እርሷን ሲያዩ የተያያዙት ይላቀቃሉ። እርሷን ለመንካትም የሚደፍር አይኖርም።
ምክንያቱም ለእነርሱ ባህላቸው ህግ ነው። ህጉን ከምንም በላይ ያከብራሉ። ‹‹ህግ ከገዛው ባህል የገዛው ይልቃል›› የሚባለውን አባባል አንስተው ወይዘሮ ወይንሸት እንዳሉት፤ የሲንቄ እናቶች መዝሙር የድረሱልኝ ጥሪ ነው። ጥፋት እየተሠራ መሆኑን ቀድመው ይናገሩበታል። ከዚያ አባገዳዎች ይመጡና ምን እንደተፈጠረ ይጠይቃሉ። ያለውን ሁኔታ አስረድተው እርቅ እንዲፈጸም ያደርጋሉ። እንክብካቤ ለወላድ በዚህ ባህላዊ ስርዓት ውስጥ ሁለት ዓይነት የአፈጻጻም ተግባር ይከናወናል፤ይሄ ግን ከአካባቢ አካባቢ ይለያያል። አንዳንድ ቦታ ስምንት ሌላው ጋር ደግሞ ስድስት ወር ይሆናል። ተግባሩ አንዲት እንስት ከወለደች በኋላ የሚደረግላትን እንክብካቤ የሚያሳይ ሲሆን፤ ባለቤቷ ልዩ አክብሮት የሚሰጥበት፣ ማህበረሰቡ ከምንም በላይ እንክብካቤ የሚያደርግበት ጊዜ ነው።
ለዚህም ማሳያው አራስ፣ እመጫት ወይም ነብሰጡር መሆኗን የሚያሳይ በባህሉ አጠራር ‹‹ቀነፋ›› የሚባል ከእንጨት የተሠራ ጌጥ በግንባሯ ላይ ማድረጓ ነው። «ቀነፋ» ያደረገች ሴት ባልየው ጫፏን አይነካትም፣ ልዩ እንክብካቤም የማያደርግላት ከሆነ ይቀጣል። ተሳስቶ እንኳን ክፉ ነገር ቢናገራት ሲንቄዋን ይዛ እልል ካለች ጉዱ ነው የሚፈላው። ምክንያቱም እልልታዋን ሰምተው የአካባቢው ሴቶች ሲንቄያቸውን ይዘው ይሰበሰባሉ። ወደ ቤት በማምራት ያደረገውን አጣርተው ቅጣት ይጥሉበታል። እልል አሉበት ማለት ደግሞ በባህሉ መሰረት ረገሙት ተብሎ ስለሚታመን መዋሸት አይፈልግም። ስለዚህ የተጣለበትን ቅጣት በጸጋ ተቀብሎ ይፈጽማል። በሲንቄ ባህላዊ ስርዓት ጥፋት ተሠርቶባት ባለቤቷን ለመጠበቅ ብላ ጥፋቱን ችላ የምትል
እንስት ወይም እልል ብላ የማትወጣ ሴት ብትኖር አንድ የሚወሰድባት ዕርምጃ አለ። ምክንያቱም ባህሉን ንቃለች፤ በዚያ ላይ ለወንዱ የእርሷን ነፃነት አሳልፋ ሰጥታለች ተብሎ ይታመናል። ስለዚህ የሲንቄ እናቶችና የአካባቢው ማህበረሰብ ወደ ቤቷ በመሄድ ያላትን በሙሉ ይበሉባታል። ቤት ውስጥ ያለውን በሙሉ ይወስዱባታል። በዚህ ቅጣት ይደርስባታል። ከዚያአልፎ ማህበረሰቡ ያገላታል። ስለዚህም በምንም ምክንያት ይህንን ለማድረግ አትደፍርም። ግድ ለነፃነቷ መታገልና ድምፅዋን ማሰማት ይኖርባታል።
ሌላው «ቀነፋ» ያጠለቀች እናት የትኛውም የአገልግሎት መስጫ ተቋም ስትሄድ እርሷን ቀድሞ የሚገባም ሆነ የሚገለገል አይኖርም። ለእርሷ ሁልጊዜ ቅድሚያ መስጠት ግዴታ ነው። ዛሬ ላይ ነብሰጡር እናቶችን ስንመለከት ቅደሙ እንደምንለው ዓይነት። ነገር ግን ፅንሱ ገፋ ብሎ የማይታይ ከሆነ ይህንን አናደርግም። ሕፃን ልጇን እቤቷ መተው አለመተዋን ማረጋገጫ የለንም። ስለዚህ በምንም መልኩ ቅድሚያ አንሰጣትም። በዚህ የባህል ስርዓት ግን መለያ ቀነፋ በግንቧሯ ላይ ስለምታደርግ ሁሉም ክብር ይሰጣል። እርሷን ዓይቶ መንገድ ለማቋረጥ እንኳ የሚደፍር አይኖርም። በጣም ከተጣደፈ እንኳን ሳር ነጭቶ ይቅርታ ጠይቆ እንደሚያልፍ በጥናቱ ያገኙትን በመጥቀስ ወይዘሮ ወይንሸት ነግረውናል።
የማህበረሰብ እምነት ለሴቷ ስለ ስርዓተ ጾታ ሲነሳ በጣም እያስቸገረ ያለው የመደፈር ጉዳይ ሲሆን፣ ስድብና ዘለፋ በዚህ ባህል ቅጣት እንዳለው የምንመለከትበት ነው። አንዲት ሴት ጾታዊ ጥቃት ደረሰብኝ ካለች ማህበረሰቡ ያምናታል። አስፈላጊውን ቅጣትም በወንዱ ላይ ይጥላል። እርሷ ልዋሽ ብትል እንኳ ማህበረሰቡ ከማመን ወደኋላ አይልም። ምክንያቱም በውሸቷ ዋጋ እንደምትከፍል ይታመናልና። ሴት ትወልዳለች በውሸቷ በልጆቿ ትቀጣለች ተብሎ ይታመናል። እናት ደግሞ «ከልጄ እኔን ያስቀድመኝ» ብላ የምታስብ ነችና ለልጆቿ እዳ ላለመጣል ስትል ማህበረሰቡን ለመዋሸት አትደፍርም። በዚህም ቀጥታ ቅጣቱን እንዲያገኝ ታደርጋለች። ደፋሪው ወይም ጥቃት አድራሹ ከቅጣቱ ባሻገር ይቅርታ የመጠየቅ ግድታም
ይጣልበታል። ይህንን አሻፈረኝ ካለ ግን ይረግሙታል። እልል ይባልበታል። በዚህም በህይወቱ ደስተኛ ሳይሆን ይኖራል። ጥቃት አድራሹ ስነልቦናዊ ችሎት ስለሚጣልበት በፍጹም ከዚህ ራሱን ለማሸሽ አይሞክርም። እንደውም ተገዝቶ ነው የሚኖረው። በዘመናዊ የህግ ስርዓት ሴት ልጅ ጥቃት ደረሰብኝ ካለች የሚጠየቀው ማስረጃና መረጃ ነው። በማስረጃ እጦት ስነልቦናዊ ጉዳቷን ተሸክማ የምትኖር ብዙ ሴት መኖሯን ነጋሪ አያሻንም። ይህ ስርዓት ግን ከዚህ ይታደጋል። ስለዚህ ማንኛውም ወንድ ሴትን በዘለፋም ሆነ ልብሷን በመንካት አያስቸግርም።
ሲንቄ ለልጃገረዶች በዚህ ባህላዊ ስርዓት ውስጥ ለሴት ልጅ የሚሰጠው ክብርና ሞገስ እጅግ የሚማርክ መሆኑን የምናይበት አንዱ መለያ ደግሞ ለልጃገረዶች የሚሰጠው መብት ነው። ሲንቄ የሚያዘው በእናቶች ቢሆንም በልጃገረዶችም የሚያዝበት አጋጣሚ አለ። በእርግጥ ልጃገረዷ የምትይዘው አባት ከአሮሬሳ ዛፍ በሚገባ የሠራውንና ለእናት የሚሰጠውን ዓይነት ተከትሎ አይደለም። የእናቷን ሲንቄ ነው አንስታ ይዛ ልትሄድ የምትችለው። ልጃገረዷ ይህንን የምታደርገውም ለአንድ ነገር ብቻ ነው።
የምታፈቅረውን ወንድ ለመጠየቅ ስትል። በኦሮሞ ባህል ወንድ ልጅ ብቻ አይደለም የሚጠይቀው። ሴቷ የወደደችውን ወንድ መጠየቅ ትችላለች። ይህ የሚሆንበት ግን የራሱ የሆነ ባህላዊ ስርዓት አለው። ልጃገረዷ የእናቷን ሲንቄ ይዛ በወደደችው ወንድ ቤተሰብ ግቢ ውስጥ ትወረውረዋለች። ከዚያም በግቢው ውስጥ ገብታ ትዘምራለች፤ መውደዷን ትገልጻለች። ማንን እንዴት እንደወደደችም ታስረዳለች።
ይህንን ያዩ የቤተሰቡ አባላትም ለእዛች ልጅ ምላሽ ለመስጠት ይዘጋጃሉ። ቤተሰብም ሆነ ልጁ አልስማማም ማለት አይችሉም። እንዳውም ሁለት ሴቶች አንድ ወንድ ቢያፈቅሩና የእናታቸውን ሲንቄ በአንድ ግቢ ውስጥ ቢጥሉ ቀድማ ለጣለችው የሚዳርበትም ስርዓት አለው። እናም ይህ ባህል ለልጃገረዶችም መብት የሰጠ መሆኑንና ሴት ልጅ ብቻ ያልወደደችውን ማግባት ግዴታ ውስጥ
እንዳልነበረች እናይበታለን። ያው በአወንታዊ ሲታይ ምርጫ በሴቶችም ይከናወናል የሚለውን ለመጠቆም ነው። እናቶች ለልማት ብዙ ጊዜ በሲንቄ እናቶች የሚሠራው የእርቅ ተግባር ቢሆንም ልማታዊ ተግባራትም በእነርሱ አማካኝነት ይፈጸማል። ለአብነት በአካባቢው ላይ የደረሰ እህል ሳይታጨድ ለብልሽት ቢጋለጥ ገበሬው ዕርዳታ ጥሩልኝ ካላቸው ሲንቄያቸውን ይዘው ይወጣሉ። በህብረት እንታደገውም ይላሉ። ገበሬው ወደእነርሱ የሄደበት የራሱ ምክንያት አለው። የሲንቄ እናቶች የለመኑት ነገር ይፈጸማል፤ እነርሱን እንቢ ማለትም አይቻልም። ስለዚህም በተነገራቸው መሰረት በየቤቱ እየዞሩ በደቦ እንዲያግዙት ይለምኑለታል።
ተሰሚነታቸው የላቀ በመሆኑም ሥራቸውን እንኳ ቢሆን ትተው የእነርሱን ልመና ለማሳካት ይጥራሉ። ገበሬውም እህሉ ሳይበላሽ ጎተራውን ይሞላል። እነዚህ በባህላዊ ስርዓቱ ውስጥ ያሉት እናቶች አምላክ ከእነርሱ ውጪ አይሰማም ተብሎ ይታመንባቸዋል። እንደውም «ሃዳ» ገዳ ይሏቸዋል።
እነዚህ እናቶች ሰላም አምጪ ናቸው። ሰላም ካለ ልማት፣ ብልጽግና ይኖራል። ማህበረሰቡም በአንድነት ተቻችሎ እንዲኖር ያደርጋል። አለመግባባቶችም አይኖሩም። በዚህም የልማት ምሶሶ እንደሆኑ ይነሳል። የራስ መብት «ሲንቄ» በገዳ ስርዓት ሴቷን ከአባጋዳ ጋር አቻ የሚያደርጋት የ«ሀዳ ሲንቄ” ምልክት ሲሆን፤ የተለያየ መብትም ለሴቷ ያጎናጸፈ መሆኑን ያነሳሉ ወይዘሮ ወይንሸት።
እርሳቸው እንዳሉት፤ ሴት ልጅ በዚህ ባህላዊ ስርዓት ውስጥ በተሰጣት ሙሉ ንብረት ላይ የመወሰን መብት አላት። መጀመሪያ ከቤተሰብ የተሰጣትን ከብት ሳይቀር ያለእርሷ ውሳኔ ባለቤቷ ምንም እንዲያደርግ አይፈቀድለትም። ምክንያቱም በባህሉ ዘንድ ገና ከብቱ ሲሰጣት በሲንቄዋ ትነካካዋለች። ይህ ደግሞ መባረክን የሚያሳይ ነው። በባህሉ ለእርሷ ስጦታ የተደረገ ነው ብሎ ስለሚታመንም ወንዱ ሳያስፈቅድ ቢያደርገው አደጋ እንደሚደርስበት ያምናል። ስለዚህም ያለእርሷ ውሳኔ ምንም አይነካም። አወን /እናቶች/ እየተንቀሳቀሱ ማንም አቋርጧቸውም ሆነ ክብር ሳይሰጣቸው አያልፍም። እነርሱ እያሉ ወንዝም መሻገር አይቻልም።
ቅድሚያ የእነርሱ ነው። በዚህም መብታቸው ይከበራል። ይህ ባህል ብዙ ጠቀሜታ ቢኖረውም ተተኪው ትውልድ ግን እያወቀና እየተገበረው እንዳልሆነ ይነገራል። ኋላ ቀር አመለካከት አድርጎ ይወስደዋል፤ አይኖርበትም። በዚህም የፈለገውን ያህል የሴቶችን መብት እንዳያስከብር አድርጎታል ይላሉ።
አንድ ባህል የለም ማለት አንድ ማህበረሰብ የለም እንደማለት ነው። በመሆኑም የሲንቄ ባህላዊ ስርዓትን በማጥናት ቀጣይነቱን ማረጋገጥ፣ በሀገርም ሆነ በዓለም አቀፍ ደረጃ ማስተዋወቅ ይገባል። እኛም ባህላችን ያልተነገረለት፣ያልተጠቀምንበት ግን ደግሞ ከዘመናዊዎቹ የፍትህ ስርዓት የበለጠ ጠቀሜታ አለውና እናውጣው፤ እንጠቀምበት በማለት ሃሳባችንን ቋጨን። ሰላም!
ጽጌረዳ ጫንያለው