ዛሬ ወደኋላ መለስ ብለን ከሁለት አመታት በፊት ከዚህ አለም በሞት የተለየውን ታላቅ የጥበብ ሰው አርቲስት ታደሰ ወርቁን እንዘክራለን። አንጋፋዋ ዓለምጸሀይ ወዳጆ ባረፈበት ወቅት ስለታደሰ የሕይወት ታሪክ ያቀረበችውን ጽሁፍ እሱ ራሱ በአንድ ወቅት በታዛ መጽሄት ላይ ካረገው ቃለመጠይቅ ጋር አዋህደን እንደሚከተለው አቅርበነዋል።
ዕውቁ መራሔ ጥበብ ታደሰ ወርቁ ከትልቅ ቤተሰብ ከደጃዘማች ብዙነህ በዛብህ ልጅ ከወ/ሮ ወደርየለሽ ከሚወለዱት እናቱ ከወ/ሮ የሺሐረግ ወ/አረጋይና ከግራዝማች ወርቁ ባልቻ በከፋ ክፍለ አገር ሚዛን ተፈሪ የሁለተኛ ጋብቻ የመጀመሪያ ልጅ ሆኖ እንደ ኢትዮጵያ አቆጣጠር ጥር 23 ቀን 1942 ዓ.ም ተወለደ:: እናቱ ከመጀመሪያ ትዳራቸው ከአቶ አስፋው እጅጋየሁንና ግርማን ወልደው ነበርና ለእናቱ ሦስተኛ ልጅ ሆኖ ተቆጠረ::
ወ/ሮ የሺሐረግ በተከታታይ ሁለት ልጆች ከወለዱ በኋላ ግን በቤት ውስጥ የነበረው ሰላም ደፈረሰ። ደጃዝማች አለማየሁ ፍላቴ ሁለቱን ልጆች ማለትም ታዴንና አሰለፍን አዲስ አበባ ወስጄ ላስተምር ብለው ይዘዋቸው ሄዱ። እነሱ በት/ቤት እያሉ በእናትና ልጆች መሀከል ያለው ናፍቆትና መፈላለግ በማየሉ ለወ/ሮ በወቅቱ ለፊታውራሪ አለማየሁ መመለሻ በተዘጋጀው አውሮፕላን ውስጥ ሸኚ በመምሰል የተገኙት ወ/ሮ የሺ ሐረግ ከአውሮፕላኑ አልወርድም ብለው በማስቸገር ወደ አዲስ አበባ ተጓዙ።
በአማቻቸው በወ/ሮ ወደሬ ቤት ተቀምጠው ልጆቻቸውን እየተመላለሱ መጠየቅ ያዘወትሩ ስለነበር ከእለታት ባንዱ ቀን ግብር ገብቶ እራት ተበልቶ ካበቃ በኋላ ደጃዝማች እረፍት በማድረግ ላይ እንዳሉ ወ/ሮ የሺሀረግ የተኛውን ልጃቸውን ታደሰንና አሰለፍን ሰርቀው ድሮ ዶቅዶቄ ወይም ኩርኩር በምትባል መኪና ኮንትራት ይዘው ጠፉ። የተኮናተሩትን መኪናም መንገድ አቁመው ፀጉር ቆራጭ ቤት ጎራ ብለው አሳምረው ይዘውት በመሄድ ከአያቱ ከወ/ሮ ወደር የለሽ ቤተሰብ ተደባለቀ።
ሚዛን ተፈሪ ውስጥ በወላጆቹ የተሰራችው ሚካኤል ቤተክርስቲያን አለ፡- በቤት ውስጥ በእንክብካቤ የሚያሳድገው ለማ የተሰኘው ግለሰብ በበቅሎ እየወሰደው በዚህ ቅጥር ግቢ የሚያሳልፈው የልጅነት ትዝታ ነበረው። የእሱም ሆነ የእናቱ ደስታ ወደር አልነበረውም። በኋላም ወ/ሮ የሺሐረግ ባለብዙ ንብረትና ሐብት ባለቤት የነበሩትን አቶ ከበደ ደገፋን አግብተው መርካቶ ወሰን ሰገድ አጠገብ መኖር ሲጀምሩ ሌሎች ወንድሞች እና እህቶች ተወለዱለት።
ከዚያ የ1953ቱ የታኅሳስ ግርግር መጣ:: ትምህርት ቤቶች ተዘጉ:: ቤተሰቦቹም ከቤት እንዳይወጣ ፈለጉ:: ታደሰም ትዕዛዛቸውን ማክበር ነበረበት:: በአጋጣሚ የነሱን ቤት ተከራይቶ የሚኖር የአስር አለቃ ታምሩ የሚባል ወጣት መርማሪ ፖሊስ ነበር:: ታዲያ አንድ ቀን ለራሱ ጉዳይ ወደ ኮልፌ ሙዚቃ ክፍል ሲሄድ ታደሰን ይዞት ይሄዳል:: እዚያ ሙዚቀኞቹን ይመለከታል፤ የፋንፋር ባንድ አለው፣ ኦርኬስትራው ዘመናዊና የተሟላ ነው:: የቴያትር ክፍልም አለው:: አቶ ተስፋዬ አበበ የግጥምና ዜማ ደራሲ የቴያትር ክፍሉም ኃላፊ ነበር:: ከዚያች ዕለት ጀምሮ የታደሰ ልብ ወደ ሙዚቃው አዘነበለ::
እንደአጋጣሚም ሆኖ በጥቂት ሳምንታት ውስጥ ወጣቶችን ለመቅጠር ማሰባቸውን ይሰማል:: ከዚያ ቤተሰቡን ሳያማክር ይሄድና ይመዘገባል:: ተቀበሉት:: እዚያው ካምፕ ውስጥ ሆኖም መሰልጠን ጀመረ:: መጀመሪያ ወታደራዊ ስልጠና ወሰደ:: ቀጥሎ የክላርኔት አጨዋወትን ተማረ:: መምህሩ ሚስተር ሃጎፕ የሚባሉ ሲሆኑ ነርሲስ ናልቫንዲያንም የኦርኬስትራው መሪ ነበሩ::በወቅቱ የፖሊስ ኦርኬስትራን የዳንስ ቡድን የሚያሰለጥነው ሽፈራው ከበደ ስለነበር ከእሱ ሥር በመሆን ይመለከት ነበር። ብዙም ሳይቆይ ደነሰ በመቀጠልም አሰልጣኝነቱን ተረከበ።ከጥቂት አመታት በኋካ ግን የፖሊስ ቤት ዲሲፕሊን ሲሰለቸው ስራውን ትቶ ቤት ቁጭ አለ።ብሄራዊ ቴአትሮች ቤቱ ድረስ መጥተው እኛ ጋር ና አሉት።ብሄራዊ ቴአትር ገባ።
በአንጋፋውና ዕውቁ አውላቸው ደጀኔ የሚሰለጥነው የቲያትር ቤቱ የባህል ቡድን ለዓለም አቀፍ ዝግጅት ተሳታፊነት ያጠናውን ትርኢት ለ5 የወቅቱ ሚኒስትሮች ያስገመግም ነበር። የአዳራሹ መብራት የግቢው ፅዳት፣ የአካባቢው ድባብ፣ የመድረኩ ስፋትና ውበት የታዴን ልብ ሰረቀው።
በእንደዚህ አይነት መድረክና ከእንደዚህ አይነት ሙያተኞች ጋር የመስራት ዕድል አገኝ ይሆን ? በማለት እራሱን ጠየቀ። ያቺ ቀን ናት የታዴን መጪ ሕይወት ጥያቄ ያጫረችው። እንደተመኘው አልቀረም ቅጥሩ ፀንቶ ሲመጣለት የዘመናዊ ክፍሉ ተወዛዋዥ በመሆን ነበር የተቀጠረው። የክፍል ኃላፊው ሌላው ሁለገቡ ባለሙያ አቶ ተስፋዬ ሣህሉ (አባባ ተስፋዬ) ባልተመቻቸው ቀን የጀመሩትን ስራ እንዲጨርስ በመደቡት ጊዜ ታዴ ውዝዋዜ ማሰራቱን ተያያዘው። ውስጡ ያለውን ችሎታ ለማየት የቴአትር ቤቱ የወቅቱ አስተዳዳሪም ጊዜ አልፈጀባቸውም::
ታደሰ ዘናጭ ነው። በአለባበሱም ቢሆን በኪሱ ውስጥ ምንም ገንዘብ ባይኖረው እንኳን ፅድት ያለ ውብ አለባበስ እንዲለየው ከቶም አይፈቅድም ነበር። ቆንጆና ውብ ነገር መልበስ መውደዱን ጠንቅቆ የሚያውቀው አብሮ አደግ ጓደኛው ዕውቁ ድምፃዊ መልካሙ ተበጀ በደርግ ዘመን ዩኒፎርም መልበስ ሲታዘዙ “አይይ ታድዬ መሬት ሲታወጅ አንተን አይመለከትህም ቤት ቢወረስም አንተን አይመለከትህም አሁን ግን በአለባበስ ስለመጡ ያንተ መሰደጃ ሰዓት አሁን ነው …. ” ብሎ ቀልዶበታል::
መቼም እንደሚታወቀው የቀድሞው ቀዳማዊ ኃይለሥላሴ ትያትር ቤት ከውጭ አገር በሚመጡ የተውኔት የሙዚቃና የዳንስ አሰልጣኞች ከመታደሉም ሌላ የተሳታፊ አርቲስቶችም አልባሳትና ጌጥ ሜካፕና ቁሳቁስ ከተለያዩ ዓለማት ይመጡ ነበር። በዚህ አጋጣሚም ዕውቋ የሜክሲኮ የዳንስ አሰልጣኝ አና ሜሪዳን ተገኝታ ነበርና የቴያትር ቤቱን ተወዛዋዦች የዳንስ ችሎታና ዕውቀት እጅጉን ከፍ አደረጋቸው።
በተለይም ታዴ ዘወትር እንደሚያነሳት ሁሉ በውስጡ የነበረውን የዳንስ ጥበብ እይታ በጣም በእመርታ አሳደገችለት:: በወቅቱ በቴአትር ትወናም በውዝዋዜም በሁለቱም ሙያ በጋራ መሳተፍ የተለመደ ነበርና የኢትዮጵያ ፈርጥ ባለሙያዎች እነአስናቀች ወርቁ እነጠለላ ከበደ እነጀምበሬ በላይ ….. ወዘተ አብረው መድረኩን አስውበውት ነበር። እያደርም የታዴ ችሎታና ልምድ እያየለ ሄዶ የክፍል ኋላፊነቱን መያዝ ብቻ ሳይሆን በዓለም አቀፍ መድረክም ለመሳተፍ በቃ። ከሜክሲኮና ከአልጄሪያ ፌስቲቫሎች ተሳትፎ ከተመለሰ በኋላ ታዴ በተውኔቱ መድረኩም በትወና መታየት ጀመረ።
የሥርዓት ለውጥ ተካሂዶ አዳዲስ ትርኢቶች በዓይነታቸውም በቁጥራቸውም እየጨመሩ ሲመጡ “በእናት ዓለም ጠኑ ” ላይ በላይ ዘለቀን በመሆን ፤ “በዋናው ተቆጣጣሪ “፡- ዳኛውን ፤ “በአሉላ አባነጋ ” አጋፋሪውን” በመሆን ተጫወተ።
የዓለም አቀፍ የጥቁሮች በዓል በናይጄሪያ ዋና ከተማ በሌጎስ ሲካሄድ ” ትግላችን ” የተሰኘውን የመጀመሪያውን ሙዚቃዊ ዳንስ ድራማ ከሌላው ድንቅ ባለሙያ ከሃይማኖት ዓለሙ ጋር በመሆን አዘጋጀ። ከዚያ በኋላ እውነት ለመናገር የኢትዮጵያን የዳንስ እንቅስቃሴ ጥበብ ባልተለመደ መልኩ ደረጃውን አሳምሮ ቀየረው። ለወጠው።
የሚቀርቡት እንቅስቃሴዎች በሙሉ በአልባሳት – በወግ ዕቃ -በጌጣጌጥ ከመዋባቸው በላይ ምክንያታዊ እንቅስቃሴዎችና ትርጉም ሰጪዎች እንዲሆኑ አደረገ። በየሙዚቃው እሪትም የተወዛዋዡ ሰውነትና እንቅስቃሴ እንዲታሰር በማድረግ ከተወዛዋዦቹ ጋር ብቻ ሳይሆን ከሙዚቃ ፈጣሪዎችና አቀናባሪዎች ጋር አብሮ መስራትና ማጋመድ ጀመረ። ባልተለመደ መልኩ ጉልበታም ስራዎችን አቀረበ።
በቴአትር ጥበብም በዝግጅት ድንቅ ባለሙያ ሆነ። “ትግላችን ” “ትግል ነው ፣ መፍትሔው ፣ ” ” ፍልሚያ፣ ” “አምታታው በከተማ” ን አዘጋጀ። በማከታተልም ለዓለም አቀፍና ለአገር አቀፍ ዝግጅቶችና ለውጭ እንግዶች የሚሰሩ ስራዎችን እንዲመራና እንዲያስተባብር በተከታታይ ይታጭ ገባ። በተለይ “ደማችን ” የተሰኘውን ሙዚቃዊ ዳንስ ድራማ ከ100 በላይ በሚሆኑ የአራት ቴአትር ቤቶች ባለሙያዎች (ማዘጋጃ ቤት፣ ሀገር ፍቅር፣ ብሔራዊ ቴአትርና ራስ ቴአትር ) ከተውጣጡ ምርጥ ባለሙያዎ ች ጋር የሰዓት እላፊ የፈቃድ ወረቀት አስወጥቶ እስከ ለሊቱ፣ ሰባት ሰዓት ማለትም በቀን እስከ 15 ሰዓት በማሰራት ድንቅ የጥበብ ውጤት አበረከተ።
በተወዛዋዦችና በባለሙያዎች ህሊና የማይፋቁ – ከሙዚቃ ባለሙያዎች ልቦና የማይጠፉ ከተመልካቾች ትውስታ የማይርቁ ሥራዎችን በተደጋጋሚ አቀረበ። ይሁን እንጂ ወቅቱና የተጓዘበት ስፍራ ታሪኩን ከፍ አድርጎት እስከዛሬ ድረስ በመላው ኢትዮጵያዊ አእምሮ ተቀርፆ ከፍተኛ የኩራት ስሜትን የፈጠረው “የሕዝብ ለሕዝብ” የሀገረሰብ ሙዚቃዊ ቅንብር ልዩ ሥፍራን አስያዘው። ታዴ ይህንን ስራ በኋላፊነት ከመምራቱ በፊት የካሜራ የቪዲዮና የስዕል እውቅ ባለሙያዎችን ይዞ በኢትዮጵያ የገጠር መንደሮች በመዘዋወር የየብሔረሰቦችን ጭፈራና ዜማ በመቅረፅ ጌጣቸውን አለባበሳቸውን አኗኗራቸውን እንዲሁም የአካባቢውን ገፅታ መዝግቦ በማምጣት ለሥራው መንደርደሪያ አበጀ። ያንንም ያጠናውን ጥናት ወደመድረክ በማምጣት የማይጠፋ አሻራውን አሳረፈ።
በዚያን ወቅት ነበር አጋጣሚውን በመጠቀም ከሚዛን ተፈሪ በለቀቀ በግምት ከ40 ዓመታት በኋላ ወደትውልድ ሥፍራና መንደሩ ያዘገመው። በጣም ተቀያይሮ ተለውጦ ጠበቀው። ሰፈርተኛውን እየዞረ ያሳደገውን ለማን ለማየት ተማፀነ። ቤቱን አሳዩት ተኝቶ የነበረው ለማ ሰው እንደሚፈልገው ተነግሮት ሲወጣና ታዴን ሲያየው ለጥቂት ደቂቃ እንኳን ሳይጠራጠር “ታድዬ” ብሎ አቅፎ ሳመው ። እየተላቀሱ ወደአባቱ መኖሪያ ቤት ተያይዘው ሄዱ።
“የሕዝብ ለሕዝብ” ትርኢት ከመሰረተ ሀሳቡ መፀነስ ጀምሮ በእያንዳንዱ የሙዚቃ ሕይወትና አሰራር በመድረኩ ላይ በቀረበው እንቅስቃሴ አልባሳት ጌጣጌጥ የመድረክ ሲናሪ የዚህ ሙያተኛ የታደሰ ወርቁ ድካምና ፈጠራ ነው። ይህንንም አብረው ጥበቡን የሠሩት ባለሙያዎች በሙሉ ሁሉም በሕይወት ኖረው በእንባ እየተራጩ መመስከራቸው ትልቅ ነገር ነው:: ስህተት ኖሮ ቢሆን በጥፋቱ ተጠያቂ ሊያደርገው እንደሚገባው ሁሉ ሥራው ተዋጥቶ ሲደነቅና ሲሞገስም አብሮ መደነቅና መሞገስ ያለበት ታደሰ ወርቁ ነው። የኢትዮጵያውያንን የጥበብ ሀብት ጉልበት ያሳየ ሥራ ለመሆኑ ሁሉም ይመሰክራል።
ወደ አገሩም እንደተመለሰ በየግዜው ጠይቆት የነበረው የሙያ ስልጠና ትምህርቱ ጉዳይ መልስ ባለማግኘቱ የሚወዳቸው እናቱን አንድ ልጁን አገሩንና መድረኩን እንዲሁም ለሩብ ክፍለ ዘመን ገደማ የሰራበትን ብሔራዊ ቴአትር በእንባ ተለይቶ በ1981 ወደ አሜሪካ ተሰደደ ። ከረዥም ዓመታት ቆይታ በኋላ በዶ/ር ዮናስ አሰባሳቢነት በስደት የሚገኙ ባለሙያዎችን ሰብስቦ ከአዳዲስ ወጣቶች ጋር በተወሰኑ ከተሞች የጥበብ ውጤቱን አቀረበ። ከሙያና ከጥበብ ፍቅርና ችሎታ መሳ ለመሳ በሰው አክብሮቱና መወደዱ በቸርነቱና በጥሩነቱ በለጋስነቱ በትህትናው የሚታወቀው ታደሰ ከግለሰብ እስከ ማህበረሰብ ያልረዳውና ያልደገፈው አልነበረም። ባለ ብዙ ተሰጥኦው የአገር ባለውለታ ከሁለት አመታት በፊት ጳጉሜ 1 ቀን 2012 አ.ም ከዚህ ዓለም በሞት ተለይቷል።
ከመሞቱ በፊት ጥቂት ቀደም ብሎ በአገረ አሜሪካ በተካሄደ የምስጋና መርሀ ግብር ላይ እንደ ታማኝ በየነ፤ ኩሪባቸው ወልደማሪያም እና ከታደሰ ጋር በነበራቸው ግንኙነት አንድ ልጅ የወለደችው አንጋፋዋ አርቲስት ዓለምጸሀይ ወዳጆ በርከት ያለ አድናቆት እና መወድስ አቅርበውለት የነበረ ሲሆን በተለይም አርቲስት ታማኝ በየነ ታደሰን ሲገልጸው የኢትዮጵያን የባህል ውዝዋዜ ከአውላቸው ደጀኔ ተቀብሎ ያሳደገው ታደሰ ወርቁ ነው ብሎታል። የታሪካዊው የሕዝብ ለሕዝብ ዘመቻ ዋነኛ ባለቤትም ማንም ሳይሆን ታደሰ ወርቁ ነው ብሏል ታማኝ።
የሞቱ ዜና ከተሰማ በኋላ ደግሞ ታዋቂው የኪነ ጥበብ ሀያሲ ሰርጸ ፍሬስብሀት የሚከተለውን ጽሁፍ በፌስቡክ ገጹ አጋርቷል። ሥራቸው በዓለም ተደንቆ፣ በአገር ተወዶ፥ እነርሱ ግን በሙያ ጓደኞቻቸው ዘንድ ብቻ ተከብረውና ታውቀው፣ አገር ሳታመሰግናቸው ካለፉ ኢትዮጵያውያን የጥበብ ሰዎች መሐል ታደሰ ወርቁ አንዱ ነው።
ታደሰ ወርቁ፥ “የሕዝብ ለሕዝብ ኢትዮጵያ፥ የዐደይ አበባ ሙዚቃዊ ትርዒት” ኹለንተና ነበር። በየክፍለ አገሩ ዞሮ የየነገዶቹን ባህል እና አጨዋወት አጥንቶ፣ ከሙያ ጓደኞቹ ሠዓሊ ታደሰ መስፍን እና ከሙዚቀኛው ኩት ዑጁሉ ጋር በዕይታዊው ባህል እና በሙዚቃዊው ባህል የተሟላ ጥናት ይዘው በመምጣት፤ በድርሰት ለተቀናበረው ትርዒት መሠረት ከጣሉት ባለሙያዎች መካከል የመጀመሪያው ሰው ታደሰ ወርቁ ነበር።
ከመስክ ጥናቱ በኋላ፤ ለስምንት ወራት፥ በኮሎኔል መንግሥቱ ኃይለ ማርያም ቢሮ አቅራቢያ ባለው የጉባኤ አዳራሽ፣ ከየቴአትር ቤቱ ራሱ የመረጣቸውን ባለ ልዩ ተሰጥዖ የውዝዋዜ ባለሙያዎችን ይዞ፣ የዳንስ ድርሰቱን በጥብቅ ዲሲፕሊን ካስጠና በኋላ፤ በሶሻሊስታዊው ፖለቲካ በሚመራው መንግሥታችን ምክንያት የተዘጋውን የምዕራቡን ዓለም በር፣ በባህል እና በጥበብ እንዲከፈት፣ ዓለምም ኢትዮጵያን እንዲያደንቅ፣ ማድረግ የቻለ ታላቅ መራኄ ጥበብ ነበር፥ ታደሰ ወርቁ!!!
የእርሱን ታላቅነት፥ ታላላቆቹ የጥበብ ጓደኞቹ፥ ደበበ እሸቱ፣ ዓለም ፀሐይ ወዳጆ፣ ታማኝ በየነ፣ ሠዓሊ ታደሰ መስፍን፣ ሙላቱ አስታጥቄ፣ መርዓዊ ስጦት፣ አያልነህ ሙላት፣ እንዬ ታከለ፣ ንዋይ ደበበ፣ ፀሐይ ዮሐንስ፣ ኃይልዬ ታደሰ…በተለያዩ መድረኮችና አጋጣሚዎች ገልፀውታል።
ከኅልፈቱ በላይ፥ ለሠራው ሥራ ትልቅ ክብር ሳይሰጠው ማለፉ በእጅጉ ያስቆጫል። የተጠበባት መድረክ እና ሥራዎቹ ግን ሁሌም እንደሚያስጠሩት፣ ከኅልፈቱ በኋላም በሥራዎቹ ትንሣኤን እንደሚያገኝ አልጠራጠርም። “የጥበብ ሰው ሥራው ሐውልቱ ነውና።” ፈጣሪ ኩሉ ዓለም ለነፍስህ ሰላማዊ ዕረፍት ይስጥልኝ። ነፍስ ኄር ታደሰ ወርቁ!!!”
አቤል ገ/ኪዳን
አዲስ ዘመን መጋቢት 18/2014