የማለዳ ሀሳቦች የሰው ልጅ ዘመን ድሮች፣ የጊዜ ዘሮች ናቸው። በእያንዳንዳችን ነፍስ ላይ አጎንቁለው በትዝታ ረመጥ የሚፋጁ። ትናንትን ከዛሬ፣ አምናን ከዘንድሮ እያደሩ የሚቋጩ የናፍቆት ሸማኔዎች። እኚህ የልጅነቴ መልከኛ ሀሳቦች ከወንድነቴ ገዝፈው፣ ከወጣትነቴ ልቀው ልጅነቴን ያስመኙኛል። በረገጥኩት የግሬ ዳና ላይ ማለዳዬን ስለው፣ ማምሻዬን ኩለው ይከተሉኛል። በመዳፌ እርቃን በአይበሉባዬ ላይ አርፈው አሁን እንደሆኑ ያህል የትም አያቸዋለው፤ የማለዳ ሀሳቦቼን።
ጠዋት ጀምበር ምስራቅ አድማስ ላይ ስታቅላላ፤ ምሽት ምዕራብ ራስጌ ላይ ስትንፏቀቅ በነዚህ ሁሉ ውስጥ ልጅነቴ ይታወሰኛል። ዛሬም ድረስ የድሮዋ ጸሐይ፣ የልጅነቴ ጀምበር የምታበራ ነው የሚመስለኝ።
ከቤቴ አቅራቢያ ካለው የግራር ዛፍ ላይ የሚያንቃርሩት አሞራዎች፣ የሚያፏጩት አእዋፍት የልጅነቴ አድባሮች ሆነው ዛሬም ድረስ አሉ። መኪና መንገዱን ተሻግሮ ካለው ካቴድራል የሚሰማኝ የካህኑ ዜማ፣ የአጥቢያው እግዚኦታ፣ የደጀ ሰላሙ ቡራኬ እኚህ ሁሉ፤ አበባ ለመቅሰም የሚያጠዘጥዙ ንቦች፣ አፈር ጭራ ያገኘቻትን አንዲት ትል ልጆቿን ለማብላት የምታንቃርር ዶሮ፣ ጫጩት ለመያዝ የምታደባ ጭልፊት እኚህ ሁሉ።
ከሁሉም በኋላ አይ ጊዜ እላለሁ፤ የጊዜ እውነት ያስደንቀኛል። የጊዜ ፍርድ፣ የጊዜ ሚዛን ያስገርመኛል። ሕይወት ምንድነው ላለኝ ጊዜ ነው እለዋለሁ፣ ጊዜ ምንድነው ላለኝ ህይወት ነው ስል እመልስለታለሁ። የጊዜ ሽርፍራፊዎች የህይወትን ሙላት ያጎላሉ። የሕይወት ሙላት በጊዜ ሽርፍራፊ የሚጎል ነው። በትካዜ ስንባክን፣ በሀሳብ ስንባዝን ከሕይወት እየጎደልን ነው።
ቀጠሮ ስናረፍድ፣ በማይጠቅሙን ነገሮች ስንጠመድ እየደበዘዝን ነው። የሕይዎት ሙላት የደስታ ባህር ነው። የፍሰሀ ውቅያኖስ፣ የፈንጠዝያ ደሴት ነው። መከራዎቻችን ሁሉ ከሸራረፍናቸው የጊዜ ሽራፊ ውስጥ የወጡ ናቸው፤ ይሄን ሳስብ የሸራረፍኩት የሕይወት ጠባሳ ይታወሰኛል። ይሄን ሳስብ በልጅነቴ ውስጥ፣ በወጣትነቴ ውስጥ የሸረፍኳቸው የጊዜ ሽራፊዎች ይመጡብኛል። ሁሉም ሰው የህይወት ጠባሳ አለው። በጎደለ ቀን፣ ባልሞላ ጊዜ የተገጠበው የህይወት ትውስታ።
ህይወት በጊዜ የተሸመነች የፈጣሪ ድርና ማግ ናት። የህይወት ነጠላ የለውም፤ እግዜር ሲሸምነን በአንድ አይነት ድርና ማግ ነው። ባለጁ በጊዜ ውስጥ እንድናብብ፣ በጊዜ ውስጥ እንድንጠወልግ አድርጎ አበጅቶናል።
ልጅነት የሕይወት ቀለም ነው፤ ወጣትነትን ያስናቀ፣ ጉልምስና የማይደርስበት ባለቀለም የላመ መልክ። እኚህ የሕይወት ቀለም እስከ እድሜአችን አፋፍ ድረስ የሚዘልቁ የሰውነት አውራ ናቸው። ቢሸራረፉም፣ ቢገማመሱም ከነእድፍና ኩነኔአቸው ጸዐዳ ናቸው።
የማለዳ ሀሳቦቼ ከወጣትነቴ አንሰው አያውቁም፤ ከወደፊቴ የተለቁ የህይወቴ ራስ ናቸው። በትላንት ውስጥ የሚያኖሩኝ፣ የልጅነቴን ማምሻና ንጋት የሚያስቃኙኝ መስተዋቴ ናቸው። በተለይ እማዬና አባዬ ያሉበትን የልጅነት ጠዋቴን አልረሳውም።
ከማለዳ ሃሳቦቼ አንዱ፡-
ጠዋት ከእንቅልፌ የሚያነቃኝ አባቴ ነው፤ ከሰፈራችን ከአቶ ታከለ አውራ ዶሮ ጩኸት እኩል ከእንቅልፉ ይነቃል። ከእናቴና ከአባቴ መካከል ነው የምተኛው፤ እንዳይቀሰቅሰኝ ቀስ ብሎ ይነሳና ዛሬም ድረስ በሚገርመኝ አባታዊ ጥንቃቄ በሩን ይከፍትና ነጭ ሀጫ ጋቢውን እስከ ቁርጭምጭሚቱ ድረስ ለብሶ ወደ ውጪ ይወጣል።
የእናቴን አላውቅም፤ እኔ ግን እነቃለሁ፤ አልጋዬ ላይ ትንፋሼን ውጬ ዝም እላለሁ። ወዲያው እናቴ እግሩን ተከትላ ከአባቴ ባልተናነሰ ጥንቃቄ እንዳትቀሰቅሰኝ እየተሳበች ከአልጋው ትወርድና ወደ ማዕድ ቤት ትሄዳለች። ሰፊው አልጋ ላይ ብቻዬን ሆኜ የአባቴን እግዚአብሄራዊ ወንድነት፣ የእናቴን አምላካዊ ሴትነት በማይገባኝ ልጅነታዊ ሀሳብ አስባለሁ።
የአባቴ ዳዊት መድገሚያ ከመኝታ ክፍላችን መስኮት አጠገብ ስለነበር የአባቴን የማለዳ ጸሎት መስማት ግዴታዬ ነበር። በተኛሁበት የአባቴን የሰርክ ጸሎት አደምጣለሁ። የሚለው አይገባኝም፤ ግን እመሰጣለሁ፤ ግን እደመማለሁ። ልጅ ሆኜ አባቴ የእግዚአብሄር ወንድሙ አሊያም ደግሞ አጎቱ አሊያም ደግሞ ጓደኛው ነበር የሚመስለኝ።
ምንም እንኳን ከእንቅልፌ ተነስቼ እንደ አባቴ ባልደግምም ፈጣሪ ግን ከአባቴ እኩል የሚያጸድቀኝ ይመስለኛል። በዚያ ሌሊት የአባቴን ዳዊት እየሰማሁ እናቴ ለቁርስ እስከምትቀሰቅሰኝ ድረስ እጋደማለሁ።
ከማለዳ ሀሳቦች ሌላ..
እናቴ ለእኔ ምን አይነት እናት፣ ለአባቴ ምን አይነት ሚስት እንደሆነች ብጠይቁኝ አላውቀውም። የእናቴ ሴትነት፣ የእናቴ እናትነት፣ የእናቴ ሚስትነት ዛሬም ድረስ ያልደረስኩበት ተፈጥሮ ነው። እናቴ ሴት ብቻ አይደለችም። እናቴ እናት ብቻ አይደለችም። ሚስትም ብቻ አልነበረችም።
እናቴ ለአባዬ ሚስቱ ብቻ አልነበረችም፤ ምንም ነገር ፈልጎ የማያጣበት የጸጋ አድባሩ ናት። አንድ ሴት በአንድ ወንድ ልብ ውስጥ የትም ቦታ ስትገኝ እናቴን ነው ያየሁት።
እስከ ዛሬ ድረስ ብዙ ሴቶችን አውቃለሁ እንደ እናቴ በባላቸው ልብ ውስጥ ሁሉም ቦታ ላይ ሲገኙ አላየሁም። ልጅ ሆኜ እናቴ አንድ ስለመሆኗ ብዙ ጊዜ የተጠራጠርኩበት ጊዜ ነበር። እማ ስላት ሳሎን ወይ ብላኝ ወዲያው እጇ መኝታ ቤት ራሴን ሲዳብሰኝ አገኘዋለሁ። የት ነሽ ስላት ኩሽና ነኝ ብላኝ በማላውቀው ፍጥነት ፊቴ ቆማ አያታለሁ።
ሳሎን፣ መኝታ ቤት፣ እቃ ቤት በአንድ ጊዜ ሁሉም ቦታ እናቴ አለች። ሩቅ ናት ስል ቅርቤ ናት። የለችም ስል አጠገቤ አገኛታለሁ። እዚህ ዓለም ላይ የእናቴን አይነት ሴት በማግባቱ እንደ አባቴ እድለኛ ወንድ ያለ አይመስለኝም። አባቴ በእናቴ የተባረከውን ያህል በምንም አልተባረከም። ለካ ወንድ በሴት ነው የሚባረከው፣ ለካ ባል በሚስቱ ነው ቀን የሚወጣው።
እማዬና አባዬ ያሉበት የልጅነት ጠዋቴ የህይወቴ ምርጡ ጠዋት ነው። የአባዬ ሚስት እማዬ የአብረሀም ሚስት ሳራን ትመስለኛለች። አባዬ ደግሞ አብረሀምን.፤ እኔ ደግሞ ይስሀቅን፤ በእዚህ ሁሉ ውስጥ ካራ አሲዞ ወደ ሞርያ ተራራ ወስዶ ልሰዋህ ቢለኝ እንቢ የምለው አይመስለኝም።
የሕይወቴ ትልቁ ኩራቴ የእናቴ ልጅ መሆኔ ነው። የአባቴን ነፍስ ነጋ ጠባ አነባታለሁ፤ እንደ እማዬ ደስታ በምድር የላትም። የእናቴ ደስታ ምን እንደሆነ ግን ዛሬም ድረስ አልደረስኩበትም፤ እኔና አባዬ እንደሆንን ግን ይሰማኛል። አንዳንድ ነፍሶች በዝምታ ውስጥ የሚስቁ ናቸው፣ አንዳንዶች ደግሞ በጩኸት ውስጥ። የእማዬ ደስታ እንደ ሳራ ደስታ በዝምታ ውስጥ የሚገለጥ ነው። በዝምታ ትወደናለች፣ በዝምታ ታፈቅረናለች። እዚህ ዓለም ላይ የዝምታን ፍቅር እማዬ ብቻ ነው ም ታውቀው።
ካደኩ በኋላ እንደ እማዬ አይነት ሴት ለማግኘት ያልገባሁበት አልነበረም። ልባም ሴት በፍለጋ እንደማትገኝ ሳላወቅ በመልካም ሴት ልብ ውስጥ ልቤን ላሳርፍ ብዙ ደክሜያለሁ። መልካም ሴት በፍለጋ እንደማትገኝ ያወኩት ግን ሳራ ሚስቴ ሆና ወደ ሕይወቴ ከገባች በኋላ ነበር። ሳራና እማዬ የተለያዩ ሴቶች ናቸው። መላዕክና አጋንንት።
ለካ እማዬ ለዚህ ምድር አንድ ሴት ነበረች፤ ከእማዬ በኋላ ምድር ላይ ሌላ መልካም ሴት ዳግመኛ አልተፈጠረችም። የእሷ ልጅ በመሆኔ እኮራለሁ፤ አባዬ ሌሊት ከጋሽ ታከለ ዶሮ ጩኸት ጋር ከእንቅልፉ እየተነሳ ለፈጣሪ ጸሎት የሚያደርሰው እማዬን ስለሰጠው ይሆን እያልኩ ልክ ባልሆንም አስባለሁ፤ ይሆን እንዴ እያልኩ ዛሬ ላይ እንደ ቂል የማለዳ ሀሳቦቼን እመዛለሁ።
ካደኩ በኋላ ሁሉም ገባኝ፤ ፈጣሪ ከአባቴ እኩል እንዳላጸደቀኝ ያወኩት ሳራን ሳገባ ነው። ሳራና እማዬ የሁለት ዓለም ሰዎች ናቸው።
በተለይ እማዬና አባዬ ያሉበትን የልጅነት ጠዋቴን። ያቆነ ካደኩ በኋላ ደግሞ ልጅነቴ በጣም ይናፍቀኛል። የአባዬ ሚስት እማዬ የዘእኔ እናት እማዬ ትመስለኛለች። እንደ እማዬ አይነት ሚስት ብትኖረኝ እላለሁ፤ በልጅነቴ ውስጥ እንደ እማዬ አይነት ሚስት ስመኝ ነው ያደኩት።
እዚህ ምድር ላይ እንደ አባዬ አይነት እድለኛ ወንድ ያለ አይመስለኝም። ሰፈሩ ውስጥ በእማዬ የማይቀና የለም።
በትረ ሙሴ (መልከ ኢትዮጵ)
አዲስ ዘመን ዓርብ መጋቢት 16 ቀን 2014 ዓ.ም