እሁድ መጋቢት 1 ቀን 2011 ዓ.ም ከጥዋቱ ሁለት ሰአት ከ38 ደቂቃ ሲል፤ ከአዲስ አበባ ቦሌ አለም ዓቀፍ አውሮፕላን ማረፊያ ተነስቶ ወደ ኬንያ ዋና ከተማ ናይሮቢ በረራ የጀመረውና ንብረትነቱ የኢትዮጵያ አየር መንገድ የሆነው ቦይንግ 737 ማክስ 8 አውሮፕላን ከስድስት ደቂቃ በኋላ ችግር እንዳጋጠመው ፓይለቱ ሪፖርት ማድረጉንና በዚያው ቅፅበትም ከራዳር ውጭ በመሆን መከስከሱ ይታወቃል:: አውሮፕላኑ በአጠቃላይ ከ35 አገራት የተውጣጡ 149 መንገደኞችንና 8 የበረራ ሰራተኞችን አሳፍሮ የነበረ ሲሆን ሁሉም ተሳፋሪዎችና የበረራ ሰራተኞችም ህይወት ማለፉ ይታወቃል፡፡
አውሮፕላኑ የተከሰከሰው በኦሮሚያ ክልል ቢሾፍቱ ከተማ አቅራቢያ ኤጄሬ በተባለ ስፍራ ሲሆን የአደጋው መንስኤም በመጣራት ላይ ይገኛል፡፡ ይህን ተከትሎ በአለም ዙሪያ አየር መንገዶችና መንግስታት ቦይንግ 737 ማክስ 8 አሜሪካ ሰራሽ አውሮፕላን በአምስት ወር ውስጥ ሁለት ጊዜ የመከስከስ አደጋ የደረሰበት በመሆኑ፤ የተለያዩ ሀገሮችና አየር መንገዶች ማክስ 8 አውሮፕላን በአገራቸው እንዳይበር እገዳ ጥለዋል። በዚህም ቻይና፣ ኢንዶኔዥያና ኢትዮጵያ ሰኞ ዕለት ተመሳሳይ ሞዴል አውሮፕላኖቻቸው እንዳይበሩ አዘዋል። የአርጀንቲናው ኤሮላይነስ፣ የሜክሲኮው ኤሮሜክስኮ እና የብራዚሉ ጎል አየር መንገዶችም በተመሳሳይ በዚሁ አውሮፕላን የሚደረጉ በረራዎችን አቋርጠዋል።
ማክሰኞ እለትም የሲንጋፖር ሲቪል አቬሽን ባለስልጣናት ሁሉንም የተለያዩ የቦይንግ 737 ማክስ አውሮፕላን ሞዴሎች ወደ ሲንጋፖር እና ከሲንጋፖር ወደ ሌላ ቦታ እንዳይበሩ በጊዜያዊነት ከልክለዋል። እንዲሁም የእንግሊዝ ሲቪል አቪዬሽን መሥሪያ ቤት ነገሮችን ከቅርብ ሲቆጣጠር የነበረ ሲሆን፣ የኢትዮጰያ አየር መንገድ አውሮፕላን የደረሰበትን የመከስከስ አደጋ ተከትሎ በቂ መረጃ እስከሚገኝ ድረስ ለጥንቃቄ ሲባል አውሮፕላኖቹን ከማብረርም ሆነ በእንግሊዝ የአየር ክልል እንዳይበሩ አግደዋል። ከነዚህ ሀገሮች በተጨማሪ የግብጽ አየር መንገድ በቦይንግ 737 ማክስ 8 አሜሪካ ሰራሽ አውሮፕላን በአየር ክልሏ ውስጥ እንዳይበር እገዳ ከጣሉ ሀገሮች ተርታ ተሰልፋለች። የግብጽ የሲቪል አቪዬሽን ባለስልጣናት ለሲ.ኤን. ኤን እንደተናገሩት፣ የግብጽ አየር መንገድ የመንገደኞችን ደህንነት ለመጠበቅ ሲል ቦይንግ 737 ማክስ 8 አውሮፕላን በግብጽ አየር ክልል ውስጥ እንዳይበር እገዳ እንደተደረገ ገልጸዋል።
የኢትዮጵያ አየር መንገድ ንብረት የሆነው ማክስ 8 አውሮፕላን የተከሰከሰበት ምክንያቱ በግልጽ ስላልታወቀ ሀገሪቷ በአየር ንብረቷ እንዳይበር አግዳለች ብለዋል። ባለስልጣናቱም አክለው፤ የአብዛኞቹ ሀገሮች አየር መንገዶች ማክስ 8 አውሮፕላን እንዳይበር በሰፊው እገዳ አድርገዋል። የግብጽ ሲቪል አቬሽን ባለስልጣኖችም ስለማክስ 8 አውሮፕላን አስተማማኝነት ከአለም አቀፍ አቪዬሽን ባለስልጣን ጋር በመሆን ጥናት እያደረጉ እንደሆነ ጠቁመው፤ የአውሮፕላኑ የአምራች ኩባንያና የደህንነት ድርጅቶች የሚያወጡትን መረጃ በአትኩሮት እንደሚከታተሉት አክለው ገልጸዋል።
ከትናንት በስቲያ ደግሞ አሜሪካ የቦይንግ 737 ማክስ 8 አውሮፕላኖች እንዳይበሩ እገዳ መጣሏ ታውቋል፡፡ የአሜሪካው ፕሬዚዳንት ዶናልድ ትራምፕ ሁሉም ቦይንግ 737 ማክስ 8 የተሰኙ አውሮፕላኖች ከበረራ አገልግሎት እንዲወጡ አስቸኳይ ትእዛዝ ማሳለፋቸው ተነግሯል። ፕሬዚዳንት ትራምፕ፣ ሁሉም ቦይንግ 737 ማክስ አውሮፕላኖች ከበረራ አገልግሎት እንዲወጡ ያደረገው ለአሜሪካ ህዝብ እና ለሌሎች ህዝቦች ደህንነት ሲባል ነው ብለዋል። ከዚህ ውሳኔ ላይ መድረሳቸውም በስነ ልቦናም ይሁን በሌሎች በርካታ መንገዶች ያለው ጠቀሜታ ከፍተኛ መሆኑንም ነው ፕሬዚዳንት ትራምፕ የገለፁት። ፕሬዚዳንት ትራምፕ አክለውም፣ ሁሉም የአሜሪካ አየር መንገዶችና የአውሮፕላን አብራሪዎች የእገዳው መልእክት እንደደረሳቸው እና አውሮፕላኖቹ በደረሱበት ቦታ እንዲቆሙ ትእዛዝ መተላለፉን አስታውቀዋል።
በዚህም መሰረት የአሜሪካ የፌዴራል አቪዬሽን አስተዳደር ቦይንግ 737 ማክስ የተሰኙ አውሮፕላኖች ላልተወሰነ ጊዜ በአሜሪካ አየር መንገዶች ጥቅም ላይ እንዳይውል እና አውሮፕላኑ በአሜሪካ የአየር ክልል ውስጥ እንዳይበር ትእዛዝ አሳልፏል። የኢትዮጵያ አየር መንገድ ከተከሰከሰበት ስፍራ እና ከሳተላይት ላይ የተገኙ አዳዲስ ማስረጃዎች ላይ በመመስረት ከዚህ ውሳኔ ላይ መደረሱንም የአቪዬሽን አስተዳደሩ አስታውቋል። ሀገራቱ ቦይንግ 737 ማክስ አውሮፕላኖች ከበረራ አገልግሎት እንዲወጡ መወሰናቸውን ተከትሎም ኩባንያው አጣብቂኝ ውስጥ ገብቷል ነው የተባለው።
በሌላ በኩል የናይጀሪያ አየር መንገድ ከዋሽንግተን ቦይንግ አውሮፕላን አምራች ኩባንያ ለመግዛት ያዘዛቸውን አስር ቦይንግ 737 ማክስ 8 ሞዴል አውሮፕላኖችን በስምምነቱ መሰረት ግዢ ለመፈጸም ሆነ ለማቋረጥ ለመወሰን እንደተቸገረ የአየር መንገዱ ቃል አቀባይ ለሲ.ኤን.ኤን ተናግሯል። የናይጀሪያው አየር መንገድ ቃል አቀባይ ክሪስ ኢዋራህ ለሲ.ኤን.ኤን እንደተናገረው፤ አየር መንገዱ ግዢውን ለመፈጸም ከመወሰኑ በፊት አውሮፕላኑ የገጠመውን የመከስከስ አደጋ መንስኤ ምን እንደሆነ ጥናቶችን እየተከታተለ መሆኑን ጠቁመዋል። ቃል አቀባዩ እንዳብራሩት፤ አየር መንገዱ 737 ማክስ 8 ሞዴል አውሮፕላኖቹን ከቦይንግ ኩባንያ ለመግዛት ትዛዝ የሰጠው የኢትዮጰያ አየር መንገድ ንብረት የሆነው አውሮፕላን የመከስከስ አደጋ ከደረሰበት በፊት ነበር። ነገርግን አውሮፕላኑ በአምስት ወራት ውስጥ ሁለት የመከስከስ አደጋ የገጠመው በመሆኑ፤ አየር መንገዱ ትዕዛዙ እንዲዘገይ አድርጓል። እንዲሁም አሁንም ድረስ በአውሮፕላኑ ቅርጽና ቴክኒካል የሆኑ ተያያዥ ጉዳዮች ላይ ከቦይንግ አምራች ኩባንያ ጋር እየተነጋገረ መሆኑን ገልጸዋል። ‹‹እሁድ እለት አደጋው ከመፈጠሩ በፈት 350 ማክስ 8 አውሮፕላኖች በመላው አለም በስራ ላይ ነበሩ።
ነገር ግን አሁን ላይ በአደጋው ምክንያት የተለያዩ ሀገሮች አየር መንገዶችና መንግስታት አውሮፕላኑ እንዳይበር እገዳ ቢጥሉም፤ አደጋው ከመድረሱ በፊት ሌሎች 4ሺ 661 ማክስ 8 አውሮፕላኖችን ለመሸጥ ትእዛዝ እንደነበረው የአሜሪካው ቦይንግ ካምፓኒ ሪፖርት ያሳያል። ስለዚህ ከኩባንያው አውሮፕላኖቹን ለመግዛት የተዋዋልነው የኛ አየር መንገድ ብቻ ሳይሆን የሌሎች ሀገር አየር መንገዶችም ስምምነት ስላላቸው፤ እነሱ የሚወስኑትን ውሳኔ አይተን ግዥውን እንወስናለን። እስከዛውም በኢትዮጵያ አየር መንገድ የደረሰው አደጋ ተጣርቶ ውጤቱ የሚታወቅ ስለሚሆን ነገሮችን ቀድመን ለመወሰን አንቸኩልም›› ብለዋል ቃል አቀባዩ።
ከዚህ በተጨማሪም የኢትዮጵያ አየር መንገድ ዋና ስራ አስፈጻሚ አቶ ተወልደ ገብረ ማርያም ከቢ.ቢ.ሲ ጋር ባደረጉት ቃለ ምልልስ፣ አስተማማኝነታቸው እስኪረጋገጥ አየር መንገዶች ሁሉ ቦይንግ 737 ማክስ 8 አውሮፕላኖችን ለጊዜው መጠቀም እንዲያቆሙ ጥሪያቸውን አስተላልፈዋል። የኢትዮጰያ አየር መንገድና ቦይንግ ለ60 አመታት የዘለቀ የጠበቀ ግንኙነት እንዳላቸው የገለጹት አቶ ተወልደ፤ የአደጋው መንስኤ ገና መጣራት ያለበት ቢሆንም አውሮፕላኑንን ግን ለጊዜው ከአገልግሎት ውጭ ማድረግ ያስፈልጋል ብለዋል። አቶ ተወልደ በምክንያትነት የሚያስቀም ጡት፤ እሁድ እለት የኢትዮጵያ አየር መንገድ ያጋጠመው አደጋ ከአምስት ወራት በፊት በላየን አየር መንገድ ተመሳሳይ አውሮፕላን ቦይንግ 737 ማክስ 8 በኢንዶኔዥያ ጃካርታ ካጋጠመው አደጋ ጋር የሚመሳሰል መሆኑ ነው። ሁለቱም አውሮፕላኖች በተነሱ በጥቂት ደቂቃዎች ውስጥ ነው የተከሰከሱት ብለዋል።
ስራ አስፈጻሚው አክለውም፤ ምንም እንኳ የአሜሪካ ሴናተሮችና የሰራተኛ ማህበራት የአውሮፕላኑ በረራ እንዲታገድ ግፊት ቢያደርጉም፤ የአሜሪካው የፌዴራል ሲቪል አቬየሽን ባለስልጣን ቦይንግ 737 ማክስ 8 ሞዴል አውሮፕላኖች አገልግሎት እንዳይሰጥ የማድረግ ፍላጎት እንደሌላቸው አስታውቀዋል። ምንም እንኳን ቦይንግ 737 ማክስ 8 አሜሪካ ሰራሽ አውሮፕላን በአምስት ወራት ውስጥ ሁለት ጊዜ የመከስከስ አደጋ ደርሶበት በአለም ላይ የተለያዩ ውዝግቦችና ጥርጣሬዎች ቢነሱበትም፤ የአሜሪካ የፌዴራል አየር መንገድ አስተዳደር ግን ቦይንግ 737 ማክስ 8 ሞዴል አውሮፕላን ምንም የደህንነት ስጋት የለበትም፤አውሮፕላኑ ለመብረር ብቁ ነው ሲል ማረጋገጫ የሰጡ ቢሆንም፤ እስካሁን ከ50 የሚበልጡ አገራት በቦይንግ 737 ማክስ 8 አውሮፕላን ላይ እገዳ መጣላቸው ታውቋል:: ይህንንም ተከትሎ የቦይንግ አለማቀፍ የገበያ ድርሻ 12.9 በመቶ መውረዱ ተሰምቷል። በተያያዘም አደጋ የደረሰበት የኢትዮጵያ ቦይንግ 737 ማክስ 8 አውሮፕላን የመረጃ ሳጥን መገኘቱን ተከትሎ የምርመራ ስራው የት ይከናወን ይሆን የሚሉ ጥያቄዎች ሰሞኑን መነጋገሪያ ሆነው የከረሙ ሲሆን ከትናንት በስቲያ ግን ሳጥኑ ወደ ፈረንሳይ እንደሚሄድ ታውቋል፡፡
አዲስ ዘመን መጋቢት 6/2011
በሶሎሞን በየነ