የየካቲት ወር ለኢትዮጵያ ብዙ ታሪክ የተሠራበት ነው። ባለፉት ሳምንታትም ከእነዚህ ታሪካዊ ክስተቶች የተወሰኑትን ተመልክተናል። በዛሬው የሳምንቱን በታሪኩ አምዳችን በ1988 አ.ም ኢትዮጵያን በእብሪት በወረረው የጣልያን ጦር ላይ ኢትዮጵያውያን የካቲት 23 ቀን የተቀዳጁትን ታላቅ ድል የተመለከተ ዘገባ ይዘናል። ይህ ድል ሳምንቱን በሙሉ በተለያዩ መልኮች ሲዘገብ የቆየ ቢሆንም፣ የዓድዋ ድል ብዙ ሊባልለት የሚችል እንደመሆኑ ብዙም ያልታዩ ያልናቸውን መረጃዎች ይዘን ቀርበናል።
እንደሚታወቀው ይህ የዓድዋ ድል በዓል በመላ ኢትዮጵያ በድምቀት ተከብሯል። ዓድዋ ብዙ የተባለለትና ብዙ ሰው የሚያውቀው ቢሆንም፣ ‹‹ዓድዋ ዛሬ ናት ዓድዋ ትናንት›› ስለተባለለት፤ ከታዋቂው የታሪክ ጸሐፊ ጳውሎስ ኞኞ ‹‹አጤ ምኒልክ›› መጽሐፍ፣ ከተክለጻድቅ መኩሪያ ‹‹አፄ ምኒልክና የኢትዮጵያ አንድነት›› መጽሐፍ፣ ከተለያዩ ድረ ገጾች እና የመገናኛ ብዙኃን ባገኘናቸው መረጃዎች ዓድዋን እናስታውሳለን።
የዓድዋ ድል ጀግኖች ኢትዮጵያውያን የዛሬ 126 አመት የካቲት 23 ቀን 1888 አ.ም በዓድዋ ላይ ኢትዮጵያን የወረረውን የጣልያን ሰራዊት ገጥመው ድል ያደረጉበት ቀን ነው። ኢትዮጵያውያን ከመላ ኢትዮጵያ ተውጣጥተው በአንድነት ሆነው ዘመናዊ መሣሪያ የታጠቀውን አውሮፓዊ ኃይል በማሸነፍ ሊደርስባቸው ይችል የነበረውን ቅኝ ግዛት በአጭር ያስቀሩበት፣ በቅኝ ግዛት ውስጥ ለነበሩ የአፍሪካ አገሮችና በመላ ዓለም ለሚኖሩ ጥቁሮች ጭምር ትግል መቀስቀስና መቀጣጠል አስተዋጽኦ ያደረገ ድል ነው።
ጣልያኖች በኢትዮጵያ ላይ ሴራ መጠንሰስ የጀመሩት ከዓድዋ ጦርነት 12 ዓመታት በፊት በፈረንጆቹ የዘመን ቀመር 1884 ነው። የአውሮፓ አገሮች በርሊን ላይ ባደረጉት ስብሰባ አፍሪካን ለመቀራመት ሲወስኑ የጣሊያን ድርሻ ኢትዮጵያ ሆነች። ዳሩ ግን ያሰቡት ሊሳካ አልቻለም።
ኢትዮጵያ በቅድመ ዓድዋ ከወራሪዎችና ከኢምፔሪያሊስት ኃይሎች ጋር ተዋግታም ድል አድርጋለች። ከእነዚህም አንዱ በአጼ ዮሐንስ አራተኛ ዘመነ መንግሥት 1879 ዓ.ም. ዶግዓሊ ላይ በራስ አሉላ አባነጋ አዝማችነት በጣሊያን ላይ ለመጀመሪያ ጊዜ የተቀዳጀችው ድል ነበር። በዚህም የጣሊያን ወታደሮች ለወሬ ነጋሪ ሳይተርፉ ዶግ አመድ ሆነዋል።
በጦርነቱ እንደማይሳካላት ቁርጧን ያወቀችው ጣሊያን እንደገና ደግሞ በውል ለማጭበርበር ሞከረች። ይህም ለዓድዋ ጦርነት ምክንያት ሆነ፤ የውጫሌው ውል። በውሉ በአንቀጽ 17 በጣሊያንኛ ትርጉሙ ኢትዮጵያ የጣሊያን ጥብቅ ግዛት ነች። የውጭ ግንኙነቷም በጣሊያን በኩል ይሆናል የሚለው ሐረግ መዘዝ አመጣ። ኢትዮጵያ ይህማ አይታሰብም አለች፤ ጣልያኖች በኃይል ለማስፈጸም የኢትዮጵያን ግዛት አልፈው መያዝ ጀመሩ። በዚች አንቀጽ ምክንያት ጦርነቱ የማይቀር መሆኑ ተረጋገጠና ዳግማዊ አጼ ምኒልክ ለጦርነቱ የአገራቸውን ሕዝብ ‹‹ክተት›› ጠሩ።
‹‹አሁንም አገር የሚያጠፋ ሃይማኖት የሚለውጥ ጠላት እግዚአብሔር የወሰነልንን ባሕር አልፎ መጥቷል። በእግዚአብሔር ረዳትነት አገሬን አሳልፌ አልሰጠውም። ያገሬ ሰው፣ ጉልበት ያለህ በጉልበትህ እርዳኝ። ጉልበት የሌለህ ለልጅህ፣ ለምሽትህ፣ ለሃይማኖትህ ስትል በኀዘን እርዳኝ፤ ……..›› የሚለውን አዋጅ ተናገሩ።
ኢትዮጵያውያንም ውስጣዊ ችግሮቻቸውንና አለመግ ባባታቸውን ወደጎን ትተው፤ ከሰሜን እስከ ደቡብ፣ ከምሥራቅ እስከ ምዕራብ ተጠራርተው እንደ አንድ ቃል ተናጋሪ፣ እንደ አንድ ልብ መስካሪ ሆነው የመሪያቸውን ጥሪ ተከትለው ወደ ጦር አውድማው ተመሙ።
የዓድዋ ድል 100ኛ ዓመት መታሰቢያ ሲከበር፤ በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ በታተመ የጥናት መድበል ላይ እንደተጻፈው፤ የጦርነቱ አዝማቾች፡- ዳግማዊ አጼ ምኒልክና እቴጌ ጣይቱ፣ ንጉሥ ተክለሃይማኖት፣ ራስ መንገሻ ዮሐንስ፣ ራስ አሉላ አባነጋ፣ ራስ መኰንን፣ ራስ ሚካኤል፣ ራስ ወሌ፣ ራስ ስብሐት፣ ደጃዝማች ሐጎስ ተፈሪ፣ ራስ አባተ፣ ፊታውራሪ ገበየሁ፣ ደጃዝማች ባልቻ ሳፎ (ባልቻ አባ ነፍሶ) እና ዋግ ሹም ጓንጉል ናቸው።
እውቁ የታሪክ ጸሐፊው ተክለ ጻድቅ መኩሪያ እንደገለጹት፤ የኢትዮጵያ ተዋጊዎች የጣሊያንን ወታደር ከበው እየተፏከሩ በጥይትና በጎራዴ ሲደበድቡት የኢጣሊያ ጦር አራት ሰዓት ከተዋጋ በኋላ ሽሽት ጀመረ። በዚህ ጊዜ ኢትዮጵያውያን እየተከታተሉ ሲወጉት፣ የጦር አዝማቹ ጄኔራል አልቤርቶኒ ተቀምጦበት የነበረው በቅሎ ተመቶ ወደቀ። ወዲያው ተነሥቼ አመልጣለሁ ብሎ ለመነሣት ሲጥር ከቅምጡ ሳይነሳ እየተሽቀዳደሙ የሚሮጡት ኢትዮጵያውያን ደርሰው ማረኩት።
የአንደኛው ክፍለ ጦር አዛዡ ተማርኮ፣ ሠራዊቱ በጭራሽ ከጠፋ በኋላ ሁለተኛው ክፍል የጦር ሠራዊት ‹‹ራአዮ›› ከሚባለው ስፍራ ላይ ሆኖ፣ ካራት እስከ ዘጠኝ ሰዓት ድረስ የሦስተኛውን ክፍል የጄኔራል ኤሌናን ጦር ጨምሮ ተዋግቶ በመጨረሻ የጦር አዛዡ ጄኔራል አሪሞንዲ እዚያው እጦርነቱ ላይ ሞቶ ተገኘ።
ከዚህም በኋላ፤ በመጨረሻ ያለው የጣሊያን ጦር በተለይ ማርያም ሸዊቶ ከሚባለው ስፍራ ላይ ተጋጥሞ ከቀድሞው የበለጠ ጦርነት ተደረገ። ይልቁንም የመጨረሻው ድል የሚፈጸምበት በመሆኑ የሁለቱም የጦር ሠራዊት ተደባልቆ በጨበጣ በሚዋጉበት ጊዜ፣ በጨበጣ በሚደረገው ዘመቻ ከኢጣሊያኖች ይልቅ ኢትዮጵያውያን በጎራዴ አነዛዘር ቀልጣፎች ነበሩ።
ይሁን እንጂ ጣሊያኖች ተስፋ በቆረጠ ኃይል እስከ አሥራ ሁለት ሰዓት ድረስ በጉብዝና ሲዋጉ በመጨረሻ አዛዣቸው ጄኔራል ዳቦርሚዳ በጥይት ደረቱን ተመቶ ሞተ።
የጳውሎስ ኞኞ ‹‹አጤ ምኒልክ›› መጽሐፍ በወቅቱ የነበረውን ክስተት፡- ‹‹የተተከለው ድንኳን ሲታይ ከብዛቱ የተነሳ አፍሪካ አውሮፓን ለመጠራረግ የተነሳች ይመስላል። የጦርነቱ ዕለት ኢትዮጵያውያኑ ደማቅ ቀለም ያለው ካባ ለብሰው፣ ጠመንጃና ጦር ይዘው፣ ጎራዴ ታጥቀው፣ የነብርና የአንበሳ ቆዳ ለብሰው፣ አዝማሪዎቹ እየዘፈኑ፣ ቄሶች፣ ልጆች፣ ሴቶች ሳይቀሩ ፀሐይዋ ፈንጠቅ ስትል በተራራው ላይ በታዩ ጊዜ የጣሊያንን ጦር አሸበሩት›› ሲል ገልጾታል።
በወቅቱ በአሥራዎቹ ዕድሜ ውስጥ የነበሩት ፊታውራሪ ተክለሐዋርያት ተክለማርያም በዓድዋው የጦር ግንባር በመሰለፍ ያስተዋሉትን ‹‹ኦውቶ ባዮግራፊ›› በተሰኘው መጽሐፋቸው፡ – ‹‹የሰው ብዛት እንደ ጎርፍ ሆነ። እግረኞችም በቅሎኞችም ተደባልቀን እንርመሰመሳለን። ፈረሰኞች በጎን እያለፉን ይቀድማሉ። ይሮጣሉ! እንደተቻለን እንሽቀዳደማለን።
ጠመንጃ ሲንጣጣ ሰማን፣ መድፍ ወዲያው ያጓራ ጀመር። ተኩሱ እያደር እየባሰበት ተቃረበን፣ አረሮቹ ማፏጨት ጀመሩ። የቆሰሉ ሰዎች ተቀምጠው አገኘን። አያ ታደግ እጁን ተመትቶ ከመንገዱ ዳር ከዛፍ ሥር ተቀምጧል። ገና በሩቁ አይቶን ተጣራ፣ ቁስሉን በመቀነቱ አሰርንለት። ጥለነው እንዳንሄድ ለመነን፣ ፈይሣ ጠመንጃ የለውም፤ የቁስለኛውን ጠመንጃ ተሸከመና እዚያው ቀረ። እኔ ዝም ብዬ ወደ ግንባር አለፍኩ። የማውቀው ሰው አንድም አላጋጠመኝም። ተኩስ ስለበዛ መሮጥ የማይቻል ሆነ። የሰውም ብዛት እንደልብ አያስኬድም።
ደጃዝማች ማናዬ እና ልጅ አስፋው ሁለቱም ቆስለው ድንጋይ ተንተርሰው ተጋድመው አገኘኋቸው። ልጅ አስፋው (በኋላ ፊታውራሪ አስፋው) አወቀኝና ጠቀሰኝ። ዝም ብዬው እንዳላየ ሰው ወደ ግንባር ሮጥኩ። ጦራችን ተደባልቋል። ሰውና ሰው አይተዋወቅም። ሴቶች ገምቦ ውሃ እያዘሉ፣ በበቅሎዎቻቸው እንደተቀመጡ፣ ለቁስለኞች ውሃ ያቀርባሉ። ሲነጋገሩ ሰማኋቸው። «ኧረ በጣይቱ ሞት» ይላሉ። እቴጌ የላኳቸው ይሆናሉ እያልኩ አሰብኩ።
ነጋሪቱ ከግንባርም፣ ከጀርባም፣ ከቀኝም ከግራም ይጎሸማል። የተማረኩ ጣልያኖችን አየሁ። ወዲያው ምርኮኞቹ በዙ፣ አንዳንዶቹ ወታደሮች፣ ይበልጡን ጣልያኖችን እየነዱ መጡ። በኋላ የምርኮኞች ብዛት ለዐይን የሚያሰለች ሆነ፤ ድል ማድረጋችንን አወቅሁ። ጣልያኖች መዋጋታቸውን ትተው ማርኩን እያሉ ይለምናሉ። እንደዚህ የዓድዋ ጦርነት ዕለት አንድ ጥይት እንኳ ሳልተኩስ ጦርነቱ አለቀ።›› ሲሉ በወቅቱ የሆነውን ገልጸውታል።
በዚህ ሁኔታ ነው ታልፎም ነው የዓድዋ ጦርነት በድል የተጠናቀቀው። ክብር ለጀግኖቻችን እና ታሪክን ሰንደው ላቆዩልን ጸሐፊዎች!
ዋለልኝ አየለ
አዲስ ዘመን የካቲት 27/2014