መኖር ማለት ስህተት መሥራት፣ ግን አለመውደቅ ነው፡፡ ከስህተት መማርና ሁልጊዜ ቀና ማለትም እንደሆነ ይገለጻል። በዚህም ሰዎች በሕይወት ጉዟቸው ውስጥ ይህንን እያደረጉ ኑሯቸውን ይገፋሉ፡፡ ወድቀው እየተነሱ ዛሬያቸውን ያድሳሉ፡፡ ለልጆቻቸውም ይህንን እያሳዩ ያልፋሉ፡፡ ማንም ዝም ብሎ ስኬት ላይ አይደርስም። የተቃና ሕይወትም አይኖረውም፡፡ ብዙ በመልፋት ውስጥ ትክክለኛውን መስመር ይይዛል እንጂ፡፡ የህይወት ውጣ ውረድን በድል አሸንፈው ከድል ማማ ላይ የደረሱትን አቶ አዳነ አትርሳው ወደ ድል የሄዱበትን መንገድ አስተማሪ በመሆኑ ለዛሬ የሕይወት ገጽታ አምድ እንግዳችን አድርገናቸዋል። መልካም ንባብ ተመኘን።
የራስ ጥረት የሰራው ልጅ
ተወልደው ያደጉት በምስራቅ ጎጃም ዞን ቢቡኝ ወረዳ ደብረሲና ጉስቋም ቀበሌ ጉርስም በምትባል ቦታ ነው፡፡ ብዙ ጊዜያቸውን አሳልፈውባታል፡፡ ፍየሎችና በጎችን ሲያግዱ አድገውባታል፡፡ ከጓደኞቻቸው ጋር የቦረቁባትና ከማህበረሰቡ መልካም የሚባሉ ባህሪያትን የወረሱባት ስፍራም ናት፡፡ ከዚያም ሁለተኛው የልጅነት ቆይታቸውን ወዳሳለፉባት ምስራቅ ወለጋ ሄዱ፡፡ በዚህም ከአባታቸው ጋር በመኖር የተለያዩ ተግባራትን ወደ ማከናወኑ ገቡ፡፡ ለዓመታት በቦታው ሲቆዩም ቤተሰብን በማገዙ ዙሪያ እንደቀደመው ጊዜ ዋና ስራቸው ከብት መጠበቅ ብቻ ነበር፡፡ በዚህም ደስተኛ ሆነው ልጅነታቸውን አጣጥመዋል፡፡
ከከብት ጥበቃው ጎን ለጎን የንግድ ሥራንም አቶ አያሌው ከሚባሉ በዚህ ስፍራ ያገኙዋቸው ቤተሰባቸው ዘንድ ተምረዋልና የልጅነት ህልማቸውን እንዲያገኙት ሆኑ፡፡ ይህም ነጋዴ መሆን ሲሆን፤ በተለይ አርሶ አደሩን ከችግር የሚያላቅቅ ሥራ ቢሰሩ ምርጫቸው ነበር፡፡ ውጤታማ እንደሚያደርጋቸውም ያምናሉ፡፡ በዚህም ለዓመታት እያሰቡትና እየሠሩበት እንደቆዩ ያስታውሳሉ፡፡
አቶ አዳነ በልጅነታቸው ጭምትና ነገሮችን በመልካም ጎኑ የሚመለከቱ ናቸው፡፡ ከሰዎች ጋር መጣላትን አምርረው ይጠላሉም፡፡ የተቸገረ ሰው ሲያዩ የማያስችላቸውና ያላቸውን ዘርግፈው የመስጠት ባህል ያዳበሩ ልጅም ነበሩ፡፡ ዛሬም ቢሆን ይህ ባህሪያቸው እንዳለ ይናገራሉ፡፡ ዛሬ ላለሁበት አስተሳሰብም ይህ መመሪያ ሆኖኛልም ይላሉ፡፡ ያሳደጋቸው ማህበረሰብ ትልቅ ሚና እንደነበረውና በተለይም መልካምነትና፣ ለተሻለ ነገር መትጋትን እንደተማሩበት ያነሳሉ፡፡
ሌላው ልጅነታቸው ላይ ጥሩ አሻራ ነበራቸው የሚሏት አክስታቸውን ነው፡፡ እርሷ በተለይም የከተማ ሕይወትን እንዴት መኖር እንደሚቻልና ከልጅነት ወደ ወጣትነት እንዴት መሸጋገር እንዳለባቸው በሚገባ አስተምራቸዋለች። መስመር የያዘ መንገድ ቀያሻቸውም ናት፡፡ በዚህም ዘወትር ያመሰግኗታል። ለቤተሰቦቻቸውም ቢሆን እንዲሁ ምስጋናቸውን ይቸራሉ፡፡
ተቆራራጩ ትምህርት
የትምህርት «ሀሁ»ን የጀመሩት ካደጉ በኋላ ማለትም በ14 ዓመታቸው ነው፡፡ በወቅቱ ከስራቸው እንዲርቁቸው ባለመፈለጋቸው ትምህርት ቤት አላስገቧቸውም፡፡ እንደውም ከአባታቸው ጋር ወደ ምስራቅ ወለጋ ባይሄዱ ኖሮ መማር አይችሉም ነበር፡፡ በእርግጥ እዚያም አይደለም ትምህርታቸው የተጀመረው፡፡ በራሳቸው ጥረት እየሠሩ ለመማር ምስራቅ ጎጃም ከተመለሱ በኋላ ነው፡፡ ይህም መጻፍና ማንበብ ስለሚችሉ ሦስተኛ ክፍል በመግባት ከዘመናዊ ትምህርት ጋር ተዋውቀዋል፡፡
የመጀመሪያ ደረጃ ትምህርታቸውን የጀመሩት በወይን ውሃ የመጀመሪያ ደረጃ ትምህርት ቤት ሲሆን፤ በዚህ ትምህርት ቤትም እስከ አራተኛ ክፍል ያለውን ትምህርታቸውን ለመከታታል በቅተዋል፡፡ ወደ አምስተኛ ክፍል ሲዛወሩ ግን ትምህርቱ ተቋረጠ፡፡ ምክንያቱም ወደ አዲስ አበባ ሄደው ሳይመለሱ በሄዱበት አዲስ አበባ ዓመት ያህል በመቆየታቸው ነበር፡፡ ስለዚህም ዳግም ትምህርቱን የተቀላቀሉት ከዓመት በኋላ ሲሆን፤ አሁንም በወይን ውሃ የመጀመሪያ ደረጃ ትምህርት ቤት ተምረዋል፡፡ ግን ይህም ቢሆን እስከ ስድስተኛ ክፍል ብቻ ነበር፡፡
ከስድስት ወደ ሰባተኛ ክፍል ቢዛወሩም ወደ ደብረማርቆስ ከተማ ሄደው መሥራት በመፈለጋቸው ምክንያት መማር ያልቻሉት ባለታሪካችን፤ ከዓመታት ቆይታ በኋላም በእስር ላይ ሳሉ ነበር የሰባተኛ እና ስምንተኛ ክፍል ትምህርታቸውን እንዲማሩ የሆኑት፡፡ ይህም በሁለት ቦታ ላይ የተከታተሉት ሲሆን፤ ቃሊቲ ማረሚያ ቤት ሰባተኛን፣ ዝዋይ ማረሚያ ቤት ደግሞ ስምንተኛ ክፍልን ተምረዋል፡፡ በተመሳሳይ በዝዋይ ቴክኒክና ሙያ ማሰልጠኛ በእንጨት ሥራ ትምህርት ሰርተፊኬት አግኝተዋል፡፡ በእርግጥ ከዚያም በፊት የእንጨት ሙያን አዲስ አበባ አክስታቸው ጋር ሳሉ “ሰንቦ” የሚባል እንጨት ቤት በመግባት ሰልጥነው ሙያውን አውቀውታል፡፡
ከእስር ከተለቀቁ በኋላ ደግሞ ከሥራቸው ጎን ለጎን የማንዴላ የርቀት ትምህርትን በመቀላቀል የመደበኛውን ትምህርት መከታተል ችለዋል፡፡ በዚህም ዘጠነኛና አስረኛ ክፍልን እንዲያጠናቅቁ ሆነዋል፡፡ ከዚያ በኋላ ያለው የትምህርት ጉዟቸው የተለያዩ ስልጠናዎችን በመውሰድ ላይ ያተኮሩ ናቸው፡፡ በተለይም ሙያዬን ያዳብርልኛል የሚሉትን ትምህርት በፍጹም መተው አይፈልጉም፡፡ ከእነዚህ መካከል የኮምፒውተር ስልጠና አንዱ ነው፡፡
እድገት ከሸቀጥ ሱቅ ወደ ፋብሪካ
አቶ አዳነ ከሥራ ጋር የተዋወቁት ራሳቸውን በራሳቸው ሲያግዙ ባደረጉት ጥረት ነው፡፡ ይህም አባታቸው የሰጡዋቸውን መሬትና እህል ሸጠው ባገኙት ገንዘብ ወደ ምስራቅ ጎጃም ተመልሰው የሸቀጣሸቀጥ ሱቅ ከፍተው የሠሩት ነው፡፡ ከዓመታት ቆይታ በኋላ ደግሞ በእንጨት ሥራ ላይ ተሰማሩ፡፡ ውጤታማም ሆነውበታል፡፡ ምክንያቱም ከአዲስ አበባ ምስራቅ ጎጃምን መርጠው የተመለሱት በሁለት ምክንያት ነው፡፡ የመጀመሪያ ግብዓትን በቀላሉ ማግኘት መቻላቸው ሲሆን፤ ሁለተኛው ሥራው ስለማይታወቅ ማህበረሰቡንም ሆነ ራሳቸውን በቀላሉ ማገልገልና መጥቀም ይችሉበታልና ነው። በዚህም ከትምህርት ቤት ወንበር ጀምሮ እስከ ቢሮ እቃዎች ድረስ ይሠራሉ፡፡ ትርፋማም ናቸው፡፡
አቶ አዳነ በአካባቢያቸው ያልተለመዱ ነገሮችን የመሥራት ልምድ አላቸው፡፡ ከእንጨት ቤቱ በተጨማሪ ፎቶ ቤት የከፈቱ ሲሆን፤ በዚህም በከፍተኛ ደረጃ ተጠቃሚ መሆን ችለዋል፡፡ ቀጥለው ቦታው የበለጠ ያዋጣኛል ወደ’ሚሉት ደብረማርቆስ ሮብ ገበያ አቀኑ፡፡ የእንጨት ሥራውንም መሥራት ጀመሩ፡፡ ግን ያሰቡትን ያህል አልሆነላቸውም፡፡ በዚህም ብዙ ሳይቆዩ ትተውት አዲስ አበባ ገቡ፡፡ በዚያም የተለያዩ ሥራዎችን ማከናወን ጀመሩ፡፡ ቋሚ ቦታ ባይኖራቸውም አልባሳትን በጅምላ እየተረከቡ ማስረከባቸው እንዲሁም የእንጨት ሥራው ላይ መሰማራታቸው አንዱ ነበር፡፡ ጥሩ ገንዘብ የያዙበት እንደነበርም አይረሱትም፡፡
ገንዘብ መያዛቸው ከወጣትነታቸው ጋር ተዳምሮ ችግር ውስጥ ከቷቸው እንደነበር የሚያነሱት ባለታሪካችን፤ ወደ ውጪ እንላክህ በሚል ተጭበረብረው ነበር፡፡ ብራቸውን በእምነት በመስጠታቸው ብዙ ስቃይም ደርሶባቸዋል፡፡ መጀመሪያ የተተዋወቋት ሴት የውሸት ስም በመያዝ ከፍተኛ ገንዘብ ኪሳራ አደረሰችባቸው፡፡ ይህን ተከትሎ ገንዘቤ ተወሰደ በማለት ክስ አቀረቡ፡፡ ክስ በማቅረባቸውም ምክንያት ለምን ከሰስክ ተብለው ለወራት ያህል በጨለማ ውስጥ ሆነው ተገረፉ። ከፍተኛ በደልም ተፈጸመባቸው፡፡
ፖለቲከኛ ለማድረግም ያልሞከሩት ነገር የለም፡፡ በተለይም በወቅቱ በመፈንቅለ መንግስት ሙከራ በሚል ከአካባቢያቸው የመጡ ሰዎች በእስር ላይ ነበሩና የእነርሱ ደጋፊ መሆናቸውን እንዲናገሩላቸው፤ ከእነርሱ ተልከው እንደመጡ እንዲያስረዱላቸውና ግንኙነት እንዳላቸው እንዲናገሩላቸው ያስገድዷቸው ነበር፡፡ ለሁለት ወር ያህልም ፍርድቤት አላቀረቧቸውም፡፡ ግን እርሳቸው ምንም ነገር ሊያደርጉላቸው ፈቃደኛ አልሆኑም፡፡ በዚህም ከመገረፉም በላይ እስሩ እንዲጸናባቸው ብዙ ሸር እና ደባዎችን ፈጸሙባቸው፡፡
ክስ የመሰረቱባትን ሴት ለምን ከሰስክ በሚል በስም ማጥፋት ክስ እንዲመሰረትባቸው አደረጉ፡፡ በዚህም አራት ዓመትና ሦስት ሺህ ብር ተቀጡ፡፡ ቃሊቲና ዝዋይ ማረሚያ ቤትም ባላጠፉት ጥፋት ለዓመታት ተሰቃዩ፡፡ ከእስር በኋላም ቢሆን ይህ ጠባሳ አለቀቃቸውም ነበር፡፡ ምክንያቱም ማረሚያ ቤት መቆየታቸው የብዙዎችን ምልከታ ቀይሯል፡፡ ራሳቸውም ቢሆኑ ያለጥፋታቸው መታሰራቸው አበሳጭቷቸዋል፡፡ በዚህም ማንንም ማግኘት ስለማይፈልጉ መኖሪያቸውንም ማደሪያቸውንም ጎዳና አደረጉ፡፡
ጓደኞቻቸው አቀባበል ሊያደርጉላቸው ፈልገው ነበር፤ ሆቴልም ተከራይተውላቸዋል፡፡ ግን ሊያገኙዋቸው አልፈለጉም። በዚህም የወጡበትን የመጀመሪያ ቀን ከጎዳና ተዳዳሪዎች ጋር አሳልፈዋል፡፡ በማግስቱ ግን በዚያ መቆየት አልቻሉም፡፡ ስቃዩ በእርሳቸው ደረጃ አይመከትም፡፡ ስለዚህም ወደ ተያዘላቸው ሆቴል አመሩ፡፡ የተከፈለላቸውን ቀንም ጨረሱ፡፡ ከዚያ በኋላ ግን የት እንደሚያርፉ ግራ ተጋቡ፡፡ ግን ለነገሮች ፈጣን ምላሽ መስጠትን ያውቃሉና ሌላ አማራጭ ወደ መፈለጉ ገቡ፡፡ ከአንድ ጓደኛቸው ጋር በመዳበል የእለት ጉርሳቸውን እየሞሉ መኖር ጀመሩ፡፡
ቤቱን ለመሙላትና የቤት ኪራይ ለመክፈል የእንጨት ሥራ ላይ የተሰማሩ ሲሆን፤ ዘላቂ ግን አልነበረም፡፡ በዚያ ላይ ቤት አከራያቸው ይረብሿቸዋል፤ በቤታቸው የሚበላም የሚጠጣም ብዙ አይኖርም፡፡ ስለዚህም ልጁንም አብሬ ከማሰቃየው በሚል የከበዳቸውን የአንድ ቀን አዳር መዋያቸው ማደሪያቸው ለማድረግ ወደ ጎዳና ወጡ፡፡ ይህንን ግን ማንም አያውቅም ነበር፡፡ ምክንያቱም ራሳቸውን ጠብቀው ይንቀሳቀሳሉ፡፡ ከወር በላይም ስቃዩን በውስጣቸው አድርገው ሲቆዩም ማንም ምንም ብሏቸው አያውቅም፡፡
ከጎዳና ሕይወት እንዲወጡ ያደረጋቸው የእጅ ሙያ ባለቤት መሆናቸውና ከሰዎች ጋር በስፋት መቀራረባቸው ሲሆን፤ ያገለገሉ እቃዎችን ከአንዱ በመረከብ ለቋሚ ተረካቢዎች በማስረከብ እንዲሠሩ ሆነዋል፡፡ ጎን ለጎንም የእንጨት ሥራውን ማከናወን ችለዋል፡፡ ይህ ደግሞ ዳግም የገቢ ምንጫቸውን የሚያሳድጉበትን እድል ሰጥቷቸዋል፡፡ ሕይወታቸው ወደ ነበረበት የተመለሰውም ከዚህ በኋላ ነው፡፡
የገቢያቸው ምንጭ ማደጉና ገንዘብ መያዛቸው በፊት ይሰሩበት ወደ ነበረው ምስራቅ ጎጃም ሞጣ ላይ እንዲጓዙና የተሻለ ነገር እንዲሰሩም አግዟቸዋል፡፡ ከከተማ አስተዳደሩ የመኖሪያ ቦታ ተረክበው ነበርና ቤት ሠሩ፡፡ ይህ ደግሞ የኢትዮጵያ ልማት ባንክ ባመቻቸው የብድር እድልም ተጠቃሚ እንዲሆኑ አገዛቸው፡፡ ምክንያቱም የሚያሲዙት ገንዘብ ሲጠየቁ ቤቱ ደርሶላቸው እቅዳቸውን አሳክተውበታልና ነው፡፡ በብድሩ የሠሩት የጠጠር ማምረቻ ፋብሪካ ሲሆን፤ ለእርሳቸው ብቻ ሳይሆን ለበርካቶች የሥራ እድል የፈጠረ ነበር፡፡
እንግዳችን ሥራ በቃኝ የማያውቁ ናቸው፡፡ በዚህም ለፋብሪካው የተበደሩትን የግለሰቦችን ብድር ከመለሱ ከዓመት በኋላ ሌላ ፋብሪካ ጀመሩ፡፡ ይህም በሙያ የሰለጠኑበትና የተካኑበት የእንጨት ሥራ ሲሆን፤ እቅዳቸውን በብዙ መልኩ ያሳኩበት ነው፡፡ ምክንያቱም ከሀሳቡ ጥንስስ ጀምሮ ብዙ ነገር በፈለጉት መንገድ ሄዶላቸዋል፡፡ የመጀመሪያው የከተማ አስተዳደሩ በኢንደስትሪ መንደር ውስጥ በሺህዎች የሚቆጠር ካሬ ሜትር መስጠቱ ሲሆን፤ የደን ውጤቶች ማቀነባበሪያ ፋብሪካን ሁለት ዓመት ባልሞላ ጊዜ ውስጥ ግንባታውን ማጠናቀቃቸው ሌላው ስኬታቸው ነበር፡፡ አሁን የማሽን ተከላ ሥራውን ለማከናወን ለልማት ባንክ የፋይናንስ ጥያቄ አቅርበው በመጠባበቅ ላይ ይገኛሉ።
ፋብሪካው ወደ ሥራ ሲገባም በትንሹ በቀን ባለ 18 ሴንቲ ሜትር ውፍረት ያለው አምስት ሺህ ፍሬ ኤም ዲ ኤፍ የማምረት አቅም ይኖረዋል፡፡ በዓመት 40 ሺህ ሜትር ኪዩብ የደን ውጤቶችን ማቀነባበር ያስችላል። ከዚህ ደግሞ አገሪቱ ከውጭ የምታስገባውን ከ20 እስከ 30 በመቶ የሚደርስ የኤም ዲ ኤፍ ፍጆታ በአገር ውስጥ ምርት እንድትሸፍን ትሆናለች፡፡ ከሁሉም በላይ በሺዎች የሚቆጠሩ ዜጎች የሥራ እድል ያገኙበታል፡፡ በዚህም ደስተኛ ናቸው፡፡
እንግዳችን፤ የጠቅላላ ሥራ ተቋራጭ ፈቃድ አውጥተውም ይሠራሉ፡፡ በእርሳቸውና በባለቤታቸው ሽርክና የጣውላ ማለስለሻና መሰንጠቂያ ፋብሪካ አላቸው፡፡ ሞጣ ላይ ፎቅ ሰርተው እየተጠቀሙበት ይገኛሉ፡፡ በርከት ያሉ መኪኖችም ባለቤት ስለሆኑ የገቢ ምንጫቸውን በተለያየ መንገድ አስፍተዋል፡፡ ይህም ሆኖ ገና ብዙ ያላሳካሁት ነገር አለ ባይ ናቸው፡፡ ከእነዚህ መካከል የመጀመሪያው የጅብሰም ፋብሪካና የበሬ ማድለቢያና የወተት ተዋጽኦዎችን ማቀነባበሪያ ፋብሪካ መክፈት ሲሆን፤ 20 ሺህ ካሬ ሜትር ቦታ ስለተረከቡ የጀመሩት ሥራ ሲጠናቀቅ ወደዚህ ይገባሉ፡፡
ሌላው በጎዳና የሚኖሩ ሰዎችን ሊያነሳ የሚችል ፕሮጀክት ላይ መሰማራት ሲሆን፤ የእኛን አገር ችግር ባንቀርፈውም የቻልኩትን ያህል ሰው ከጎዳና ለማንሳት እጥራለሁ ብለውናል። እንደሚሳካላቸው ያምናሉ፡፡ እንደውም አሁን በቅርቡ ይጠናቀቃል ባሉን ኤም ዲ ኤፍ ፋብሪካው አካል ጉዳተኛው ቅድሚያ እንዲሰጠው የሚያደርጉበት ዘርፍ መኖሩን አጫውተውናል፡፡ ለአብነትም ያነሷቸው አይሲቲ ክፍሉና ሕግ ክፍሉ በዋናነት ይጠቀሳሉ፡፡ ምክንያታቸውን ሲያስረዱ ለመጻፍ እጅ እንጂ እግር አያስፈልግም፤ ጠበቃ ለመሆን አዕምሮ እንጂ ዓይን ፋይዳው የጎላ አይደለም፡፡ ስለሆነም አካል ጉዳታቸው እየታየ እርሳቸውንም ሆነ ራሳቸውን እንዲያገለግሉ እንደሚያደርጉ አጫውተውናል፡፡
ጎዳና በጎዳና አዳሪው ዕይታ
ማረሚያ ቤት በቆዩበት ጊዜ ሁል ጊዜ መብራት ብቻ ያያሉ፡፡ ይህ ደግሞ መምሸቱንና መንጋቱን እስከመርሳት አድርሷቸዋል፡፡ በዚህም ጨለማን የማየት ጉጉት አደረባቸው። ስለዚህም በጓደኞቻቸው ሆቴል ቢያዝላቸውም ለአንድ ቀን አልተኙበትም ነበር፡፡ ጎዳና ላይ በማደር ሌሊቱን አሳለፉ። በሚቀጥለው ቀን ግን አልደገሙትም፡፡ ምክንያቱም ያለው ሌሊቱን ቢያሳያቸውም ቅዝቃዜና ሽታውን ግን መቋቋም ተሳናቸው፡፡ በዚህም ጊዜ ሳይፈጁ ወደ ተያዘላቸው ሆቴል ገቡ፡፡ ይህም ቢሆን ብዙ ቀን የቆዩበት አልነበረም፡፡ ስለዚህ ለተወሰኑ ወራት ከጓደኛቸው ጋር ከቆዩ በኋላ ጎዳና የወጡትም ለዚህ ነው፡፡ በእርግጥ የጎዳናው ሕይወት ለእርሳቸው የስቃይ ቦታ አልነበረም፡፡ ምክር ቤትና ትምህርት ቤት እንጂ፡፡
ብዙዎች በተለያየ ምክንያት ቢሰቃዩበትም ለእርሳቸው ግን ፍቅር፣ ነጻነት፣ ማህበራዊነትና እርስ በእርስ መግባባትን ያገኙበት ነው፡፡ ዛሬ ድረስ የሚጠቀሙበትን መርህም ያገኙትም ከዚህ ቦታ ነው፡፡ በዚህም ብዙ ነገር ከእነርሱ ለማግኘት አዲስ አበባ ሲመጡ ከእነርሱ ጋር ያድራሉ፡፡ ደስተኛ ሌሊትም ያሳልፋሉ፡፡ ሰዎች ይህንን ልምዳቸው ቢያደርጉ ብዙ የሚጠቀሙት ነገር እንዳለም ይመክራሉ፡፡
እንግዳችን ጎዳና ላይ ያሉ ልጆች በፍቅር ቢታከሙ አገርን ብቻ ሳይሆን ግለሰቦችን ጭምር በብዙ መልኩ ይጠቅማሉ። ምክንያቱም ወደ ጎዳና ሕይወት የገቡት በአጋጣሚ እንጂ ወደውት አይደለም፡፡ ስለዚህም ነገ እነርሱም ጎዳና ተዳዳሪ እንደማይሆኑ ማስተማመኛ የላቸውምና ሰዎች እነርሱን ሲያስቡ ራሳቸውን ማካተትም ይኖርባቸዋል፡፡ ጎዳና የወለደው አንድም ሰው እንደሌለና ለጎዳና ተብሎ የተወለደም አለመኖሩን መረዳት አለባቸው፡፡ ሁሉም ከሰው ሆድ የወጣና በፍቅር ከተያዘ ሊለወጥ የሚችል መሆኑንም ሊገነዘቡ ይገባልም ይላሉ፡፡ ምክንያቱም እርሳቸው የጎዳና ሕይወትን የተቀላቀሉት በድንገት ስለሆነ፡፡
ሁኔታውን ሲያስረዱ በሁለት ምክንያቶች መሆናቸውን ይናገራሉ፡፡ የመጀመሪያው ለዓመታት ከቤተሰብና ከማህበረሰብ በመገለላቸው ከእነርሱ ጋር አብሮ ለመሆን መቸገራቸው ሲሆን፤ ሁለተኛው የቤተሰብ ለምን ታሰረ የሚል ጥያቄ ነው። በዚህም ነጻነትን ፍለጋ ጎዳናን ቤቴ ብለው ከወር በላይ አሳለፉ። በዚህ ቆይታቸው ጊዜም ብዙ መልካም ልምዶችን ቀሰሙ፡፡ አመለካከታቸው ጭምር የተቀየረበትን ልምድ አዳበሩ፡፡ በዚህም ‹‹ለእኔ የሰው ልጅ ሀብት ነው፡፡ በተለይ ጎዳና ላይ ያሉት፡፡ ምክንያቱም ባሰማራናቸው ቦታ ሁሉ ሠርተው እንዲያልፍልን ያደርጉናል፡፡ አንፈልጋቸውም፤ አይለወጡም ብለናቸውም በብሩህ አዕምሯቸው ያሸንፉናል፡፡ አይችሉም ተብሎ በመታሰቡ ከሱስ ሳይወጡ ጊዜቸውን በአልባሌ ነገር ቢያሳልፉም ግን በፍቅር ሲታከሙ በብዙ መልኩ በልጠውን ይገኛሉ፡፡›› እንዲሉ ሆነዋል፡፡
ጎዳና የወጡ ልጆች እድሜያቸው ለመቀየር (ለመለወጥ) የጠነከረ አይደለም፡፡ ሰው ወስዶ ቢያሳድጋቸውም የጎዳና ልጅ ባይላቸው አቅማቸውን ሙሉ ተጠቅመው ብዙዎችን ከችግር ከመታደጋቸውም በላይ ለራሳቸውም ሆነ ለአገር የሚያበረክቱት ቀላል እንደማይሆን ያነሱት አቶ አዳነ፤ የጎዳና ላይ ተዳዳሪዎችን ባለተገባ መልኩ ማየት ነውርም ሀጢያትም ነው ይላሉ፡፡ ዛሬ ቀና ልናደርጋቸው ካልቻልን ተጠያቂዎች ብቻ ሳንሆን ዋጋ እንከፍላለን፡፡ ስለሆነም ከመቀጣት ለመዳን ልባችንንም በራችንንም መክፈት አለብን ሲሉ ይመክራሉ፡፡
የሕልውናው ዘመቻ ሕላዊነት
በችግር ጊዜ መድረስን የመሰለ ነገር እንደሌለ ማንም ይረዳዋል፡፡ በተለይ ለአገር ሲሆን ልዩ ጣዕም አለው፡፡ ይህንን ደግሞ የሚነግሩን ያደረጉ ናቸው፡፡ ከእነዚህ መካከል አቶ አዳነ አንዱ ሲሆኑ፤ አሁን ኢትዮጵያ በገባችበት የሕልውና ዘመቻ ላይ ያላደረጉት ነገር የለም፡፡ ብዙዎችን ከወደቁበት አንስተዋል። ብዙዎችንም ህክምና እንዲያገኙ አድርገዋል፤ የታረዙትን አልብሰዋል፣ የተጠሙትን አጠጥተዋል፡፡ ብዙዎችን መግበዋል። የሕልውናው ዘመቻ በሚጠይቀው ሁሉ ተሳትፈዋል፡፡
ይህ ቀንና ጊዜ ለእርሳቸው ልዩ ትርጉም እንዳለው ያውቃሉ። በዚህም አንድም ቀን ሳይሠሩበትና ሰዎችን ከችግራቸው ሳይታደጉበት እንዲያልፋቸው አይፈቅዱም፡፡ የህልውና ዘመቻው ሲጀመር ጀምሮም በብዙ መልኩ የማገዛቸው ምስጢር ይኸው ነው፡፡ ለጥምር ኃይሉ የሚያስፈልገውን ግንባር ድረስ በመሄድ ደግፈዋል፤ ስልጠና የሚሰጥበትን መንገድ አሳልጠዋል፤ ተፈናቃዮችም ድጋፍ የሚያገኙበትን መንገድ ከራሳቸው አልፈው ለሌሎችም አመቻችተዋል፡፡ አሁን በሚደረገው የመልሶ ግንባታ ሥራ ላይም ይሳተፋሉ። የህብረተሰቡን ችግር በአቅማቸው ይፈታልኛል የሚሉትን ተግባር ይፈጽማሉ፡፡ ለአብነት በሰሜን ወሎ ከተፈናቀሉና በመጠለያ ውስጥ ከሚገኙ ተማሪዎች ውስጥ አምስት ልጆችን ዞኑ እንዲሰጣቸው በማድረግ ማስተማር መጀመራቸው አንዱ ነው፡፡
ከወሰዷቸው ተማሪዎች ውስጥ ሦስቱ የ12ኛ ክፍል ተማሪዎች ሲሆኑ፤ ሁለቱ ደግሞ 10 እና 11ኛ ክፍል ናቸው። እንደ ልጆቻቸው አድርገው እየተንከባከቧቸውም ይገኛሉ፡፡ ሲያስተምሩዋቸውም ከስነ-ልቦና ጫና ውስጥ የሚወጡበትን ጭምር በማመቻቸት ነው፡፡ ለትምህርታቸው ብቻ ትኩረት እንዲሰጡ የሚያስችሉትን ሁሉ ያደርጉላቸዋል፡፡ በተለይም ከነበሩበት ሁኔታ እንዲወጡ ሰራተኛ ጭምር ቀጥረውላቸው እንክብካቤ በማድረግ ላይ ናቸው፡፡ ወደ ትልልቅ ተቋማትም እየወሰዱ የምክር አገልግሎት እንዲያገኙ ያግዟቸዋል፡፡ ቤተሰባዊነት እንዲሰማቸውም በቅርበት ይከታተሏቸዋል፡፡
በእርሳቸው እምነት ሥራም ሆነ ሕይወት የሚኖረው ሰላም ሲኖር ብቻ ነው፡፡ በዚህም ሰላም ማስፈን ውዴታ ሳይሆን ግዴታ ነው፡፡ በተለይ ባለሀብቱና ተሰሚነት ያለው አካል እጁን አጣጥፎ ከተቀመጠ ወደ ፊት የሚከፍለው ዋጋ ቀላል አይደለም፡፡ እናም ዛሬ ላይ ለተቸገረ ደራሽነቱን ማሳየት አለበት፡፡ እርሳቸውም እያደረጉት ያለው ይህንኑ ነው፡፡ መደበኛ ሥራቸውን እስከመተው ደርሰውም እስከ ሕይወት ፍጻሚያቸው እንደሚያገለግሉ ይናገራሉ፤ ባደረጉት ነገር አይቆጩምም፡፡
የሕይወት ፍልስፍና
ሀብት በብቻ ልፋት የሚመጣ ሳይሆን በበርካቶች ገንዘብ፣ ጉልበትና እውቀት መዋጮ የሚፈጠር ነው፡፡ ስለዚህም ሀብታሞች ብቻዬን ጥሬ ግሬ እዚህ ላይ ደረስኩ የሚያስብላቸው ሀብት የላቸውም፡፡ በዚህም ሀብቱን በወረሰው ስም ሊመዘገብ ይችላል እንጂ ሥራው የሕዝብ ነው፡፡ ውጤቱም በበርካቶች የተከናወነ ስለሆነ የሕዝብ መሆን ይኖርበታል የሚለው የመጀመሪያ ፍልስፍናቸው ነው፡፡
ሕይወት የምትጣፍጠው ለሰዎች መኖር ሲቻል ነው የሚለው ሌላው መርሃቸው ነው፡፡ ይህንን ሲያደርጉ ሀብታቸው እንደሚበረክት፣ ኑሯቸው እንደሚቃናና ተስፋ ቸው እንደሚለመልም ያምናሉ፡፡ አዳዲስ የሥራ ፈጠራ መንገዶችን ለማየት እንደሚችሉበትም ያስባሉ፡፡ ምክንያቱም በሕይወታቸው እየተፈጸመ ያለ በመሆኑ ይከተሉታል፡፡
መልዕክት
አገራችን አሁን በብዙ ነገር እየተፈተነች ነው፡፡ በዚህም ሁሉም የቻለውን እያደረገ ወደ ነበረችበት መመለስ አለበት። አሁን ላይ በብዙ መንገድ በብዙዎች መስዋዕትነት ነገሮች እየተቀየሩ ናቸው፤ ግን ማጠናከርን ይጠይቃል፡፡ ሥራችንም ሆነ አበርክቷችን በቂ አይደለም፡፡ ስለዚህ ማንኛውም ሰው በተለይ ባለሃብቱ ተደራጅቶ ለሰው መኖር መቻል አለበት፡፡ ሀብቱ የእርሱ ብቻ እንዳልሆነ ማወቅና ማገዝ ላይም ማተኮር ይገበዋል የሚለው የመጀመሪያው መልዕክታቸው ነው፡፡
ከእያንዳንዱ ባለሀብት ጀርባ በብዙ መንገድ ያገዙ ዜጎች አሉ የሚለውን መርህ የሚከተሉት ባለታሪካችን፤ የተፈራው ሀብት ምንም እንኳን ፈቃድ ያወጣበትና እየተንቀሳቀሰበት ያለው ባለሀብት ቢሆንም በሁሉም ዜጎች የመጣ በመሆኑ ማህበረሰቡን እንዲያገለግል ማድረግ የውዴታ ግዴታ መሆን አለበት፡፡ በተለይም በአሁኑ ጊዜ የብቻዬ የሚባል ሀብት ሊኖር አይገባም ሌላኛው መልዕክታቸው ነው፡፡
ከቢዝነስ አኳያ ሰዎች ጥሩ ህንጻ ሊሠሩ ይችላሉ፡፡ በዚህ ደግሞ የአገርን ገጽታ ይቀይራሉ፡፡ ግን ደግሞ በአምስት መቶ ሚሊዮን ብር ሕንጻ ከመሥራት በብሩ ፋብሪካ ከፍተን ብንሠራበት በመቶዎች ለሚቆጠሩ ሰዎች የሥራ አድል እንፈጥራለን፡፡ እድገታችንንም እናፋጥናለን፡፡ ስለዚህም አሁን አገር የሚያስፈልጋት ገንዘብን በባንክ ወይም በማይጠቅሙ ነገሮች ላይ ማፍሰስ ሳይሆን ዜጎችን በሚጠቅም መልኩ መሥራት ነውና ባለሀብቶች ይህንን ሊያስቡበት እንደሚገባም ያስገነዝባሉ፡፡
ባለሃብቶች አሁን ባለንበት ሁኔታ ወገናቸውን ዘወር ብለው ማየት የሚችሉበት ጊዜ ላይ ናቸው፡፡ ጎመን በጤና ከሚል እሳቤ መውጣትም አለባቸው፡፡ ምከንያቱም የተደላደለ አልጋ ላይ የሚተኛበት ጊዜ አይደለም፡፡ ዜጎች በተለያዩ መንገዶች ተጎድተዋል፤ እየተሰቃዩም ናቸው፡፡ እናም በዚህ ጊዜ አልደርስም ማለት ደግሞ አገር ምን ታደርግልኛለች ከሚል እሳቤ አለመራቅ ነውና በሁሉም ነገር መድረስና ሕዝቡን መታደግ ያስፈልጋል በማለትም ያሳስባሉ፡፡
ሌላው ያነሱት ነገር ከችግራችን ለመውጣት ማህበረሰቡ አፋጣኝ እርምጃዎችን መውሰድ አለበት የሚል ሲሆን፤ ለዚህም አንድነቱን ሊጠብቅ እንደሚገባ ያስገነዝባሉ፡፡ ወደ አንድ መጥተን ችግሩን የምንከፋፈልበት ጊዜ ላይ እንዳለን ይናገራሉ፡፡ ችግሩ የበዛው በኢትዮጵያ ሰሜኑ ክፍል በመሆኑም በመረዳዳት ወደ ነበርንበት መመለስ ያስፈልጋል፡፡ ህጻናት ጎዳና ላይ እያደሩ እኛ ዝም ማለት አይገባንም፡፡ እናቶቻችን እህቶቻችን በጎዳና እና በዋሻ ውስጥ እየወለዱ ሀብታችን እንዳይጎድል መንገብገብም የለብንም ብለዋል፡፡
ጊዜው ሀብታምነታችን የሚፈተንበት ነው፡፡ ለተቸገሩ በምንደርስበት ልክ እንመዘናለንም፡፡ ስለሆነም በጦርነቱ ያሳየነውን ትጋት በመልሶ መገንባቱም ልንደግመውና ኃላፊነታችንን ልንወጣ ያስፈልጋል፡፡ ክብርን የሚነካውን ቆሻሻ ድህነት ማስወገድም አለብን፡፡ ለዚህ ደግሞ በአስቸኳይ በጦርነቱ ለተጎዱ ወገኖቻችን መድረስና ማገዝ ይኖርብናል። ብዙ እውቀት እያላቸው እገዛ ባለማግኘታቸው ወድቀዋል፣ ገንዘብና ንብረት እያላቸው በደረሰባቸው ችግር ሳቢያ ጎዳና ላይ ወጥተዋል፡፡ ስለሆነም እነርሱን የመታደጉ ሥራ በተለይ የባለሀብቱ ነውና ፈተናውን በጋራ እንለፈው ሲሉ ይመክራሉ፡፡
‹‹እናት የሚያዋልዳት ሃኪምና ቁሳቁስ አጥታ በምትሞትበት ሀገር ባለሃብት ነኝ ማለት ውርደት ነው፡፡ ወገኔ በሁለት መቶ ወይም ሶስት መቶብር መድሃኒት መትረፍ እየቻለ ገንዘቡን በማጣቱ በሚሞትብት አገር እኔ ባለሃበት ነኝ ማለት ሞራል ማጣትም ነው፡፡›› የሚሉት አቶ አዳነ፤ የተወለደን ህጻን አራዊት እየበላው፣ ማህበረሰቡ አሰቃቂ ችግር እየገጠመው ሀብታችን እንዳይጎል የምንሳሳ ከሆነ ሀብታም ነኝ አንበል፡፡ ምክንያቱም ይህ ቀን ያልፋል፡፡ ሲያልፍ ደግሞ ያስተዛዝበናል፡፡ እናም ትዝብት ላይ እንዳንወድቅ ከአሁኑ እንሥራ – የማጠቃለያ መልዕክታቸው ነው፡፡
ጽጌረዳ ጫንያለው
አዲስ ዘመን ጥር 16/2014