ውልደት እና እድገቱ በውቢቷ ጎንደር ከተማ እንኮዬ መስክ በተባለ አካባቢ ነው። ወቅቱም 1975 አ.ም ነው። አባቱ አቶ ይስማው ሰንደቄ የበረሀ ሰው ነበሩ። የአርማጭሆ አካባቢ ሰው በመሆናቸው ወደ ወልቃይት በክረምት እየሄዱ እያረሱ ነበር የሚኖሩት።
ከዚያ ቀድሞ የኢዲዩ ሻምበል የነበሩት አቶ ይስማው ጦረኛ የበረሀ ሰው ነበሩ። እናቱ ህዝባአየ ይክረም በበኩላቸው በቤታቸው ጠላ እየሸጡ ቤታቸውን የሚያስተዳድሩ የቤት እመቤት ነበሩ።
በትምህርት ሕይወቱ የመጀመሪያ ደረጃውን በጎንደር ጻዲቁ ዮሀንስ የተማረ ሲሆን ከዚያው አየ በካፋ የተማረ ሲሆን ሁለተኛ ደረጃ ትምህርቱን ደግሞ አጼ ፋሲለደስ አጠናቅቋል።
ዩኒቨርሲቲ ሲገባ አዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ የንግድ ስራ ኮሌጅ ተመደበና ወደ መዲናይቱ መጣ። በፕሮኪዩርመንት እና ሰፕላይስ ማኔጅመንትም የመጀመሪያ ዲግሪውን ያዘ። ከልጅነቱ አንስቶ በሲኒማ ፍቅር የተለከፈ ሰው ነበር።
ነገር ግን እንደ ማንኛውም ታዳጊ ፊልምን ለመዝናኛነት ፍጆታ ብቻ የሚያይ ብቻ ሳይሆን በፊልም የሚመራመር ፤ በአእምሮውም የራሱን ርእይ እንደ ፊልም የሚጠቀም ነበር። ከፊልሙ አስቀድሞ ግን ሰው መሆን ታሪክ መስማት የሚወድ ሰው ነው።
ታሪክና መስማትም ብቻ ሳይሆን ግን ታሪክን መተረክም ይወዳል። ታሪክ በመስማት እና በመንገር ሂደት ውስጥ ደግሞ በአእምሮ ውስጥ የሚፈጠር ምስል አለ። እነዚያ በአእምሮ በሌላ ውስጥ የሚከሰቱ ምስሎች በብዙዎች ዘንድ ብዙም ከቁም ነገር የማይታዩ ወይም ውልብ ብለው የሚጠፉ ሲሆኑ ለጥቂቶች ግን የጥበብ መነሻ ይሆኗቸዋል። ከነዚያ ጥቂቶች መሀከል አንዱ ደግሞ የዘመናችን ቁንጮ ሲኒማቶግራፈር ሰው መሆን ይስማው ነው።
ሰው መሆን በተለይ እድገቱ ከቤተ ክርስቲያን ጋር የተቆራኘ በመሆኑ ታሪኮችን ለመስማት እና በአእምሮው ምሰል ለመከሰት እድል ነበረው። በቤቱም ቢሆን አያቱ፤ አጎቱ እና እናቱ ጎበዝ ታሪክ ነጋሪዎች ነበሩ።
አብሯቸው ከሚውላቸው ሰዎችም አንዳንዶቹ ሲያወሩ ምሰል መከሰት የሚችሉ አንደበተ ርቱአን ናቸው። ያም የመተረክ እና የመስማት ልምምድ በኋላ ላይ ከፊልም መመልከት ፍቅሩ እና ከካሜራ ጋር ካለው መሳሳብ ጋር ተዳምሮ፤ አድጎ እና በልጽጎ ወደሲኒማቶግራፊው ሙያው የተሻገረው። ይህ በእንዲህ እንዳለ ሰው መሆን እና ፊልም የተዋወቁት በአጎቱ ካሜራ ነው።
የሁለተኛ ደረጃ ትምህርቱን አጠናቅቆ ወደ ዩኒቨርሲቲ ሲቀላቀል በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ንግድ ስራ ኮሌጅ ተማሪ ነበር። ምንም እንኳ ትምህርቱ ንግድ ተኮር ቢሆንም ለዩኒቨርሲቲ ትምህርቱ በአዲስ አበባ መቆየቱ ወደ ፊልም ስራ የሚሳብበትን አጋጣሚ ግን ፈጥረለት። ሰው መሆን ትምህርቱን የሚከታተልበት የንግድ ስራ ኮሌጅ የማደሪያ አገልግሎት የማይሰጥ በመሆኑ አጎቱ ሻለቃ ተስፋዬ ይግረም ዘንድ እንዲያርፍ ይሆናል።
ፎቶ አንሺ የሆኑትን አጎቱን ለመርዳት ከትምህርቱ ጎን እርሳቸው ፎቶ ቤት ያዘወትርም ያዘ። ያኔ እንዳሁኑ ለአጠቃቀም ቀላል የሆኑ ዲጂታል ፎቶ ካሜራዎች አልነበሩም እና በአናሎግ ካሜራዎች ሲሰራ ቆየ።
“አንዳንድ ሰርጎች አነሳ ነበር። ሌላም ሌላም ስራዎች እየሰራሁ ከዚያ ቀስ ብሎ ከፎቶግራፍ ማንሳት ወደ ቪዲዮ መቅረጽ መጣ። ግን ምንድነው ከድሮም ጀምሮ ሲኒማ ላይ ለየት ያለ ፍላጎት ነበረኝ።
ልጅ እያለሁ፣ ሁለተኛ ደረጃም ሆኜ ቪዲዮ ቤቶች አዘወትር ነበር። ሲኒማ ይሄ ታሪክ መንገር የሚባለው አካባቢ መንፈሴ ነበር። እና ቀስ እያለ ወደ ፊልም እያደገ መጣ” ይላል ያን ጊዜን ሲያስታውስ። በአንድ ወቅት ቪዲዮ የማከራየት ስራ ይሰራ ነበር።
ስለዚህም ፊልም የማየት እድል ነበረው። አንድ ቀን የታዋቂውን የፊልም አዘጋጅ ኩዊንተን ታራንቲኖ ያዘጋጀው ሪዘርቪየር ዶግ የሚል ፊልም ተመለከተና ገረመው። የገረመው የፊልሙ አወቃቀር ነበር። ገርሞት ብቻ ግን አላበቃም።
የራሱን ፊልም ሊሰራ ተነሳ። የፊልሙ ርእስም 8፤62 የሚል ሆነ። ስለ ወቅቱ ሲያስታውስ ስለ ፊልም ምንም እውቀት ሳይኖረኝ ልሰራው የተነሳሁት ፊልም ነበር ይላል። ፊልሙ ተሰራ። በተመልካች ዘንድ የተደበላለቀ አስተያየትን ፈጠረ። ፊልሙን ከተመለከቱት መሀከል አንዳንዶቸ ገንዘባችንን ተበላን ብለው ሲናደዱ ሌሎች ደግሞ እነ ሰው መሆን ያደረጉትን ሙከራ አደነቁ።
ከዚያም ቀጠለ ሌላ አዲስ ሙከራ። ፔንዱለምን ሰራ። ፔንዱለም የመጀመሪያው በፎቶ ካሜራ የተቀረጸ ፊልም ነው። ይህም አዲስ ሙከራ ነበር። እንዲህ እያለ ሌሎችንም ፊልሞች ቀጠለ። አዳዲስ ሙከራዎችን እና አዳዲስ ተግዳሮቶችን የሚወደው ሰው መሆን ከሰራቸው ፊልሞች ብዙ የፈተነኝ የሚለው እውር አሞራ ቀላቢ የተሰኘውን ፊልም ነው። ወጣቱ ፊልም ሰሪ ስራው ከአገር ተሻግሮ ዓለም አቀፍ እውቅና ያገኘው በዚሁ “እውር አሞራ ቀላቢ” በተሰኘው ፊልሙ ነው።
ዘካሪያስ ጥበቡ በተባለ ኢትዮጵያዊ የስደት እውነተኛ ታሪክ ላይ ተመስርቶ የተሰራው ይህ ፊልም በፌስቲቫሎች ሽልማቶች እና እውቅናዎች አግኝቷል። የኒውዮርክ አፍሪካ ፊልም ፌስቲቫል ላይ የፌስቲቫሉ ዋና ፊልም ሆኖ ተመርጧል። በዳላስ ኢንተርናሽናል አፍሪካ ፊልም ፌስቲቫል ላይ ደግሞ ሽልማት አግኝቷል።
ከአዲ ዳዕሮ-አዲግራት እስከ ገላባት ሱዳን፣ ከመተማ እስከ ጅቡቲ ድንበር፣ ከአፋር እስከ ትግራይ፣ ከአዲስ አበባ እስከ ጎንደር ተዘዋውሮ የተቀረጸው ይህ ፊልም በመጪው መስከረም ወር በኢትዮጵያ መታየት ይጀምራል ተብሏል። ወጣቱ የፊልም ባለሙያ በዚህኛው ፊልም ከሙከራዎች አልተገታም። ሁልጊዜም በንባብ እና በዩቲዩብ ትምህርቶች ያገኛቸውን አዳዲስ አሰራሮች ይሞካክራል።
ሰው መሆን የታላቁ ኢትዮጵያዊ የፊልም ሰው ሀይሌ ገሪማ አድናቂ ነው። “ሀይሌ ገሪማ በጣም የምከተለው ሰው ነው ፤ ሶሚክ ከጤዛ በፊት እና ከጤዛ በኋላ ብዬ ነው ራሴን የምገልጸው” ይላል። ከታላቁ ሰው ጋር ስለሚጋራው ሙያ ሲናገር ደግሞ እንዲህ ይላል። “ሲኒማቶግራፊ ስሜት ነው። ልክ እንደትወና፣ እንደ ዝግጅት እና እንደሌሎችም የኪነ-ጥበብ ቅርፆች ሁሉ፣ በካሜራ፣ በብርሃንና በሌሎች ነገሮች ስሜትህን ለሌሎች የምታጋባበት፣ ለሌሎች ሃሳብህን የምትገልጽበት መንገድ ነው። ሲኒማቶግራፊ ውስጥ በርካታ ጉዳዮች አሉ።
አንድ ስዕል ውስጥ መብራት አለ- ብርሃኑ፣ ቅንብር
፣ ምስሉ የሚዋቀርበት፣ ገፀ- ባህርያቱ የሚቆሙበት መንገድ፣ ሌሎችም በርካታ ጉዳዮች አሉ። እናም ሲኒማቶግራፊ ስሜትንና ሃሳብን ለሌሎች የማጋባት ትልቁ የፊልም መሳሪያ ነው። በአገራችን እየሰራንበት አይደለም። በእርግጥ አሁን ቴክኖሎጂው እያደገ ሲመጣ የካሜራው ሁኔታ ከፍ እያለ ሲታይ በትንሽ ብርሃን የተለየ ዓይነት ድባብ ለመፍጠር የሚዳረጉ ጥረቶች አሉ። ሲኒማቶግራፊ የሃሳብ ጉዳይ ነው። ቆንጆ ምስል ስለተቀረፀ ብቻ ታዋቂ ሲኒማቶግራፈር መሆን አይቻልም።
” ሶሚክ ባለትዳር እና የ4 ልጆች አባት ነው። በሚሰራቸው ስራዎች ሁሉ ስለማህበራዊ እሴቶች ይጨነቃል። “ፊልም ከመስራቴ በፊት ስክሪፕት አነባለሁ፤ ከ20 አመት በኋላ ልጆቼ ያንን ያዩታል።በአባታቸው እንዲያፍሩ አልፈልግም” ይላል። ከዚያ ባለፈ ፊልሞቹ በሙሉ ከራሱ የኑሮ ተሞክሮ የተቀዱ እና አለም እንዲህ ብትሆን ብሎ ከሚያስበው ርእይ የተያያዙ ናቸው። በአሁኑ ወቅት ከሌሎች የሱ ቢጤ ተመራማሪ የፊልም ሰዎች ጋር በመሆን ሳቢሳ ፊልምስ የተባለ ፕሮዳክሽን ከፍቶ እየሰራ ይገኛል።
አብረውት የሰሩት ሰዎች የሰው መሆን የስራ አጋር ብቻ ሳይሆን አድናቂም ናቸው። ከነዚህም መሀከል የሜካፕ ባለሙያው ተስፋዬ ወንድማገኝ አንዱ ነው። የጀርመን ድምጽ ራዲዮ ስለ ሰው መሆን በሰራው ዘገባ ላይ ተስፋዬ ስለ ሰው መሆን እንዲህ ይላል። “እውነት ለመናገር ሰው መሆን 24 ሰዓት ስለፊልም የሚያወራ ፊልም የሚወድ ልጅ ብዙ ቮካብለሪ ያለው ልጅ ነው።
ሶሚክ ከልጅነቱ ጀምሮ ያሳለፋቸው ጊዜያቶች በጠቅላላ ቀጥታ ወደ ፊልም ስራ እያንደረደሩ ነው ያመጡት። ሁልጊዜ ስለአባቱ፣ እናቱ፣ ስለሰፈሩ ልጆች እንዳለ ታሪካቸውን በሚያወራኝ ጊዜ በቃ ይሄ ልጅ ታሪክ ተናጋሪ እንዲሆን ተመርጧል ብዬ አስባለሁ።
እርሱ ጋር ያለው የፊልም ፍቅር ከዚያን ጊዜ ጀምሮ የመጣ ነገር ነው” በዚሁ ዘገባ ላይ ሌላኛው የሰው መሆን የስራ አጋር የሆነው ዳይሬክተር ዳዊት ስለ ሰው መሆን ሞካሪነት የሚከተለውን ይላል።
“ሲኒማቶግራፊ ላይ ስንመጣ ብዙ ጊዜ በአቀራረጽ፣ በተለይ ደግሞ በመብራት እና ብርሃን አጠቃቀም የራሱን ዘይቤ የፈጠረ ሲኒማቶግራፈር ነው ማለት እንችላለን። በዳይሬክተርነት እንደእኔ ሰው መሆን እየተጓዘ ያለ ዳይሬክተር ነው ብዬ ነው የማስበው። ብዙ ነገሮችን እየሞከረ፣ እርሱ የሚወደውን እና የሚያምንበትን አይነት ነገር ላይ ለመድረስ እየሞከረ ያለ ዳይሬክተር ነው።
‘የጸሃይ መውጫ ልጆች’ን ምሳሌ ብናደርግ፣ ሌሎቹንም ፊልሞቹንም ብናያቸው ተመሳሳይ ሙከራዎች ውስጥ ያልሆኑ በጣም ብዙ አይነት ሙከራዎች እና ሙከራ ብቻ ሳይሆን የሲኒማ ስኬቶችን ጭምር የሚያገኝ ዳይሬክተር ነው።
‘የጸሃይ መውጫ ልጆች’ ፣ ‘ዓለሜ’ን ካየኸው ሌሎችም ፊልሞቹን የሚወጡትን፣ የወጡትን ፊልሞችም ካየኻቸው አንደኛ ታሪኩ የሚፈልገውን ነገር በመገንዘብ አዲስ ነገርን ለመፍጠር ይሞክራል።
ሁለተኛ ደግሞ ከታሪኩም ውጭ እርሱ እንደፊልም ሰሪ የራሱን ቀለም እና አሻራ [ያሳርፋል]። ምናልባት እርሱ ቀለም እና አሻራ ለማሳረፍ የሚያደርገው ሙከራ ላይሆን ይችላል ግን የሚያደርገው ጥረት አሻራውን እንዲያሳርፍ ያደርገዋል ብዬ አስባለሁ። ‘ዓለሜ’ን ከወሰድኸው በጣም ቀዝቀዝ ባለ ፍጥነት፣ በጣም ጥልቅ የሆነ ታሪክን ለመንገር የሚሞከርበት ፊልም ነው።
“የጸሃይ መውጫ ልጆች’ን ደግሞ ካየኸው ፈጠን ባለ ፍጥነት፣ በጣም የሚያስገርም፣ በስሜት ልብ የሚያንጠለጥል አድርጎ ለመንገር የሚሞከርበት ነው። ለሁለቱም እንደሲኒማቶግራፈርም፣ እንደዳይሬክተርም ሁለቱም ላይ የሞከራቸውን እና ያደረጋቸውን ነገሮች ስታይ የተለያዩ ግን ለየፊልሞቹ በጣም ተገቢ የሆኑ ነገሮችን የሞከረው” ይላል ዳዊት ስለሰው መሆን ሙከራዎች እና ጠንካራ ጎኖች ሲተነትን።
የዘመኑ ኮከብ ሲኒማቶግራፈር ሰው መሆን ለወጣቶች መልእክት ሲያስተላልፍም የሚከተለውን ብሏል።
“ሲኒማቶግራፊ ላይ የተፃፉ በርካታ መፅሐፎች አሉ። እነሱን ቢያነቡ መልካም ነው። ፊልም ማየት እና መስራት አንዱ የመማሪያ መንገድ ይመስለኛል። በቀላሉ ካሜራ ተከራይተው ከተማ ውስጥ እየተዟዟሩ በመቅረፅ ኤዲት ቢያደርጉ ብዙ ነገሮች መማር ይችላሉ።
በተንቀሳቃሽ ስልክም ቢሆን መሞከር፤ በተጨማሪም ፎቶግራፍ ማንሳት፣ በሲኒማቶግራፊ ማራኪ ስለተባሉ ትዕይንቶች ከሰዎች ጋር ማውራት፣ አሰራራቸውን መፈተሽ በሲኒማቶግራፊ የታጩ ፊልሞችን ማየት ከካሜራ ጀርባ ያሉ ቪዲዮዎችን፣ የሥዕል ኢግዚቢሽኖችን መመልከት ልምድን ያጠናክራል። የተለያዩ ቪዲዮዎችን ከተመለከቱ በኋላ ሳቢ የሆኑ ምስሎችን በመምረጥ እኛ ብንሆን እንዴት እንሰራቸዋለን ወይም ዕድሉን ብናገኝ እንሞክራቸዋለን ብለው ማሰብ አለባቸው።
በእዚህ መንገድ አቅማቸውን ሊያሳድጉ ይችላሉ ብየ አስባለሁ።” ይህ በእንዲህ እንዳለ ሰው መሆን የኢትዮጵያ የፊልም ዘርፍ ጉዳይ ያሳስበዋል። ሳይወለድ የሞተ ነው ይላል።
የሲኒማ ኢንዱስትሪው በቴሌቪዥን ዘርፉ ተደፍቆ ሞቷል የሚለው ሰው መሆን የቴሌቪዥን እጣ ፈንታም በኢንተርኔት እየተፈተነ ነው ይላል። ስለዚህም ለከርሞው የራሱን ጣቢያ ከፍቶ ሲኒማውን ስለማሳድግ እና እራሱን ስለመግለጽ እያሰበ ይገኛል። ሰው መሆን ስለ እረፍት ጊዜው ሲናገር “የእረፍት ጊዜዬን የማሳልፈው ከልጆቼ ጋር ወይም ከወዳጆቼ ጋር በመሆን ፊልም በማየት፤ ስለሲኒማ በማውራት እና መሰል ነገሮች ነው የማሳልፈው” ብሎናል።
ለወጣቶች በሚያስተላልፈው መልእክት ላይም “አሁን ለመተኛት ጊዜው አይደለም። በቀን ውስጥ ቢበዛ ከ4 ሰዓት በላይ መተኛት የለብንም” ሲልም ይመክራል።
እኛም ከሰው መሆን ስራዎች የተወሰኑትን በማስታወስ የዛሬው ዘገባችንን እናጠቃልላለን 8፡ 62 (ደራሲ ፣ዳይረክተር)፣ የፀሃይ መውጫ ልጆች (ዳይረክተር)፣ ዓለሜ (ሲኒማቶግራፍ፣ ዳይረክተር)፣ እውር አሞራ ቀላብ (ዳይረክተር)፣ ሰውነቷ (ዳይረክተር)፣ ይሉኝታ (ረ/ዳይረክተር)፣ ባለሀገሩ (በሲኒማቶግራፍ)፣ ያልታሰበው (ሲኒማቶግራፍ)፣ አባይ ወይስ ቬጋስ (ሲኒማቶግራፍ)፣ ፔንዱለም(በሲኒማቶግራፍ)፣ አዲናስ (በሲኒማቶግራፍ)፣ ያ ልጅ(ሲኒማቶግራፍ)፣ ሲቲ ቦይስ (ሲኒማቶግራፍ)፣ ቀሚስ የለበስኩለ’ት (ሲኒማቶግራፍ) በተጨማሪም በሕዝብ ዘንድ ከፍተኛ ተቀባይነት ያስገኙለትን የቴዲ አፍሮ ማር እስከ ጧፍ እና የእሱባለው ይታየው ዘፈን ማሞቂያ አይደለም ሰርቷል።
በማስታወቂያ ዘርፍ በጣም በርካታ ሕዝብ የሚያስታውሳቸውን ስራዎችን ሰርቷል። ሽልማትን በተመለከተም በ3ተኛው ጉማ አዋርድ ላይ በዓለሜ ፊልም ምርጥ ሲኒማቶግራፈር አሸናፊ። በ9ኛው ኢትዮጵያ ኢንተርናሽናል ፊልም ፌስቲቫል በቀሚስ የለበስኩለት ፊልም በምርጥ ሲኒማግራፈር አሸናፊ ሆኗል።
(አቤል ገ/ኪዳን)
አዲስ ዘመን ጥር 8/2014