አገራችን ኢትዮጵያ ሊያንበረክኳት ከሚፈልጉ ኃይሎች ጋር የሕልውና ትግል ከገጠመታ ወራት ተቆጥረዋል። ምእራባውያኑም አልንበረከክ ያለቻቸውን አገር ለመቅጣት ያላቸውን አቅም በሙሉ እየተጠቀሙ ሲሆን፣ ከእነዚህ ስልቶች መካከልም አንዱ አገሪቱን ኢኮኖሚያዊ ጫና ውስጥ መክተት ነው። በዚህም መሰረት ኢትዮጵያ ብድር እና እርዳታ እንዳታገኝ፣ የውጭ ንግዷ እንዲዳከም ማድረግ ፤ የውጭ ምንዛሬ እጥረቱን ማባባስ እና መሰል ስልቶች ጥቅም ላይ እየዋሉ ነው። እነዚህ ስልቶች በአብዛኛው አፋጣኝ መፍትሄ የሚያስፈልጋቸው ሲሆኑ፣ መፍትሄ የማመንጨቱ ሥራም የመንግሥት ብቻ ሳይሆን የዜጎችም የጋራ ኃላፊነት እንደሆነ የታወቀ ነው። ዛሬም ዜጎች አሁን አገሪቱ የገባችበትን የሕልውና ጦርነት ለማሸነፍ ከፋሽን እና አልባሳት አንጻር ምን ማድረግ ይችላሉ የሚለውን እንዳስሳለን።
እንደሚታወቀው አገራችን ራሷን ካልቻለችባቸው ዘርፎች መካከል አንዱ የጨርቃ ጨርቅ እና አልባሳት ዘርፍ ነው። በዚህ በኩል ጥቂት የማይባሉ ኢትዮጵያውያን ዛሬም ቢሆን በዓመት አንዴ እንኳን ልብሳቸውን የማይቀይሩ ናቸው፤ በሌላ መልኩ ጥቂቶች በዓለም አዲስ መጣ የተባለውን ፋሽን ሁሉ ሲሸምቱ ይውላሉ። የገጠሩ ሕዝብ በአብዛኛው ልባሽ ጨርቆችን /ሰልቫጅ/ እና ባህላዊ ልብሶችን አዳቅሎ ይጠቀማል።
የከተማው በበኩሉ ልባሽ ጨርቆችን /ሰልቫጅን/ ከአገር ውስጥ የፋብሪካ ምርቶች እንዲሁም ከውጭ ከሚሸመቱ ልብሶች ጋር አደባልቆ ይለብሳል። የሆነ ሆኖ አገራችን ልብስ ለመሸመት የምታወጣው ወጪ ከዓመት ዓመት እየጨመረ የመጣ ሲሆን፣ ልብስ አስመጥቶ ለመሸጥ ዶላር እየያዙ ወደ ዱባይ ፤ ቻይና ፤ ታይላንድ ፤ ቱርክ እና ሌሎች አገራት የሚሄዱ እንዲሁም በኮንቴነር ልባሽ ጨርቆችን የሚያስገቡ ነጋዴዎችም ተበራክተዋል። በተቃራኒው በተለይ የጨርቃጨርቅ ምርቶችን ወደ ውጭ በመላክ ደህና ገቢ ታገኝበት የነበረው የአሜሪካ ነጻ የንግድ ገበያ ደግሞ ሕወሓትን በምትደግፈው አሜሪካ መንግሥት ውሳኔ ኢትዮጵያ ከገበያው ተጠቃሚነት እንድትወጣ ተደርጓል።
ስለዚህም ይህን ጫና እንዴት እንመክት በሚለው ዙሪያ ለመወያየት ተገቢው ጊዜ አሁን ሆኗል። በቅርቡ ማህበራዊ ሚዲያ ላይ አንዳንድ ግለሰቦች ኢትዮጵያውያን በፍጥነት ወደ አገር ውስጥ ገበያ በመዞር እና የአገር ውስጥ ምርቶችን በመጠቀም ይህን ኢኮኖሚያዊ ጫና መመከት እንደሚችሉ ሲናገሩ ተሰምተዋል። በእርግጥም በዚህ መልኩ ኢኮኖሚያዊ ብቻ ሳይሆን ፖለቲካዊ ተጽእኖንም መመከት እንደሚቻል ከዚያም አልፎ ለጨርቃጨርቅ ኢንዱስትሪው ሁነኛ መሠረት በዚህ ወቅት ላይ መጣል እንደሚቻል ታሪክ ያመላክታል።
ለዚህም ጥሩ ምሳሌ የሚሆነው የማህተመ ጋንዲ ታሪክ ነው። ጋንዲ ቅኝ ገዢዋን ብሪታንያን ከህንድ እንድትወጣ ለማድረግ ከተጠቀማቸው ነገሮች አንዱ የአልባሳት አብዮት መቀስቀስ ነው። አብዮቱም ህንዳውያን ከሀገረ እንግሊዝ የሚሸምቱትን ልብስ በመተው ራሳቸው በእጃቸው የሰሩትን ልብስ እንዲለብሱ ማድረግ እና ለቅኝ ገዢዎች ያላቸውን ተቃውሞ ማሳየት ነበር። ካዲ በሚል ስም የሚጠራው ይህ ልብስ መነሻ ነጥብ ሆኖ ዛሬ ላይ ህንድ ከአንድ ቢሊየን የሚበልጥ ህዝቧን ለብሶ እንዲውል ማድረግ ያስቻላት የጨርቃጨርቅ ኢንዱስትሪ ዘርፍ እንዲነሳ ማድረግ አስችሏታል።
ዛሬ ላይ የህንድ የጨርቃጨርቅ ኢንዱስትሪ በዓለም ሁለተኛው ግዙፉ ኢንዱስትሪ ነው። መረጃዎች እንደሚያሳዩት፤ በፈረንጆቹ 2019/20 ዓመት የህንድ የጨርቃ ጨርቅ ኢንዱስትሪ 108 ቢሊየን ዶላር ገደማ ገቢ ያስገኘ ሲሆን፣ ከዚህ ውስጥ 75 በመቶው ለአገር ውስጥ ገበያ የሚውል ነው። የቀረው 28 ቢሊየን ዶላር ደግሞ ህንዳውያን አምርተው ወደ ውጭ የሚልኩት ነው።
በዚህም መሠረት አሁን ላይ አገሪቱ ከምታመርተው ጠቅላላ አገራዊ ምርት 5 በመቶው ገደማ ከዚሁ ዘርፍ የሚገኝ ሲሆን፣ ከአገሪቱ የውጭ ንግድ ገቢም 12 በመቶው የጨርቃጨርቅ ዘርፍ ውጤት ነው። ህንድ ከጨርቃጨርቅ ዘርፍ የምታገኘው ገቢ በ2025 እ.ኤ.አ ወደ 190 ቢሊየን ዶላር ይደርሳል ተብሎም ይገመታል። ይህ ሁሉ የሆነው ግን ህንዳውያን ያኔ በመሪያቸው ጋንዲ ምክር ተማምነው ወደ አገራቸው ምርት እና ወደ አገራዊ ፋሽን ፊታቸውን ለማዞር በመወሰናቸው ነው። እንዲያ ባይሆን ኖሮ ዛሬ ላይ ህንድ ባላት ከፍተኛ የሕዝብ ቁጥር ብዛት በዓለም ከጨርቃጨርቅ ኢንዱስትሪ መሪዎች ተርታ ሳይሆን ከዓለም ቀዳሚ ሸማቾች ተርታ ትሰለፍ ነበር።
በቻይናም ቢሆን ነገሩ ከዚህ የተለየ አይደለም። የቻይናን የባህል አብዮት የመሩት ማኦ አገር በቀል ልብስ ይለብሱ የነበረ ሲሆን፣ ብዙዎችም ይህን ባህላዊ ልብስ እሳቸውን ተከትለው ለብሰውታል። የልብሱ ዋነኛ አላማ የቻይናን ሉዓላዊነት ማረጋገጥ ነበር። ዛሬ ላይ የቻይና የጨርቃ ጨርቅ ኢንዱስትሪ የዓለም ገበያን የተቆጣጠረ ሲሆን፣ የቻይና መንፈስ ያለባቸው የአልባሳት ፋሽኖችም በትልልቆቹ የምእራቡ ዓለም የፋሽን መድረኮች በስፋት የሚታዩ ሆነዋል።
የእነዚህ ሁለት አገራት ተሞክሮ የሚያሳየን አንድ ነገር አሁን ኢትዮጵያ ያለችበትን አይነት የፖለቲካ ጫና ወቅት በፋሽን ዘርፍ አቅጣጫ ለመቀየር እና ወደ አገር ውስጥ ገበያ ትኩረት ለማድረግ በቂ መንስኤ እንደሚሆን ነው። ኢትዮጵያውያን በውድ ዋጋ
በውጭ ምንዛሬ ከአውሮፓ እና አሜሪካ ብሎም ሌሎች አገራት ልብስ እየሸመትን የምንዘልቅበት ጊዜ ማብቃት እንዳለበት የሚያሳይ ምልክት ታይቷል። አገር በቀል የጨርቃጨርቅ ምርቶች፤ አገር በቀል ጫማዎች፤ አገር በቀል ቦርሳዎች ፤ አገር በቀል ጌጣጌጦች ፤ አገር በቀል ሽቶዎች እና ሌሎች ገበያውን ሊቆጣጠሩበት የሚገባው ጊዜ አሁን ነው። ለዚህ ደግሞ የፋሽን ዲዛይነሮቻችን ከጨርቃጨርቅ ፋብሪካዎች ጋር ተናብበው መሥራት አለባቸው።
ብዙውን ጊዜ ብዙዎች የአገር ውስጥ ምርት የጥራት ችግር እንዳለበት ሲናገሩ ይሰማል። ይህ ከፊል እውነት ቢኖረውም ሙሉ ለሙሉ እውነት ነው ለማለት አይቻልም። የጥራት ችግሩ ቢኖርም እንኳ ይህ የጥራት ችግር ሊቀረፍ የሚችለው የጨርቃጨርቅ ፋብሪካዎች በቂ ገበያ እና በቂ ትርፍ ሲኖራቸው ነው። ያኔ ፋብሪካዎችም የአቅም ግንባታ ሥራዎችን ማካሄድ ይችላሉ። በተመሳሳይም የፋሽን ዲዛይነሮች የአገር ውስጥ ፍላጎት እየጨመረ ሲሄድ የፈጠራ አቅማቸውም እየጨመረ ይሄዳል።
ይህ በእንዲህ እንዳለ ባለፉት ጥቂት ቀናት የሰማናቸው ዜናዎች የሚያመለክቱትም ይሄንን ነው። የኢንዱስትሪ ፓርኮች ልማት ኮርፖሬሽን ዋና ስራ አስፈፃሚ ሳንዶካን ደበበ በትዊተር ገፃቸው እንዳሰፈሩት፤ በድሬዳዋ እና ባህር ዳር ኢንዱስትሪ ፓርኮች የሚገኙ ኢትዮጵያውያን ፋብሪካዎች “በኢትዮጵያ የተመረቱ” ጫማዎችን እና አልባሳትን ወደ ውጭ አገራት ልከዋል። ይህ የሚሳየው የሚባለው የጥራት ችግር እንደሌለ ነው። ኢትዮጵያውያን አምራቾች ወደ ውጭ መላክ ከቻሉ ለአገር ውስጥ ገበያም ማቅረብ ይችላሉ ማለት ነው። አሁን የሚጠበቀው ተጠቃሚው ትኩረቱን ወደ አገር ውስጥ ገበያ እንዲያዞር ነው።
(አቤል ገ/ኪዳን)
አዲስ ዘመን ኅዳር 13/2014