ከጦርነት በፊት፣ በጦርነት ወቅትና ከጦርነት በኋላ ስለ ጦርነትና ጦርነቱ ሊያስከትል ስለሚችለው፤ ወይም ያስከተለውን ሁለንተናዊ ቀውስ (“Effects of war” እንዲሉ) በየፈርጁ መጻፍ፣ መሰነድ፣ መተንተን፣ ማብራራት ወዘተርፈ የተለመደ እንጂ አዲስ አይደለም። በመሆኑም እኛም ዛሬ በዚህች ግማሽ ገጽ አማካኝነት፣ በጦርነቱ ሰበብ በአገራችን የተከሰተውን ሰፊ ማሕበራዊ ቀውስ በወፍ በረር እንቃኛለን።
“ለመሆኑ ጦርነቱ ሲጀመር እንዴት ነበር?” ከሚል “የዘገየ” ጥያቄ እንጀምር። “እንዴት ነበር?” የሚለውን በወቅቱ በቦታው የነበሩትና ከአዲስ ዘመን ጋር ቆይታ ያደረጉት የክሊኒካል ሳይኮሎጂ ባለሙያው አቶ ሳምሶን ይመልሱልናል።
ጦርነቱ ሲጀመር እኔ ማይፀብሪ እሚባለው ቦታ ባለ የስደተኞች ካምፕ ውስጥ በማማከርና ሥልጠናዎችን በመስጠት እሰራ ነበር። ጦርነቱ ከተጀመረ በኋላ አንድ ወር ቆይቼ ነው የወጣሁት። ሁሉንም ነገር በቅርብ አውቀዋለሁ፤ አይቼዋለሁ። ጦርነት ሲጀመር ቀላል ይመስላል። በኋላ ግን፣ ቀናት እየጨመሩ በሄዱ ቁጥር እንደመጀመሪያው ቀን ቀላል አይደለም። መውጫ ቀዳዳ ነው የሚጠፋው። በመሆኑም እዛ በነበርኩበት ጭንቅ ሰአት ውስጥ በአካባቢው ሰዎች ላይ የደረሰውን የአእምሮም ሆነ የመንፈስ ጭንቀት አይቼዋለሁ። ተፈጥሮ የነበረውን ማሕበራዊ ትርምስና አለመረጋጋት በቀላሉ መግለጽ ያስቸግራል።
“እንደ እውነቱ ከሆነ ያ ሁሉ መረበሽ፣ መጨነቅና የመሳሰሉት ሰብአዊና ማሕበራዊ ቀውሶች ሊደርሱ አይገባም ነበር፤” የሚሉት አቶ ሳምሶን አሁንም ሁሉም በተለይም ሕዝቡ ወደ ጦርነቱ እንዲገባ ምክንያት የሆነው ክፍል ቆም ብሎ ሊያስብ እንደሚገባ ይናገራሉ።
የአሸባሪውን ትሕነግን የሀሰት ፕሮፓጋንዳና በሕብረተሰቡ ውስጥ አለመረጋጋትና አለመተማመን ለመፍጠር የሚደረገውን ስራና ሴራ በተመለከተም “የሀሰት ፕሮፓጋንዳንና ተጨባጭ ያልሆነ መረጃ ስርጭትን በተመለከተ ሕብረተሰቡ በእንደዚህ አይነት ውዥንብሮች ፈጽሞ ሊረበሽ አይገባም። ተግባሩ የተለያዩ ፍላጎቶች ያሏቸው ወገኖች ተግባር መሆኑን ተገንዝቦ ተስፋ ከመቁረጥ ሊቆጠብ፤ ሊረጋጋ፤ ወጣቶችም ይህንን በአገር ላይ የመጣን አደጋ ከማክሸፍ፣ የሀሰት ፕሮፓጋንዳን ከማጋለጥ አኳያ ሚናቸው ከፍተኛ እንዲሆን ይጠበቃል። ሚዲያውም እንደዛው ሚናውን ሊወጣ ይገባል” ሲሉ ያብራራሉ።
በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ የልህቀት ማእከል የአፍሪካ ሬልዋይ ሴንተር የፕሮኪዩመንት ስፔሺያሊስት የሆነው ወጣት ጥላሁን ውቤም ይሄንኑ ሃሳብ ይጋራል። ይሄን በማሳያ ሲያስረዳም፤ “ከግንባር (ማይካድራ) እንደምንም ሕይወቱን አትርፎ የመጣ ጓደኛ አለኝ። ይህ ወዳጄ ሳግ እየተናነቀው እንደነገረኝ ከሆነ የተሰራው ሥራ በቃል የሚገለጽ አይደለም። ኢ-ሰብአዊ እና ኢ-ሞራላዊ ሥራ ነው የተሰራው። ባጭሩ ከሰው ልጅ የማይጠበቅ፤ መቸም የማይፋቅ ታሪካዊ ስህተት ነው ቡድኑ የፈጸመው። ቡድኑና አባላቱ በሰሜኑ እዝ ላይ በፈጸሙት ክህደት፤ በሕብረተሰቡ ላይ የተሰራው ሥራና የፈጠረው ቀውስ አሁን ብቻም አይደለም እስኪስተካከል የተወሰነ ጊዜን ይፈልጋል፤ እስከዚያው ግን መከላከያ ሥራውን ይስራ፣ ሕዝቡም ከጎኑ ይቁም፣ ለሀሰት ፕሮፓጋንዳ ጆሮውን አይስጥ፤ ይህ ከሆነ ሁሉም ልክ ይሆናል፤” በማለት ነበር፡፡
አቶ ጥላሁን እንደሚለው፤ አሁን ላይ አብዛኛው ጦርነት እየተካሄደ ያለው በፕሮፖጋንዳ ነው፤ ከዚህ አኳያ በተለይ ለሀሰት ፕሮፓጋንዳው መስፋፋት ምቹ መደላድል የፈጠሩት ማሕበራዊ ሚዲያዎች በጉዳዩ ላይ ቆም ብለው ሊያስቡበት ይገባል።
አቶ ሳምሶንም በበኩላቸው እንደሚሉት፤ የመገናኛ ብዙሃንም ይሁኑ የማህበራዊ ሚዲያው ተሳታፊዎች ከእንደዚህ አይነቱ፣ ከጦርነቱ በባሰ ሁኔታ ህዝብና አገርን ከሚጎዳ ተግባር በፍጥነት መቆጠብና እውነታውን ለሕዝብ በማሳወቅ ሕዝቡን የማረጋጋትና ሁለቱ ተዋጊ ኃይሎች ወደ ሰላም እንዲመጡ መስራት አለባቸው። ማንኛውም (የአገር ውስጥም ሆነ የውጭ) ሚዲያ፣ በከፍተኛ ሃላፊነት፣ በሙያዊ ግዴታና ሕጋዊ አግባብ ሊንቀሳቀስ ይገባል፡፡
አገርና ሕዝብ በሌለበት ሁኔታም የእነዚህ ወገኖች ህልውና ሊቀጥል አይችልምና ሁሉም ከዚሁ አኳያ መስራት አለባቸው። በጦርነቱም ሆነ እሱን ተከትለው የመጡት ችግሮች በአካባቢው ሕብረተሰብ ላይ ብቻ ሳይሆን በአጠቃላይ አገሪቱ፤ ከዛም ባለፈ በውጭ የሚኖሩ ወገኖች አእምሮ ላይ እያሳደሩት ያለው ጫናም በቀላሉ የሚታይ አይደለምና ሊታሰብበት ይገባል።
ጦርነቱ በጥቂት ሰዎች ስሜትና ውሳኔ እንጂ ሕዝቡ አውቆት፣ አስቦበትና ተዘጋጅቶበት የተገባበት ባለመሆኑ ጉዳቱ ከፍተኛ ሊሆን እንደቻለ አቶ ሳምሶን የተናገሩ ሲሆን፤ ይህም ሁሉንም የሕብረተሰብ ክፍል፤ በተለይም ወጣቱን የዚህ ጦርነት ሰለባ እንዲሆን አድርጎታል ሲሉም የችግሩን ስፋት ያስረዳሉ። “ጦርነቱ የሕዝብ ፍላጎት የታከለበትና የሕዝብም የ”ልዋጋ” ጥያቄ ባለመሆኑ ምክንያት ከሕብረተሰቡ፣ በተለይም ከሴቶችና ሕፃናት ሥነልቦና ጀምሮ እስከ የሰው ልጅ ክቡር ሕይወት መጥፋትና አካላዊ ጉዳት ድረስ ከፍተኛ ጉዳትን አስከትሏልና ሊታሰብበት ይገባል” ሲሉም ይመክራሉ።
ሌላው ከዚሁ ከማሕበራዊ መመሰቃቀል ጋር በተያያዘ፣ በተለይም ከወጣቱ ወቅታዊ ይዞታ አኳያ ያለውን አስተያየት እንዲያካፍለን የጠየቅነው የባንክ ባለሙያው አቶ አብረሃም ማርቆስ ነው። አቶ አብረሃም “ባለፉት ሁለት አስርት ዓመታት ወጣቱ ላይ ባልተገባ መንገድ የተሰራው ሥራ እጅግ የሚያሳዝንም፣ የሚያሳፍርም ነው። ለዚህ ለዛሬው ማሕበራዊ መመሰቃቀል፣ ሕይወትና ንብረት መጥፋት ሁሉ መነሻው በእነዚህ ዓመታት ውስጥ የተሰሩት አገርን ያላማከሉ ስራዎች ናቸው። ያሳዝናል፤ በጣም ያሳዝናል። ይሁንና አሁን የሚታየው ደግሞ ተስፋ ሰጪ ነው።” ይላል፡፡
“ወጣቱ ከእንደዛ ያለ የሰፈር ፖለቲካ ወጥቶ፣ ከመከላከያ ጎን ቆሞ ለዚህች አገር መስዋእትነት ሲከፍል ማየት በእውነት ተስፋ ሰጪ ነው። ይህች አገር እውነትም ተስፋ ያላት አገር ነች። ወጣቱ አገሩን እንደሚወድ የታየበት አንዱ አጋጣሚ ነውና ሊመሰገን ይገባዋል። ተመልሶ ወደ እዛ፣ ወደ ጠባብ አተያይ እንዳይሄድ ግን ሁላችንም የየድርሻችንን መስራት አለብን።” በማለት አስተያየቱን ሰጥቷል።
ባጠቃላይ ጥቅምት 24/2013 ዓ.ም በሽብር ቡድኑ የሰሜን እዝ መከላከያን ከጀርባው በመምታት የተጀመረው ጦርነት አንድ ዓመት አለፈው። አሸባሪው ሕወሓት በቀሰቀሰው የጦርነት ሂደት ውስጥ ምን ምን ማሕበራዊ ቀውሶችን (የታሪክ አሻራዎችን) ጥሎ ሄደ? የሚል ጥያቄ ከተነሳ መልሱ፤ ኢ-ሰብአዊ እና ኢ-ሞራላዊ፣ እጅግ ዘግናኝ ሥራዎች በራሱ በአሸባሪ ቡድኑ ተፈጽመዋል። አፈና፣ እስር፣ ግድያ፣ ጅምላ ጭፍጨፋ፣ ዘረፋ፣ ማንነት ተኮር ጥቃት በዚህ ቡድን የተፈጸሙ የሰብዓዊ መብት ጥሰቶች ናቸው።
ይህን ተከትሎ የሰዎች መፈናቀል፤ የትምህርት መቋረጥ፣ የአዝመራ (በግብርናው ዘርፍ) መስተጓጎል፣ የሕዝብ ማሕበራዊ አገልግሎቶች መቋረጥ (ከትራንስፖርት ጀምሮ)፣ የመሰረተ ልማት አውታሮች መውደም፣ ከባእዳን ጋር ወግኖ አገርን መውጋት፣ በሰዎች ላይ የአካል ጉዳት ማድረስ፣ የአርሶ አደሩ የጀርባ አጥንት የሆኑትን የቤት እንስሳት ሳይቀር መግደል … የሚሉት በሕብረተሰቡ አኗኗር ላይ የተስተዋሉ ማህበራዊ ጫናዎች ናቸው። እዚህን ጠቀስን እንጂ አሸባሪ ቡድኑ የፈጸማቸው ቆጥረን የማንጨርሳቸው ወንጀሎችና ማሕበራዊ ችግሮች ተከስተዋል። ይህ ሁሉ ማህበራዊ ቀውስ አሁን መቋጫ ሊያገኝ፤ መጠየቅ ያለበትም አካልም በስራው ሊጠየቅ ይገባል፡፡
ግርማ መንግሥቴ
አዲስ ዘመን ሕዳር 2/2014