የትምህርት ጉዳይ ሲነሳ ጆሮው የማይቆም፣ ልቦናው የማይነቃ፤ የስሜት ህዋሳቶቹ የማይነቃቁና ስለ ጉዳዩ ለማወቅ የማይጓጓ የለም። “ለምን?” ምላሹ “‘የሁሉም ሰው’ በሚባል ደረጃ የሚመለከተው በመሆኑ፤ “የሚመለከተው” ሲባልም ወይ የሚማር፣ ወይ የሚያስተምር (ልጁን)፣ ወይም ደግሞ የመጪው ትውልድ ጉዳይ የሚያሳስበው ከመሆኑ አንፃር ነው።” የሚል ይሆናል። ይህን ስንል እንደ አንድ ጋዜጠኛ እንጂ እንደ አንድ የትምህርት (ጥናትና ምርምር) ባለሙያ አይደለምና ሌሎች ጉዳዮችም ይኖራሉ።
ለዛሬው አምዳችን ይዘነው የመጣነውም ይህንኑ ጉዳይ ነው።በርዕሳችን ላይ እንደተመለከተው ነፃ የትምህርት እድል (ስኮላርሺፕ)ን የሚመለከት ሲሆን፤ በተለይም ለአገራችን “አዲስ ጉዳይ” የሆነውን የአገር ውስጥ ነፃ የትምህርት እድልን በተመለከተ በተደራጀና አላማ ተኮር በሆነ መልኩ የሚያቀርብ “ፋውንዴሽን” (በአማርኛችን “ተቋም” እንበለውና) እዚሁ አገራችን ላይ እውቅና አግኝቶ በመመዝገብ (በ2019) ወደ ስራ መግባቱን ነው።
ከተቋሙ ሃላፊና ሰነዶች የተገኘው መረጃ እንዳመለከተው፤ ተቋሙ መሰረቱን ከ”የክርስቲያን ዲሞክራሲ ህብረት” (“The Konrad-Adenauer-Stiftung is a German political foundation with a Christian-Democratic profile.” (CUD)) ጋር ያደረገና በመራሄ መንግስት ኮንራድ የፖለቲካ አስተምህሮ ላይ የጣለ ሲሆን፣ ይህም ነባሩንና መልካም አገራዊ እሴቶችን – ባህል፣ ታሪክ፣ ስነምግባር ወዘተ ጠብቆ የማቆየት ተግባር ላይ ያተኮረ እንደሆነ ተገልጿል።
ይህ “አዲስ ጉዳይ” ያልነው ርዕሰ ጉዳያችን ከእስከ ዛሬዎቹ ለየት ያለ ሲሆን፤ “ልዩ”ነቱም ከአላማና ፋይዳው የሚጀምር ነው።ዝቅ ብለን እንደምንመለከተው የመጠነ ርዕዩም ሩቅነት እንደዚሁ ልዩ የሚያደርገው በመሆኑና ከእድሉ ተጠቃሚ ዜጎችና መንግስትም ባለፈ አጠቃላይ የአገርና ህዝብ ተጠቃሚነትን፣ የዲሞክራሲ ስርአት መስፈንን፣ የትምህርት ጥራትንና ተደራሽነትን፣ የፍትህ ስርአት መዘመንን፣ የዜጎች እኩልነትን፣ የሕግ የበላይነትን፣ አብሮነትን፣ ልዩነትን ተቀብሎና አክብሮ መኖርን፣ የፖለቲካ ስርአትና ተቃውሞ ማስተናገድን፤ የነባር ታሪካዊ፣ ባህላዊ፣ መንፈሳዊ ቅርሶችን ወዘተ ሁሉ የሚያቅፍ ከመሆኑ አኳያ ነው።
ይህን ሁሉ እያልንለት ያለነውና የሁለተኛው የአለም ጦርነት መጠናቀቅን ተከትሎ ጀርመንን መልሶ የመገንባት ሀላፊነትን ተሸክመው በነበሩትና ለዛሬዋ ጀርመን መሰረት በጣሉት፣ በመጀመሪያው የፌደራል ሪፐብሊክ ጀርመን ቻንስለር (ለ14 አመታት መራሄ መንግሥት የነበሩ)፣ ፀረ-ናዚ አቋም አራማጅ፣ የኮለኝ ከተማ ከንቲባ፤ የመጀመሪያና ዛሬም ድረስ ካሉት ስድስት የፖለቲካ ፓርቲዎች አንጋፋ የሆነውን የፖለቲካ ፓርቲ መስራች ኮንራድ አዴኑር፣ በ1955 (እአአ) “The Konrad Adenauer Foundation” “Konrad Adenauer Foundation” በሚል ስያሜ የተቋቋመ ነው።
ፋውንዴሽኑ በሂደት ራሱን እያሳደገ፣ ወሰኑን እያሰፋ በመሄድ ነፃ የትምህርት እድልን “konrad-adenauer-stiftung” (KAS) scholarship” በማካተት አለም አቀፍ አገልግሎትን እየሰጠ ያለ፤ በ2019 “Foundation Office Ethiopia / African Union” በሚል መጠሪያ በኢትዮጵያ መንግስት እውቅናን በማግኘት በአዋጅ የተቋቋመና በአሁኑ ወቅት በበርካታ አካዳሚያዊ፣ ፖለቲካዊ፣ ዲሞክራሲያዊ፣ ማህበራዊና ሕዝባዊ አገልግሎት እንዲሁም የማማከር አገልግሎት፣ የተንታኝ ቡድን (ቲንክ ታንክ) ተግባራት ወዘተ ዙሪያ (አፍሪካ ህብረትን ጨምሮ በአለም አቀፍ ደረጃ ለበርካታ ተቋማት) በመስራት ላይ ይገኛል።
በኢትዮጵያ መንግስታዊ ያልሆነ የውጭ ድርጅት / foreign organization” ስም የተቋቋመው ይህ ፋውንዴሽን፤ ከስነ ምግባር ጋር በተያያዘ በ”ሲቪክ ኤጁኬሽን” አማካኝነት የተሻለ ትውልድ ለመፍጠር በሚያስችሉ ተግባራት ላይ በቀጥታ ከመሳተፍ ጀምሮ በተለያዩና ለአንድ አገር ጠቃሚ ናቸው ባላቸው ዘርፎች ልምድን የሚያካፍል በፋውንዴሽኑ ሰነድ ላይ እንደተቀመጠው (“share the values of democracy, the Rule of Law, Social Market Economy, and human rights of Konrad-Adenauer-Stiftung (KAS)”) ነው።
በእነዚህና ሌሎች በርካታ ዘርፎች የጋራ መግባባት የሚፈጥሩ ሴሚናሮችን፣ ዎርክሾፖችን፣ ፖለቲካዊ ውይይትችን ወዘተ የሚያስተናግዱ መድረኮችን ማዘጋጀትን ጨምሮ በሌሎች ላይም ይሰራል።በአለም አቀፍ ደረጃ ከ120 በላይ ከሆኑ አገራት ጋርም ትስስሮሽ (ኔትዎርክስ) ያለው ስመጥር ፋውንዴሽን መሆኑን ከሃላፊዎቹ ማብራሪያና ሰነዶች እንዲሁም ከተቋሙ ድረገፅ (https://www.kas.de/en/web/aethiopien/sur-place-scholarship-program) ተመልክተናል፡፡
“ይህ ፋውንዴሽን/ተቋም ማን ነው?” የሚለውን በተመለከተ በተወሰነ ደረጃም ቢሆን ግንዛቤ ያስጨብጣል በማለት ይህንን ያህል ከመለስን ወደ ተነሳንበት ርዕሰ ጉዳይ እንመለስ።ርዕሳችን “የአገር ውስጥ ነጻ የትምህርት እድል ቀዳሚ ያደረገው ፋውንዴሽን – ይመዝገቡ!” ሲሆን፤ ቋሚነቱም (Sur-place scholarship program in Ethiopia (For excellent performance in academic studies and society) ከሚለው የተቋሙ ፕሮግራም ጋር በቀጥታ የተያያዘ መሆኑን ልብ ይሏል።ስለተቋሙ አጠቃላይ አሁናዊ ይዞታ ከዛሬው የአምዳችን እንግዳ የፋውንዴሽኑ ካንትሪ ዳይሬክተር ከሆኑት ከሚስተር በኖ ሙሽለር ጋር ያደረግነውን ቃለ ምልልስና ያገኘነውን ምላሽ ከእሳቸው አንደበት እንደወረደ አቅርበነዋልና ተከታተሉን።
በመላ አገሪቱ የሚገኙ ኢትዮጵያውያንን ብቻ የሚመለከተው የነፃ የትምህርት እድል ፕሮግራሙ በተቋሙ (በKAS Office Ethiopia/AU) ዘርፍ አማካኝነት በዓመት አንዴ የሚከናወን (“sur place” project) ነው።ፕሮግራሙ ሁለት አይነት ሲሆን፤ የመጀመሪያው ኢትዮጵያ ውስጥ የመጀመሪያ ዲግሪያቸውን አጠናቅቀው ለሁለተኛ ዲግሪያቸው ተመዝግበው ለመከታተል በዝግጅት ላይ ለሚገኙ ወይም በመከታተል ላይ ላሉ መደበኛ ተማሪዎች የሚሰጥ ነው።በተጨማሪ በመጀመሪያ ዲግሪ ተመርቀው በስራ ላይ የሚገኙ ወጣት ኢትዮጵያዊያንን በፕሮግራሙ (monthly academic scholarship) መሳተፍ ይችላሉ።
ሁለተኛው ደግሞ በተለያዩ የሙያ ዘርፎች የሰለጠኑና በስራ ላይ ያሉ ወይም ወደ ስራ ለመግባት በዝግጅት ላይ ያሉ ኢትዮጵያዊያንን የሚመለከቱ አጫጭር ስልጠናዎች የሚሰጡበት የፕሮግራም አይነት (training grant) ነው። ይህ የነጻ የትምህርት እድል ፕሮግራም ሙሉ የነጻ ትምህርት እድል ፕሮግራም ሳይሆን ከፊል የሆነና ተማሪዎቹን ለማበረታታት፣ የሙያ ላይ ስልጠናን ለመስጠትና ክሂሎታቸውን ለማዳበር፣ ለሚማሩት ትምህርትና ጥረታቸው እውቅና ለመስጠት እንዲሁም በማንኛውም መስክ አገራቸውንና ህዝባቸውን በሙሉ ፈቃደኝነትና ታማኝነት የሚያገለግሉ (“civic engagement” ያላቸው፤ ሊኖራቸው እንደሚገባ ያመኑና ማህበረሰቡን ለማገልገል ሙሉ ፍቃደኛ የሆኑ) ወጣት ምሁራንን ለማፍራት ተብሎ የሚሰጥ ነው።
ይህንንም ልናደርግ ያቀድነው ኢትዮጵያ ወደ ፊት በሙሉ ፍቃደኝነት አገሩንና ማህበረሰቡን ማገልገል የሚፈልግ፣ በዲሞራሲያዊ አሰራር የሚያምንና ተግባራዊ የሚያደርግ፣ ልዩነቶችን ተረድቶና አቻችሎ በጋራ እሴት ላይ በማተኮር የሚሰራ ትውልድ እንዲኖር በማሰብ ነው።
ይህ ኢትዮጵያዊያንን ብቻ የሚመለከተው ነፃ የትምህርት እድል ፕሮግራም የመጀመሪያው (monthly academic scholarship) ለአንድ ዓመት የሚቆይና እንደ አስፈላጊነቱ ለተጨማሪ አንድ ዓመት (እንደየ ጥናት መስኩ ሁኔታ) ሊራዘም የሚችል ሲሆን፤ ሁለተኛው (training grant) ደግሞ እስከ አንድ ዓመት ሊዘልቅ የሚችል ፕሮግራም ነው። እነዚህ ላይ ትኩረት ሊደረግበት የሚገባው ነገር የመጀመሪያው ትምህርታቸውን በውጭ አገር የሚከታተሉና እዚህ አገር ውስጥም የመጀመሪያና ሶስተኛ ዲግሪያቸውን የሚከታተሉ ወጣት ኢትዮጵያዊያንን እንደማይመለከት ነው።
የመጀመሪያው ፕሮግራም አገሪቱ ውስጥ ባሉ ዩኒቨርሲቲዎች በሚሰጥ መደበኛ ትምህርት የሚሸፈን ሲሆን፤ ሁለተኛው ግን በተለያዩ የስልጠና ኮርሶች (On-site training courses) የሚሸፈን ይሆናል። በዚህም የነፃ ትምህርት እድሉ ተጠቃሚ ለመሆን የሚያስፈልጉ ሰዎች መስፈርቱን ማሟላት ያለባቸው ሲሆን፤ የመጀመሪያው ኢትዮጵያዊ መሆን ነው። ከዛ ቀጥሎ ለመጀመሪው የነጻ የትምህርት እድል ለመመዝገብ መጀመሪያ ዲግሪ መመረቂያ ድምር ውጤት 3 ነጥብ 5 (GPA) ያለው/ላት መሆን ያስፈልጋል።እንደ ሁኔታው 3 ነጥብ 4 የሚታይበት እድል ይኖራል።
ለሁለተኛው ለመመዝገብ የሚፈልጉ ደግሞ መስፈርቱ 3 ነጥብ 5 (GPA) እና ከዛ በላይ አጠቃላይ የመመረቂያ ውጤት ይዞ መገኘትን የግድ ይሆናል። ፕሮግራሙ በከፍተኛ ደረጃ ውድድር የሚኖርበት (a very competitive program) ከመሆኑ አኳያ ተወዳዳሪዎች ከወዲሁ ራሳቸውን ማብቃት ይኖርባቸዋል። ይህ የሚሆንበት ዋናው ምክንያት ደግሞ ለመመዝገቢያነት ከሚያገለግሉት ሰነዶች (ሲቪ) ውጪ ሌሎች የተለያዩ ፈተናዎችም (የጽሑፍን ጨምሮ) ስለሚኖሩና ተፎካካሪዎችን የማጣራቱ ስራ የተለያዩ ሂደቶችን ስለሚያልፍ ነው።
ይህንን ውድድር ለማለፍና የፕሮግራሙ ተጠቃሚ ለመሆን የአካዳሚክ እውቀት ብቻ በቂ አይደለም። ከላይ እንዳልነው ተወዳዳሪው የወጣበትን ህብረተሰብ ለማገልገል ያለው ከእምነት የመነጨ ተነሳሽነትና ፍላጎት መሰረታዊውን ስፍራ ይይዛሉ።አንድ አገር እንዲያድግ ከተፈለገ እያንዳንዱ ዜጋ የድርሻውን ሊወጣ ይገባልና ከተወዳዳሪዎችም ይህ ይጠበቃል። ከስልጠናው በኋላም የሚጠበቅባቸው አገራቸውንና የወጡበትን ማህበረሰብ በቅንነትና ታማኝነት በማገልገል ኢትዮጵያን ወደ ፊት ማራመድ ነው።
በስልጠናዎቹ ከቋንቋ ጀምሮ የተለያዩ መስኮች የሚካተቱ ሲሆን፤ ከእነዚህም ውስጥ ጋዜጠኝነትና ፖለቲካን የመሳሰሉት ሁሉ ይገኙበታል። ህግና ሰብአዊ መብትን የሚመለከቱ ጉዳዮችም እንደዛው። ስለሆነም ተወዳዳሪዎች ስለ ፖለቲካ የማወቅና በፖለቲካ ውስጥም በንቃት የመሳተፍ፣ ስለ ብዙሀ ዲሞክራሲ አስፈላጊነት፣ የሕግ የበላይነት፣ ሰብአዊ መብቶች፣ ማህበራዊ ገበያ ኢኮኖሚ እንዲሁም ስለ አለም ወቅታዊ ሁኔታ የማወቅ ፍላጎት ማለትም የፖለቲካ ዝንባሌ፣ የብዝሃ ፓርቲ ዴሞክራሲ ጠቀሜታ፣ የህግ የበላይነት፣ የማህበራዊ ገበያ ኢኮኖሚ፣ ሰብዓዊ መብቶች፣ እና ወቅታዊ የዓለም ሁኔታን በተመለከተ ቢኖራቸው የበለጠ ተመራጭ ነው።
የነጻ ትምህርት እድሉ ተጠቃሚዎች ትምህርታቸውን ካጠናቀቁ በኋላ የተለያዩ እድሎች ያሏቸው ሲሆን፣ የፋውንዴሽኑ አባል ይሆናሉ።ፋውንዴሽኑ በአለም አቀፍ ደረጃ ባሉት ከ120 በላይ አገራት ትስስሮሽ (ኔትዎርክስ) ውስጥ ይቀላቀላሉ።ተቋሙ በተለያዩ አገራት በሚያዘጋጃቸው ሴሚናሮች፣ ዎርክሾፖች፣ ኮንፈረንሶች ወዘተ ይሳተፋሉ። (ለመወዳደር የሚፈልጉ ሁሉ የተቋሙን ድረ ገጽ በመመልከት ዝርዝር ሀሳቡን ከዛው ማግኘት ይችላሉ።)
ማጠቃለያ፡-
ጀርመንና ኢትዮጵያ በጋራና በትብብር ሲሰሩ ይህ የመጀመሪያቸው አይደለም። ጀርመን ከአለም በአምስተኛነት ኢትዮጵያ ውስጥ “የጀርመን ለጋሲዎን” በሚል ስያሜ የዛሬዋን ኤምባሲ ከከፈተችበት ከ1896 ዓ.ም ጀምሮ የሁለቱ አገራት ግንኙነት ሳይቋረጥ እዚህ የደረሰ መልካም ግንኙነትን ያነገበ ነው። በዚህ የታሪክና ጊዜ ሂደት ውስጥም ሁለቱ አገራት ከዲፕሎማሲያዊ ተግባርና ሀላፊነቶች በተጨማሪ በርካታ ተግባራትን በጋራ አከናውነዋል።አንዳቸው ከአንዳቸው ሀሳብ ተዋውሰዋል።በልማት፣ በትምህርት መስፋፋትና ተደራሽነት የመሳሰሉት ተግባራት ላይ በጋራና በግል (በድጋፍና ትብብር መልክ) ሰርተዋል።
በባህልና ኪነጥበብ (ለምሳሌ የጀርመን ባህል ተቋም ወይም ጎት ኢንስቲቱት) እና በሌሎች በርካታ ዘርፎች የጀርመን መንግስት ትብብር፣ ድጋፍና እርዳታ ይሰጣል። በቴክኒክ በኩልም እንደዚሁ። ይህ ዛሬ በአምዳችን ላይ ያስተናገድነውም ፋውንዴሽን የእነዚሁ እና የሁለቱ አገራት ታሪካዊ ግንኙነት ውጤት ነው።ስለሆነም የተሻለና አገራችን ለተያያዘችው ሽግግር ብቻም ሳይሆን ለዘላቂ እድገትና ብልፅግናዋ ፋይዳው የጎላ ነው።ዜጎችም ተቋሙ ካዘጋጀው የነፃ ትምህርት እድል መርሀ ግብር ተጠቃሚ ይሆናሉ ብለን እንጠብቃለን።
በመጨረሻም የምዝገባው የመጨረሻ ቀን በአውሮፓውያን አቆጣጠር ጥቅምት 31 መሆኑን በመጠቆም፤ KAS Office Ethiopia/AU ለሀገራችን የትምህት ጥራትና ተደራሽነት፣ ዲሞክራሲያዊ ስርአት ግንባታ፣ መልካም አስተዳደር፣ ማህበረሰብ አቀፍ አገልግሎት ወዘተ ዘርፎች ማስረፅና ተግራዊነት ላይ እያደረገ ያለውን አስተዋፅኦ ሳናደንቅ አናልፍም። ሌሎችም አገሪቱ እያከናወነች ባለችው የሰው ሀይል ልማት፤ የትምህርት ጥራትና ተደራሽነትን ማስፋት ላይ ተመሳሳይ ድጋፍ እንዲያደርጉ በዝግጅት ክፍላችን ስም እናሳስባለን።
ግርማ መንግሥቴ
አዲስ ዘመን ጥቅምት 8 ቀን 2014 ዓ.ም