ቢጠጣ ጥም የሚቆርጥ፣ለምግብ ውህደትና ጤናን ለመጠበቅ አስፈላጊ፣ለምግብ ማብሰያ፣የግልና የአካባቢን ንጽህና ለመጠበቅ፣ለልማት ሥራ ለእነዚህና ለሌሎችም ዘርፈብዙ ጥቅሞችና ግልጋሎቶች የሚውለው ውሃ ሕይወት ስለመሆኑ ጥናትና ምርምር ሳያስፈልግ ፍጥረታት ሁሉ የሚመሰክሩለት ሀብት ነው። ሰው ካለውሃ በህይወት የመቆየቱ ዕድል አነስተኛ እንደሆነም ተደጋግሞ ይነሳል።ሕይወት አድኑ ውሃ መገኛ ምንጩ ሁለት ነው።ከርሰምድርና ገፀምድር።የከርሰምድሩ በምድር ውስጥ ከሚገኙ ሀብቶች መካከል ይመደባል።የዛሬ ርዕሰ ጉዳይ ወይም የጽሁፋችን ትኩረትም ምድር ካፈራቻቸው ሀብቶች ወይንም የምድር በረከት ውስጥ አንዱ በሆነው የከርሰምድር ውሃ ላይ ያጠነጠነ ነው።በተለይም በኢትዮጵያ ይህን ሀብት በመጠቀም ረገድ ስላለው እንቅስቃሴና በሀብቱ ዙሪያ በዲላ ዩኒቨርሲቲ የአካዳሚ ጉዳዮች ምክትል ፕሬዚዳንትና በጂኦሎጂ ትምህርት ክፍል መምህር ከሆኑት ዶክተር ፍቃዱ ወልደማርያም ጋር ቆይታ አድርገናል።
እንደ ዶክተር ፍቃዱ ማብራሪያ የከርሰምድር ውሃን በሁለት መንገድ ማየት ይቻላል።አንዱ አፈር ውስጥ የሚገኘው ወይንም ሶይል ዋተር የሚባለው ሲሆን፣ሌላው የከርሰምድር ግራውንድ ዋተር ነው።የአፈር ውስጥ ውሃ የሚባለው የአፈር እርጥበትን የሚጠብቅና ለተክሎች ዕድገት የሚውለው ሲሆን፣ ከአፈር በታች በጥልቀት የሚገኘው ወይንም የከርሰምድር ውሃ የሚባለው ደግሞ በአብዛኛው በቁፋሮ የሚገኘ ሲሆን የጉድጓድ ውሃ በመባልም ይታወቃል።ውሃው የሚገኘው ጥልቅ ጉድጓዶችን በመቆፈር ሲሆን፣የቁፋሮውን ሥራ በአካባቢ በሚገኝ ቁሳቁስ በአካባቢ ላይ ጭምር ማከናወን የሚቻል ከፍ ሲልም በተሻለ የቁፋሮ መሳሪያ በመጠቀም በስፋት መጠቀም ይቻላል።በቁፋሮ የሚገኘው ውሃ እንደአካባቢው ሥነምህዳር ወይንም የመሬት ሁኔታ የሚለያይ ሲሆን፣በአብዛኛው ግን እስከ 40 እና 60 ሴንቲሜትር ጥልቀት በሚከናወን ቁፋሮ ውሃው ሊገኝ ይችላል።ይህም በአጭር ርቀት የቁፋሮ ጥልቀት ተከናውኖ የሚገኝ ውሃ ነው።ከዚህ በታች የሆነው ደግሞ በጥልቅ ርቀት ላይ የሚገኝ ውሃ ነው። 10 ሜትር የቁፋሮ ጥልቀት የሚገኝባቸው ቦታዎች በርካታ ናቸው።በኢትዮጵያ ተጨባጭ ሁኔታ ሀብቱ በተለያየ ሥነምህዳር አቀማመጥ ይገለፃል።ከመሬት ከዚህ በታች የሚገኘው ውሃ ከድንጋይ በታች እንደሆነም መዘንጋት የለበትም።በመሆኑም በጥራትና በመጠን የሚገኘው ውሃ አንዱ ከሌላው አካባቢ እንደየ አካባቢው ተጨባጭ ሁኔታ ይለያያል።ይህ የገፀምድር የውሃ ሀብት በኢትዮጵያ ከፍተኛ እንደሆነም ይገመታል።እንደመሬት ምድርም ሲወሰድ የሰው ልጆችን ጨምሮ ለፍጥረታት ሁሉ ለመጠጥና ለተለያየ አገልግሎት የሚውል ለዚያውም በእንግሊዝኛው አጠራር ፍሬሽ ወተር ከከርሰምድር ውስጥ የሚገኝ ሲሆን፣ሀብቱም ሰዎች በሚኖሩበት አካባቢ ይገኛል።በቁፋሮ በቀላሉ የሚገኝ ሀብት መሆኑም የተለየ ያደርገዋል።ከወንዞች ወይንም ከገፀምድር የውሃ ሀብት አንፃርም የከርሰምድር ውሃ ከዓለም አንጻርም ሲቃኝ በመጠን ከፍተኛ ነው።ይህ የዓለም ነፀብራቅ በኢትዮጵያ ተጨባጭ ሁኔታ ከወንዞችም በላይ ከፍተኛ ክምችት የሆነ ሀብት ነው።ይህን ዕምቅ የሆነ ሀብት በአግባቡ ፈልጎ ጥቅም ላይ ማዋል ይጠበቃል።
እንደ ዶክተር ፍቃዱ ገለጻ፤በኢትዮጵያ የሚገኙ ወንዞች በቁጥር አነስተኛ መሆናቸው ብቻ ሳይሆን የተወሰነ መስመር ይዘው ነው የሚፈሱት።በመሆኑም የሚፈለገውን ቦታ ሁሉ ማዳረስ አይችሉም።በተሻለ በሁሉም ሥፍራ ተደራሽ የመሆን አቅም ያለው ከመሬት በታች የሚገኘው የከርሰምድር የውሃ ሀብት ነው።መጠኑ ከቦታ ቦታ ልዩነት ቢኖረውም ውሃው አይታጣም።የሀገሪቱን በተለይም የገጠሩን አካባቢ የውሃ ፍላጎት በመሸፈን ድርሻ ያለው ከከርሰምድር ውስጥ የሚገኘው ውሃ ነው።ለአጠቃቀም ቀላልም መንገድ ነው። የገፀምድር ውሃን ወይንም ወንዝ ጠልፎ ከአንድ ቦታ ወደሌላ አጓጉዞ መስኖ ለመጠቀም በጊዜ፣በጉልበት፣በወጭ፣በጥራትም ጭምር አዋጭ አይደለም።ውሃን ከማዳረስ አንጻር የከርሰምድር ውሃ በቁፋሮ በማውጣት መጠቀም በጣም ቀላል፣ተመራጭና አዋጭ ነው።ይሁን እንጂ በትኩረት ማነስ ያለው ተጠቃሚነት አናሳ ነው።ዘላቂ ጥቅም በሚያስገኘው ላይ ሳይሆን በፊትለፊት የሚገኘውንና ወቅታዊ ገበያው ላይ ትኩረት ማድረግ በስፋት ይስተዋላል።የከርሰምድር ውሃ ከላይ የሚታይ አለመሆኑም ዕቅድ የሚያወጣው አካል በማያየው ነገር ለማቀድ ድፍረት ያጣል።እንዲህ ያለው አካሄድ ወይም ምልከታ ያለውን ሀብት ለማስተዋል ተግዳሮት ፈጥሯል።በገፀምድር ላይ ባለሙያ የሆነ ሰው ስለከርሰምድር ውሃ ላይጨነቅ ይችላል።የውሃ ልማቱ በሁሉም አቅጣጫ እንዲቃኝ ከተፈለገ የተቀናጀ የውሃ ልማት የሚከናወንበትን ሥርአት መዘርጋት ያስፈልጋል።በዘርፉ የሰለጠኑ ባለሙያዎች ቢኖሩም ጥቂት ናቸው።በአጠቃላይ የከርሰምድር ውሃ በሚፈለገው ልክ ጥቅም ላይ እንዳይውል ያደረገው የቴክኖሎጂ አለመኖርና የመዋዕለ ነዋይ እጥረት ጉዳይ ሳይሆን የትኩረት ማነስ ነው።በአብዛኛውም በዘርፉ ሲከናወን የቆየው ለመጠጥ አገልግሎት ለሚውል እንጂ በመስኖ ለሚከናወን ልማት አልነበረም።እንደሀገር ምርትና ምርታማነትን በማሳደግ በምግብ እህል እራስን ለመቻል ከተፈለገ ግን የከርሰምድርንና የገፀምድር የውሃ ሀብት በተቀናጀ መልኩ ማከናወን ይጠበቃል።
ዶክተር ፍቃዱ እንደሚሉት በተለይም የዝናብ ወቅትን ጠብቆ የሚከናወን የመኸርና የበልግ የሰብል ልማት ግብርና እንዲሁም የአትክልትና ፍራፍሬና ሌሎች ልማቶች ለማከናወን የከርሰምድር ውሃን መጠቀም ይመረጣል።የአነስተኛ የግብርና ሥራንም ያበረታታል።በከተማም ሆነ በገጠር ማህበረሰቡ በደጃፉ ላይ ጉድጓድ ቆፍሮ በቀላሉ ውሃ በማውጣት የተለያዩ ልማቶችን ማከናወን ይችላል።በአንዳንድ ቦታም እንደውሃው መገኘት መጠን ጥልቅ ጉድጓድ በመቆፈር ውሃ በማውጣት ሰፋፊ እርሻዎችን ማልማት ይቻላል።ለአብነትም እንደ ቆቦ አካባቢ ፕሮጀክቶችን በመቅረጽ በከርሰምድር ውሃ ሰፋፊ ልማቶችን ማከናወን ይቻላል።ከቤተሰብ ጀምሮ እስከ ከፍተኛ ደረጃ የደረሰ ልማትን በማከናወንና ለመጠጥም በመጠቀም ግብርናውን ከተለመደው አሰራር በማውጣት ምርትና ምርታማነት እንዲጨምር ማድረግ የሚቻልበትን ዕድል መፍጠር ይቻላል።
በኢትዮጵያ አሁን ባለው ተጨባጭ ሁኔታ የከርሰምድር ውሃን ጠቅም ላይ ከማዋል ይልቅ የገፀምድር ወይንም የወንዝ ውሃን ጠልፎ መጠቀም ላይ ነው ትኩረቱ።በቀላሉ ስለሚገኝ ብቻ የወንዝ ውሃ ላይ ትኩረት ማድረግ ተጠቃሚነትን ይቀንሳል።የዚህ አይነቱ አካሄድ የውሃ እጥረት ያለባቸውን አካባቢዎች ከመጉዳቱ በተጨማሪ ፍትሐዊ የሆነ ልማት እንዳይኖር ያደርጋል።የከርሰምድር ውሃ ሀብትን ማዕከል ያደረገ የልማት ዕቅዶችን ወይንም ፕሮጀክቶችን መንደፍ ክፍቶችን ለመቅረፍ ያግዛል።
ዶክተር ፍቃዱ የሌሎች ሀገሮችን ተሞክሮ ዋቢ አድርገው እንዳስረዱት፤የከርሰምድር ውሃን በመጠቀም ልማታቸውን እያፋጠኑ ከሚገኙ ሀገራት ህንድ ትጠቀሳለች።በሀገሪቱ የከርሰምድር ውሃ በቅርብ ርቀት ላይ የሚገኝ ሲሆን፣ህዝቡ በአካባቢው የልማት ሥራ በማከናወን በቀላሉ በምግብ እህል እራሳቸውን ችለዋል።የሌሎች የዓለም ተሞክሮም ይህንኑ ያጠናክራል።ኢትዮጵያም ይህን መልካም ተሞክሮ በመቅሰም መጠቀም ይኖርባታል።ይህ ሲባል ግን ኢትዮጵያ የከርሰምድር ውሃ ሀብትን አትጠቀምም ማለት አይደለም።ጥቅም ላይ እየዋለ ቢሆንም በሚፈለገው ደረጃ ግን አመርቂ አይደለም። የግብርና ትራንስፎርሜሽን ኤጀንሲ በሚል ስያሜ የተቋቋመው ድርጅት በሀገሪቱ በቅርብ ርቀት ላይ ውሃ የሚገኝበትን ቦታ ለመለየት ሰፊ የዳሰሳ ጥናት መካሄዱን ዶክተር ፍቃዱ ያስታውሳሉ።ጥናቱ የት እንደደረሰ መረጃው ባይኖራቸውም ጥናቱ አስፈላጊ እንደሆነና መጠናከር እንዳለበትም ያምናሉ።ጥናት ማካሄድ ብቻ ሳይሆን፣የጥናት ግኝቱ ወደ ተግባር መለወጥ ይኖርበታል።በጥናት ግኝቱ መሰረት ማህበረሰቡ ተጠቅሞ ኑሮውን ሲለወጥና እንደሀገርም ውጤቱ ከፍ ብሎ ሲመዘገብ ነው ጥቅሙን ማወቅ የሚቻለው ሲሉም አስረድተዋል።
ዶክተር ፍቃዱ የከርሰምድር ውሃን ላለመጠቀም እንደክፍተት ያነሱት ቅንጅታዊ አሰራር አለመኖር አንዱ ምክንያት ሲሆን፣ሌላው በውሃ ላይ የሚካሄደው ጥናትም በገፀምድር በሚገኘው ላይ ትኩረት የማድረግ ሁኔታ ይስተዋላል።ነገር ግን ያለውን የሀብት አቅም ለይቶ ጥቅም ላይ ለማዋል በጥናትና ምርምር የታገዘ ሥራ መሥራት፣መረጃንም በማደራጀትና ትኩረት ሰጥቶ መንቀሳቀስ ይጠበቃል።
ሀብቱን ለይቶ ጥቅም ላይ እንዲውል ማድረግ የአንበሳውን ድርሻ የሚወስደው መንግሥት ቢሆንም፣የዘርፉ የሰለጠኑ ባለሙያዎች፣እንዲሁም እንዲህ ያሉ ኢኮኖሚያዊና ማህበራዊ ፋይዳ ያላቸውን በተለይም የምድር በረከቶች በጥናትና ምርምር በማመላከትና ፖሊሲ አውጭዎችም ጥናቱን መሠረት አድርገው እንዲንቀሳቀሱ ከፍተኛ የትምህርት ተቋማት ሚና እንዳላቸው ይታወቃል።በዚህ ረገድ የትምህርት ተቋማት ሚናቸውን እንዴት እየተወጡ ነው ለሚለው ጥያቄ ዶክተር ፍቃዱ ከፍተኛ የትምህርት ተቋማትን ጨምሮ በዘርፉ ላይ በሚሰሩ የተለያዩ ተቋማት ሰፊ የምርምር ሥራ ተሰርቷል ብለው ያምናሉ።በተለይም የከርሰምድር የውሃ ሀብት በማጥናት ረገድ ቀድሞ ጂኦሎጂካል ሰርቬይ የሚባል ተቋም ባዋቀረው የጥናት ቡድን በሀገር ደረጃ መነሻ የሚሆን የዳሰሳ ጥናት በማካሄድ መረጃውን ሰንዶ ለመያዝ ያደረገውን ጥረት አስታውሰዋል።የውሃ ሀብት ሚኒስቴርም በተመሳሳይ በራሱ ይደረግ የነበረውን እንቅስቃሴም ጠቅሰዋል።በተጨማሪም በተባበሩት መንግሥታት የህፃናት አድን ድርጅት(ዩኒሴፍ) ሥር የሚገኝ የውሃ ዘርፍና ሌሎችም ተቋማት ከዩኒቨርስቲዎች ጋር በመተባበር ሀገራዊ ይዘት ያላቸው ሰፋፊ መረጃዎችን ማደራጀታቸውን ገልጸዋል። ምርምሮችን መሠረት አድርጎ መተግበሩ ላይ ግን ተከታታይነት ያለው ሥራ ተሰርቷል የሚል እምነት የላቸውም።ሥራዎቹ የተቆራረጡ እንደሆነ ይገልጻሉ።አሁንም ቢሆን አልረፈደም የሚሉት ዶክተር ፍቃዱ፤ ቀድሞ የተሰሩትንም ሆነ አዲስ የጥናት ግኝቶች በአንድ ላይ ሰንዶ ጥቅም ላይ እንዲውል ማድረግ ይገባል ሲሉ ምክረሀሳብ ሰጥተዋል።እንደ ዶክተር ፍቃዱ ገለጻ ኢትዮጵያ ያላት የከርሰምድር ውሃ ሀብት መጠን በተለያየ ጊዜ የተለያየ መረጃ ነው የወጣው።ይህን የተለያየ የቁጥር መረጃ አጥርቶ ማደራጀት ያስፈልጋል።
በዘርፉ ባለሙያ ከማፍራት አንጻር በተለይም የከፍተኛ ትምህርት ተቋማትን ሚና በተመለከተ ዶክተር ፍቃዱ እንዳብራሩት፤ ከመጀመሪያ ዲግሪ እስከ ሶስተኛ ዲግሪ በዘርፉ በሀገር ውስጥ ትምህርት እየተሰጠ ይገኛል።በተለይም በአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ በከርሰምድር ውሃ ላይ በሶስተኛ ዲግሪ ባለሙያዎች ማፍራት ከጀመረ ወደ ሰባት አመት ሆኖታል።አሁን እያጋጠመ ያለው ባለሙያ ማፍራት ሳይሆን ፍልሰት ነው።የተማሩና ልምድ ያካበቱ ባለሙያዎች በሀገር ውስጥ ከመሥራት ይልቅ በተለያዩ ሀገሮች መሥራት ይመርጣሉ።በአሁኑ ጊዜም በሙያው ቀዳሚ የሆኑና በፕሮፌሰርነት ማዕረግ የሚገኙት በደቡብ አፍሪካና ቦትስዋና ሀገራት ውስጥ እየሰሩ ይገኛሉ።እርሳቸውም በቅርበት የሚያውቋቸው የዘርፉ ሶስት ባለሙያዎች በደቡብ አፍሪካ ሀገር ውስጥ እየሰሩ ይገኛሉ።የፍልሰቱ መንስኤም ከትኩረት ማነስ ጋር ይያያዛል።ባለሙያዎቹ በሙያቸው በሀገራቸው ውስጥ ምቹ ሁኔታ ተፈጥሮላቸው እንዲሰሩ አልተደረገም።ፍልሰቱን ለማስቀረት የተደረገ ጥረት አለመኖሩም አንዱ ማሳያ ነው።
የከርሰምድር የውሃ ሀብት ከገፀምድሩ የተሻለ ነው እየተባለ ነገር ግን የዝናብ ማነስና የውሃ እጥረት ችግር ይነሳል።የዛፍ ችግኝ ተከላም በስፋት እንዲከናወን ይመከራል።ይሄ ከሀብቱ ጋር እንዴት ይጣጣማል።ለዶክተር ፍቃዱ ጥያቄውን አነሳንላቸው።በምላሻቸውም የከርሰምድርና የገፀምድር ውሃ እንዲሁም ዝናብ የሚነጣጠሉ አይደሉም።ምክንያቱም አንዱ ሌላውን ይመግባል።ለምሳሌ በበጋ ወቅት ዝናብ የለም።ወንዞች ግን አሉ።ወንዞቹ የመኖራቸው ሚስጥር ከከርሰምድር ውስጥ በምንጭና በተለያየ መንገድ ውሃ ወጥቶ ወንዝ ይሆናል።ገፀምድር ላይ ያለው ውሃ ደግሞ በትነት ወደላይ ወጥቶ በዝናብ መልክ ወደ ምድር ወይንም ከርሰምድር ይመለሳል ወይንም ይገባል።መልሶ ወደ ወንዝነት ይቀየራል።ሂደቱ ዑደት ነው።ዑደቱን የተመጣጠነ ለማድረግ፣የውሃ ዑደቱ ቀጣይነት እንዲኖረው የዛፍ ችግኞችን ማልማት ያስፈልጋል። ዛፍ ዝናብ እንዲፈጠር የማድረግ አቅም ከመፍጠሩ በተጨማሪ የአፈር መሸርሸርንም ይከላከላል።የአፈር መሸርሸር ማቆም ከተቻለ ዝናቡ ቀጥታ ወደ ከርሰምድር ይገባል።በዝናቡ ወደ ውስጥ የገባው ውሃ በበጋው ወቅት ወደ ወንዝነት ይቀየራል።ዘለቄታውንም ያረጋግጣል።
ለምለም መንግሥቱ
አዲስ ዘመን ጥቅምት 5 ቀን 2014 ዓ.ም