ወጣት ሰሚራ መርጋ ትባላለች ተወልዳ ያደገችው ቱሉ ቦሎ በምትባል አንዲት የገጠር ከተማ አቅራቢያ በምትገኝ ትንሽ መንደር ነው። እናትና አባቷ አርሶ አደሮች ናቸው። ነገር ግን ገና በልጅነቷ ተለያይተው ስለነበር የእሷ እድገት የነበረው ከአያቷ ጋር ነበር። ሰሚራ ለቤተሰቧ የመጀመሪያ ልጅ ስትሆን ከሷ በታች የተወለዱ ሶስት ወንድምና ሁለት እህቶችም አሏት።
የገጠሩ ህይወቷ ብዙ ፈተናዎች ስለነበሩትም ገና በልጅነት እድሜዋ ነበር ወደ አዲስ አበባ በመምጣት ሳሪስ አካባቢ በተለምዶ ኤርምያስ ሰፈር የሚባለው በቤት ሰራተኝነት በመቀጠር ኑሮዋን የመሰረተችው። በረጅም ጊዜ ሃሳቧም ለቤተሰቦቿ በተለይ ለእህት ለወንድሞቿ አንዳች ነገር የመዋል እቅድ ስለነበራት ቀን ቀን በቤት ሰራተኝነት እየሰራች ማታ ማታ ትምህርቷን መከታተል ጀምራ ነበር። ሰሚራ አገሯ እያለች እስከ አራተኛ ክፍል የተማረች ቢሆንም በኦሮሚኛ ቋንቋ ስለነበርና በወቅቱ ደግሞ በ2002 ዓ.ም በአዲስ አበባ በኦሮምኛ ቋንቋ የሚያስተምር ትምህርት ቤት ባለመኖሩ እንደአዲስ ከአንደኛ ክፍል ለመጀመር ትገደዳለች።
በዚህ ሁኔታ ውስጥ እያለች ተቀጥራ በምትሰራበት ቤት ይመጣ ከነበረ አንድ ትልቅ ሰው ጋር ግንኙነት ትጀምራለች። በወቅቱ ስለራሱ ከነገራት ውጪ የምታውቀው ነገር አልነበራትም። ግንኙነታቸው እየተጠናከረ መጥቶ የምትሰራበትን ቤት ለቃ እሱ ቤት ገብታ አንድ ልጅ ከወለደችለት በኋላ ግን ከዚህ ቀደም ትዳር የነበረውና ወንድ ልጅም እንዳለው ታውቃለች። ነገር ግን እሱ ከበፊት የትዳር አጋሩ ጋር ባለመስማማቱ ትታው እንደጠፋች አሁን የት እንዳደለች እንደማያውቅና በፍርድ ቤት አሳውጆ ፍቺ መፈጸሙንና የእሷ ፋይል የተዘጋ መሆኑን ያስረዳታል። ስለዚህም የእሷ ነገር ያበቃለት በመሆኑ እንደአዲስ እሷን አግብቷት መኖር እንደወሰነና እቤቱ እንዳመጣትም ይነግራታል። ከተወሰነ ጊዜ በኋላ ደግሞ የቀድሞ ሚስቱ ከኢትዮጵያ ውጪ በመሆኗ የእሱን የመጀመሪያ ልጁን ይዛለት ኑሯቸውን ይጀምራሉ። በዚህ ጊዜ የሆነ የማይስማማት ነገር እየተፈጠረ ቢሆንም ሰሚራ አማራጭ ስላልነበራት አብራው መኖሩን ትቀጥላላች።
ከትንሽ ጊዜ በኋላ ግን ነገሮች ጠንከር ብለው መስመር እየሳቱ መምጣት ይጀምራሉ። ባለቤቷ ቀስ በቀስ የቤት ወጪ መስጠቱን እየቀነሰ መጥቶ ጭራሽ ያቆመውና ካለፍ አገደም ብቻ የተወሰነ ሳንቲም ይወረውርላት ይጀምራል። እሷ መሄጃም ሆነ ጉዳቷንም የምታዋየው የቅርብ አይዞሽ ባይ ዘመድ ስላልነበራት የሆዷን በሆዷ ይዛ የጎዳና ላይ የእትክልት ጉሊት ንግድ ትጀምራለች። ይህን በማድረጓ በተወሰነ ለእሷና ለልጆቿ የሚጎረስ ነገር ማግኘት ብትችልም ስራዋ ግን ሌላ ችግር ይዞባት ይመጣል። ባለቤቷ በየቀኑ ስራ ቦታ ከሌላ ወንድ ጋር ግንኙነት ጀምረሻል በሚል ሰበብ በጭቅጭቅ የጀመረውን ነገር ወደ ዱላ ያሳድገውና በገባች በወጣች ቁጥር ይቀጠቅጣት ይጀምራል።
ስራውን እንዳታቆመው እሱ የቤት ኪራይ የሚያገኝ ቢሆንም እየቃመ ሺሻና ሲጋራ እያጨሰበት አንዳንድ ጊዜም እየጠጣበት ስለሚጨርሰው እሷና ልጆቿ በርሃብ እንዳያልቁ በማለት ዱላውን ችላ ስራዋን በመቀጠል የቤት ወጪዋን ለመሸፈን ትገደዳለች። ይህም ሆኖ ነገሩ እየተካረረ ሲመጣ ምክንያቱ ባይገባትም ጭቅጭቁ ካለ ምክንያት ባያት ቁጥር እየሆነባት ይመጣል። ይደርስባት የነበረው ዱላ ግን በጣም ተደጋጋሚ ስለነበር አንድ ጊዜ ጆሮዋ ላይ፣ አንድ ጊዜ እጇ ላይ ከፍተኛ ጉዳት ደርሶባት እየተሰፋችና ከፍተኛ የህክምና ክትትል እየተደረገላት ድናለች። ነገር ግን እከሌ ጋር ልደበቅ የምትለው ዘመድ ስላልነበራት የሚደርሰውን ሁሉ ደጋግሞ ከመቀበል ውጪ ምርጫ አልነበራትም። አንዳንድ ጊዜ ስቃዩ ሲበረታባት ጨከን ብላ ወደ ፖሊስ ጣቢያ ለመሄድ ብትሞክርም አንዳንድ ጊዜ በባልና ሚስት ጉዳይ አንገባም፣ በሌላ ጊዜ ተስማሙ እያሉ ስለሚመልሷት ተስፋ ቆርታ ለመቀመጥ ትገደዳለች።
በመጀመሪያ አካባቢ የባለቤቷ ፀባይ እየተቀየረ ሲመጣ አማራጭ አድርጋ የነበረው እናቱን እህቶቹንና ወንድሞቹን አማላጅ በመላክ ለማስመስከር፣ ለማስገሰጽ ነበር። እነሱ ግን ይህ ባህሪው ከልጅነቱ ያደገበት በመሆኑ ምንም እንኳን እሷ አለማጥፋቷን ቢረዱም ሊያደርጉት የሚችሉት ነገር እንደሌለ ይገልጹላታል። እናትየውም በተደጋጋሚ ካዋዩዋት በኋላ «የልጄ ጥፋት መሆኑን አውቃለሁ፣ እኔ እሱን ባጠባሁበት ጡት አንቺን መርቄሻለሁ፣ ከዚህ በኋላ ምንም ብታደርጊም አልፈርድብሽም» ብለው ያሰናብቷታል። አንድ ሁለቱንም ይቀርባቸው የነበረ ጓደኛውም በተደጋገሚ ለመምከር ከጣረ በኋላ ከአቅሙ በላይ በመሆኑ የፈለገችውን እንድትወስን ነግሯት ይሄዳል።
በዚህ ሁኔታ ውስጥ እያለች በአስር አመት ጊዜ ውስጥ አንድ ወንድ፣ ሶስት ሴት ልጆችን ወልዳ እያሳደገች ነበር። ከዓመት በፊት ግን በተደጋጋሚ በደረሰባት ድብደባ ጭንቅላቷ ውስጥ የደም መፍሰስ በመከሰቱ ራሷን ስታ ሆስፒታል ለመግባት ትገደዳለች። በወቅቱ ሆስፒታል ይዟት የሄደው ራሷን ስታ በመሆኑ የተከሰተውን ነገር አታስታውስም ነበር። ነገር ገን ተከታታይ ህክምና ከተደረገላት በኋላ የነርቭ ችግርና የአጥንት መሳሳት ስለገጠማት ረዘም ላለ ጊዜ ህክምናዋን መከታተል እንዳለባት ይነገራታል። ይህ ነገር የተፈጸመው አራተኛ ልጇን ወልዳ ገና የሁለት ወር አራስ እያለች ስለነበር ከነቃችም በኋላ ትኩረቷ የነበረው ወደ ልጇ ነበር። በዚህ ጭንቀት ውስጥ እያለች ባለቤቷ ለሀኪሞቹ አንዴ ከጎዳና ነው ያነሳኋት፣ አንዴ ደግሞ የማሳክምበት ብር የለኝም ሲል ቆይቶ በጊዜ ድና የመመለሷ ነገር የማይሆን መሆኑን ሲረዳ እዛው በተኛችበት ጥሏት እብስ ብሎ ይቀራል።
በዚህ ጊዜ ለራሱም በጥበቃ ሰራተኝነት ከእጅ ወደ አፍ ይኖር የነበረው ወንድሟ ብቻ ከጎኗ በመሆን ይረዳት ይጀምራል። ወንድሟ እንደምንም የቻለውን ሁሉ ሲያደርግላት በተለይ ለአንዳንድ ምርመራዎች ወደ ውዳሴ ዳያግኖስቲክ ስትላክ ከሰው እየተበደረ ሲያሳክማት ቆይቶ ነገሩ ከአቅሙ በላይ እየሆነበት ይመጣል። ከዚህ በኋላ ደግሞ በሆስፒታሉ የነበሩ የማህበረሰብ አገልግሎት ሰጪ ሰራተኞች ትብብር እያደረጉላት ህክምናዋን በመከታታል በተወሰነ ደረጃ ለማገገም ትበቃለች። ህመሙ ሙሉ ለሙሉ የመዳን እድሉ ጠባብ በመሆኑ የምትወስደው መድሃኒት ሊቀንስ ይችል ይሆናል እንጂ መቋረጥ የለበትም። በመሆኑም የጀመርሽውን ክትትል መቀጠል አለብሽ ብለው ሀኪሞች ይነግሯታል።
በዚህ ሁኔታ ከጊዜ ብዛት ከህመሟ እያገገመች ብትመጣም ሌሎች ሶስት ተደራራቢ ችግሮች አይናቸውን አፍጠውባት ይመጡባታል። የመጀመሪያው ባለቤቷ አንዳንድ ጊዜ እየመጣ ይዝትባት የነበረ መሆኑ ሲሆን ይህም በሆስፒታሉ ዶክተሮች ማስፈራሪያ እንዲቀር ይደረግላታል። ሁለተኛው ነገር ግን በዚሁ በህመም ውስጥ እንዳለች ወትሮም ያማቸው የነበሩት እኗቷን ማረፋቸውን ትሰማና ምንም የሚያድርጉላት ባይሆንም እናት አለችኝማለት እንድማትችልና የታናናሾቿም ሃላፊነት ሙሉ ለሙሉ እሷን ብቻ እንደሚመለከት ትረዳለች። ሶስተኛው ነገር ግን ከምንም በላይ ያስጨነቃትና ለዳግም ህመም የዳረጋትም ባለቤቷ በልጆቿ ላይ ያደረገውን ነገር መስማቷ ነበር።
እሷ በሆስፒታል እያለች የምታውቀው ልጆቿ ከአባታቸው ጋር እቤት መሆናቸውን ነበር። ነገር ግን አንድ ቀን ስለልጆቿ ስትጠይቅ አባታቸው ለትልቋ ልጅ ትንሿን አሳቅፎ፤ አንዱንም አስከትሎ ከቤት አባሯቸው፤ ጎዳና ወጥተው እንደነበርና በአሁኑ ወቅት ግን በፖሊስ ተነስተው ክበበ ጸሀይ የህጻናት ማቆያ ውስጥ እንደሚገኙ ይነገራታል።
በዚህ ወቅት ጤናዋ ትንሽ የተመለሰላት ቢሆንም ራሷን ችላ መንቀሳቀስ ስለማትችል ሁሉንም ነገር የምታደርገው በሰው ድጋፍ ነበር። በዚህ ሁኔታ ውስጥ እያለች ምንም ልታደርግለቸው እንደማትችል ስለገባት ዝም ብላ በሽታዋን ማስታመም ትቀጥላለች፤ እንዳሰበችውም ከተወሰነ ወራት በኋላ ጤናዋ ሙሉ ለሙሉም ባይሆን በተወሰነ ደረጃ ይመለስላትና ከሀኪም ቤት ትወጣለች።
በዚህ ጊዜ ልጆቿ ወደ ክበበ ጸሀይ ሲገቡ ጀምሮ ይከታተል የነበረው አንድ የበጎ አድራጎት ድርጅት የተወሰነ ድጋፍ ያደርግላትና ከአምስት ወር ቆይታ በኋላ ልጆቿን ከማቆያ አውጥታ በድጋሚ የጉሊት ንግድ እየሰራች ማሳደጉን ትቀጥላለች። በዚህ ሁኔታ መኖር የጀመረችው የጤናዋ ነገር ደፍሮ የሚያንቀሳቅሳት ስለሆነ ሳይሆን ልጆቿ ከእሷ እንዳይለዩ ስለወሰነች ብቻ ነበር።
በዚህ አይነት ከሀኪም ቤት ከወጣች በኋላ ኑሮዋን ያደረገችው ቦሌ ቡልቡላ አካባቢ የነበረ ቢሆንም አራት ልጆች በመያዟ ሰፊ ቤት ትፈልግ ስለነበርና የነበረችበት ዋጋውም ስለተወደደባት ወደ ዳር ለመውጣት ትወስናለች። እንዳሰበችውም ታገኝና ሰፈራ የሚባል አካባቢ አዲስ የተሰራ ቤት ተከራይታ መኖሯን ትቀጥላለች። ባለቤቷ አንዳንድ ጊዜ ሲያገኛት እቤት ተመለሺ እያለ ሲያስፈራራት ስለነበር ያለሁበት ይመጣ ይሆናል የሚል ስጋት ስለነበራት ለአካባቢው ጥበቃዎች አሳውቃ ቢያንስ በአካል ይደርስብኛል ከምትለው ስጋት ለመላቀቅ ትበቃለች።
ከዚህ ውጪ ከባለቤቷ ጋር ተገናኝተው የማያውቁ ቢሆንም ባለበቤቷን የመጀመሪያ ሚስቱ እንደከሰሰችውና እሷም በዚሁ አጋጣሚ ለልጆቿ አንዳንድ ነገር እንድታገኝ ጥያቄ ማቅረብ እንዳለባት ተነግሯት በፍርድ ቤት ክስ ትመሰርታለች። ነገር ግን በፍርድ ሂደቱ ምስክሮች ከተሰሙ በኋላ ለእሷ ግልጽ ባልሆነላት ምክንያት ዳኛው መገኘት ስላልቻሉ እስኪመጡ አልያም ዳኛ እስኪቀየር እንድትጠብቅ ተነግሯት እየጠበቀች ትገኛለች።
በዚህ ጊዜ ተቀራርበው ለመነጋገር ባይችሉም ለመጀመሪያ ጊዜ የመጀመሪያ ባለቤቱን ፍርድ ቤት አግኝታታለች። የመጀመሪያው የዘጠኝ ዓመት ልጇ ትምህርት ጀምሮ የነበረ ቢሆንም በተፈጠረው ነገር ትምህርቱን አቋርጦ ቆይቷል። ዘንድሮ ግን ሶስቱንም ትምህርት ለማስጀመር አስመዝግባ እየተጠባበቀች ትገኛለች።
ይህም ሆኖ ሰሚራ የወደፊት ሀይወቷ ነገር ዛሬም እጅግ እያሳሰባት ይገኛል። የመጀመሪያው ለህክምና ክትትል፣ ለምርመራ በተለይ በየወሩ ያለማቋረጥ ለምትገዛው መድሃኒት የሚሆን በቂ ገንዘብ እያገኘች አይደለም። የጤና መድህን ሽፋን ያላት ቢሆንም በቂ ግን አልሆነላትም።
ሁለተኛው ነገር ደግሞ በአንድ በጎ አድራጎት ድርጅት እየተደረገላት ያለው ድጋፍ ሙሉ ለሙሉ ወጪዋን የሚሸፍን ባለመሆኑ አንዳንድ የጉልበት ስራዎችን እየሰራች ጉድለቷን ለማሟላት ትጥራለች። ሀኪሞቹ ደግሞ የጉልበት ስራ መስራት እንደሌለባትና የምትጨናነቅ ከሆነ ህመሙ እየተባባሰ በመምጣት አካለ ጎዶሎ ሊያደርጋት እንደሚችል ነግረዋታል። ሰሚራ ያለችበት ሁኔታ ግን ይህንን ለማድረግ የሚፈቅድ አይደለም።
እስካሁንም ይከዚህ የበጎ አድራጎት ድርጅት የሚደረግላት ድጋፍ ምርኩዝ እየሆናት እንጂ የቤት ኪራዩ አጠቃላይ የኑሮ ወድነቱ እንደሷ ላለው አቅመ ደካማ እንኳን አራት ልጅ ይዞ ለማስተዳደር ይቅርና ለአንድ ራሷም የሚገዳደራት ነው። ልጆቿን ከክበበ ጸሀይ ማቆያ ባወጣችበት በዛ የጭንቅ ጊዜ አንሶላ፣ ብርድ ልብስ፣ ፍራሽ፣ ዳይፐር፣ የህጻን ወተት፣ ዘይት፣ ጤፍና ለስራ መነሻ የሚሆን ብር፤ እንዲህም በክትትል ከዛም በኋላ የተለያዩ ድጋፎች እንዳደረጉላት የምትናገረው ሰሚራ ተቋሙ ዛሬ ላለችበት ሁኔታ ከፈጣሪ ቀጥሎ መሰረት እንደሆኗትም ትናገራለች።
ራስወርቅ ሙሉጌታ
አዲስ ዘመን መስከረም 5/2014