የኢትዮጵያና ኢትዮያውያን ብቻ የሆነችው አስራ ሦስተኛዋ የጳጉሜን ወር ከፊት አስቀድሞ የሚመጣው መስከረም ከወራት ሁሉ ልዩ ግርማ ሞገስ አለው። ጋራ ሸንተረሩ በአደይ አበባ ደምቆ፣ በአረንጓዴ ልምላሜዎች ታጅቦ ጨለማውን ክረምት አልፎ ብቅ ሲል ሁሉም ሰው በተስፋ ልቡ ይሞላል። ከቁዘማ ይወጣል፤ የናፈቀውን ፀሐይ በስስት እያየ የሌለው እንደሚኖረው፤ ያጣ እንደሚያገኝ ፤ የወደቀ እንደሚነሳ ፤የሠራም እንደሚበለጽግ አስቦ በተስፋ ተሞልቶ ያሰበውን ለማሳካት የመጀመሪያ ዕቅዱን የሚጀምረው ያኔ ነው በወርሃ መስከረም መጀመሪያ።
የዕውቀት ሁሉ መገብያ የሆነው ትምህርት ቤት በአዲስ መንፈስ የሚጀመረው መስከረም ሲጠባ ነው። ሱስ ውስጥ ያለውም በአዲስ ዓመት መስከረም ላይ ለማቆም ዕቅድ ያወጣል፤ አዲስ የንግድ ሥራን ለመጀመርም ይሁን ቀድሞ የነበረውን ሥራ በአዲስ መልክ አሻሽሎ ለማስቀጠል፤ ውጤታማ ለመሆን የወራት ንጉሥ የሆነው መስከረም በጉጉት ይጠበቃል። ‹‹መስከረም ሲጠባ አደይ ሲፈነዳ እንኳን ሰው ዘመዱን ይጠይቃል ባዳ›› የተባላለትም ለዚሁ ይመስላል። ውሃ ያቆራረጠው የከተማና የገጠሩ ነዋሪ የሚገናኘው በዚሁ ወቅት በመሆኑ።
መቼም አሮጌ ዓመት አልፎ በአዲስ ዓመት ሲተካ አሮጌ የሆኑ ነገሮች ሁሉ ከዙሪያችን በነው የሚጠፉና አዳዲስ ሁነቶች የሚተኩ ቢመስልም ለአዲስ ዓመት አዲስ ዕቅድ የራስ ጥንካሬና ፍላጎት ወሳኝ መሆኑ ይታመናል። ብዙዎች በአዲስ ዓመት አዲስ አስተሳሰብና አዲስ አሠራር በመከተል በተሰማሩበት ዘርፍ ሁሉ ስኬታማ ለመሆን ፍላጎት ያላቸው ስለመሆኑ ከቃላቸው ይደመጣል። በድርጊትም ይስተዋላል።
ትናንት በተሰናበትነው አሮጌው ዓመት 2013 ዓ.ም ውስጥ መንግሥትን ጨምሮ እያንዳንዱ ኢትዮጵያዊ በብዙ ተፈትኗል። ፈተናዎቹም ኢኮኖሚያዊ፣ ማህበራዊ፣ ፖለቲካዊና ስነልቦናዊ ቀውስ በዜጎች ላይ መፍጠር የቻሉ ቢሆንም ሰዎች ያለተስፋ መኖር አይችሉምና ነገን ተስፋ በማድረግ በተለይም የዛሬዋን አዲስ ዓመት መስከረም 1 ቀን 2014 ዓ.ም ብዙዎች ልብን በሚያሞቅ አዲስ ተስፋ የተቀበሉት ስለመሆኑ ጥርጥር የለውም ቢባል ማጋነን አይሆንም።
ምክንያቱም ኢትዮጵያን ለማስተዳደር በትረ ስልጣኑን በተጠናቀቀ ማግስት ኢትዮጵያውያንን በመከፋፋል ሀገር የመበተን ሴራውን ለ27 ዓመታታ የጎነጎነውና የተንኮል ድሩን ሲያደራ የከረመው አሸባሪው የህውሓት ቡድን ዛሬ መንግሥት በነበረበት ሀገር ውስጥ የተራ ሽፍታነት ቦታን እንኳ አጥቶ መድረሻ እየጠፋው ይገኛል። ቡድኑ በከፈተው ጦርነት ኢትዮጵያውያን መተኪያ የሌለው ክቡር ህይወታቸውን ጨምረው ብዙ ዋጋ ቢከፍሉም ነገን ተስፋ በማድረግ ከመንግሥት ጎን ተሰልፈው ደጀንነታቸውን እያስመሰከሩ ነው።
ኢትዮጵያውያን መሰረታዊ የሀገር ጠላት የሆነውን አሸባሪው የህውሓት ቡድንን ለይተው እየተፋለሙ ባሉበት ማግስት የተቀበሉት አዲስ ዓመት በርካታ አዳዲስ ድሎችንና ተስፋዎችን ይዞ ስለመምጣቱ የተጀማመሩ ዘርፈ ብዙ የልማት ሥራዎች ምስክሮች ናቸው። ምንም እንኳን መንግሥት ሰፋፊ የመሰረተ ልማት ሥራዎችን እየተገበረ ባለበት ወቅት አሸባሪው የህውሓት ቡድን ሀገርን ለማፍረስ የዘረጋው የጥፋት እጁን ቢሰነዝርም ማደናቀፍ ካልሆነ በስተቀር ፍጹም ሊያስቆመው የማይችል መሆኑን መረዳት ችሏል። ይህን እውነት ቢያንቀውም ውጦታል።
አሸባሪው የህውሓት ቡድን በሀገር ላይ ባደረሰው ጥፋት ቁጭት የገባው ኢትዮጵያዊ በተሰማራበት የሥራ ዘርፍ ሁሉ በከፍተኛ ሞራልና ተነሳሽነት ኃላፊነቱን ለመወጣት ጥረት እያደረገ ይገኛል። ይህም ጠቅላይ ሚኒስተር ዶክተር ዐብይ አሕመድ እንዳሉት፤ ‹‹ኢትዮጵያውያን እያሉ ኢትዮጵያ አትፈርስም›› የሚለው አባባል ዕውን መሆን ችሏል።
ለውጥ በመጣ ሦስት ዓመታት ውስጥ መንግሥት አበረታችና ተስፋ ሰጪ የሆኑ የልማት ሥራዎችን እና የተለያዩ ፕሮጀክቶችን ቀርጾ ለዜጎች ተደራሽ ለማድረግ ጥረት ሲያደርግ እንደነበር ይታወሳል። በተለይም በመዲናዋ አዲስ አበባ እንዲሁም በክልል ከተሞች ጭምር ሰፊ ክፍተት በሚታይበት በቤት ልማት ዘርፍ ያለውን ችግር ለመቅረፍ ከመቼውም ጊዜ በበለጠ መንግሥት የተለያዩ አማራጮችን ተጠቅሞ መኖሪያ ቤትን ለዜጎች ተደራሽ ለማድረግ ጥረት እያደረገ ይገኛል።
አቅርቦትና ፍላጎቱ ‹‹ፍየል ወዲህ ቅዝምዝም ወዲያ›› ሆኖበት ከሁለት አስርት ዓመታት በላይ ያስቆጠረው የጋራ መኖሪያ ቤት ግንባታ ከነችግሩም ቢሆን በተወሰነ መጠን ችግሩን ማቃለል የቻለ ስለመሆኑ ይታመናል። ይሁን እንጂ ብዙዎች የቤት ልማት አቅርቦቱን በበለጠ መጠንና ጥራት ማቅረብ ይቻል እንደነበር በማንሳት በፍላጎትና አቅርቦት መካከል የተፈጠረው ክፍተትም አማራጮችን መጠቀም ባለመቻሉ ነው ይላሉ።
መኖሪያ ቤትን ጨምሮ ግዙፍ መዋለ ንዋይን የሚጠይቁ የተለያዩ መሰረተ ልማቶችን ማሟላት የሚቻለው በመንግሥት አቅም በመሆኑም ጥያቄዎቹ መንግሥት ላይ ያነጣጥራሉ። መንግሥትም የተነጣጠሩበትን ጥያቄዎች መመለስ የሚያስችለውን ፖሊሲና ስትራቴጂ ነድፎ ለተግባራዊነቱ እየተጋ ይገኛል። ይሁን እንጂ በአሁን ወቅት በኢትዮጵያ በከፍተኛ ፍጥነት እያደገ የመጣውን የመሰረተ ልማት ፍላጎት ለማርካት እንዲሁም ያለውን ክፍተት ለመሙላት በመንግሥት አቅም ብቻ የሚሸፈን ባለመሆኑ የግሉን ዘርፍ አጋርነት ማጠናከር ወሳኝ መሆኑ ታምኖ ወደ ሥራ ተገብቷል። በመሆኑም በአዲስ ዓመት በተለይም በቤት ልማት ዘርፉ በርካታ ተስፋ ሰጪ ጅማሮዎች ተጠናክረው የሚቀጥሉ ይሆናል። ቤት ያጣው ባለቤት የሚሆንበት ፤ ዕድለኛ ያልሆነውም በተስፋ ዕድሉን የሚጠብቅበት ጊዜ ይሆናል።
መንግሥት የቤት ልማት ዘርፉን ለማሳለጥ አዳዲስና የተለያዩ አማራጭ መንገዶችን እየተከተለ ባለበት በዚህ ወቅት የመኖሪያ ቤት አቅርቦትና ፍላጎት የሰማይና የምድር ያህል ተራርቆ ይታያል። እየታየ ያለውን ሰፊ ክፍተት ለመሙላትም መንግሥት በዋናነት አምስት የቤት ልማት አማራጮችን ዘርግቶ እየሠራ ይገኛል። እነዚህ አማራጮችም ትልቅ ተስፋ የተጣለባቸውና ችግሩን ለማቃለል የጎላ ሚና አላቸው።
እነዚህ ትልቅ ትኩረት የተሰጣቸውና ለችግሩ መፍቻ ቁልፍ ናቸው ተብለው ተስፋ የተጣለባቸው የቤት ልማት አማራጮችም አንደኛው በትግበራ ላይ ያለው የ40/60 እና የ20/80 ፕሮግራም፣ የሕብረት ሥራ ማህበራት፣ የመንግሥት ኪራይ ቤቶች፣ መንግሥትና የግል ባለሀብቱ በጋራ በመሆን የሚገነቡት እንዲሁም በመንግሥትና በግል ሽርክና (public privet partnership) የተባሉ አማራጮች ናቸው።
ከአማራጮቹ መካካል አንዱ የሆነው የመንግሥትና የግል ሽርክና የቤት ልማት አማራጭ ፍላጎትና የማልማት አቅም ያላቸውን የሀገር ውስጥና የውጭ ባለሀብቶችን የሚጋብዝ ፕሮግራም ነው። ከተማ አስተዳዳሩም ይህንኑ ፕሮግራም ተግባራዊ ማድረግ ከሚያስችለው የተለያዩ የውጭ ሀገር ኩባንያዎች ጋር የውል ስምምነት በመፈጸም ወደ ሥራ ለመግባት የሚያስችለውን የቅድመ ዝግጅት ሥራ አጠናቅቋል።
ከአማራጮቹ አንዱ የሆነው የመንግሥትና የግል አጋርነት ፕሮግራም የፋይናንስ ምንጭ ከመሆን ባለፈ የተለያዩ ጥቅሞች ይኖሩታል። ፕሮግራሙ ቀዳሚ ከሆነው የፋይናንስ አቅርቦት በተጨማሪ የዕውቀትና የቴክኖሎጂ ሽግግር ወደ ሀገሪቱ እንዲገባ ይጋብዛል። በፕሮጀክት ትግበራ ሂደትም የግሉ ሴክተር ቅልጥፍና እና ውጤታማነት በአብዛኛው የተሻለ በመሆኑ ተደራሽነቱ ፈጣን ይሆናል። ከዚህ ባለፈም የህዝብ አቅምን ያገናዘበ አገልግሎት ለማግኘት፣ ተመጣጣኝ የሆነ ወጪ እንዲኖር እና የመንግሥት የዕዳ ጫና እንዳይጨምር የማድረግ ጠቀሜታዎችን ያስገኛል።
የከተማ ልማትና ኮንስትራክሽን ሚኒስቴር ባጠናው ጥናት መሰረት የተገኘው ውጤት የሚያመለከተው ቤት ፈላጊው ህዝብ አንድ ነጥብ አምስት ሚሊዮን ደርሷል። ይህን ከፍተኛ የቤት ፈላጊ ቁጥር ታሳቢ ያደረጉ የቤት ልማት አማራጮችን ተግባራዊ በማድረግ ከተማ አስተዳደሩ በቀጣይ አምስት ዓመታት አብዛኛውን የህብረተሰብ ክፍል የቤት ባለቤት ለማድረግ እየሠራ ይገኛል። በዚህም በቀጣይ አምስት ዓመታት ውስጥ አንድ ነጥብ ሁለት ሚሊዮን የጋራ መኖሪያ ቤቶችን ገንብቶ ለዜጎች ተደራሽ ለማድረግ አቅዶ እየሠራ ይገኛል።
መንግሥት ይህን ሰፊ ዕቅድ በአምስቱ አማራጮች ተግባራዊ ለማድረግ ሲነሳ በከተማ ውስጥ ያለውን የመኖሪያ ቤት ጥያቄ የዜጎች ዋና የቅሬታ ምንጭ መሆኑን በመረዳት ነው። ዜጎች በመኖሪያ ቤት እጥረት እየደረሰባቸው ያለውን ስቃይና እንግልት ከመረዳትም በላይ የችግሩ ስፋትና ጥልቀት ለከተማ አስተዳደሩ ህመም እየሆነበት የመጣ በመሆኑም ጭምር ነው። ስለሆነም በአዲስ ዓመት ከመቼውም ጊዜ በተሻለ አሠራር የቤት ልማት ዘርፉ እንዲመራ በማድረግና አዳዲስ የግንባታ ቴክኖሎጂን በመጠቀም ጥራት ያለውና የተፋጠነ ሥራ በመሥራት ችግሩን ለማቃለል እየተደረገ ያለው ጥረት ተስፋ ሰጪ ነው።
መንግሥት በራሱ አቅም ብቻ መኖሪያ ቤት ገንበቶ ለዜጎች ተደራሽ ለማድረግ የማይቻል መሆኑን በማመን የተጀመረው አማራጭ በጥንቃቄ ተመርጦ የተገባበት ፕሮግራም ሲሆን፤ መንግሥት ባደረገው ድርድርና የዲፕሎማሲ ሥራ የአረብ ኢምሬትስ ኩባንያ እንዲሁም የደቡብ አፍሪካ ኩባንያ መኖሪያ ቤቶችን ለመገንባት የውል ስምምነት ፈጽመዋል። በቀጣይም ከፍተኛ ፍላጎትና ጥቂት አቅርቦት ያለውን መኖሪያ ቤት ለማጣጣም ሌሎች ኩባንያዎችን በመጋበዝ ተደራሽ ለማድረግ የሚሠራ ይሆናል። ከቤት ልማቱ ጎን ለጎንም በግንባታው ወቅት ሰፊ የሥራ ዕድል በመፍጠር በርካታ ዜጎችን በሥራ ዕድሉ ተጠቃሚ ማድረግና የቴክኖሎጂ ሽግግር ማግኘት ያስችላል።
እቅዱ ምንም እንኳን እስከአሁን ከተሄደበት መንገድ በመነሳት የተጋነነ ወይም የማይደረስበት ቢመስልም የነበረው አሠራር ተፈትሾ አዋጭ አለመሆኑን በማመን አዋጭ በሆኑ አሠራሮች የተተካ በመሆኑ ዕቅዱን ማሳካት እንደሚቻል ይታመናል። ከዚህም በላይ የቤቶች ልማት ዘርፍ ከላይኛው እስከታችኛው መዋቅር ድረስ አቅም ባለው አመራር ትኩረት ተሰጥቶት እየተመራ መሆኑን ከቤቶች ልማት ቢሮ የተገኘው መረጃ ያመለክታል።
መንግሥት በአዲስ ዓመት አዳዲስና አዋጭ የቤት ልማት ፕሮግራሞችን ነድፎ ከሚሠራው ሥራ በተጨማሪ በከተማው የተለያዩ አካባቢዎች ተጎሳቁለው የሚታዩ ቤቶችንም በማደስ ሰፊ ሥራ ተሠርቷል። ከጉስቁልናቸው ብዛት አቅመ ደካማ ለሆኑ ነዋሪዎች ፈተና፣ ስቃይና ሰቀቀንን ያተረፉት ዕድሜ ጠገብ የሆኑ የግልና የቀበሌ ቤቶችን በተለይም በጠቅላይ ሚኒስትር ዐብይ አሕመድ፣ በአዲስ አበባ ከተማ አስተዳዳር ጽህፈት ቤት፣ በተለያዩ ሚኒስቴር መስሪያ ቤቶች እንዲሁም በፈቃደኛ ግለሰቦችና ወጣቶች አማካኝነት በርካታ ቁጥር ያላቸውን ቤቶች መጠገን ተችሏል።
በክረምት በጎ ፈቃድ አገልግሎት ከአዲስ አበባ ከተማ ውጪ በክልል ከተሞችና ዞኖች ሳይቀር ጥቂት የማይባሉ የአቅመ ደካማ እናቶችና አባቶችን ቤት ካዘመሙበትና አንገታቸውን ከደፉበት ቀና ማድረግ መቻሉ የበርካቶችን ተስፋ አለምልሟል። የብዙዎችን ሕይወት ብሩህ ማድረግ በመቻሉም ተደቅኖባቸው የነበረው ስጋት ከክረምቱ ጽልመት ጋር ተሻግሮ ከአሮጌው ዓመት ጋር ላይመለስ ተሰናብቷል። በመሆኑም ዛሬ በሺዎች የሚቆጠሩ ዜጎች በአዲስ ቤት እፎይታን አግኝተው አዲስ ዓመትን በአዲስ መንፈስና ልብን በሚያሞቅ ተስፋ መቀበል ችለዋል።
መንግሥት የችግሩን ስፋትና ጥልቀት በተረዳበት አግባባ አዳዲስ አማራጮችን ለመጠቀም ሲወስን በተለይም የግሉን ዘርፍ ትልቅ ተሳትፎ ከአዳዲስ የቤት ልማት አማራጮች ጋር ማስተሳሰርን ቀዳሚ ማድረግ መቻሉ በአዲስ ዓመት አዲስ ተስፋን ይዞ የሚመጣ መሆኑ ሳይታለም የተፈታ ነው። አማራጮችን በማስፋት ችግሩን ለማቃለል እየተደረገ ባለው ጥረት የግል አልሚዎችን ጨምሮ ሰፋፊ የግል ይዞታ ያላቸው ነዋሪዎች ይዞታቸውን በማጋራት ቤት ፈላጊዎች በማህበር ሆነው የሚገነቡበት አማራጮችም እየሰፋ የመጣ በመሆኑ በቀጣዮቹ አምስት ዓመታት ችግሩን በማቃለል ረገድ ትርጉም ያለው ሥራ የሚሠራ ይሆናል። በዘርፉ የታሰቡት ዕቅዶች ወደ ውጤት ተለውጠው ቤት ፈላጎው ባለቤት እንደሚሆን ተስፋ እናደርጋለን። በአዲስ ዓመት አዳዲስ ተስፋዎች ይታዩናል። መልካም አዲስ ዓመት ተመኘን ሰላም!
ፍሬህይወት አወቀ
አዲስ ዘመን መስከረም 1 ቀን 2013 ዓ.ም